text
stringlengths
384
122k
አቶ ፈለቀ አጥናፌ ይባላሉ የ76 አመት የዕድሜ ባለፀጋ ናቸው፡፡ ቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 03 አዲሱ አደይ አበባ ስቴድየም አካባቢ ነዋሪ ናቸው፡፡ ስታዲየሙ ውስጥ በሚመሸጉ ሌቦች በደረሰባቸው ጉዳት ከአገር ውስጥ እስከ ውጪ ሆስፒታሎች ተመላልሰው ህክምና ተከታትለው አሁን መጠነኛ ለውጥ ማሳየታቸውን ይናገራሉ፡፡ ከ30 አመት በላይ ኖረዋል፡፡ ክፉ ደጉን ባየንበት እንቅስቃሴያችን ሁሉ በፍርሀት በሰቆቃ ሆነ፣ ሰላምና አጣን፤የመኖር ዋስትናችን ተነጠቀ ብለዋል፡፡ ወደ ሰፈሩ ስንመጣ ቦታው ባዶ ስለነበር የምንፈራው ጅብ ነበር፣ አሁን ደግሞ ያኔ ጅቡን ከምንፈራው በላይ የምንፈራው ሰው ነው ይላሉ:: ከውጪ የመጣች ዘመዳቸው ፤ ሀገር ቤት የገባች ቀን መዘረፏን የነገሩን አቶ ፈለቀ፤ እኔንም በቃ ገለነዋል ብለው የወሰዱብኝን ሞባይል ይዘው የዘመዴንም የልጆቿንም ፓስፖርት የያዘውን ቦርሳ ይዘው የገቡት ወደ ስታዲየም ነው ብለዋል፡፡ በአካባቢው የጭፈራና የሺሻ ቤቶች እንቅልፍ ማጣታችን ሳያንስ የማያልቀው ስታዲየም ለሌቦቹ መመሸጊያ በመሆን የመኖር ዋስትናችን ነጠቀን ሲሉ ምሬታቸውን ገልፀዋል፡፡ ሌላው በአካባቢው ባለ አራት ወለል ያለው ህንጻ ቤት ሰርተው እያከራዩ የሚኖሩት አቶ መሰከረ ረታ፤ በአካባቢው በተንሰራፋው ሌብነት ምክንያት ፤ተከራዮች ዘራፊዎቹን ፈርተው በመልቀቃቸው ቤቴ ከተከራየ 1 አመት ከ 6 ወር አለፈው ብለውናል፡፡ግዙፎቹ የቻይና ቴሌኮም ኩባንያዎች ሁዋዌና ዜድ ቲ ኢ ፤ ቤቴን ተከራይተውት ነበር ያሉ ሲሆን ሁለቱም በዘረፋ ተሰላችተው ለቀው ሄደዋል ብለዋል፡፡ በአካባቢው ወደ ሚገኘው ቻይና ሬስቶራንት የሚመጡ የውጪ ዜጎችን መዝረፍ ብቻ ሳይሆን ተሰብስበው ይደበድባሉ ብለዋል፡፡የአካባቢው ነዋሪዎች፣ስራቸው በዚያው አካባቢ የሆነ እንዲሁም በአዲሱ አደይ አበባ ስቴዲየም አካባቢ ሲያልፉ የተዘረፉ ሰዎች ብሶታቸውን ለጣቢያችን ያጋሩን ሲሆን ሁሉም ወንጀለኞቹ ከዘረፉን በኋላ ወደ ስታዲየም ነው የሚገቡት ብለዋል፡፡ ከጓደኛዋ ጋር በቅርቡ ወደ ገባንበት በአካባቢው ወደ ሚገኘው ቢሮዬ እየሄድኩ ነበር የምትለው ደግሞ መስከረም ነች፡፡ ሁለት ሆነው መጥተው ስልኬን በግድ ታግለው ተቀበሉኝ ፤ ጓደኛዬ በዣንጥላዋ ለመከላከል ሞከረች፣ ግን አልተሳካም ስትል በቁጭት ተናግራለች፡፡ በጣም የገረመኝ ትላለች መስከረም፤ በጣም የገረመኝ ፤ ከሰረቁን በኋላ ምንም እዳልተፈጠረ፣ የራሳቸውን ንብረት ተቀብለው እንደሚሄዱ ሁሉ ዘና ብለው ነው ወደ ስታዲየም የገቡት ያለች ሲሆን በጣም ብዙ ሰው የሆነውን እያየ ዝም ማለቱ ለራሳቸው ደህንነት በመስጋታቸው እንደሆነ ነግራናለች፡፡ በአዲሱ ስታዲየም አካባቢ እያለፈ የነበረው ናሆም ደግሞ በመንገድ መዘጋጋት ምክንያት መኪናው ውስጥ ተቀምጦ ረዘም ላለ ጊዜ መንቀሰቀስ ባለመቻሉ አዲስ አይፎን ስልኩ የሌቦች ሲሳይ መሆኑን በሀዘኔታ አጫውቶናል፡፡ አንድ ልጅ መጣና የመኪናውን ስፖኪዮ በሀይል መቶ አጠፈው፤ እኔ በንዴት ጦፌ ትኩረቴን ወደሱ በማድረግ ምን መሆኑ እንደሆነ ስጠይቀው፤ለካ ጓደኛው ክፍት በነበረው በሌላኛው የመኪናው መስኮት ስልኬን ይዞ እየሮጠ ነበር ብሏል፡፡ተከትየው ወደ ገባበት ስታዲየም ልገባ ስል ፤ አብደህ ካልሆነ እንዳታደርገው፣ ተደብድበህ ሌላ እቃም አስረክበህ ነው የምትወጣው አሉኝ ፣ ስለዚህ ስልኬን አስረክቤ ተመለስኩ ብሎናል፡፡ ስሟን መጥቀስ ያልፈለገችው በአካባቢው ተወልዳ እንዳደገች ያነገረችን ወጣት ደግሞ ፤ ሁልጊዜም የአካባቢው ሰዎች ሌቦች እየተከተሉሽ ነው፣ ተጠንቀቂ ስለሚሉኝና በሌሎች ላይ የሚደርሰውን ዝርፊያ ስለማውቅ በጣም ነበረ የምጠነቀቀው ያለች ሲሆን የስራ ሰርቪስ ልይዝ ከቤት በወጣሁበት አንድ ጠዋት ግን የሌሎቹ ክፉ ዕጣ እኔ ላይም ደርሷል ብላናለች፡፡ መሬት ላይ በጭንቅላቴ ፈጥፍጦኝ ቦርሳዬን ይዞ አላልቅ ወዳለው አደይ አበባ ስታዲየም ገባ ብለለች፡፡ ሆስፒታል በመሄድ ጭቅላቴ ላይ የደረሰው ጉዳት የከፋ እንዳልነበረ ባውቅም ከዚያ በኋላ ኑሮዬ ሁላ የፍርሀትና የሰቆቃ ሆነ ስትል ህግና መንግስት ባለበት ሀገር መሀል ከተማ ላይ በጭንቀት መኖሯ እንደሚያንገበግባት ነግራናለች፡፡ሰፈሩ እኮ የለየለት የውንብድና ሰፈር ሆኗል የሚሉት እነዚህ ሰዎች ስታድየሙ መቼ ነው የሚያልቀው? እንዴት ስቴዲየሙስ የሌቦች መመሸጊያ ሲሆን መንግስት ዝም ብሎ ያያል? ሲሉ ትዝብታቸውንና ጉዳታቸውን አጋርተውናል፡፡ በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 03 በተለምዶ ሀያ አምስቱ አፓርትማ ተብሎ በሚታወቀው መንደር ውስጥ የሚኖሩ 450 እና ከዚያ በላይ የሆኑ አባወራዎች ለስፖርት ኮሚሽን፣ ለወረዳ፣ ለክፍለ ከተማ እና ለከተማ አስተዳደሩ ስቃያቸው እንዲቆምላቸው ተደጋጋሚ አቤቱታ አስምተዋል፡፡ ነዋሪዎቹ ለጣቢያችን እንተናገሩት በነዚህ ወንበዴዎች ምክንያት ሴቶች ይደፈራሉ፣ህፃናት ወንዶች ላይ ጥቃት ይደርሳል፣የውጪ ዜጎች ሳይቀር ይደበደባሉ፣ እስከ ሞት አደጋ የደረሰበትም አለ ሲሉ ነግረውናል፡፡በመኖርያ ቤቶች ላይ በተገጠሙ ካሜራዎች ዝርፍያ ሲፈፀም የተቀረፁ ቪዲዮዎች ነዋሪዎቹ ለጣቢያችን የላኩ ሲሆን ሌቦቹ ለመዝረፍ ከአደይ አበባ ስታዲየም ሲወጡ፣ ከነጠቁ በኋላ ደግሞ ወደ ስታዲየሙ ሮጠው ሲገቡ ቪዲዮው ያሳያል፡፡ በስፖርት ኮሚሽን የስፖርት ፋኩልቲ ዳይሬክተር አቶ አስመራ ግዛው ለኢትዮ ኤፍ ኤም እንደተናገሩት ፤ እኛም ተቸግረናል፣ ጥበቃ እየተደበደበ የሳይቱ ዕቃ እየዘተረፈ ነው ፣ ነዋሪዎቹ ለኛ ደብዳቤ ፅፈዋል፣ እኛ ደግሞ ክፍለ ከተማ ደብዳቤ ፅፈናል ብለዋል፡፡ዋናው ችግር የሆነብን በህገ ወጥ መንግድ በቦታው ሸራና ላስቲክ ወጥረው የሚኖሩት ናቸው ያሉ ሲሆን ከተፈቀደ በር ውጪ መስጊድ አለ፣ በመስጊዱ በኩል ደግሞ ፤ ሌላ በር አለ፣ በዚያ በኩል ነው የሚገቡት እሱን ለመቆጣጠር ደግሞ በፍርድ ቤት ሂደት ላይ ያለው መስጊድ ሌላ ምትክ ቦታ ማግኘት አለበት ሲሉ ተናግረዋል፡፡ ፕሮጀክቱ ሳይጀመር ጀምሮ ባለፈው ሳምንት ፤ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ በተገኙበት እስከተደረገው የምክር ቤት ጉባኤ ድረስ ይሄን ጉዳይ ሺህ ጊዜ ጠይቀናል ፤ ያሉ ሲሆን ክፍለ ከተማው ለመስጊዱ ምትክ ቦታ እፈልጋለሁ ብሏል ሲሉ የነገሩን ሲሆን ፖሊስ ያኔ ህገ ወጥ ሰፋሪዎችን አጸዳለሁ ብሏል ብለውናል፡፡ ስታዲየሙ በፕሮግራሙ መሰረት እየተሰራ ነው የሚሉት አቶ አስመራ አንደኛው ምዕራፍ አልቆ ሁለተኛው የማጠቃለያ ምዕራፍ ተጀምሯል፤ የሚመለከተው ክፍል ህገ ወጥ ሰፋሪዎቹን ካላነሳልንና ለመስጊዱም ሌላ ምትክ ቦታ ካልሰጠ ግን ነዋሪው ላይ ብቻ ሳይሆን ፕሮጀክቱ ላይም ከፍተኛ አሉታዊ ተፅዕኖ ያሳድራል ሲሉ አሳስበዋል፡፡ የአዲስ አበባ ከተማ ፖሊስ ኮሚሽን ጋር ሄደን ስለ ጉዳዩ ጠይቀናቸዋል፡፡ የተለየ ትኩረት ሰጥተን የምነከታተከውና የምንጠበቀው ቦታ ነው ሲሉ ነግረውናል፡፡ በኮሚሽኑ የህዝብ ግንኙነት ሀላፊ ኮማንደር ፋሲካ ፋንታ በህገ ወጥ መንገድ ሸራና ላስቲክ ወጥረው የሚኖሩት ካልተነሱ ችግሩ ዘላቂ መፍትሄ አያገኝም ያሉ ሲሆን የሚመለከተው አካል ይሄን እንዲያደርግ አሳስበዋል፡፡ በአካባቢው የሚገኙ ጭፈራና ሺሻ ቤቶች ለችግሩ መበርከት ሌላ ምክንያት እንደሆኑም ገልፀዋል፡፡ ከወንጀለኞቹ ጋር ቀጥታ ግንኙነት ያላቸው ከነዚሁ ዲስኮ ቤቶች የሚወጡ ረጅም እጅ ያላቸው ሰዎች ጥቂት አይደሉም ብለዋል፡፡በቋሚነት ከተመደቡ ፖሊሶች በተጨማሪ ቦታው አደገኛ በመሆኑ ምክንያት በየትኛውም የአዲስ አበባ ክፍል ያላደረግነውን በቋሚነት ፓትሮል መኪና እየተሸከረከረ እንዲጠብቅ መድበናል ሲሉ ተናግረዋል፡፡ እስከ ሰበር ሰሚ ችሎት ድረስ ሄዶ መፍትሄ ያላገኘው መስጊድና የአየር ካርታ ጭምር አለን በማለት ከቦታው አንነሳም የሚሉ ሕገ ወጥ ሰፋሪዎቹን የሚመለከተው ክፍል መፍትሄ ካላበጀላቸው ግን የአካባቢው ችግር ዘላቂ መፍትሄ አያገኝም ብለዋል፡፡ ተለዋዋጭ ባህሪ ያውን በከተማዋ የተንሰራፋውን ስርቆት ለመቀነስ በግጭትና በተለያዩ ምክንያቶች ወደ መዲናዋ የሚፈልሱት ወጣቶች ላይ እልባት መሰጠት አለበት የሚሉት ኮማንደር ፋሲካ ህዝቡም የስርቆት ወንጀል ሲፈጸምበት አንዴ አመልክቶ ምላሽ ካላገኘ ወደ በላይ አካል ሄዶ ጉዳዩን የማስፈፀም ልምድ ማዳበር አለበት ሲሉ ምክራቸው ለግሰዋል፡፡ በስቴዲየሙ ዙርያ በህገ ወጥ መንገድ ስለሚኖሩት፣ስለሚነግዱትና፣ ምትክ ቦታ ይፈልግለታል ስለተባለው መስጊድ ልንጠይቅ ወደ ቦሌ ክፍለ ከተማ ያደረግነው ተደጋጋሚ ሙከራ አልተሳካም፡፡
የመለስ ዜናዊ አስተሳሰብና ምግባር ሕዝብን በተለይም ፖለቲከኞችን በተራራቀ ተቃራኒ ጫፍ እንዳቆሙ መሞታቸዉ የኢትዮጵያን ፖለቲካ በበጎ ወይም በመጥፎ፥ ወይም በሁለቱም መሐል-ክፉኛ መንካቱ እንደማይቀር ያኔ ተብሎ ነበር። አሁንም አልቀረም። የቀድሞዉ ጠቅላይ ሚንስትር ተሸኙ። ሁለት ሺሕ አራትም ተሰናበተ። እና አዲስ ዓመት። ሁለት ሺሕ አምስት። ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ-ክርስቲያን ርዕሠ-ሊቃና ጳጳሳት እና፥ በአቶ መለስ ዜናዊ ሞት ማግስት የባተዉ ሁለት ሺሕ አምስት ካዲስ መሪ፥ ካዲስ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሹመት ጋር አዲስ ተስፋ አጭሮም ነበር። ዓመቱ ዛሬ-አርጅቶ ሊሰናበት ሁለት ቀን ቀረዉ። የዓመቱን የኢትዮጵያ አበይት ፖለቲካዊ ክንዉኖች እየጠቃቀስን፥ ተስፋዉ መጠዉለግ-መፅደቁን፥ ላፍታ እንቃኛለን። አብራችሁኝ ቆዩ። መለስ በተቀበሩ በሳምቱ ሁለት ሺሕ አምስት እንደ አዲስ ዓመት ሲብት ሁለት የስዊድን ጋዜጠኞችን ጨምሮ በሺሕ የሚቆጠሩ እስረኞች በምሕረት መፈታታቸዉን የኢትዮጵያ መንግሥት ማወጁ፥ የአዲሱ ዓመት አዳዲስ መሪዎች አሮጌዉን ከፋፋይ መርሕ ከአሮጌዉ ዓመት ጋር ለማሰናበት ፍንጭ ማሳየታቸዉ መስሎ ነበር። ከእስረኞቹ የመፈታት ዜና በተጨማሪ የኢትዮጵያ መንግሥት ከኦጋዴን ብሔራዊ ነፃዉጪ ግንባር (ኦብነግ) ጋር ለመደራደር መወሰኑን አስታዉቆም ነበር።ኦብነግ የመለስ ዜናዊ መንግሥት ለረጅም ጊዜ ባሽባሪነት የወነጀለዉ፥ ከሁለት ሺሕ ሁለት ጀምሮ ደግሞ ከአልቃኢዳ፥ ከአልሸባብ፥ እና ከሁለት ሐገር በቀል ድርጅቶች ጋር በሕግ-በአሸባሪነት የፈረጀዉ ቡድን ነዉ። በዚሕም ሰበብ በመለስ ሞት ማግሥት አዳዲሶቹ መሪዎች ከኦብነግ ጋር ለመደራደር መስማማታቸዉን ሲያስታዉቁ፥ ለኢትዮጵያ ፖለቲካ አዲስ ተስፋ ማጫሩ አልቀረም። በአዲሱ ዓመት ዋዜማ ናይሮቢ ኬንያ ዉስጥ በኢትዮጵያ መከላከያ ሚንስትር ሲራጅ ፈርጌሳና በኦጋዴን ብሔራዊ ነፃ አዉጪ ግንባር የዉጪ ግንኙነት ሐላፊ በአብዱረሕማን መሕዲ መካካል የተደረገዉ ድርድር እንዲደረግ የወሰኑት አቶ መለስ ዜናዊ ከመሞታቸዉ በፊት መሆኑ ሲነገር ግን ተስፋዉ የአዲሱ ዓመት ፀጋ፥ የአዲሶቹ መሪዎችም ብልሕነት እንዳልሆነ ግልፅ ሆነ። እስረኞቹ የተለቀቁትም በመለስ ዉሳኔ እንደነበር ተነግሯል። የሁለቱ ወገኖች ተደራዳሪዎች በድርድሩ ሥነ-ሥርዓታዊ ጉዳዮች ተስማምተዉ፥ ለመስክረም ማብቂያ ለሁለተኛ ዙር ድርድር ለመገናኘት ተቀጣጥረዉ ነበር። መንግሥት አማፂዉ ቡድን ሕገ-መንግሥቱን ካልተቀበለ አልደራደርም በማለቱ፥ አማፂዉ ቡድን ቅድመ ሁኔታዉን ባለመቀበሉ ቀጠሮዉ-በቀጠሮ ቀረ። ተስፋዉም ቢያንስ ለዚሕ ዓመት ተጨናጎለ። ተስፋ የማይቆርጠዉ ወይም ተስፋ ላለመቁረጥ፥ ተስፋ የሚያደርገዉ የኢትዮጵያ ሕዝብ ሌላ ተስፋ የሚያደርግበት ሰበብ ምክንያት አላጣም። የአዲሱ መሪዉ ቃል ዋናዉ ነበር። የአቶ መለስ ዜናዊ ሞት ከታወጀበት ጊዜ ጀምሮ የጠቅላይ ሚንስትርነቱን ሥልጣን በጊዚያዊነት የያዙት ምክትል ጠቅላይ ሚንስትር ሐይለ ማርያም ደሳለኝ የጠቅላይ ሚንስትርነትቱን ሥልጣን በይፋ ተረከቡ። መስከረም አስር። አዲሱ ጠቅላይ ሚንስትር ኋላ እንዳሉት የዚያን ቀን ያደረጉትን ንግግር ፍሬ ሐሰብ ከማርቀቅ በስተቀር ንግግሩን የፃፉት ሌሎች ናቸዉ። ንግግሩን እንደ ኦጋዴኑ ድርድር ሟቹ ጠቅላይ ሚንስትር መለስ ዜናዊ የወሰኑት ወይም ፅፈዉ የተዉት ነዉ ማለት ግን አይቻልም።የንግግሩ ይዘት፥ ቃሉም ብዙ አዲስ አይደለም። ግን የአዲሱ ጠቅላይ ሚንስትር ነዉ። የሐይለ ማርያም ደሳለኝ። ሁሉም ተባለ። የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች ጥሪ፥ የነፃ ጋዜጠኞች አቤቱታ፥ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ስሞታ፥ የሙስሊሞች ጩኸትም ቀጠለ። ታሕሳስ መባቻ። የአል-ጀዚራዋ ጋዜጠኛ አዲሱን የጠቅላይ ሚንስትር ጠየቀች። «ሙስሊሞችን በተመለከተ በቀጠለዉ የተቃዉሞ ሠልፍ ምክንያት (እና በሌላም ምክንያት) በሐገሪቱ ዉስጥ ብዙ ችግሮች አሉባችሁ። በሺ የሚቆጠሩ ሰዎች ታስረዋል። ብዙዎቹ እንደሚሉት መንግሥት አህባሽ የተሰኘዉን የእስልምና (ሐራጥቃ) በሕዝቡ ላይ በሐይል ጭናችኋል፥ መንግሥት ሐይማኖቱን በሐይል ባዲስ መልክ ለመቅረፅ ጠንካራ እርምጃ ወስዷል ይላሉ። ጠንካራ እርምጃ ነዉ።» ጠቅላይ ሚንስትሩ መለሱ። «እንደሚመስለኝ ይሕ የአናሳዎች ድምፅ ነዉ። የአብዛኞቹ ድምፅ አይደለም። የአብዛኞቹ ሙስሊሞች ጥያቄ የራሳቸዉ የአስተዳደር ሥርዓት እንዲኖራቸዉ ነዉ። መንግሥት በነሱ የአስተዳደር ሥርዓት ዉስጥ የሚያገባዉ የለም። ለሐይማኖት ያልወገነ መንግሥት ነዉ ያለዉ።ሕገ-መንግሥቱም መንግሥት በሐይማኖታዊ ጉዳይ ጣልቃ እንደማይገባ ይደነግጋል።» ጥር ማብቂያ። ጠቅላይ ሚንስትር ሐይለ ማርያም ደሳለኝ «በሐይማኖታዊ ጉዳይ ጣልቃ አይገባም ያሉት መንግሥት የሚቆጣጠረዉ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ጉዳያቸዉ በፍርድ ቤት የሚታይ የሙስሊም መሪዎችን በአሸባሪነት የሚወነጅለዉን ፊልም አሰራጨ። ርዕስ፥ ጅሐዳዊ ሐረካት። ጠቅላይ ሚንስትር ሐይለ ማርያም ለአል-ጀዚራ ቴሌቪዥን ጣቢያ በሰጡት ቃለ ምልልስ በፖለቲካ ምክንያት የታሠረ አንድም ሰዉ እንደሌለ ተናግረዉ ነበር። ጥር ማብቂያ። ዓለም አቀፉ የሠብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት ሑዩማን ራይትስ ዋች ባወጣዉ ዘገባዉ ኢትዮጵያ ዉስጥ ከጥር ሁለት ሺሕ አራት እስከ ታሕሳስ ሁለት ሺሕ አምስት በነበረዉ አንድ ዓመት ብቻ ሰላሳ የተቃዋሚ ፓርቲ ፖለቲከኞች እና ጋዜጠኞች በአወዛጋቢዉ የፀረ-ሽብር ሕግ ተወንጅለዉ እስራት ተበይኖባቸዋል። የቀድሞዉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ-ክርስቲያን ርዕሠ-ሊቃነ ጳጳሳት ከሞቱበት እስከ ዓመቱ አጋማሽ ድረስ የዉጪ እና የሐገር ዉስጥ በሚል ለሁለት የተከፈሉት የሐይማኖት አባቶች ይታረቃሉ የሚል ተስፋ አሳድሮ ነበር። ድርድር፥ ዉይይትም ነበር። የካቲት-ሁሉም ቀረ። የሐገር ዉስጡ ሲኖዶስ የዉጪዉን ጥያቄ ዉድቅ አድርጎ ርዕሠ-ሊቃነ ጳጳሳት ሾመ። ሚያዚያ፥ ምርጫና ጉብኝት ነዉ። መስከረም ላይ ጠቅላይ ሚንስትሩ ቃል ገብተዉ ነበር። ሚያዚያ ላይ ሠላሳ ሦስት ተቃዋሚ ፓርቲዎች ምርጫ ቦርድን ጨምሮ ከመንግሥትና ከገዢዉ ፓርቲ ይደርስብናል ያሉት ጫና እንዲቃለልላቸዉ ያቀረቡት ጥያቄ ዉድቅ ሆነብን በሚል ከአካባቢያዊና ከከተሞች አስተዳድር ምርጫ እራሳቸዉን አገለሉ። ገዢዉ ፓርቲ እና ተባባሪዎቹ ብቻቸዉን ተወዳድረዉ አሸነፉ። ጠ/ሚ/ር ሐይለ ማርያም ደሳለኝ ከአዉሮጳ ሕብረትና ከፈረንሳይ ባለሥልጣናት ጋር ለመነጋገር ብራስልስን፥ ሽትራስቡርግንና ፓሪስን የጎበኙትም ሚያዚያ አጋማሽ ነበር። ግንቦት፥ የአፍሪቃ መሪዎች የአፍሪቃ ሕብረት የተመሠረተበትን ሐምሳኛ ዓመት አዲስ አበባ ዉስጥ በደማቅ ሥነ-ሥርዓት አከበሩ። መሪዎቹ በተሰናበቱ በሳምንቱ ሰማያዊ ፓርቲ የጠራዉ የተቃዉሞ ሠልፍ አዲስ አበባ ዉስጥ ተደረገ። ከ1997 ወዲህ ሕዝብ፥ መንግሥትን በመቃወም አደባባይ ሲወጣ የመጀመሪያዉ ነበር። ግንቦት ሃያ-አምስት። በወሩ አንድነት ለፍትሕና ለዲሞክራሲ የጠራዉ ሠላማዊ የተቃዉሞ ሠልፍ ጎንደርና ደሴ ዉስጥ ተደረገ። የአደባባይ ተቃዉሞ ሠልፍ የማድረጉ ጥረት፥ ሙከራ፥ ዝግጅትም ቀጥሏል። የዚያኑ ያክል ተቃዋሚ ፖለቲከኞች እንደሚሉት በአባሎቻቸዉና በደጋፊዎቻቸዉ ላይ መንግሥት የሚፈፅመዉ እስራት እንግልትም አላባራም። ግንቦትና ሰኔ፥-የኢትዮጵያንና የግብፅን የቃላት እንኪያ ሰላንታ እንዳሰሙን-ሐምሌ ተካቸዉ። የአዉሮጳ ምክር ቤት የሰብአዊ መብት ጉዳይ ኮሚቴ ሰብሳቢ ወይዘሮ ባርባራ ሎኽቢኸር የመሩት የመልዕክተኞች ቡድን ኢትዮጵያን ጎብኝቶ ነበር። ሐምሌ – ቡድኑ ከመንግሥትና ከተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎች ጋር ከተነጋገረ በኋላ እስረኞችን ለመጎብኘት ጠይቆ ተፈቅዶለት ነበር። ቃሊቲ ሲደርስ «ማን ፈቀደልህ» ተባለ። የዘንድሮዉ ሐምሌ ለሙስሊሞች የቅዱስ ረመዳን ወር ነበር። የድምጻችን ይሰማ የመስጊዱ ተቃዉሞ ጩኸታቸዉ ግን አላባራም። በተቃዉሞዉ ሰበብ ከፀጥታ አስከባሪዎች የሚደርስባቸዉ ወከባ እስራት ዘረፋና ግፍም ብሶ ቀጥሏል። ለኮፈሌ፥ ለኢዶ፥ ለዋቤ፥ ለቆሬ ከተሞች ደግሞ የዘንድሮዉ ረመዳን የአሳዝኝ ግድያ ወርም ነበር። ሐምሌ ማብቂያ ፀጥታ አስከባሪዎች በተሰበሰቡ ሙስሊሞች ላይ በከፈቱት ተኩስ ሲያንስ አስር ሲበዛ ሃያ-ስድስት ሰላማዊ ሰዎች ገድለዋል። ኢድ-አልፊጥር የፌስታ፥ ደስታ፥ ታላቅ ዕለት ነዉ።የአዲስ አበባ ሙስሊሞች የዘንድሮዉን ረመዳን የፈጠሩት፥ ኢድን ያከበሩት የከብት፥ የበግ፥ የዶሮ ደም አፍስሰዉ ሳይሆን በፖሊስ ቆመጥ የራሳቸዉን ደም አዝርተዉ ነበር። ሁለት ጋዜጠኞችም ታስረዉ ነበር። ዓለም አቀፉ የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ድርጅት የጋዜጠኞቹን መታሰር አዉግዟል። በዓለም ላይ በሸሪዓ ሕግ የሚገዙ ሁለት ሐገራት አሉ። ኢራንና ሳዑዲ አረቢያ። ጠቅላይ ሚንስትር ሐይለማርያም ደሳለኝ በኢድ አልፊጥር ማግሥት እንዳሉት ደግሞ የኢትዮጵያ ሙስሊሞች ኢትዮጵያን በሸሪዓ ሕግ የምትገዛ ሦስተኛ ሐገር ለማድረግ ይጥራሉ። ዘንድሮ- ሦስት ሚንስትሮች የተሻሩ፥ ከሦስቱ አንዱ ከተከታዮቻቸዉ በሙስና የታሰሩበት፥ አዳዲስ ሚንስትሮች የተሾሙበት፥ ኢትዮጵያ ባለ-ሦስት ምክትል ጠቅላይ ሚንስትር ካቢኔ የሰየመችበትም ዓመት ነዉ። ዓመቱ በርካታ የህወሃት ቁልፍ ሰዎች እና የደኅንነት አመራሮች እንዲሁም አይነኬ ባለሃብቶች ከሥልጣናቸው እየተነቀሉ ሌሎችን ሲያጉሩበት በነበረው እስርቤት የተወረወሩበት ነው፡፡ የሙስናው መዘዝ ተመዝዞ መጨረሻው የት እንደሚደርስና ወደየት አቅጣጫ እንደሚነጉድ መጪው ዓመት ብዙ ያሳየናል፡፡ ዋናዎቹን የሙስና ሻርኮችንም ይደርስባቸው ይሆን ወይም አልፏቸው ይሄድ ይሁን አዲሱ ዓመት ያሳየናል፡፡(ምንጭ፡ የጀርመን ድምጽ ሬዲዮ፤ ዘገባው ለጋዜጣችን እንዲመች ሆኖ ለመታረሙ ኃላፊነቱን እንወስዳለን)
“ወይኔ ልጄ፣ እጅ እግሬ ልጄ፣ ወይኔ ልጄ፣ ወዴት ነህ ልጄ፣ የት ላግኝህ ልጄ? እምኑ ጋር ነህ? ልጄ … ልጄ … ልጄ … ልጄ …” ጥቁር ቦርሳቸውን በወገባቸው ተሸክመው፣ ቂሊንጦ እስር ቤት ደጅ የሚያነቡ እናት ለቅሶ!! ሁሉም ያነባሉ። ሁሉም ያለቀሳሉ፣ የሚሰማ ግን የለም። እንደውም “ዘወር በሉ” እየተባሉ ይደገንባቸዋል። “ሊታረሙ በህግ ከለላ ስር ሆነዋል” የተባሉ ወገኖች “ተረሽነዋል” የሚለው አስተሳሰብ እየጠነከረ መጥቷል። ለቤተሰቦቻቸው እንደምን ተቆጥረው ይሁን? ይህ ሁሉ የጭካኔ ግፍ ወዴት ይመራን ይሆን? የብዙዎች ጥያቄና ስጋት ነው። በየሰዓቱ የሚወጡት መረጃዎች ደግሞ ስጋቱን የሚያግሉና ቁጣን የሚቀሰቅሱ ሆነዋል። የህወሃት ሹሞችም “የሆነው ነገር ሁሉ የተከሰተው በዕቅድ አይደለም” ይላሉ፡፡ በአልሞት ባይ ተጋዳነት የሚውተረተረው ህወሃት አሁንም አለሁ ቢልም የቂሊንጦ ጉዳይ ማቆሚያ ላጣው ፈተናው ተጨማሪ ነዳጅ ሆኗል፡፡ ይህ አገራዊ ሃዘን ምናልባትም ህወሃት የራሱን ማክተሚያ እያጣደፈ ነው የሚሉ አሉ፡፡ የታሳሪ ቤተሰቦች “እስከ አርብ ጠብቁ” ተብለዋል – ከአርብ በፊትስ ምን ታስቧል? “ህወሃት አብቅቶለታል” በማለት እየተናገሩ ያሉት ምዕራባውያን በተለይም አሜሪካ በህወሃት ላይ ያላትን አቋም ጠበቅ እያደረገች መጥታለች፡፡ ፊት እየዞረባቸው እንደሆነ የተገነዘቡት እነ አባይ ጸሃዬ ጌቶቻቸው ዘንድ ቀርበው በሚችሉት ቋንቋ ኦሮሞና አማራ ተባብረውብናል፤ ሰግተናል በማለት ለሦስት ሳምንት ያህል እየተመላለሱ ቢለምኑም እንደ ቀድሞው የጌቶቻቸውን ይሁንታ ሊያገኙ አልቻሉም። ለጉዳዩ ቅርብ የሆኑ እንደሚሉት ህወሃት የሚመዘው የማደናገሪያ ካርታ ስላለቀበት ትዕዛዝ እንዲቀበል እየተገደደ ነው። ከእውነታው በተገላቢጦሽ የትግራይ ሕዝብ ነጻ አውጪ ግምባር (ህወሃት) አገር እየገዛ እንደሆነ ለማሳመን ቢጥርም አልተሳካለትም። የአገሪቱ በርካታው አካባቢዎች ከቁጥጥሩ ውጪ ሆኗል፡፡ በከመረው እርምና ባፈሰሰው የንጹሃን ደም ህዝብ ፊት ነስቶታል። ሁኔታውን በውል የተረዱት ጌቶቹም እንደቀድሞው ሊጠጋገኑት ከመሞከር ይልቅ ፊታቸውን አዙረውበታል፤ ባደባባይ ሊለዩት ጫፍ ላይ ናቸው። በዚሁ መነሻ እንደ ዱሮው ስብሰባ አይጠራም፤ አይጋበዝም፤ አይፈለግም፡፡ በጎረቤት አገራት በሚካሄዱ ስብሰባዎች እንኳን “አትፈለግም” ተብሏል፡፡ ዥጉርጉር ሚዲያዎች “መንግሥት” እያሉ የሌለውን ወግና ማዕረግ የሰጡት ህወሃት ከትክክለኛ ማንነቱ ጋር የሚመጣጠን ተግባር ላይ የተጠመደውም ለዚሁ እንደሆነ ብዙዎች እየመሰከሩ ነው። የሌለውን ስብዕና ተጎናጽፎ እመራዋለሁ የሚለው ህዝብ ላይ ጦርነት የሚያውጅ የወንበዴ ቡድን፣ እየዋለ ሲያድር ማንነቱና ለመንግስትነት ወግ ሊበቃ የማይገባው እንደነበር ያረጋገጠው የመለስ ህወሃት፣ የህዝብ ተቃውሞን በጸጋ ተቀበሎ ከማስተናገድ ይልቅ የመረጠው መንገድ እርቃኑን ያወጣው ሲሆን፣ ሰሞኑንን የረሸናቸው ወገኖች ጉዳይ ይህንኑ አውሬነቱን ያመላከተ እንደሆን በውጪም ሆነ ባገር ውስጥ ስምምነት አለ። ባለፈው ቅዳሜ የበርካታ ወገኖችን ህይወት የቀጠፈው የቂሊንጦ እስር ቤት ቃጠሎ፣ በውስጡ ሌላ እሣት ፈጥሮበታል፡፡ “አንድ ሰው ሞተ” ሲል ጀምሮ 23 የደረሰው የሟቾች ቁጥር እጅግ በርካታዎች እንደሞቱ በውል የሚያረጋግጥ ሆኗል፡፡ በራሱ በህወሃት/ኢህአዴግ ሁለት ዜጎች በጥይት ተመትተው መሞታቸው መናገሩ ምን ያህሉ በጥይት ተመትተው ይሆን የሚል ጥያቄ ፈጥሯል፡፡ በ1998 ዓም ላይ “የኦነግ አባላት ናችሁ” በሚል ታስረው የነበሩና “ከቃሊቲ ሊያመልጡ ሲሉ ሰባት ታራሚዎች ተገደሉ” ያለው ህወሃት በኋላ ግን ከ160 የሚበልጡ ታራሚዎች በተተኮሰባቸው ጥይት በግፍ ህይወታቸውን አጥተዋል፡፡ ቢታሰሩም ድምጻቸው ያልታሰረውና የህወሃትን የመኖር ዋስትና አደጋ ላይ የጣሉት እነ በቀለ ገርባ የታሰሩበት ቂሊንጦስ? እንዴት ሆኖ ይሆን? አንድ እናት እዚያው ቂሊንጦ ደጅ “ወይኔ ልጄ፣ እጅ እግሬ ልጄ፣ ወይኔ ልጄ፣ ወዴት ነህ ልጄ፣ የት ላግኝህ ልጄ? እምኑ ጋር ነህ? ልጄ … ልጄ … ልጄ … ልጄ …” እያሉ ያነቡ ነበር። የእናት አንጀት!! ከእሣቱ በፊት 45 ደቂቃ የወሰደ የቀለጠ የተኩስ ድምጽ መሰማቱ፣ እሣት አደጋ መከላከያ እሣቱን ለማጥፋት በቦታው የተገኘበት ሰዓት፣ እሳቱ የተነሳበት ቦታ የት እንደሆነ በውል አለመነገሩና በህወሃት/ኢህአዴግ ሹሞችና አፍቃሪዎች የሚነገረው የተምታታ መሆኑ፣ እሣቱን ያስነሳው ምን እንደሆነና ያስነሳው ማን እንደሆነ ከህወሃት በኩል የሚጣረስ መረጃ መሰጠቱ፣ ሐኪሞች የሟቾች ቁጥር 60 እንደሆነ መናገራቸውና የግለሰቦቹን ማንነታቸውን እንዳይለዩ በአስከሬን ላይ ቁጥር እንዲጠቀሙ መታዘዛቸው … ከዚህ አልፎ ደግሞ ከአገዛዙ የሚሰጠው መረጃ እርስበርሱ የሚጋጭ መሆኑ በህወሃት ውስጥ የተፈጠረውን ሁኔታ ቁልጭ አድርጎ የሚያሳይ ሆኗል፡፡ በዚህ ጉዳይ ለጎልጉል አስተያየታቸውን የሰጡ የሰብዓዊ መብት ድርጅት ከፍተኛ አመራር “ይህ ሁኔታ በራሱ የሟቾቹን ማንነት ለመደበቅ ሆን ተብሎ እየተቀናበረ ያለ ሤራ እንዳለ አመላካች ነው” ብለዋል፡፡ ቪኦኤ ያነጋገራቸው ቤተሰቦች “እስከ አርብ ጠብቁ” መባላቸውን ተናግረዋል፡፡ ከአርብ በፊትስ የታሰበው ነገር ምን ይሆን? በቂሊንጦ የተሰዉትን ስም ህወሃት ይፋ እንዲያደርግ ምዕራባውያን ፖለቲከኞችና እና ሚዲያው አስጨንቀው መያዛቸው ጎልጉል ያገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡ ከዚህ አንጻር በተደጋጋሚ የእስረኞቹ ማንነት እንዲናገሩ ጥያቄው ከቀረበባቸው ከፍተኛ የህወሃት ባለሥልጣናት መካከል አንዱ የማውቀው ነገር የለኝም፤ ሆኖም ግን የተከሰተው ነገር ሁሉ በዕቅድ የተደረገ አይደለም፤ ሆን ተብሎ የተከናወነ ድርጊት አይደለም በማለት ማስተባቤ መስጠታቸው የሟቾቹን ማንነት ከፍተኛ ጥርጣሬ ላይ የጣለ አድርጎታል፡፡ የተከሰተው ቃጠሎ ነው፤ የፈረሰና የተቆለለ ክምር የለም፤ ከፍርስራሽ ውስጥ ሰዎችን የማውጣት ሥራ አይደረግ፤ … የሞቱት ሰዎች ማንነት በቃጠሎው አልጠፋ፤ ታዲያ ለምን ይሆን ቤተሰብ እንዲህ የሚንገላታው? “እናቶች ልጆቻቸውን ፍለጋ ወገባቸውን በመቀነት አስረው በጉልበታቸው እየሄዱ” እንደሆነ ትላንት የተሰራጨው የቪኦኤ ዘገባ ላይ የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ የወጣቶች ክፍል ኃላፊ አቶ ጉርሜሳ አያና ባለቤት ወ/ሮ ዐይናለም ደበላ ተናግረዋል፡፡ እርሳቸውም እንደሌሎቹ የባለቤታቸውን መኖር በተመለከተ እስከ አርብ ጠብቁ ተብለው ጭንቅ ውስጥ ናቸው፡፡ ከእነዚህ ወገኖች ሌላ ህወሃት በግፍ በሚገዛት ኢትዮጵያ እጅግ በርካታ ዜጎች በየቀኑ እየተገደሉ፣ እየተሰወሩ፣ እየተሰቃዩ፣ … ይገኛሉ፡፡ መኖራቸው የማይታወቅ፣ የሚጮህላቸው ወገን የሌላቸው፣ የሚዲያ ሽፋን የማያገኙ፣ … የእነዚህስ ቤተሰቦችና ወገኖች እስከመቼ ይሆን የሚጠብቁት? “ልጅን ያህል ነገር ያለበትን ሳላውቅ እንዴት ዝም ልበል?” ያሉትን የዮናታን ተስፋዬን እናት ወ/ሮ ሙጪት ተካን ጨምሮ የአቶ በቀለ ገርባ ባለቤት ወ/ሮ ሃና እና ልጃቸው ወ/ት ቦንቱ በቀለ፣ የአቶ ደጀኔ ጣፋ ባለቤት ወ/ሮ አሰለፈች ሙላትና የመኢአድ ማዕከላዊ ኮሚቴ አባል አቶ አሰጋ አሰፋ ልጅ ወ/ት ህይወት አሰፋ ቤተሰቦቻቸው ያሉበትን ሁኔታ አለማወቃቸው ጭንቀት ውስጥ እንደከተታቸው ለአሜሪካ ድምፅ መግለፃቸው ይታወሳል፡፡ በግፍ መታሰራቸው፣ በየቀኑ ግፍ መቀበላቸው፣ መንገላታቸው ሳያንስ አሁን ደግሞ “ንገሩን” እያሉ የሲቃ ድምጽ እያሰሙ ነው፡፡ ቀን አልፎ ቀን እየተተካ መሄዱ በራሱ የግፉዓኑን በሕይወት መኖር ጥርጣሬ ላይ እየጣለው መጥቷል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ቃጠሎው የዓለምአቀፉን ሚዲያ ትኩረት መሳቡ በህወሃት ላይ ከፍተኛ ጫና እያመጣ ነው፡፡ “አብቅቶልሃል” ባሉት አንጋሾቹ ዘንድ ይህ ዓይነቱ አካሄድ ብዙም የሚወደድ ባለመሆኑ ህወሃትን ውጥረት ውስጥ ከቶታል። ዜጎችን በግፍ እየጨፈጨፈ ያለው ህወሃት ከአንጋሾቹ ጋር ፍጥጫ ውስጥ በመግባቱ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የሚታየው ነገር “ስሉሱ” የዞረ መሆኑን የሚያመካልት ሆንዋል። እየተገደሉ ያሉትን ዜጎች በተመለከተ ለተባበሩት መንግሥታት መርማሪ ቡድን ህወሃት/ኢህአዴግ በሩን መክፈት እንዳለበት አክርረው የተናገሩት ሳማንታ ፓወር ህወሃት ዜጎችን እየፈጀ መሆኑን ሲናገሩ በዲፕሎማሲያዊ ቋንቋ የጸጥታ ኃይላት “ከልክ ያለፈ ኃይል” መጠቀማቸውን ይፋ አድርገዋል፡፡ የሁልጊዜ የፖለቲካ ወዳጅ ከሌላት አሜሪካ እንዲህ ያለ የከረረ ነገር መስማት የማይወደው ህወሃት በቂሊንጦ ጉዳይ ውሳኔውን ይፋ ለማድረግ መስማማት አቅቶታል፡፡ ይህም ከአንጋሾቹና ከዓለምአቀፍ ሚዲያ ከሚመጣው ተጽዕኖ ጋር ተዳምሮ ኅልውናውን የሚፈትንበት ሰዓት ላይ አድርሶታል፡፡ “እስከ አርብ ጠብቁ” ብሏል! ሰሞኑን የቀድሞው የበረሃ ጓድ እና የድል ተካፋይ ታምራት ላይኔ ከኤስቢኤስ ሬዲዮ ጋር በሁለት ክፍል ባደረጉት ቃለምልልስ የቀድሞ ጓዶቻቸው ምን ማድረግ እንዳለባቸው በርካታ ምክር ሰጥተዋል፡፡ የወቅቱን የሕዝቡ ጥያቄ “በምን ዓይነት መልኩ እንፍታው በሚለው ጥያቄ ላይ የኢህአዴግ መሪ አካላት (ህወሃትን ማለታቸው ነው) ወታደራዊውና ሲቪል መሪዎች በጉዳዩ ላይ አንድ ቁመና ይዘው የማይገኙበት ሁኔታ ይፈጥራል፤ … ቅራኔው ስለተባባሰ በዚህ እንሂድ ወይስ በዚያ እንሂድ በሚለው ጉዳይ ላይ” የማይቀር ክፍፍል እንደሚከሰት ተናግረው ነበር፡፡ የቂሊንጦ ሟቾችን በተመለከተስ? የሟቾችን ማንነት ይፋ ከማድረግ ጋር የተፈጠረ ነገር ይኖር ይሆን? ስምምነት ወይስ መለያየት? ከአርብ በፊት የታሰበውስ ምንድነው? አንዳንድ “ታማኝ ጋዜጠኞች” በፌስቡክ ገጻቸው “የሟቾች ስም ዝርዝር ሃሙስ ይለጠፋል” እያሉ ነው። የሰው ልጅ ሞት እንደ ኮንዶሚኒየም ወይም እንደ ትምህርት ፈተና ውጤት ወይም “ስማቸው ይለጠፋል” ማለት ሰብዕና የሌለው ህወሃት ራሱ የሚመልሰው እንኳን አይደለም፡፡ ውዶቻቸው የሞቱባቸውና ያልሞቱባቸው እንደ ሎተሪ ዕጣ ነገ ስማቸው ሲለጠፍ ያያሉ፤ ለመሆኑ የህወሃት ግፍና የጭከና መጠን የሚለካበት ገደብ ይኖር ይሆን? ጉዳዩ የታዋቂ ፖለቲከኞች ጉዳይ ስለሆነ ብቻ አይደለም፤ የማንም ህይወትስ ቢሆን እንዴት “የስም ዝርዝር ይለጠፋል” ይባላል? በተመሳሳይ የቂሊንጦ እስር ቤት የተፈጸመውን አሳዛኝ ትራጀዲ አዲስ ስታንዳርድ (addis standard) ሲዘግብ “እስረኞች ሲረሸኑ አየሁ” ያለ እማኝ ጠቅሶ ጽፏል። ቃጠሎው ሲደርስ በቂሊንጦ እስር ቤት ጥበቃ ላይ የነበረ የዓይን እማኝ ጠቅሶ የሚሰቀጥጥ መረጃ ያስነበበው አዲስ ስታንዳርድ እስረኞች ላይ ጥይት መርከፈከፉን አርጋግጧል። እንደ ዘገባው ከሆነ የጥበቃ ሰራተኛው ማንነቱ እንዳይጠቀስ ጠይቆ፣ ቂሊንጦ እስር ቤት ሰራተኛ መሆኑንን የሚያረጋግጥ የስራ መታወቂያውን አያይዞ ነው እልቂቱን በኢሜይል ያጋለጠው። የዓይን ምስክሩ እንዳለው እሳቱ እንደተነሳ 5 እስረኞች ከሁለት ማማ ላይ በተቀመጡ ጠባቂዎች ተገድለዋል። እሳቱን ለማጥፋት ሲረባረቡ የነበሩ እስረኞች ላይ የጥይት እሩምታ ሲወርድባቸውም ተመልክቷል። የ18 እስረኞች አስከሬን ከእስር ቤቱ ሲወጣ ማየቱን የተናገረው የዓይን እማኝ፣ ሁሉም በጥይት መገደላቸውንና እሳት የሚባል ነገር እንዳልነካቸው ያየውን መስክሯል። የእማኙ ገለጻ በቂሊንጦ እስር ቤት ታሳሪዎች “በጅምላ ተጨፍጭፈዋል” የሚለውን ዜና ያጠናክረዋል። በፋሽስት የሚመሰለው ህወሃት “ለማምለጥ የሞከሩ” ሲል የጠራቸው ሁለት እስረኞች በጥይት መገደላቸውን፣ 21 ደግሞ እሳትና ጭስ ተባብረው እንደገደሏቸው የፋሽስት ልሳን የሆነው ራዲዮ ፋና መዘገቡ አይዘነጋም። “የእርም ሽንት፣ የባንዳ ዘር ፍሬ” የሚባለው ፋና የፊታችን ዓርብ ውይም ሐሙስ ደግሞ ምን እንደሚል ይጠበቃል። ማሳሰቢያ፤ በተለይ በስም ወይም በድርጅት ስም እስካልተጠቀሰ ድረስ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® ላይ የሚወጡት ጽሁፎች በሙሉ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ®ንብረት ናቸው፡፡ ይህንን ጽሁፍ ለመጠቀም የሚፈልጉ ሁሉ የዚህን ጽሁፍ አስፈንጣሪ (link) ወይም የድረገጻችንን አድራሻ (https://www.goolgule.com/) አብረው መለጠፍ ከጋዜጠኛነት የሚጠበቅና ህጋዊ አሠራር መሆኑን ልናሳስብ እንወዳለን፡፡
ክርስቶስ በደረሰበት ከፍተኛ ድብደባ ምክንያት በመድከሙ፥ ሮማውያን ስምዖን መስቀሉን ተሸክሞ ክርስቶስ ከሁለት ወንበዴዎች ጋር ወደሚሰቀልበት ከከተማ ወጣ ያለ ስፍራ እንዲያደርስ አስገደዱት። ብዙውን ጊዜ ወንጀለኞች ወንጀላቸው የተዘረዘረበት ጨርቅ ከአንገታቸው ላይ ይደረግና መስቀሉን ተሸክመው ወደሚሰቀሉበት ስፍራ እንዲወሰዱ ይገደዱ ነበር። ማርቆስ መስቀሉን የተሸከመው ስምዖን፥ የአሌክለንድሮስና የሩፎስ አባት እንደነበር ገልጾአል። ጳውሎስም በሮሜ 18፡13 ሩፎስን ስለሚጠቅስ፥ እነዚህ ሰዎች ምናልባትም በሮም የሚኖሩ ክርስቲያኖች ሳይሆኑ አይቀሩም። ስቅላት እጅግ አስከፊ የግድያ ዘዴ በመሆኑ፥ ባሮችና ከፍተኛ ወንጀል የሚፈጽሙ ሰዎች ወይም አማፅያን ብቻ በዚህ ዓይነት ይገደሉ ነበር። የአይሁድ መሪዎች ለክርስቶስ በነበራቸው ከፍተኛ ጥላቻ ምክንያት ለዚህ ቅጣት ዳረጉት። በእጆቹና በእግሮቹ ላይ ምስማሮችን ቸነከሩባቸው። በዚህ ዓይነት ስቅላት የሚቀጡ ሰዎች ነፍሳቸው እስኪወጣ ድረስ በአብዛኛው ከሁለት እስከ ሦስት ቀናት ይሠቃዩ ነበር። የተሰቀለው ሰው ቶሎ እንዲሞት ለማድረግ፥ አንዳንድ ጊዜ ወታደርች ቅልጥሙን ይሰብሩ ነበር። ክርስቶስን የሰቀሉት ወታደሮች የክርስቶስን ልብስ ተከፋፈሉ። ከሦስት ሰዓት ጀምሮ እስከሞተበት ዘጠኝ ሰዓት ድረስ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ዋለ። ክርስቶስ ከሚቀበለው ሥጋዊ ሥቃይ በላይ ሰዎች በቃላት ይዘልፉት ነበር። ከሁሉም በላይ፥ ክርስቶስ የዓለምን ኃጢአት በመሸከሙ ምክንያት እግዚአብሔር አብ ከእርሱ ጋር የነበረውን ኅብረት አቋረጠ። ክርስቶስ በታላቅ ድምፅ ጮኾ መሞቱ፥ ክርስቶስ ነፍሱን እንደ ሰጠ ያመለክታል። ብዙውን ጊዜ የስቅላት ቅጣት የሚፈጽምባቸው ሰዎች እየተዳከሙ ሄደው ራሳቸውን ይስቱና በዚያው ያርፋሉ። በዚህ ጊዜ ማርቆስ ስለ ክርስቶስ አንድ መልካም ቃል ብቻ ተናግሯል። ክርስቶስ በሚሞትበት ጊዜ አይሁዶች ምን እየሆነ እንዳለ ወይም ክርስቶስ የተለየ ሰው መሆኑን አልተገነዘቡም ነበር። ነገር ግን ቀደም ሲል ብዙ ሰዎች ሲሰቀሉ የተመለከተው የሮም ወታደር፥ ክርስቶስ የተለየና የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ ተገነዘበ። የአርማቲያሱ ዮሴፍ ጲላጦስ የክርስቶስን አስከሬን እንዲሰጠው በጠየቀ ጊዜ፥ ጲላጦስ ክርስቶስ ቶሎ በመሞቱ ተደነቀ። የመቶ አለቃው ክርስቶስ መሞቱን ካረጋገጠ በኋላ፥ ዮሴፍ የክርስቶስን አስከሬን ለመውሰድ ፈቃድ አገኘና በራሱ መቃብር ውስጥ ወስዶ ቀበረው። በመጨረሻም፥ ከዮሴፍና ኒቆዲሞስ በተጨማሪ ለክርስቶስ ትኩረት ሰጥተው የቆዩ ሦስት ብቸኛ ሰዎች ነበሩ። እነርሱም ከክርስቶስ ጋር የኖሩ ሴቶች ሲሆኑ ክርስቶስ ሰባት አጋንንት ያወጣላት መግደላዊት ማርያም፥ የታናሹ ያዕቆብና የዮሳ እናት የሆነችው ማርያም፥ የዮሐንስና ያዕቆብ እናት የሆነችው ሰሎሜ ከእርሱ ጋር ቆዩ። አሥራ ሁለቱ ደቀ መዛሙርት ከሸሹ በኋላ፥ እነዚህ ሴቶች ጌታቸው ሊሞትና ሲቀበር ለማየት እዚያው ቆዩ። የውይይት ጥያቄ፡- ብዙውን ጊዜ ወንዶች ከሴቶች በላይ ደፋሮች እንደሆኑ ይነገራል። በዚህ ጊዜ ግን ሴቶች ከወንዶች በላይ ደፍረው የተገኙት ለምን ይመስልሃል? ይህ እነዚህ ሦስት ሴቶች ለክርስቶስ ስለነበራቸው የእምነት ጥልቀት ምን ያስተምራል? መጀመሪያ የማርቆስን ወንጌል ያነበቡ ብዙ ሰዎች ከፍተኛ ስደት ደርሶባቸዋል። አንዳንዶች በእንስሳት ቆዳ ተሸፍነው ለዱር አራዊት ተጥለዋል። ሌሎች ዘይት ተርከፍክፎባቸው በስታዲዮም እንደ ጧፍ እየነደዱ ብርሃን እንዲሰጡ ተደርገዋል። ከወታደሮች ወይም ከአናብስት ጋር ለመታገል የተገደዱም ነበሩ። አንዳንዶች እንደ ክርስቶስ ተሰቅለዋል። ነገር ግን ስደቱ ምንም ያህል ከባድ ቢሆንም፥ ጌታቸው ክርስቶስ በስቅላት እንደ ሞተ በመገንዘብ ይጽናኑ ነበር። የእርሱ ሞት ለአሟሟታቸው አርአያ ነበር። ጳውሎስ በኋላ እንደገለጸው፥ ክርስቲያኖች መከራ በመቀበልና በመሠዋት ለቤተ ክርስቲያን የጎደለውን ይፈጽማሉ (ቆላ. 1፡24)። (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)
እናፍቃለሁ… የውዳሴ እና የምስጋና ግጥም የምጽፍለት መሪና ስርዓት እንድናገኝ። እኩል ተወዳድሬ የምሰራበትና፣ በታማኝነት “ይኸው ይሄን ያህል ገቢ አገኘሁ። ተመኑን ቁረጥና አገሪቷን አቅናበት፣ ሕዝቡን አንቃበት።” ብዬ የምገብርለት ስርዓት፥ ካፌ ቆጥቤ በሰጠሁት ብር ዱላና መሳሪያ ገዝቶ፤ በጠራራ ፀሐይ በ“ለምን አየሁህ” ደምፉ፣ ሕዝብ የሚደበድብበት ወግ የሚቀርበት ቀን ይናፍቀኛል። በሰላም ወጥቶ መግባት፣ በስርዓት መኗኗሩ፤ …ማንበብና መጻፍ መቻሌን ማማረር፣ ማየትና መስማቴን መራገም የማቆምበት ቀን፤ …በገዛ መኝታ ቤቴ ስነቃ፣ በገዛ አገሬ ጎዳናዎች ስራመድ እንግዳነት የማይሰማኝ፤ …በነጻነት ስሜት፣ የነጻነትና የፍቅር ግጥሞችን ብቻ የምጽፍበት ቀን ይናፍቀኛል። ጥበቃዬ ከዳር ደርሶ፣ መገናኘትን ማንቆላጰስና፣ የሰው ልጆችንና መኖርን ማወደስ እናፍቃለሁ። ያረገዘች በሰላምና በጤና የምትገላገልበት፣ የተወለደ የሚያድግበት፣ ያደገም የነፍሱን መሻት የሚከውንበት፣ ሰው ተምሮ የሚያገለግልበት፣ በስተርጅናም በክብር ቆይቶ በደስታ የሚሰናበትበት ኑሮ እናፍቃለሁ። ፅዱና አረንጓዴ አዲስ አበባና ሌሎች ክፍላተ አገራት… ተመጥኖ በተሰጣት ቀንና ማታ ለ13 ወራት በጸሐይ አሸብርቃ፣ መስከረም ሲጠባ አደይ አበባና የመስቀል ወፍ የሚያጌጡባት ዘረኝነት ያላጠቃት ኢትዮጵያ ትናፍቀኛለች። ወጣቶች በተስፋ መቁረጥ የማይኖሩባት፣ እናቶች ለልመና የማይወጡባት፣ ህጻናት በየጎዳናው የማይበተኑባት አገሬ ትናፍቀኛለች። ይገርመኛል፥ “መጽሐፎችህ ጨለምተኞች ናቸው” ሲሉኝ፤ “ግጥሞችህ፣ እንዲሁም ፌስቡክ ላይ የምትለጥፋቸው ጽሁፎች ጨለምተኞች ናቸው።” ሲሉኝ። ኑሮዬን የሚያውቁት ይመስል ቀለምና የብርሃን ዓይነት ሲመርጡለት ሳይ ይገርመኛል። “እንዲህ አጠቋሩረኸው ስታበቃ “የብርሃን” ማለትህ ሽሙጥ ነው?” ይሉኛል፤ …ብርሃን መውደዴን፣ ብርሃን መናፈቄን ሳያውቁ። ሀሳቤን መግለጼን እንጂ፥ መንጻት፣ መጥቆራቸውንስ አውቃለሁ? ብርሃንን መተረክስ አይቀልም? ደግሞ “ጆ ሁለቱንም መጽሐፍቶችህን በ3 ዓመታት ልዩነት ልክ ግንቦት 8 ያደረግከው ለምንድን ነው?” ተብዬ ለብዙኛ ጊዜ ተጠየቅኩኝ። ባጋጣሚዎች ሳልመልሰው ያልፋል። ምክንያቴን የልደት ቀኗ ግንቦት 8 ለሆነችው ወዳጄ Kal Kidan ብቻ ነበር ነግሬያት የማውቀው። “የ1981 ዓመተ ምህረቱ መፈንቅለ መንግስት ናፋቂ ሆነህ ነው እንዴ?” ብሎ ያስፈገገኝም አለ። ዛሬ ላውራው እስኪ… “ብርሃን ብርሃን” ማለቴ፣ መጽሐፎቼን ግንቦት 8 ለማስመረቅ መፈለጌም፥ በግንቦት 7 ቀን፣ 1997 ቁጭት የተደባለቀበት ትዝታ ነው። ብርሃን ናፍቄ ነበር። ‘ምርጫው ለውጥ ያመጣልናል፣ ከዴሞክራሲ ጋርም ያስተቃቅፈናል’ ብዬ፣ በከፍተኛ መጓጓት እና መቁነጥነጥ ውስጥ ሆኜ ነበር ደርሶ ማለፉን የምጠብቀው። ሰው ለመምረጥ እንደዚያ ይስገበገባል?? (ዴሞክራሲ ግን ለምን የማናውቀው ቦታ የሄደብንና መምጫውን የማናውቅ ዘመድ ይመስለኛል?) የግንቦት7 ማግስት…ግንቦት 8ን ለብስራት ነበር ያለምኳት፤ ለለውጥ እና ለነጻነት ግጥሞች ነበር ተስፋ ያደረግኳት፤ ለመተቃቀፍና በደስታ እንባ ለመራጨት ነበር ያሰብኳት። የብርሃን ነዶዎች ዙሪያዬን እየከበቡ ያቃዡኝ ነበረ። በኑሮዬ ጣሪያ ቀዳዳዎች ሾልከው ሾልከው ወለል ላይ የቆሙ የብርሃን በትሮች፥ የተስፋ ምርኩዝ ሆነውኝ ያጽናኑኝ ነበረ። እንደ“ይቺን ብላ! ዶሮ ማታ”… ‘ሲነጋ ባህሩ ይከፈልልንና ተሻግረን አገራችን እንገባለን።’ እል ነበር ለራሴ። ፍትህ ተከብሮ፣ ሰዎች ዋጋ እንደተከፈለባቸው በክብር ሲኖሩ እየታየኝ ብቻዬን ያስወራኝ እንደነበረ የትናንት ያህል ትዝ ይለኛል። እኩል፥ ልቀላቀል የምችለው ከሙስና የፀዳ የሥራ ዓለምና መመረቄም ይናፍቁኝ ነበር። በልቤ፥ የምጽፋቸውን የደስታ ግጥሞች እያሰብኩ በቀብድ ‘poegasm’ ላይ ደርሼ አውቃለሁ። …ይናፍቁኛል እነዚያ ጊዜያት! ወደው የማያገኙትን ሰው ሲጠብቁ፥ ቁርጡ ቀን ባያልፍ ያስሸልላል። የወዳጅ ዘመድ “አይዞህ”… “እየጠበቅኩ ነው” የማለት ማጽናናት ጫፍ ላይም አይደርስም። ሲነጋ ግን እንዳይሆኑት ሆኖ ዛሬም ድረስ “እህህ” እያስባለን ያለ ነገር ተከሰተ። ጭራሽ 5 ዓመት ተቆጥሮ ጉድ አፍርቶና ጎምርቶ “100% ተመርጠናል” ብለው አረፉት። ይኸው ቀን ጠብቆ የታፈኑ ድምጾች በየቦታው ስርዓቱን ሲያወግዙ ተሰሙ። ምላሹም “እንካ ቅመስ” ሆነ። በጸሐይ ደም የትም ፈሰሰ። እስሩም ድብደባውም በገፍ ሆነ። ሆኖም፥ “ኧከሌ ታሰረ” ሲባል፥ “አርፎ አይቀመጥም ነበር።” ይሉ የነበሩ ሰዎች ዐይናቸው ተገለጸ። “እነ ኧከሌ በጸረ ሽብር አዋጁ ክስ ተመሰረተባቸው” ሲባል “የሆነ ነገር ሳያኖርማ…” ይሉ የነበሩ ሰዎች ከእውነታው ጋር ተፋጠጡ። “ፖለቲካና ኤሌክትሪክ በሩቁ” የሚሉ ወዳጆች፥ በግድ ዙሪያቸው ስለሚከናወነው ነገር ማወቅ፣ መጠየቅና ምሬትን መግለጽ ጀመሩ። የጭቆና መብዛት፥ የግዱን የነዋሪዎችን ዐይን ይገላልጣል። ይኼ እንደ ጥሩ ጭላንጭል ኾኖ ያጽናናል እንጂ፥ የተደረገብን ነገር፣ ለመናገር ያከብዳል። ዝም ለማለትም ይጨንቃል። መናፈቅ ግን አይከለከልም! …ዛሬም ብዙ ብዙ ነገር እናፍቃለሁ! ጊዜና ባለጊዜ አልፈው፥ እንደምርጫ 97 ተስገብግቤ ቀበሌ ሄጄ የምመርጥበት ሰልፍና፣ በልቤ ስዬው እንደነበረው ዓይነት የምርጫ ማግስት እናፍቃለሁ! አንሙትማ! Rate this: Posted on August 15, 2016 September 1, 2016 Categories UncategorizedTags EthiopiaLeave a comment on ብርሃን፣ ግንቦት 8 እና ናፍቆት…
ብሰንኪ ለበዳ ኮቪድ19ን ኵናትን ንክልተ ዓመታት ኣብ ወረዳ ዋጃ ኣላማጣ ተቛሪፁ ዝነበረ ከይዲ ምምሃር ምስትምሃር ምጅማሩ እቲ ወረዳ ኣፍሊጡ።ድሕሪ ሰላሳ ዓመታት ንፈለማ ግዜ ብቋንቋ ኣምሓርኛ ትምህርቲ ከምዝጀመረ ተፈሊጡ። ይኹን እምበር ክምሃሩ ካብ ዝግብኦም ተማሃሮ 10 ሚእታዊት ጥራይ ይመሃሩ ምህላዎም ተገሊጹ። ሓላፊ ማሕበራዊ ዘፈር ግዚያዊ ምምሕዳር ዋጃ ኣላማጣ ኣቶ ሙሉጌታ ኣስማማው ምምሃር ምስትምሃር ኣብዚ ሰሙን ክቕፅል ምስተገበረ ብ ቋንቋ አደ ናይ ምምሃር ሕቶ ብዝተወሰነ ደረጃ ተመሊሱ ኣሎ ኢሎም። ተወካሊ ሓላፊ ቤት ፅሕፈት ትምህርቲ ወረዳ ራያ ኣላማጣ ኣቶ ተካ ንጋቱ ኣብቲ ወረዳ ክምሃሩ ዝግብኦም ልዕሊ 19,000 ተማሃሮ እንተኾኑ እውን ኣብ ሓደ ካልኣይ ደረጃ ቤት ትምህርትን 14 ቀዳማይ ደረጃ ኣብያተ ትምህርቲ ይመሃሩ ዘለው 1,140 ተማሃሮ እዮም ኢሎም። ዕለታዊ ፈነወ ድምጺ ኣመሪካ 08/12/2022 ፈነወ ትግርኛ ሓሙስ ፈነወ ትግርኛ ብናይ`ዚ መዓልቲ ዓበይቲ ዜና ይጅምር ። ካብ ኤርትራን ኢትዮጵያን ዝረኽቦም ቃለ-መጠይቓትን ሰሙናዊ መደባትን ድማ የስዕብ ። ሰሙናዊ መደባት ሓሙስ፡ መንእሰያት/ ጥዕና
በኢትዮጲያ የውስጥ ጉዳይ ላይ በመግባት የዕጅ መጠምዘዝ ስራ ለመስራት በሚሞክሩ ተቋማት እና የታላቁ ህዳሴ ግድብ ስራ እንዲስተጓጎል በሚሰሩ አካላት ላይ ተቃውሞ ለማሰማት ሰላማዊ ሰልፍ ይደረጋል ተብሏል፡፡ የሰላማዊ ሰልፉ ዋነኛ አላማ የኢትዮጲያ ህዝብ በሀብቱ ለመጠቀም የማንንም ፈቃድ የማይሻ እና በዚህ ጉዳይ ላይ የማይደራደር መሆኑን ለዓለም ህዝብ ለማሳወቅ ነው ተብሏል፡፡ ስለ ኢትዮጲያ ትክክለኛ መረጃ ለዓለም እንዳይደርስ በሚሰሩ ሀገራት እና አለምአቀፍ ሚዲያዎች ላይ ተቃውሞ ለማሰማት ህዝባዊ ሰልፍ ለማዘጋጀት ዝግጅታቸውን ማጠናቀቃቸውን አስተባባሪ ኮሚቴዎች ዛሬ በሰጡት መግለጫ ላይ አሳዉቀዋል፡፡ በመሆኑም መላ የሃገሪቱ ህዝብ እና የኢትዮጲያ ወዳጅ የሖኑ የውጭ ሀገር ዜጎች እና ተቋማት ህዝባዊ ሰልፍ በሚከናወንበት እለት አጋርነታቸውን እንዲያሳዩ ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡ ሰላማዊ ሰልፍ የፊታችን መጋቢት 19 የሚደረገ ሲሆን በመስቀል አደባባይ ከጠዋቱ 3 ሰዓት ጀምሮ ይካሄዳል ተብሏል፡፡ የሰላማዊ ሰልፍ አስተባባሪ ኮሚቴዎች እንደተናገሩት፣ ህዝባዊ ሰልፉን ለማድረግ የሚመለከታቸው አካላት ፈቃድ እንዲሰጣቸው ከሳምንት በፊት ያቀረቡ ሲሆን፣ ተቋሙ ተቀብሏቸው የራሱን ዝግጅት እያደረገ ይገኛል ሲሉ ኮሚቴዎቹ ገልፀዋል፡፡
በጁላይ 6፣ የማሰብ ችሎታ ያለው ብጁ የቦርድ ጨዋታ ፈጠራ መድረክ “CubyFun” በቅርቡ ከፕሮፌሰር ጋኦ ቢንግኪያንግ እና ከቻይና የብልጽግና ካፒታል ጋር ከሌሎች ባለሀብቶች ወደ 10 ሚሊዮን ዩዋን የሚጠጋ የገንዘብ ድጋፍ መልአክ አግኝቷል።አብዛኛው የተቀበለው ፈንድ ለምርት ልማት እና ለሰርጥ ማስፋፊያ የሚውል ነው። በአሁኑ ጊዜ የቴክኖሎጂ እድገቶች በዋነኛነት በምናባዊ ጨዋታዎች እና በሞባይል ጨዋታዎች ውስጥ የተካተቱ ናቸው።ነገር ግን፣ ለአዲስ የቦርድ ጨዋታ፣ ከመስመር ውጭ ጨዋታ አይነት አሁንም ብዙ ቦታ አለ፣ እና ለብዙ አመታት ባህላዊ ሆኖ ይቆያል።ይህ ፈጣን የማህበራዊ ጨዋታ ከቴክኖሎጂ እና ብልህነት ጋር መቀላቀል እንዳለበት ግልጽ ነው።በዚህ ምክንያት የሼንዘን ኩባንያ CubyFun እራሱን ያዳበረ የማሰብ ችሎታ ያለው የቦርድ ጨዋታ አስተናጋጅ ምርት JOYO ን ለመክፈት እና በባህላዊው የቦርድ ጨዋታ ላይ አስተዋይ የሆነ መስተጋብር ለመፍጠር እየሞከረ ህጻናትን እና ወጣቶችን ከስክሪኑ በማራቅ እና ፊትን እንዲመሩ ያስችላቸዋል። - ፊት ለፊት መስተጋብር.በተጨማሪም CubyFun በ iPad APP መልክ የቦርድ ጨዋታ ፈጠራ መድረክን POLY በተሳካ ሁኔታ ጀምሯል፣ በዚህም ተራ ተጠቃሚዎች የራሳቸውን ብልህ ብጁ የቦርድ ጨዋታ መፍጠር ይችላሉ። የCubyFun መስራች ሱ ጓንዋ እንዳብራሩት የማሰብ ችሎታ ያለው የቦርድ ጨዋታ አስተናጋጅ ምርት ከመስመር ውጭ ጨዋታዎች መቀየሪያ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል።በአስተናጋጁ ውስጥ ከፍተኛ ትክክለኛነትን እና ምስላዊ ማወቂያን እና ሌሎች ዳሳሾችን በማዘጋጀት ከመስመር ውጭ የማሰብ ችሎታ ያለው መስተጋብር ለማግኘት የተጫዋቹን የተግባር አቀማመጥ፣ የምልክት ዳኝነት እና አስተዋይ ዳኛ ለይቶ ማወቅ ይችላል። የCubyFun ዋና አባላት በዋናነት ከዲጄ-ኢኖቬሽንስ የመጡ ናቸው።መስራቹ እና ዋና ስራ አስፈፃሚው ሱ ጓንዋ በአንድ ወቅት ለ Evernote ፣ Sinovation Ventures እና DJ-Innovations ሰርተዋል ፣ በ RobomasterS1 ፣ Spark Drone ፣ Mavic drone ፣ Osmo handheld gimbal እና ሌሎች ምርቶች ምርምር እና ልማት ላይ ተሳትፈዋል። የዚህ ዙር ባለሀብት የሆነው የቻይና ብልጽግና ካፒታል ቡድን፣ “ከአስደናቂ የፈጠራ እና የፈጠራ ችሎታው ጋር፣ የኩቢፈን ቡድን ፕሮጀክቱን ለመጀመሪያ ጊዜ ስንገናኝ በጣም አስደነቀን።ከዲጂአይ የመጣው መስራች ቡድን በርካታ የማሰብ ችሎታ ያላቸውን የሃርድዌር እና የሶፍትዌር ምርቶችን በማዘጋጀት ጥሩ ውጤት በማስመዝገብ ተሳትፏል።እራስን የመማር እና የመድገም ችሎታ ያለው ቡድን የፈጠራ እና የማሰብ ችሎታ ያላቸውን ምርቶች በመፍጠር የራሱን የምርት ስም መገንባት ሊቀጥል ይችላል ብለን እናምናለን።
የዩክሬን ፕሬዚዳንት ቮሎድሚር ዘለንስኪ የዩክሬን እና የራሽያ ሀይሎች በሲቪሮዶኔትስክ ለሚገኘው እያንዳንዷ ስንዝር መሬት እየተዋጉ መሆናቸውን ገልፀው፣ ዩክሬን ዘመናዊ የሚሳይል መቃወሚያ ሥርዓት ያስፈልጋታል ሲሉ ዓለም አቀፍ አጋሮችን ተማፅነዋል። ዘለንስኪ ምሽቱን በቪዲዮ ባስተላለፉት መልዕክት የሩሲያ ቁልፍ ኢላማ አለመቀየሩን እና በሲቪሮዶኔትስክ ምዕራብ እና ደቡብ ምዕራብ ወደሚገኙት ሊሲቻንስክ፣ ባከሙት እና ስሎቭያንስክ ከተሞች እየገፉ በሆኑን ተናግረዋል። የዘለንስኪ አማካሪ ሚኻይሎ ፖዶሊያክ ሰኞ እለት ባስተላለፉት የትዊተር መልዕክት "ጦርነቱን ለማስቆም ከፍተኛ የጦር መሳሪያዎች ያስፍለጉናል" በማለት የሚያስፍለጉዋቸውን የመሳሪያ አይነቶች እና ብዛት በዝርዝር አስፍረዋል። የመከላከያ ሚኒስትር ወኪሎች ረቡዕ እለት በብራስልስ ስብሰባ እንደሚያካሂዱ በመግለፅም ውሳኔያቸውን እንደሚጠባበቁ አስታውቀዋል። በሁለቱም ወገኖች በኩል እየደረሰ ያለውን ጉዳት ማረጋገጥ ባይቻልም በሩሲያ በኩል የሟቾች ቁጥር ከ40 ሺህ እንደሚበልጥ ዘለንስኪ በዚህ ወር ገልፀው ነበር። የእንግሊዝ መከላከያ ሚኒስቴር በቅርብ ቀናት በሲቪሮዶኔትስክ እየተደረገ ያለው ውጊያ የሚያስቆጣ መሆኑን በመግለፅ ሩሲያ ወንዝ አቋራጭ ውጊያዎችን የማካሄድ አቅሟ በቀጣይ ጦርነቱ ላይ ትልቅ ሚና የሚጫወት ይሆናል ብለዋል። ይህ በእንዲህ እንዳለ የዩናይትድ ስቴትስ የመከላከያ ሚኒስቴር ሎይድ ኦስቲን በኔቶ ዋና መቀመጫ ስብሰባ እያካሄዱ ሲሆን ባለፈው ግንቦት ወር በድህረገፅ አማካኝነት የተካሄደውን የኔቶ ስብሰባ ተከትሎ ዩክሬን በጦር ሜዳ የሚያካሂደውን እንቅስቃሴ አጠናክራ እንድትቀጥል ከዩክሬን ጋር ያለንን ጥምረት የበለጠ ለማስፋት እየጣርን ነው ብለዋል። ሩሲያ በአሁኑ ወቅት 97 ከመቶ የሚሆነውን የሉሃንስክ ግዛት መቆጣጠሯን ብታስታውቅም አብዛኛውን የዶምባስ ምስራቃዊ ክፍል ለመቆጣጠር በምታደርገው ጥረት የኢንዱስትሪ ማዕከል የሆነችው ሲቮሮዶኔትስክ ትልቅ ሚና ይኖራታል።
[ክፍል አራት] – የኦሮሚያ ክልል ፕሬዝዳንት ክቡር አቶ ለማ መገርሳ ባለፈው ሳምንት ነሐሴ 10/2009 በአዳማ ከተማ በተካሄደው የክልሉ የካቢኔ የዞንና የወረዳ አመራሮች የ2009 ዓመት አፈፃፀም እና የ2010 ዓመት እቅድ የግምገማና የውይይት መድረክ ላይ ያደረጉት ንግግር፡፡ (ከአፋን ኦሮሞ ወደ አማርኛ በHornAffairs የተተረጎመ) ድርጅታችንን ጠንካራ፣ የህዝቡን ጥያቄ መመለስ የሚችል፣ ብቁ እና በህዝቡ ዘንድ legitimacy ያለው ማድረግ አለብን፡፡ ስለዚህ ጠንክረን፤ ደከመን ሰለቸን ሳንል መስራት አለብን፡፡ ሞራሉ ተነሳስቶ፣ ተስፋን ሰንቆ፣ እውቅና የሰጠን፣ recognize ያደረገንን ህዝብ ልብ መስበር የለብንም፡፡ ትናንት እንደተናቅነው፣ ትናንት ህዝቡ አቆሽሾን እንደጠላን፣ ወደዚያ መመለስ የለብንም፡፡ እውነቴን የምላችሁ፤ ይሀ ህዝብ ብዙ ቀልቦናል፡፡ ብዙ ተሸክሞናል፡፡ ይሀ ህዝብ ባለፉት 25 ዓመታት ቀለበን፣ ቀለበን፣ ግን OPDO ማለት “ቢቀለብ ቢቀለብ የማያድግ ልጅ” ሆኖ ነው የቆየው፡፡ ይሀ ህዝብ ቢቀልበን ቢቀልበን ማደግ ያልቻልነው እኛ ነን፡፡ ከአሁን በኋላ ከዓመት እስከ ዓመት እየተቀለበ የማያድግ ልጅ መሆን የለብንም፡፡ ድርጅታችን ህዝቡ በሚፈልገው ደረጃ ማደግ መቻል አለበት፡፡ ህዝቡ በሚፈልገው ደረጃ vigilant ሆኖ፡ bold ሆኖ ወጥቶ፣ ለዚህ ህዝብ መብት ታግሎ የህዝቡን ጥቅም ማረጋገጥ መቻል አለበት፡፡ ድርጅታችን የዚህ ህዝብ ፍላጎት እና ተጠቃሚነትን ማረጋገጥ መቻል አለበት፡፡ መንግስታችንን ጠንካራ ማድረግ አለብን፡፡ ድርጅታችንንም ጠንካራ ማድረግ አለብን፡፡ ሊጠነክር የሚችለው ደግሞ በሁላችን ትግል ነው፡፡ ዛሬ ህዝቡ ጥሩ certificate ሰጥቶናል፡፡ ይሀን እውቅና የሰጠንን ህዝብ መዋረድ የለብንም፡፡ ዛሬ ህዝቡ የመጨረሻ እድል ሰጥቶናል፡፡ በታሪካችን ሰጥቶን የማያውቀውን እውቅና ሰጥቶናል፡፡ እኔ’ምላችሁ ነገር ቢኖር፤ በዚህ ትግል ውስጥ የምንቸገር ሰዎች ካለን፤ ገንዘብ የምንፈልግ ሰዎች ያለን እንደሆነ አስራሩ አለ፡፡ እናግዛችኋለን፣ ውጡና በጥቃቅን እና አነስተኛ ተደራጁ፡፡ እናግዛቿለን፣ ቃል እገባላቿለሁ፡፡ ማገዝ እንችላለን፡፡ ግን እሱ ራሱ መታገዝ የሚችለው ይህ ስርዓት ሲኖር ነው፡፡ ስለዚህ ማንም ወሬ በኩንታል እያመረተ ሊረብሸን አይገባም፡፡ አላማችን አንድ እና አንድ ነው፡፡ ለዚህ ህዝብ መታገል፡፡ እያንዳንዳቹ ወደዚህ ትግል ስትገቡ ለምን ዓላማ እንደሆነ ተመልሳችሁ እራሳችሁን ጠይቁ፡፡ እኔ ወደዚህ ትግል የገባሁት ለኦሮሞ ህዝብ ለመታገል ነው፡፡ የኦሮሞን ህዝብ ፍላጎትና ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ነው ወደ ትግሉ የገባሁት፡፡ ለምን? ፍላጎቴ እና ጥቅሜ የሚረጋገጠው፡ የኦሮሞ ህዝብ ፍላጎትና ተጠቃሚነት ሲረጋገጥ ስለሆነ፡፡ ይሀ ማለት ሌላውን መጥላት ማለት አይደለም፡፡ ይሀ ማለት ሌላው ላይ መዛት ማለት አይደለም፡፡ This is a logic. ይሀን መቀበል አቅቶት deny ማድረግ የሚፈልግ አለ፡፡ ከዚህ ህዝብ interest የሚበልጥብን ሌላ ግብ ሊኖረን አይችልም፡፡ ይሀን ማድረግ ካቃተን ትግሉን መልቀቅ ነው ያለብን፤ ህዝቡ ለራሱ ይታገል፡፡ አለበለዚያ bold ሆነን ህዝቡ በሚፈልገው ደረጃ በመገኘት በሀቀኝነት፣ በቅንነት፣ ቆራጥ ሆነን፣ ለቆምንለት ዓላማ ከልብ መታገል ነው ያለብን፡፡ አሁን አምኖን ከጎናችን የቆመውን ህዝብ ይዘን ጠንክረን መለወጥ መቻል አለብን፡፡ ከዚህ በፊት በህዝባችን ዘንድ እንደተናቅነው፡ ታሪካችንን ማበላሸት የለብንም፡፡ ለዚህ ትግል ዋጋ አስከከፈልን ድረስ ታሪካችንን ማበላሸት የለብንም፡፡ ጠንካራ ድርጅት መሆን ጀምረናል፡፡ ጠንካራ መንግስት መሆን ጀምረናል፡፡ ግን ፈፅሞ በቂ አይደለም፡፡ ገና ጅምር ላይ ነን፡፡ ድል ተቀዳጅተናል? አዎ! የነበረው አስከፊ ሁኔታን በመቀልበስ ድል ተቀዳጅተናል፡፡ መስራት ጀምረናል፡፡ ህዝቡ ከሚጠብቀው አንፃር ግን ገና ስራ አልጀመርንም፡፡ ስለዚህ ሁሉም ከክልል እስከ ቀበሌ ድረስ ሁሉም አመራር ስኬት ላይ ለመድረስ ከልብ በመናበብ፣ ከላይ እስከ ታች አንድ ቋንቋ በመናገር፣ ለጋራ ዓላማ ተሰልፎ በጋራ መታገል አለበት፡፡ ምን ይመጣል እያላችሁ ከሹመት ቦታ በመነሳት ስጋት የተለያየ illusion ውስጥ የገባችሁ አካላት፤ ሹመት ከሆነ የምትፈልጉት የሹመት ቦታ በቂ አለ፡፡ አያልቅም፡፡ እየሰራን ካለነው አኳያ ስራው ከዚህ በላይ ሃይል እየጠየቀ ነው ያለው፡፡ ግን useless የሆነ ሰው፣ ችግር መፍታት የማይችል ሰው፣ ውስጣችን ሆኖ ሊበጠብጠን አይችልም፡፡ ከስራው ይልቅ እሱ ራሱ የቤት ስራ ሆኖብን ጊዜ ልናቃጥልበት አይገባም፡፡ እንዴት ሞራላችን እንደተነካ፣ እንዴት ድርጅታችን በህዝቡ ዘንድ እንደቆሸሸ፣ እንዴት እንደተናቀ ሁላችሁም ታውቁታላችሁ፡፡ We have to change. ይሀን ታሪክ መቀየር አለብን፡፡ ይህን ታሪክ የምንቀይረው ደግሞ ወሬኛ እና ሌባን አቅፈን አይደለም፡፡ ሌብነት ነው በህዝቡ እንድንጠላ እያደረገን ያለው፡፡ ይሀን ከውስጣችን መጥረግ አለብን፡፡ ለቅመን ማስወገድ አለብን፡፡ ወዲህ ወዲያ ማየት የለብንም፡፡ ጠንከረን መስራት አለብን፡፡ እኔ ስለኦሮሞ ህዝብ ጥቅም ስለተናገርኩ የሚከፋው ሰው ካለ፤ መክፋት አይደለም ወደ ፈለገ ይገለባበጥ፡፡ ማህበር ለመጠጣት ወይም ፀበል ለመጠጣት አይደለም እኔ ወደዚህ ትግል የተቀላቀልኩት፡፡ ለዚህ ህዝብ ታግለናል እስካልን ድረስ፤ We have to protect the interest of this people. ለዚህ መስራት ነው፡፡ እኛ ይሀን ስንሰራ ስንቱ ነው ይሀ አይሆንም ያለን! ከውጭ ብቻ አይደለም እኮ! እዚህ እኛው ውስጥ ሆኖ ስንት ሴራና ደባ እኛ ላይ ለመስራት ሌተ’ቀን የሚተጋ ስንቱ አለ? ይሀን በትግላችን clear ማድረግ አለብን፡፡ ይሀ ድርጅትና መንግስት ህዝቡ አለኝታዬ ነው የሚለው መሆን አለበት፡፡ ደግመን ደጋግመን እየተናገርን ነው፡፡ ህዝቡን እንስማ፡፡ ከህዝቡ ጋራ ሆነን ህዝቡ የሚፈልገውን እንስራ፡፡ ሌላ ነገር አይደለም እንስራ እያልን ያለነው፡፡ Rocket science እንፍጠር እየተፈላሰፍን ከአቅማችን በላይ እንንጠራራ አይደለም እያለን አይደለም፡፡ ይሀ አይነት ፍላጎት የለንም፡፡ ለዚህ ህዝብ እንስራ ነው እያልን ያለነው፡፡ በየትኛውም ደረጃና በየትኛውም ቦታ ለዚህ ህዝብ ፍላጎትና ተጠቃሚነት እንቁም ነው እያልን ያለነው፡፡ ጠንክረን እንስራ ነው እያልን ያለነው፡፡ 25 ሙሉ ያልተሰራበትን የፊንፊኔ ልዩ ጥቅም ለማረጋገጥ ስንሰራ ማነው አይሆንም ያለን? የኦሮሞ ህዝብ ተጠቃሚነት ”አይ አይሆንም” ያለን ማነው? የተፋለመን ማነው? ይሀን ነው እያልን ያለነው፡፡ ጠንክረን መስራት አለብን፡፡ ሌላ አማራጭ የለንም፡፡ የሞተ ኦህዴድ ለኢህአዴግም አይጠቅምም፡፡ የተኮላሸ ኦህዴድ ለሀገሪቷም አይጠቅምም፡፡ ለሀገሪቷም ቢሆን ጠንካራ ኦህዴድ ነው የሚጠቅመው፡፡ ይህ ድርጅት ጠንክሯል እያለ ስጋት የሚሰማው ሰው ካለ ተሳስቷል፡፡ ይሀ ድርጅት ከጠነከረ ነው፣ የኦሮሚያ ክልል መንግስት ከጠነከረ ነው፣ ሀገሪቷም ሀገር የምትሆነውና የምትጠቀመውም፡፡ ሀገሪቷም የምትጠነክረው ያኔ ነው፡፡ ሌላውም ይሀን ማወቅ አለበት፡፡ ለዚህ ህዝብ ተጠቃሚነት ስለሰራን ብቻ በመጥፎ አይን መታየት የለብንም፡፡ ግን ደግሞ የፈለገ ሰው አይኑ መቅላት አይደለም ደሙ ይደፍርስ እንጂ፤ እኛ ነን በቀዳሚነት ለዚህ ህዝብ ጥቅም መታገል ያለብን፤ የዚህን ህዝብ ጥቅም ማሰጠበቅ ያለብን፡፡ ስለዚህ እንደ አመራር በአንድነት ጠንክረን በመስራት፣ ዳግም እድል ለሰጠን ህዝብ ውጤት ማሳየት አለብን፡፡ ከሰራን ደግሞ እንችላለን፡፡ ህዝቡ ይሰማናል፡፡ ትንሽዬ ሰርተን ላሳየነውም ይመሰክራል፡፡ ሌላው መታወቅ ያለበት ደግሞ፤ ይሀ ድርጅት ወድቆ አይወድቅም፡፡ የፈለገ እየዞረ ወሬ ይሸጣታል እንጂ፤ የፈለገ የሚያኖረው መስሎት በህዝብ እየነገደ ይኖራታል እንጂ፤ ይሀ ድርጅት ጠንካራ ህዝባዊ መሰረት አለው፡፡ ለመታገል 4 ሚሊዬን አይደለም 400 ሰው ይበቃል፡፡ የፈለገ ወደፈለገበት ቦታ መሄድ ይችላል፡፡ በትግል ሂደቱ ዋጋ ከፍለንበታል፡፡ ለዚህ ህዝብ ጥቅም ብለን ታመንበት፣ ተሰቃይተንበት፣ ህይወት አጥተንበታል፡፡ ስለፈለገ ማንም ሊያደናቅፈን አይችልም፡፡ ወዲያ ወዲህ ማለት ትተን ይህን ህዝብ፣ ይሀን ድርጅት፣ ይሀን መንግስት፣ በአግባቡ መምራት አለብን፡፡ በአግባቡ ለመምራት ደግሞ ሌቦችን፣ ወረኞችን፣ ውሸታሞችን፣ የሌብነት ሱስ ያለባቸው ሌቦችን፣ ፍርፋሪ ለቃቃሚዎችን፣ ከውስጣችን መጥረግ አለብን፡፡ አለበለዚያ የቆሸሸውን አቅፈን ህዝቡ እኛን ሊሆን አይችልም፡፡ ይህን ለማድረግ ደግሞ በምሬት እንታገላለን፡፡ እኛ የምንፈልገው የህዝባችን ከኛ ጎን መሰለፍ ነው፡፡ የፈለገ ወደ ፈለገው ይሂድ፡፡ ህዝባችን ከኛ ጋራ ከሆነ መስራት እንችላለን፡፡
ጉዳያችን - GUDAYACHN: ሰበር ዜና - ግንቦት 7 ንቅናቄ ''ልዩ መግለጫና ተግባሪዊ የመጀመሪያ እርከን የትግል ጥሪ'' በሚል ርዕስ ስር አዲስ የትግል ጥሪ አስተላለፈ።ጥሪው የመን፣እንግሊዝ እና ኢህአዴግ/ወያኔ ላይ ያነጣጠረ ነው ጉዳያችን - በጉዳያችን ሚድያ፣ኮምኒኬሽን እና ምክር አገልግሎት የሚዘጋጅ ሲሆን ከ2003 ዓም ጀምሮ በድረ-ገፅ ላይ የነበረ በአሁኑ ጊዜ ከአንድ ሚልዮን በላይ ጎብኚዎች ያሉት ገፅ ነው። Gudayachn is prepared by Gudayachn Multimedia, Communication and Consultant Organization. It has been online since 2011. Currently, Gudayachn is being visited by over One-million readers from all over the world. ወደ የሚፈልጉት ቋንቋ ይቀይሩ Translate to different Languages Sunday, July 6, 2014 ሰበር ዜና - ግንቦት 7 ንቅናቄ ''ልዩ መግለጫና ተግባሪዊ የመጀመሪያ እርከን የትግል ጥሪ'' በሚል ርዕስ ስር አዲስ የትግል ጥሪ አስተላለፈ።ጥሪው የመን፣እንግሊዝ እና ኢህአዴግ/ወያኔ ላይ ያነጣጠረ ነው የመንን በተመለከተ የየመን መንግሥት የዓለም ዓቀፍ ህግም ሆነ የየመን የራሷን ህግ በመተላለፍ መሪያችንን ለእርድ አሳልፎ ሰጥቶብናል። ከመጀመሪያው ጀምሮ ለየመን መንግሥት የተደረገው ተማጽኖ ሰሚ ጆሮ አላገኘም። እስካሁንም ድረስ የየመን መንግሥት አቶ አንዳርጋቸውን ማሠሩና ለወያኔ አሳልፎ መስጠቱ በይፋ አላመነም። እኛ ባለን መረጃ መሠረት በአይሮፕላን ማረፊያው ከማገት ጀምሮ በልዩ በረራ ወደ ኢትዮጵያ እስከ መላክ ድረስ ያለውን የውንብድና ሥራ በየመን በኩል ሆኖ የሠራው ቀጥታ ተጠሪነቱ ለየመን ፕሬዚዳንት የሆነው የስለላ ድርጅት ነው። በዚህም ሳቢያ የየመን መንግሥት ሊቀለበስ የማይችል እና በቀላሉ የማይፋቅ ታሪካዊ ስህተት ፈጽሟል። የየመን መንግሥትና ሕዝብ ይህን እንዲያውቁት ማድረግ ወቅቱ የሚጠይቀው የተግባር እንቅስቃሴ አካል ነው። የመንን በተመለከተ የሚቀጥለው ሳምንት ዘመቻችን ግብ ቁጣችንን የየመን ፕሬዚዳንት እና የየመን መንግሥት ብቻ ሳይሆን የየመን ሕዝብም እንዲያውቅ ማድረግ ነው። የሚከተሉት ተግባራት ለአብነት ያህል ተጠቅሰዋል። ለየመን ፕሬዚዳንት አዲስ መረር ያለ ደብዳቤ ተጽፎ በፋክስና በኢሜል በየመን መንግሥታዊ መሥሪያ ቤቶችና ኤምባሲዎች አድራሻዎች መላክ። በመልዕክት መጨናነቅ ከሚገባቸው የየመን ተቋማት አንዱ አዲስ አበባ የሚገኘው የየመን ኤምባሲ ነው። ኢትዮጵያ ውስጥ ሆናችሁ በዘመቻው የምትሳተፉ ጥንቃቄ እንዳይለያችሁ እናሳስባለን፤ የኢንተርኔትና የፋክስ መልክቶችን ስትልኩ ራስን ለጉዳት በማያጋልጥ መንገድ መደረግ ይኖርበታል። የየመን ኤምባሲዎችን ሥራ ማወክ በሚችሉ ሰልፎችና ተቃውሞዎች ማጨናነቅ። የፕሬዚዳንቱን ፎቶና የአገሪቱን ባንዲራ ማቃጠል። ይህ በውጭ አገራት ብቻ መደረግ ያለበት ነው። በውጭ አገራት በየከተሞች ለሚገኙ የየመን ኮሚኒቲዎች ደብዳቤ መፃፍና መንግሥታቸውን እንዲቃወሙ መገፋፋት፤ ይህንን ካላደረጉ ግን ከመንግሥታቸው ጎን ተሰልፈው በኢትዮጵያ ላይ ጦርነት እንዳወጁ የምንቆጥረው መሆኑን በማያሻማ መንገድ መንገር፤ በየመን አየር መንገድና በማናቸው የየመን የንግድ ድርጅቶችና ቢዝነሶች ላይ እቀባ ማድረግ፤ በቢዝነሶቻቸው ላይ አሉታዊ ቅስቀሳ ማድረግ። ይህ ተግባር በኢትዮጵያም ከኢትዮጵያ ውጭም በሚገኙ ኢትዮጵያዊያን መተግበር የሚኖርበት አቢይ ተግባር ነው። በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ የየመን ቢዝነሶችን መርጦ ምርቶቻቸው እና አገልግሎቶቻቸው እንዲጠሉ ማድረግ። ከእንግዲህ በየመን ገንዘብ የተሠራ ወይም ከየመን የመጣ ብስኩትም ይሁን ሲጃራ የወገናች ደም የነካው እቃ ነው። ብርታኒያን በተመለከተ የእንግሊዝ መንግሥት ማድረግ የነበረበትን እና ማድረግ ይችል የነበረውን ሁሉ አድርጓል ብለን አናምንም። እርምጃው ፈጣን አልነበረም፤ አሁንም አይደለም። ስለሆነም እንግሊዝን በተመለከተ የዘመቻችን ግብ የእንግሊዝ መንግሥት ለጉዳዩ ትኩረት በመንፈጉ መክሰስ እና ከአሁን በኋላም ተገቢውን ትኩረት ሰጥቶ እንዲከታተለውና መሪያችን እንዲያስፈታ መወትወት ነው። የሚከተሉት ተግባራት ለአብነት ተዘርዝረዋል። የእንግሊዝ መንግሥትን በህግ መክሰስ (ይህ በንቅናቄው ጽ/ቤት የሚሠራ ሲሆን ዝርዝሩ ወደፊት ይገለፃል)፤ ለውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አዲስ ደብዳቤ ጽፎ በፋክስና በኢሜል ለውጭ ጉዳይ ሚኒስትርና ለኤምባሲዎች በብዛት መላክ። አንዱ ትኩረት የሚደረግበት ኤምባሲ አዲስ አበባ የሚገኘው የእንግሊዝ ኤምባሲ ነው። ኢትዮጵያ ውስጥ በዘመቻው የሚሳተፉ ወገኖች አስፈላጊው ጥንቃቄ ማድረግ ይኖርባቸዋል። በለንደን በውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደጃፍ፤ በሌሎች አገሮች ደግሞ በእንግሊዝ ኤምባሲዎች ቁጣ የተቀላቀለበት የተቃውሞ ሰልፎችን ማካሄድ። ወያኔን በተመለከተ ወያኔን በተመለከተ የሚደረጉ ትግሎች በሙሉ ወያኔን ከስልጣን ማስወገድን ያነጣጠሩ መሆን ይኖርባቸዋል። ወያኔም ለመጣል ትልቁን ድርሻ የሚያበረክተው ሕይወታቸውን ለመስጠት የቆረጡ፡ ከቁም ውርደትና ባርነት ለነጻነትና ለፍትህ ከወያኔ ጋር ጉረሮ ለጉረሮ እየተናነቁ እየጣሉ ለመውደቅ ፤ መስዋእት ለመሆን በወሰኑ ኢትዮጵያዊያን ወገኖቻችንና የህዝብ ሃይሎች የሚያደርጉት ተግባራዊ እንቅስቅሴ ነው ፤ እንቀላቀላቸው። በተለያዩ ምክንያቶች ወሳኙን ትግል መቀላቀል የማይችሉ ወገኖቻችን በያሉበት ሆነው ከወያኔ የስለላ መረብ ተጠነቅቀው ራሳቸውን በቡድን ያደራጁ፤ ይህንኑ የሚያግዙ ተግባራት ለመፈጸም ራሳቸውን ያዘጋጁ። እነዚህ ተግባራት ወያኔን በገቡበት እየገቡ በማሳፈር ፤እረፍት በመንሳት፤ የፈፀሟቸውን ወንጀሎች በአደባባይ በመናገር እንዲሸማቀቁ በማድረግ፤ ማንነታቸው ለሸሪኮቻቸው ወይም ለሥራ ባልደረቦቻቸው በመንገር ወዳጅ በማሳጣት፣ ንግዶቻቸውን ኩባንያዎቻቸው እንዲከስሩ በማድረግ የፋናንስ አቅማቸው በማዳከም ረገድ የሚኖራቸው አስተዋጽኦ ቀላል እንዳልሆነ ሊታወቅ ይገባል። ከዚህ አኳያ ሊደረጉ ከሚገቡ ተግባራት የሚከተሉት በምሳሌነት ተዘርዝረዋል። በምዕራቡ ዓለም በተለያዩ ሽፋኖች ተሰግስገው ያሉት እና የሚመላለሱ ወንጀለኞች የወያኔ ሹማምንትና ደጋፊዎችን ለፍርድ ለማቅረብ መደራጀትና እንደየሀገሩ ሁኔታ አግባብ ያላቸውን የህግ መሳሪያዎች መጠቀም፤ በመላው ዓለም የወያኔ ኤምባሲዎችና የኮንሱላር ጽ/ቤቶች ሥራ መሥራት የማይችሉበት ሁኔታ መፍጠር፤ በመላው ዓለም የወያኔ አባላትና ደጋፊዎችን ከያሉበት (ከሰፈር፣ በዩኒቨርስቲዎች፣ በንግድ የተሰማሩ ..) በማደን ማስነወር፣ ማግለል፣ ማዋረድ፤ ከእነሱ ጋር አንዳችም የንግድም ፡ የሥራ ፤ የማኅበራዊ ትብብርና ግንኙነት አለማድረግ፤ ፊት መንሳት ፤ በሥራዎቻቸው ላይ አሉታዊ ቅስቀሳዎችን ማካሄድ። የወያኔ አባላትንና ደጋፊዎችን በሁሉም ዓይነት ግንኙት ማግለል፡ አለመተባበር በኢትዮጵያም ውስጥ በስፋት በሥራ ላይ መዋል ይኖርበታል። በማናቸውም የዓለም ክፍል ለሥራ ወይም ለሽርሽር የሚዘዋወሩ ከፍተኛ የወያኔ ሲቪል፣ የወታደራዊና የደህነት ባለሥልጣኖችና የጦር መኮንኖችን እየተከታተሉ ማሸማቀቅ፣ ማስነወር፣ መውጫ መግቢያ ማሳጣት፤ በየትኛውም የዓለም ክፍል ተቀባይነት እንደሌላቸው በሕዝብ ላይ ለፈጸሙት ወንጀሎች ሁሉ የሕዝብ ቁጣ ዒላማ እንዲሆኑ እንደልባቸው መፏላል እንዳይችሉ ማድረግ። በኢትዮጵያ ውስጥ ሕዝብ ራሱ በቡድን አደራጅቶ ለወያኔ ታጣቂዎች ጥቃት ሳያጋልጡ አድብቶና አስልቶ ተመሳሳይ ድርጊቶች መፈፀም የኢትዮጵያ አየር መንገድን ጨምሮ በወያኔ አገዛዝ የሚመሩ እንዲሁም በወያኔ ኤፈርት ስር ያሉ ኩባንያዎች፤ቢዝነሶች ላይ እቅባ ማድረግ፤ የሸቀጥና የአገልግሎታቸው ተጠቃሚ አለመሆን፤ በእነሱ ላይ አሉታዊ ቅስቀሳ ማድረግ፤ በልዩ ልዩ መንገዶች ሥራቸውን ማጨናገፍ ማደናቀፍ፤ አሻጥሮችን በተደራጀ መልክ፣ በጥናትና በብልሃት ተግባራዊ ማድረግ። ይህ በኢትዮጵያም በመላው ዓለም በሚገኙ ኢትዮጵያዊያን ሁሉ ተግባሪዊ መደረግ ይኖርበታል። በዌስተር ዩኒየን፣ በመኒ ግራም እንዲሁም በአሜሪካ፣ በአውሮፓ፤ በመካከለኛው ምሥራቅ በወያኔ ደጋፊዎች በመሠርቱዋቸው ልዩ ልዩ የገንዘብ ላኪ ድርጅቶች በኩል ገንዘብ ወደ ኢትዮጵያ አለመላክ፤ በየአካባቢው አማራጭ የገንዘብ መላኪያ መንገዶችን መፈለግ፤ እነዚህ በሌሉባቸው አካባቢዎች የፈጠራ ችሎታን በመጠቀም ገንዘብ ለዘመድ አዝማድ በወያኔ በኩል ሳይላክ የሚደርስበትን ሁኔታ መፍጠር፤ የወያኔን የፋሽታዊ አገዛዝ አንዱና ዋነኛ ምሰሶ የሆነውን የውጭ ምንዛሪ የማድረቂያ ዘዴዎችን ሁሉ በመፈለግ ተግባሪዊ በማድርግ የወያኔን በዘረኝነትና በዘረፋ የተገነባ የገንዘብና የኢኮኖሚ አቅም ማዳከም፤ መቦርቦር፤ መናድ። ከወያኔ ጋር የሚሠሩ የውጭ አገር ድርጅቶች ከወያኔ ጋር ያ ያላቸውን ሽርክና እንዲያቋርጡ መወትወት፤ አልሰማ ካሉ በቢዝነሳቸው ላይ አሉታዊ ቅስቀሳ ማካሄድ። (የእነዚህን ዝርዝሮች በተከታታይ ይገልጻሉ) የምዕራብ አገራት ዩኒቨርስቲዎች ከኢትዮጵያ ጋር ያላቸውን ግኑኝነት እንዲመረምሩ ማሳሰብ። በተለይ ደግሞ ሳያስተምሩ ለወያኔ ሹማምንቶች ዲግሪ የሚያድሉ ዩኒቨርስቲዎችና ኮሌጆችን ማስጠንቀቅ፤ ተግባሮቻቸውን ለተማሪዎቻቸው ጭምር መንገር (ለምሳሌ University of Greenwich ከ International Leadership Institute ጋር ያለውን ግኑኝነት እንዲሰርዝ፣ እስከዛሬ የሰጣቸውንም የማስትሬት ዲግሪዎች እንዲመረመር የሚጠይቅ ደብዳቤ ጽፎ በብዛት በፋክስ መላክ፤ ተመሳሳይ ደብዳቤ Open University እና ከወያኔ ጋር ተሻርከው ለሚሠሩ ዩኒቨርስቲና ኮሌጆች መላክ) ይህ ዘመቻ ለጊዜው በወያኔ ላይ ያነጣጠረ ቢሆንም፣ የሕዝቡን የነፃነትና የፍትህ ጥረት የሚያደናቅፉ የሀገር ውስጥም ሆነ የውጭ አገር ዜጎች በሆኑ ቱጆሮችና ከወያኔ ጋር የተያያዙ የንግድ ቤቶችና ኩባንያዎች የዘመቻው ዒላማ ሊሆኑ ይችላሉ። (ዝርዝራቸውን በተከታታይ እናወጣለን) በመጨረሻም የወጣቱ የማያልቅ የፈጠራ ችሎታ ከላይ በዝርዝሩ ውስጥ ያልተካተቱ ሆኖም ግን ውጤታማ የሆኑ የተቃውሞ መግለጫ ዘዴዎች ያፈልቃል ብለን እናምናለን። ስለሆነም ዘመቻውን በየአካባቢው በሚገኝ ሀሳብና ፈጠራ ማዳበር ይቻላል። ይህ ዘመቻ ወያኔ ከስልጣን እስኪባረር ድረስ በየጊዜ እየከረረ መሄድ እንዳለበት ታሳቢ አድርጎ መነሳት ይኖርበታል። ስለሆነም በየጊዜው አዳዲስ ነጥቦችን ተግባሪዊ የትግል ስልቶችን እንጨምራለን። ለመላው የአትዮጵያ ሕዝብ፣ በመላው ዓለም የምትገኙ ኢትዮጵያዊያን ዜጎች ሁሉ፣ ለሁሉም የኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ኃይሎች ሁሉ በኅብረት በጋራ ሆነን፤ ትከሻ ገጥመን ለተግባሪዊ ትግል በቁርጠኝነት እንድንነሳ ጥሪያችንን እናቀርባለን ። ይህ ዘመቻ ወያኔን ከስልጣን ለማባረር ምድር ላይ ከምናደርገው የመረረ ትግል ጋር ሲቀናጅ የሚፈለገውን ውጤት ስለሚያስገኝ ለነፃነቱ ግድ ያለው ዜጋ ሁሉ በሙሉ ኃይሉና አቅሙ ተሳትፎ እንዲያደርግ ግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ አገራዊ ጥሪ ያቀርባል። በመስዋዕትነት ድልን እንቀዳጃለን !!! ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ !!! ምንጭ -http://www.ginbot7.org/2014/07/06/ከግንቦት-7:-የፍትህ፣-የነፃነትና-የዲሞክ/ By ጌታቸው በቀለ ዳምጠው / Getachew Bekele Damtew Getachew Bekele Damtew at July 06, 2014 Email ThisBlogThis!Share to TwitterShare to FacebookShare to Pinterest No comments: Post a Comment Newer Post Older Post Home Subscribe to: Post Comments (Atom) የዋጋ ንረት ጉዳይ የፀጥታ አና የሀገር ደህንነት ጉዳይ ነው። የኢትዮጵያ የዋጋ ንረትን ለማቃለል መንግስት መከለስ ያለበት ቁልፍ የፖሊሲ ጉዳይ። ========= ጉዳያችን ልዩ ========= አይኢም ኤፍ የዋጋ ግሽበትን (ንረትን) ሲተረጉም ''በተወሰነ ጊዜ ውስጥ የሚለካ አጠቃላይ የዋጋ ንረት ሲሆን ይህ የዋጋ ንረት አጠቃላይ ሀገራዊ የኑሮ ውድነትን ... የ ኤርትራ ጉዳይ ና የ ሃያ አንደኛው ክ/ዘመን ልጆች አስተሳሰብ በ ካርታ ጫወጣ ጎበዝ አደለሁም። ግን ጆከር የተባለች ካርታ መኖሯን አውቃለሁ።ጆከር ካርታ በ ሁሉም ቦታ ስለምትገባ በ ካርታ ጫወታ ጆከር የደረሰው ሰው የማሸነፍ እድል ስላለው ፊቱ በ ፈገግታ ይሞላል። የ አትዮጵ... A Loud and Clear Lesson – For Ethiopia and the World ዓለም እና ኢትዮጵያ (ከምዕራቡ ዓለም የሰሞኑ የሽብርተኛው ህወሃትን መደገፍ) ትልቅ ትምሕርት ይውሰዱ! በሚል የእንግሊዙ ጸሓፊ ዛሬ ያወጣው ሙሉ ጽሑፍ በርካታ ጉዳዮችን ይዳስሳል። Without US support — milita... ጌታቸው ረዳ ''ክው'' ብሏል።በትግሪኛ የሰጠው መግለጫ።ምን ይዟል? ጌታቸው ረዳ በከፍተኛ ድንጋጤ ውስጥ ========= ጉዳያችን ምጥን ========= ጌታቸው ረዳ በትግርኛ ማምሻውን መግለጫ ሰጥቷል። ጋዜጠኞቹ ይችን ምሽት ጌታቸው አጠገብ መቀመጥ እንዳስጨነቃቸው ከጠያቂዎቹ መርበትበት ለ...
“ከሰማይ በታች እኛን የሚያሸንፍ ምድራዊ ሃይል የለም” በሚል እብሪት ልባቸው ያበጠው ህወሃታዊያን የራሳቸው ና የህዝቡ የዘመናት አጋራቸውን የሰሜን ዕዝ የሰራዊት አባላትን የወለደችውን እንደምትበላ ድመት በተኛበት በአሰቃቂ ሁኔታ ረሸኑ ፡፡ የሀገርን ክብር በሚያዋርድ መልኩ የክብር ልብሱን አስወልቀው ከክልላችን ውጡ ብለው ወደ ባዕድ ሃገር አሰደዱት ፣ ሴት ወታደሮችን ጡት እንዳልቆረጡና ከሰብዓዊ ፍጡር የማይጠበቅ የማይጠበቅ እየፈጸሙባቸውና እያሰቃዩ እንዳልገደሉ ፣ ሬሳቸው ላይ እምበር ተጋዳላይ እንዳልጨፋሩ ፣ በተኙበት አፍነው ይዘው አሰልፈው በሲኖትራክ እንዳልጨፈለቁ ፣ ከፍተኛ ጀነራል መኮንኖችን ጨምሮ በርካታ አባላትን አግተው ያለ ምግብ ውሃ በእግር እያሰጓዙ እንዳላሰቃዩ በዚህም በርሃብና በጥም በርካቶች እንዲሞቱ እንዳላደረጉ ፣ ማይካድራ ላይ ታሪክ ይቅር የማይለው የዘር ማጥፋት እንዳልፋፀሙ ሁሉ ፣ በንቀትና በትዕቢት ተነፋፍተው በደንጎላ ኮሎኔል ማራኪ የውሸትና ባረጀ ባፋጀ ስልት የጀመሩት ጦርነት ፣ በቆራጥ ኢትዮጵያዊያን መስዋዕትነት ድባቅ ሲመቱ ፣ የጦርነት ሊቆች ነን ባዮች ግብዞቹም በለኮሱት እሳት ሲፈጁ ዲጅታል ወያኔዎች ሌላ ዘፋን ይዘው ብቅ አሉና አለምን ማደናገር ጀመሩ። ትግራይ ውስጥ ሰብአዊ መብት እየተጣሰ ነው ፣ ሴቶች እየተደፈሩ ነው ፣ ንብረት በኤርትራ ወታደሮች እየተዘረፈ ነው ፣ የኢትዮጵያ መንግስት የትግራይ ህዝብን በርሃብ እየቀጣ ነው ፣ የሃገር ሉአላዊነት ተደፍሯል… የሚሉና ፣ ምድር ላይ ካለው እውነት የሚጣረሱ ክሶችን በሶሻል ሚዲያና በውጭ ሃገር የመገናኛ አውታሮች የሃሰት ፕሮፖጋንዳቸውን ማናፋሱን ተያይዘውታል። ምክኒያቱም ዛሬ ትግራይ ውስጥ ስለተፈፀመውና መቸም ከልባችን ከማይጠፋው ግፍና መከራ ከጨፈጨፋቸው ወታደሮች ህይወት ይልቅ ጦርነቱ ያስከተለው ማህበራዊ ቀውስ እንጅ ፣ የቀውሱ ጠንሳሽና ፈፃሚ የሆነውን ህወሃት የፈፀመው አሰቃቂ ግፍ በህወሃት ጀሌዎች ዘንድ ይሁን በአለም አቀፍ ሚዲያዎችም ሲወገዝም ሲወቀስም አንሰማም። ትግራይ ውስጥ በግፍ የተጨፈጨፉትን የሰሜን ዕዝ አባላትን ክብር የጠበቁት ልብስና የእግዜር ውሃ ያቀመሱት ኤርትራዊያን ወታደሮችና እናቶች ናቸው ወይስ… ? የህወሃታዊያን ሌላው ድንቁርና የባዕድ ሃገር ኤርትራ የኢትዮጵያን ሉአላዊነት ተዳፍራ ወታደሮቿን ትግራይ ውስጥ አስገብታለች የሚል ክስ ነው አስገብታለች አላስገባችም የሚለውን እውነት ለመንግስት እንተወውና ፣ አስገብታ ቢሆንስ እንደ ህወሃትና ባንዳዎች ክህደትና ሴራ ቢሆን ኖሮ ዛሬ ኢትዮጵያ ከሶሪያም የባሰች የፈረሰ ሃገር ትሆን እንደነበር ግልፅ ነው ፡፡ ከራሱ ሃገር እንደባዕድ ተቆጥሮ የሗሊት ታስሮ ከተገደለው ፣ ጡታቸው ተቆርጦ ተሰቃይተው ከሞቱት ፣ በድንጋይ እየተወገረ ልብሱ ሳይቀር እየተዘረፈ ከገዛ ሀገሩ ለተባረረው ሰራዊታችን ከለላ የሆነው ፣ ዛሬ ህወሃታዊያን ባዕድ ሃገር የሚሏት ኤርትራ አልነበረችምን ? እውነት እንነጋገር ከተባለ በወቅቱ ጁንታዎቹ ሰራዊታችንን ከሃገራችን ውጡ ብለው ሲያባርሩ የተቀበለው የኤርትራ ህዝብ ነው ባዕድ ወይስ ህወሃታዊያን? ትግራይ ውስጥ በግፍ የተጨፈጨፉትን የሰሜን ዕዝ አባላትን ክብር የጠበቁት ልብስና የእግዜር ውሃ ያቀመሱት ኤርትራዊያን ወታደሮችና እናቶች ናቸው ወይስ… ? እኔም ይሄን እላለሁ ፣ ህወሃታውያን ሆይ በጦር ሜዳ ላይ ያጣችሁትን ድልና ላይመለሱ ያሸለቡትን አለቆቻችሁን በፌስቡክና በዮቲዮብ ጋጋታ ላትመልሱት ፣ በውሸት ጫጫታና አስፖልት ላይ በመንከባለል የሚፈታ የትግራይ ህዝብ ችግር የለም ፡፡ መጀመሪያ አጎቶቻቹሁ የፈፀሙትን ወራዳ ተግባር አውግዙ ፡፡ በናንተ ዘመዶችና ሃሺሻም ታጣቂዎች የተጨፈጨፉ ወታደሮችን ህይወት አስቡ ፡፡ ሃገራችን የገባችበት ቅርቃር የሽማግሌ ህወሃታዊያን ሴራ መሆኑን እመኑ ፡፡ የኤርትራ ወታደሮች ሉአላዊነትን ተዳፍረው ትግራይ ውስጥ ገብተዋል ከማለታችሁ በፊት ዳር ድንበር ጠባቂ ወታደሮችን ከጀርባቸው የወጋውን ከሃዲ በአደባባይ ባንዳ በሉት፡፡ ኢትዮጵያንና ህዝቦቿን የካደውን የበደለውን የህወሃት የጥፋት ሃይል እናንተን እንደማይወክል በተግባር አሳዩ ፡፡ ያኔ የናንተ ህመም የሁሉም ኢትዮጵያዊ ህመም ይሆናል። ሌላው የኢትዮጵያ ህዝብ ሰራዊታችንን በመደገፍ የጁንታውን ግብአተ መሬት እንዳፋጠነው ሁሉ ፣ አሁን ደግሞ የዲጅታል ወያኔን የውሽት ፕሮፖጋንዳ በሃገራችንና በሰራዊታችን ላይ የተከፈተውን ዘመቻ እያጋለጥን በጁንታው የተፈፀሙ ግፎችን አጉልቶ ማውጣት ይጠበቅበናል።
ይህም አደረጃጀትና አሰራርን በማዘመን ተደራሽ፣ ቀልጣፋ፣ ግልጽና ጤናማ የውጭ ማስታወቂያ እንዲኖር እንዲሁም ኢንዱስትሪው ሰፊ የንግድ፣ የኢንቨስትመንት እና የሥራ እድል እንዲፈጥር ለማድረግ ያግዛል ነዉ የተባለዉ። ይህ ደንብ በቢል ቦርድ፣ በማስታወቂያ ሰሌዳ፣ በኤሌክትሮኒክ ስክሪን ወይም በተንቀሳቃሽ ምስል የሚሰራጭ፣ እንዲሁም በሕንጻ፣ በግድግዳ፣ በጣራ፣ በማናቸውም ስትራክቸር ወይም በትራንስፖርት ተሽከርካሪ፣ በተንሳፋፊ ፊኛ ወይም መሰል ነገር ላይ የሚሳል፣ የሚፃፍ፣ የሚለጠፍ፣ የሚተከል ማስታወቂያን ይመለከታል ነው የተባለው። በሌላ በኩል በተንጠልጣይ ነገር፣ በፖስተር፣ በስቲከር፣ በተባዛ በራሪ ወረቀት፣ በብሮሸር፣ ሊፍሌት፣ ፍላየር የሚሰራጭ፣ በድምጽ ካሴት፣ በድምፅ ማጉያ መሳሪያ የሚሰራጭንም ያጠቃልላል። ሆኖም የመንገድ አቅጣጫ ጠቋሚ፣ የትራፊክና የአውቶቡስ ፌርማታ ምልክትን፣ የመንገድ ስምን ወይም ቁጥርንና መሰል የሕዝብ አገልግሎት መረጃ ሰጪ ምልክቶችን አይጨምርም ተብሏል። ማንኛውም በምስል፣ በቅርጽና በድምፅ፣ በምስል የሚተላለፉ የውጭ ማስታወቂያዎች የፌደራል መንግስትና የከተማ አስተዳደሩን ህጎች፣ የህዝቡን ባህል፣ እምነት፣ ቋንቋና እሴቶች የማክበር ግዴታ አለባቸው መባሉን ኢትዮ ኤፍኤም ከባለስልጣኑ ሰምቷል። እንዲሁም ማንኛውም የውጭ ማስታወቂያ ከመሰራጨቱ በፊት በባለሥልጣኑ እና በሚመለከተው አካል የሚያወጣውን የብቃትና የጥራት ደረጃ መመሪያ የሚያሟላ የውጭ ማስታወቂያ መሆን አለበት ነው የተባለው። በማንኛውም ሁኔታ የውጭ ማስታወቂያ ማሰራጨት የሚቻለው በአዲስ አበባ ግንባታ ፈቃድና ቁጥጥር ባለስልጣን ፈቃድ ብቻ መሆኑንም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የግንባታ ፈቃድና ቁጥጥር ባለስልጣን የህዝብ ግንኙነትና ኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክቶሬት ያደረሰን መረጃ ያመላክታል፡፡
“የአምስት ዓመት ልጄን በስልክ አግኝቻት ነበር፡፡ እርሷም ‹ማሚ እባክሽ የወርቅ ሜዳሊያውያን አሸንፊ› ስትል ጠየቀችኝ፡፡ ቃል ገብቼላት ነበር፤ ቃሏን በመጠበቄ ኮርቻለሁ በቃ፣ ዛሬ እንደገና የተወለድሁ ያህል ከፍተኛ ደስታ ተሰምቶኛል፤” ይህን ቃል መሠረት ደፋር ከ2004 የአቴንስ ኦሊምፒክ በኋላ ሁለተኛውን የኦሊምፒክ ወርቅ በ5‚000 ሜትር ለንደን ላይ ካሸነፈች በኋላ ለዜና ሰዎች የተናገረችው ነው፡፡ ከፍተኛ ፉክክር የነበረበትን ውድድር ተቀናቃኟን ኬንያዊት ቪቪያን ቼሪዮትንና የቤጂንግ ኦሊምፒክ አሸናፊዋና የዘንድሮው የ10‚000 ሜትር ባለወርቅ ጥሩነሽ ዲባባን አስከትላ በ15 ደቂቃ 04.25 ሰከንድ በሆነ ጊዜ በማሸነፍ የወርቅ ሜዳሊያውን አግኝታለች፡፡ ዛሬ መጠናቀቂያው ላይ የደረሰው 30ኛው የለንደን ኦሊምፒክ የኢትዮጵያ ሴት አትሌቶችን አይበገሬነት አሳይቷል፡፡ በ56 ዓመት ታሪክ ውስጥ በአንድ ኦሊምፒክ ሦስት ሴት አትሌቶች ሦስት ወርቅ በማግኘት ታሪክ ሠርተው ድሉን አድምቀውታል፡፡ ሦስተኛውን ወርቅ ባለፈው ዓርብ ምሽት በ5‚000 ሜትር በኢትዮጵያውያትና በኬንያውያት መካከል በነበረው ከፍተኛ ፉክክር ድሉን የጨበጠችው መሠረት ደፋር ናት፡፡ መሠረት ደፋር በኦሊምፒክ 5‚000 ሜትር ሁለት የወርቅ ሜዳሊያዎችና አንድ ነሐስን ጨምሮ ሦስት ሜዳሊያዎችን በማግኘት ብቸኛዋ አትሌት ሆናለች፡፡ ደራርቱ ቱሉም በተመሳሳይ በ10‚000 ሜትር በባርሴሎናና በሲዲኒ ኦሊምፒኮች ሁለት የወርቅና በአቴንስ ኦሊምፒክ አንድ የነሐስ ሜዳሊያዎች አግኝታለች፡፡ “ሁለተኛውን ወርቅ ከስምንት ዓመት በኋላ ማግኘቴ ልዩ እመርታ ነው፤ ዛሬ ዳግም እንደተወለድኩ ነው የምቆጥረው፤” ያለችው መሠረት፣ የድሉን መስመር አልፋ እንደገባች ከጉያዋ ውስጥ ድንግል ማርያም ከልጇ ጋር ያለችበትን ምስል እያሳየች ስትስም ታይታለች፡፡ “ድሉን ዛሬ ስለሰጠኝ እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ፤ እጅግ በጣም ተደስቻለሁ፣ ይህ ለእኔ ታላቅ ነው፤” ማለቷን የኢንተርናሽናል አትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማኅበር ድረ ገጽ አስፍሯል፡፡ ዝግ ብሎ የተጀመረውን የ5,000 ሜትር ሩጫ ብሪታንያዊቷና ጣሊያናዊቷ የመጀመርያውን ሦስት ሺሕ ሜትር እየተፈራረቁ የመሩት ቢሆንም አልዘለቁበትም፡፡ ኬንያውያቷ ቼሪዮት፣ ኪፒዮጎና ኪሲዎት ወደፊት ማምራት መጀመራቸውን ያስተዋለችው ጥሩነሽ ቀዳሚነቱን ይዛ ዙሩን ስታከረው መሠረትም ተከትላታለች፡፡ አራቱን ዙር ያፈጠነችው ጥሩነሽ ለኢትዮጵያ ስኬት በሩን ከፍታለች፡፡ 100 ሜትር ላይ ማለፍ የጀመረችው መሠረት በድንቅ አፈጻጸም አንደኛ ስትሆን ሦስተኛ ላይ የነበረችው ኬንያዊቷ ቼሩዮት ጥሩነሽን አልፋ ሁለተኛ ሆናለች፡፡ ውድድሩ የምሥራቅ አፍሪካውያት የበላይነት የታየበትና ሦስት ኢትዮጵያውያትና ሦስት ኬንያውያት ተፈራርቀው የገቡበት ነው፡፡ የመሠረት ድል የኢትዮጵያን የኦሊምፒክ 5‚000 ሜትር የበላይነት ለ12 ዓመታት እንዲዘልቅ ያደረገ ነው፡፡ በ10‚000 ሜትር ሩጫ በወርቅነሽ ኪዳኔ የታየው የቡድን ሥራ በ5‚000 ሜትር ላይ በጥሩነሽ ዲባባ መቀጠሉ ታይቷል፡፡ “400 ሜትር ከቀረ ቼሪዮት አስቸጋሪ ነች፡፡ እንዳታመልጠን አራት ዙር ሲቀረው ወጣሁ፤” በማለት ለዜና ሰዎች የተናገረችው ጥሩነሽ፣ “ወርቁን እኔም አገኘሁት መሠረት ዋናው ለአገር መሆኑ ነው፤” ብላለች፡፡ በ5‚000 ሜትር በተጠባባቂነት ተይዛ የነበረችው ጥሩነሽ በርቀቱ እንደምትወዳደር በተነገረ ጊዜ እንደ ቤጂንጉ ሁሉ ድርብ ድልን ታስመዘግባለች የሚሉ ቁጥራቸው ቀላል አልነበረም፡፡ ዓርብ ምሽት ውድድሩ ሊያበቃ 100 ሜትር አካባቢ እስከቀረውና መሠረት እስካለፈቻት ድረስ ትመራ ነበር፡፡ ኢትዮጵያ ሦስተኛውን ወርቅ በመሠረት በኩል እንድታገኝ ያከናወነችው የቡድን ሥራ በአስደሳችነቱ ሲወሳ ሌላዋ አትሌት ገለቴ ቡርቃ አምስተኛ ሆናለች፡፡ ለባህሬን የሮጡት ትውልደ ኢትዮጵያውያቱ ሽታዬ እሸቴና ጠጂቱ ዳባ 10ኛ እና 12ኛ ሆነው አጠናቀዋል፡፡ መሠረት የድሉን መስመር እንዳለፈች የተፈጠረባት ደስታ ሲቃና እንባ የተሞላ ነበር፡፡ ከቤጂንግ በኋላ የዓመታት ጥረቷ ለወርቅ በመብቃቱ እፎይታን ፈጥሮላታል፡፡ በሦስት ኦሊምፒያዶች ሦስት ሜዳሊያዎች ያገኘችውና እ.ኤ.አ በ2007 የዓለም ምርጥ አትሌት ተብላ የተመረጠችው መሠረት ወደፊት ማራቶን ለመሮጥ ሐሳቡ አላት፡፡ ከሁለት ዓመት በፊት ፊላዴልቪያ ላይ ግማሽ ማራቶን ሩጣ በ67 ደቂቃ 45 ሰከንድ ማጠናቀቋ ይታወሳል፡፡ የሴቶች 5‚000 ሜትር ለመጀመርያ ጊዜ ለውድድር የቀረበው በአትላንታ ኦሊምፒክ (1996) ሲሆን፣ በወቅቱ ያሸነፈችው ቻይናዊቷ ዋንግ ጁኒያ ስትሆን ኬንያዊቷ ፓውሊን ኮንጋ ሁለተኛ ወጥታ ነበር፡፡ ኢትዮጵያን በ5‚000 ሜትር የመጀመሪያ የሜዳሊያ ባለቤት ያደረገችው ሲድኒ ኦሊምፒክ (2000) የተካፈለችው ጌጤ ዋሚ ስትሆን ሦስተኛ ወጥታ ነሐስ አግኝታለች፡፡ አየለች ወርቁና ወርቅነሽ ኪዳኔ አራተኛና ሰባተኛ ሆነው ማጠናቀቃቸው ይታወሳል፡፡ ከመሠረት ወርቃማ ድል ግማሽ ሰዓት በኋላ በተካሔደው የሴቶች 1‚500 ሜትር ፍፃሜ በከፍተኛ ደረጃ ለወርቅ ተጠብቃ የነበረችው አበባ አረጋዊ ባልተገመተ ሁኔታ አምስተኛ ሆና አጠናቃለች፡፡ ከሦስት ዓመት ወዲህ የተከሰተችውና በዳይመንድ ሊግ በርቀቱ እየመራች ያለችው አበባ፣ የመጀመርያውንና የግማሽ ፍፃሜ ማጣርያዎችን በብቃት በአንደኛነት ማሸነፏ ብዙዎች ድሉን ለእርሷ ሰጥተው ነበር፡፡ ቢያንስ ከሜዳሊያው ተርታ እንደማትርቅም ገምተው ነበር፡፡ መሐመድ አማን በ800 ሜትር ያጋጠመውን ዓይነት ሽንፈት አስተናግዳለች፡፡ ከመነሻው መጨረሻ ላይ የነበረችው አበባ ወደ መሀል ስትገባ መደነቃቀፉ የፈጠረባት ጫና በውጤቷ ላይ ተፅዕኖ ማሳደሩ አልቀረም፡፡ ከልምድ ማነስ፣ መውጣት በሚገባት ጊዜ ያለመውጣትና በሥነ ልቦና አለመዘጋጀት ከሥልጠና ችግር የመጣ መሆኑ ለውጤቱ መጥፋት እንደምክንያት እየተቆጠረ ነው፡፡ ውድድሩን ቱርካዊቱ አልሲ ካኪር አልናቴኪን በ4 ደቂቃ 10፡23 ሰከንድ ስታሸንፍ፣ ሌላዋ የአገሯ ዜጋ ጋምዜ ቡሉት ሁለተኛ፣ ለባህሬን የሮጠችው ትውልደ ኢትዮጵያዊቷ መርያም ዩሱፍ ጀማል ደግሞ ሦስተኛ ሆናለች፡፡ ትናንትና ምሽት የወንዶች 5‚000 ሜትር ሩጫ የተካሄደ ሲሆን፣ ማተሚያ ቤት ቀድመን በመግባታችን ውጤቱን አልያዝንም እንጂ ኢትዮጵያ በወጣቶቹ ደጀን ገብረ መስቀል፣ ሐጎስ ገብረ ሕይወትና የኔው አላምረው ተወክላለች፡፡ ሐምሌ 20 ቀን የተጀመረው 30ኛው ኦሊምፒያድ ከ17 ቀናት በኋላ የሚያከትመው ዛሬ ከእኩለ ቀን በኋላ በሚደረገው የማራቶን ውድድር ይሆናል፡፡ በወንዶች ማራቶን የወርቅ ሜዳሊያ ካገኘች ሁለት ኦሊምፒያዶች ያሳለፈችው ኢትዮጵያ የአበበ ቢቂላን፣ የማሞ ወልዴን፣ የገዛኸኝ አበራን ድል የሚያስቀጥልላት አትሌት ከዲኖ ስፍር፣ ከአየለ አብሽሮና ከጌቱ ፈለቀ መካከል ማን ይሆን? ኢትዮጵያ እስከ ትናንት ድረስ በጥሩነሽ ዲባባ ወርቅና ነሐስ፣ በቲኪ ገላና ወርቅ፣ በመሠረት ደፋር ወርቅ፣ በሶፍያ አሰፋና በታሪኩ በቀለ ነሐሶች 22ኛ ደረጃ ላይ ትገኝ ነበር፡፡
‹‹እኔ ያደግሁት ውጭ አገር ነው፡፡ የትም ዓለም ላይ 13 ወር የለም፡፡ ፒራሚድ ሲታይ ግብፅ ነው፡፡ አይፈልታወር ሲታይ ፈረንሣይ ነው፡፡ የነፃነት ሐውልት ሲታይ አሜሪካ አለ፡፡ እኛ የምንታወቅበት የለንም ነበር፡፡ ሁሉ ነገር ከዘር፣ ከሃይማኖት ጋር የተያያዘ ነበር፡፡ ሳላውቀው አንድ ወቅት ላይ የ13 ወር ደመወዝ ይሰጠን ብዬ ጠየቅሁ፡፡ ወዲያው ይህንን ሐሳብ ወደ ቱሪስት መሳቢያነት መቀየር እንደሚቻል አሰብኩ፡፡ ሌላው ሁሉ ከዘር ከሃይማኖት ጋር የሚያያዝ ነበር፡፡ ላሊበላን ባደርግ ኢትዮጵያ በሙሉ ክርስቲያን ባለመሆኑ ችግር ነበረበት፡፡ የአሥራ ሦስት ወር ፀሐይ ግን ከምንም ነገር ጋር አይገናኝም፡፡ ምንም የፖለቲካና የሃይማኖት ንክኪ የለውም፡፡ አሁን ከዚያ የበለጠ ከተገኘ ደግሞ ቶሎ መተካት ነው፡፡ ምንም ችግር የለበትም፡፡›› በማለት በአንድ ወቅት ከሪፖርተር ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ የተናገሩት አቶ ሀብተሥላሴ ታፈሰ በኢትዮጵያ የቱሪዝም ኢንዱስትሪ መሥራች፣ የአሥራ ሦስት ወራት ፀጋ (13 Months of Sunshine) በሚል መጠሪያ የአገሪቱ ቱሪዝም ለዘመናት ሲያስተዋውቅ የኖረውን መለያ የፈጠሩና በዘርፉ በርካታ ሥራዎችን ያስተዋወቁ፣ የተገበሩ የቱሪዝም አባት ናቸው፡፡ ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ይህንን ውለታቸውን ቆጥሮ ዕውቅና በመስጠት ለመጀመሪያ ጊዜ ሽልማት አበርክቶላቸዋል፡፡ ሰሞኑንም ከጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ እጅ ለሁለተኛ ጊዜ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡ በቱሪዝም መስክና በተያያዥ ጉዳዮች ላይ ሔኖክ ያሬድና ብርሃኑ ፈቃደ ከጥቂት ዓመታት በፊት አነጋግረዋቸው ነበር፡፡ ይኸው ቃለ ምልልስ ለትውስታ ይሆን ዘንድ እንዲህ ቀርቧል፡፡ ሪፖርተር፡- በዘርፉ በጠቅላላው ኢትዮጵያን ለምን ያህል ጊዜ አገልግለዋል? አቶ ሀብተሥላሴ፡- ከመጀመሪያው እ.ኤ.አ. ከ1954 ጀምሮ አገልግያለሁ፡፡ ያኔ ከውጭ አገር ወደ ኢትዮጵያ እንደመጣሁ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ውስጥ እሠራ ነበር፡፡ ከዚያ በግድ ይህንን ሥራ [ቱሪዝምን] እንድሠራ አዘዙኝ፡፡ ገባሁበት፡፡ ከባድ ሥራ ነው፡፡ ያን ጊዜ ካሜራ ወደ ኢትዮጵያ አይገባም ነበር፡፡ ሲገባም ጉምሩክ ይይዘዋል፡፡ ፈቃድ ከማስታወቂያ ሚኒስቴር ማውጣትም ያስፈልግ ነበር፡፡ በዚህ ሰበብ ሁለት ጊዜ ታስሬያለሁ፡፡ ፎቶግራፍ ለምን ታነሳለህ ብለው ነው ያሰሩኝ፡፡ ያን ጊዜ ፎቶግራፍ የሚያነሳ ሰው ሰላይ ተደርጐ ይታሰብ ስለነበር ነው፡፡ ሪፖርተር፡- በቱሪዝም ሙያዎ ኢትዮጵያን ምን ያህል ያውቋታል? አቶ ሀብተሥላሴ፡- ያልደረስኩበት ቦታ የለም፡፡ በእግር፣ በፈረስ፣ በግመል፣ በሄሊኮፕተር፣ በአውሮፕላን ሁሉ ተዘዋውሬ ከ100 በላይ ሰው ያልረገጣቸው የኤርትራ ደሴቶችን አይቻለሁ፡፡ ትልቅ ሀብት ናቸው፡፡ ቢያውቁበት በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ መሰብሰብ ይችሉ ነበር፡፡ በጋምቤላ በኩል ጂካው ድረስ ሄጃለሁ፡፡ የደቡብ ሱዳን ጠረፍ ነው፡፡ በኤርትራ በኩል ቤንአመር ድረስ ወዳለው የጠረፍ ቦታ ደርሻለሁ፡፡ ቤንሻንጉልን በሙሉ እስከ ሱዳን ድረስ አዳርሻለሁ፡፡ መሥራት ካስፈለገ ማየት፣ ማወቅ ግድ ይሆናል፡፡ ካየን፣ ካወቅን በኋላ ማውራት ይቻላል፡፡ ሪፖርተር፡- በእነዚህ ሁሉ ጊዜያት እርስዎ ብዙ ሠርተዋል፡፡ ከሠሯቸው መካከል አሁንም ድረስ የሚታወቀው ኢትዮጵያ የአሥራ ሦስት ወር ፀጋ የሚለው አገሪቱ መጠሪያ ነው፡፡ ይህ የኢትዮጵያ መለያ ለብዙ ጊዜ ያገለገለ ነው፡፡ አሁን መቀየር አለበት የሚሉ አሉ፡፡ ይቀየር ቢባል ምን ይሰማዎታል? አቶ ሀብተሥላሴ፡- ሁልጊዜ አንድ ነገር ሲፈጠርና የሚበልጠው ሲገኝ ያንን ማየቱ ተገቢ ነው፡፡ በአንድ ወቅት ምክትል አፈንጉሥ ገብረ ወልድ ፎቅ ቤት ሠርተው ነበር፡፡ ያን ጊዜ በንጉሡ ዘመን የመንግሥት ግልበጣ ሙከራ ነበር፡፡ መንግሥቱ ንዋይ ደግሞ ጠንሳሽና የእኛም ዘመድ ነበር፡፡ ሰውየው ሰማይ ጠቀስ ፎቅ ሠርተሃል ተብለው ታሰሩ፡፡ ይህ ከሆነማ አፍርሱት ሲሏቸው የለም አንተን ነው የምናፈርሰው ብለው ገደሏዋቸው፡፡ አሁን ደግሞ በተገላቢጦሽ ሰማይ ጠቀስ ፎቅ እንዲሠራ ነው የሚፈለገው፡፡ ሪፖርተር፡- የአሥራ ሦስት ወር የፀሐይ ፀጋን እንዴት መረጡት? አቶ ሀብተሥላሴ፡- እኔ ያደግሁት ውጭ አገር ነው፡፡ የትም ዓለም ላይ 13 ወር የለም፡፡ ፒራሚድ ሲታይ ግብፅ ነው፡፡ አይፈልታወር ሲታይ ፈረንሣይ ነው፡፡ የነፃነት ሐውልት ሲታይ አሜሪካ አለ፡፡ እኛ የምንታወቅበት የለንም ነበር፡፡ ሁሉ ነገር ከዘር፣ ከሃይማኖት ጋር የተያያዘ ነበር፡፡ ሳላውቀው አንድ ወቅት ላይ የ13 ወር ደመወዝ ይሰጠን ብዬ ጠየቅሁ፡፡ ወዲያው ይህንን ሐሳብ ወደ ቱሪስት መሳቢያነት መቀየር እንደሚቻል አሰብኩ፡፡ ሌላው ሁሉ ከዘር ከሃይማኖት ጋር የሚያያዝ ነበር፡፡ ላሊበላን ባደርግ ኢትዮጵያ በሙሉ ክርስቲያን ባለመሆኑ ችግር ነበረበት፡፡ የአሥራ ሦስት ወር ፀሐይ ግን ከምንም ነገር ጋር አይገናኝም፡፡ ምንም የፖለቲካና የሃይማኖት ንክኪ የለውም፡፡ አሁን ከዚያ የበለጠ ከተገኘ ደግሞ ቶሎ መተካት ነው፡፡ ምንም ችግር የለበትም፡፡ ሪፖርተር፡- ዛሬም ድረስ መሥራት የሚፈልጓቸው ብዙ ጉዳዮች አሉ፡፡ አቶ ሀብተሥላሴ፡- መርዳት ነው የምፈልገው፡፡ መሥራት ያለባቸው የተመደቡት ሰዎች ናቸው፡፡ እነርሱን ለመርዳት ዝግጁ ነኝ፡፡ አምስት ያህል ፕሮጀክቶች አሉኝ፡፡ ፍልውኃን በአግባቡ አልተጠቀምንበትም፡፡ ወንዶገነትና ሶደሬ አካባቢ ጥቅም ላይ ውሏል፡፡ ነገር ግን ከ3,000 በላይ ፍልውኃ በየቦታው አለን፡፡ ያ የማያልቅ፣ ከወርቅና ከከበረ ድንጋይ ሁሉ የበለጠ ሀብት ነው፡፡ ነገር ግን አልተሠራበትም፡፡ እኔጋ ጥናቱ አለ፡፡ ዩኔስኮ ውኃውን ጨምሮ ያገኘው ጉዳይ አለ፡፡ ጥናቱ በእጄ ስላለ ለመንግሥት እሰጣለሁ፡፡ ይሠሩበታል ብዬ አስባለሁ፡፡ አሁን ቱሪስቶች ያሉት እዚሁ ከጐናችን ነው፡፡ ዱባይ፣ ኤምሬቶች አሉ፡፡ ድሮ ዓረብ ድሃ ነው፡፡ አሁን ዓለምን የያዙ እነሱ ናቸው፡፡ ፍልውኃ አረንጓዴያማ መስክ ይወዳሉና አቅሙ ላላቸው ባለሀብቶች መስጠት ከተቻለ ሰው ይመጣል፡፡ ከዱባይ አዲስ አበባ የሦስት ሰዓት በረራ ብቻ ነው የሚያስፈልገው፡፡ ከአውሮፓና ከአሜሪካ ሰው ይመጣል ብሎ መጠበቅ ከባድ እየሆነ ነው፡፡ ቀውስ ላይ ናቸው፡፡ የቅርብ አገሮች ግን መምጣት የሚችሉበት አቅም አላቸው፡፡ በግብፅ ለሁለት ዓመት ቆይቻለሁ፡፡ አባቴ አምባሳደር ነበሩና በዚያ ኖረናል፡፡ በጣም ቃጠሎ ነው፣ ሲበዛ ሞቃት ነው፡፡ በክረምት ብቻ ወደ አሌክሳንድርያ እንሄድ ነበር፡፡ አሁንም በጣም ሞቃት ነው፡፡ ሪፖርተር፡- እርስዎ የአሥራ ሦስት ወር ፀጋ ብለው ነበር ብዙ ፀጋ አለን ማለት ነው? አቶ ሀብተሥላሴ፡- ደመወዝ የለውማ፡፡ የአሥራ ሦስት ወር ደመወዝ አይከፈልበትም፡፡ ሪፖርተር፡- እንደ ኬንያ ያሉት አገሮች ግን የዱር እንስሳት ሀብት ብቻ እያላቸው ነገር ግን ብዙ የተጠቀሙበት ሁኔታ አለ፤ አቶ ሀብተሥላሴ፡- እነሱ ስላሠሩ ነዋ፡፡ እኛ አንሠራም፡፡ አንዱ ሲሠራ አሥሩ ወደኋላ ይጐትታል፡፡ ምቀኝነት አለ፡፡ የሐበሻ ፀባይ አብሮ መሥራት ስለሌለው መድረስ ያለብን ቦታ አልደረስንም፡፡ ሪፖርተር፡- አየር በዕቃ ሞልተው ለመሸጥ የሞከሩበት ጊዜ እንደነበር ይነገራልና ስለእርሱ ቢነግሩን? አቶ ሀብተሥላሴ፡- የኢትዮጵያ አየር የትም ዓለም ላይ አይገኝም፡፡ አንድ ጊዜ ንጉሡ ጋር ገባሁና አየር ይሸጣል አልኳቸው፡፡ ገንዘብ ሚኒስትሩ መጡና ምን ይለፈልፋል ብለው አጣጣሉኝ፡፡ አጋጣሚ ሆኖ እ.ኤ.አ. በ1970 በኦሳካ ኤግዚቢሽን ነበርና ወደ ቶኪዮ ዞር ዞር ብዬ ለማየት ሄድኩ፡፡ አንድ ቦታ ላይ የፊጂ ተራሮች የሚል ጽሑፍ ያለበት ቆርቆሮ አየሁ፡፡ ሳነሳው ባዶ ነው፡፡ ውስጡ ያለው የፊጂ አየር ብቻ ነው፡፡ ሰው ገዝቶ በአፍንጫው መማግ ብቻ ነው፡፡ ይህንን ገዛሁና ወደ ንጉሡ አመጣሁት፡፡ ስጦታ አምጥቼሎታለሁ አልኩና ሰጠኋቸው፡፡ አንስተው ሲያዩ ምንም የሌለው መስሏቸው ምን ትቀልዳለህ አሉኝ፡፡ አየር ይሸጣል ያልኩዎትኮ ይኼ ነው፤ ገዝቼ መጣሁ አልኳቸው፡፡ ገንዘብ ሚኒስትሩን ጠሩና ታስታውሳለህ ያልከውን ይኸውልህ አየር ይሸጣል አሏቸው፡፡ ይኼንን አሁንም ማድረግ ይቻላል፡፡ አየር በዕቃ ሞልቶ እንዲማግ ማድረግና መሸጥ ይቻላል፡፡ ውኃ በፕላስቲክ እየተሸጠ እኮ ነው፡፡ ሰው ግን አያምንም፣ አይቀበልም፡፡ አገሪቱን ያጠቃት በምቀኝነት፣ በዘር፣ በሃይማኖት መከፋፈላችን ነው፡፡ አንድ ሆነን ካልሠራን ከባድ ነው፡፡ አሁን ብዙ ለውጥ መጥቷል፡፡ ከሞት የተመለስኩ ያህል የሚሰማኝ ጊዜ አለ፡፡ ሴቱ ሁሉ እንደ ልቡ ነው፡፡ ወደ ዱባይ ወደ መሳሰሉት አገሮች ሲሄዱ፣ ሲሠሩ የሚታዩ ቆነጃጅቶች ብዙ አሉ፡፡ በእኛ ጊዜ እንዲህ አይታሰብም፡፡ ብዙ ለውጥ አለ፡፡ የሰው አስተሳሰብ ተቀይሯል፡፡ ሪፖርተር፡- አንድ ኒውዝላንዳዊ ሚሊየነር ኢትዮጵያን በሄሊኮፕተር ጐብኝቶ መደነቁን ሲናገሩ ነበርና ስለእርሱ ቢገልጹልን? አቶ ሀብተሥላሴ፡- ፓይለቱ የሰውየው ልጅ ባል ነው፡፡ ሰውየው ደግሞ ባለሄሊኮፕተር ነው፡፡ የእርሱ አስጎብኚ ከእኔ ጋር የሚሠራ ነውና ተዟዙሮ አይቶ እኔን ማየት ፈለገና እራት ጋበዘኝ፡፡ ተኝታችኋል አለኝ፡፡ በሄሊኮፕተር እየተዘዋወርን ከ125 በላይ አገሮች አይተናል እንደ ኢትዮጵያ የሚሆን ግን አላየንም አለኝ፡፡ ሰውየው የምንም ፍላጎት የላቸውም፡፡ ለጥቅም ብለው ነው እንዳይባል አገራቸው ኤምባሲ እንኳ እዚህ የላትም፡፡ ሰውየው ደግሞ እጅግ ባለጠጋ ናቸው፡፡ ቢሊየነር በመሆናቸው ለጉብኝት ብቻ ነው የመጡት፡፡ ያዩትን አይተው ተኝታችኋል አሉኝ፡፡ ሪፖርተር፡- የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ሽልማት ሲሰጥዎ፣ በሕይወቴ ለመጀመሪያ ጊዜ ለሽልማት ተጠራሁ ብለዋል፡፡ ለምንድን ነው ከዚህ በፊት ይህን ሁሉ ሠርተው ያልተሸለሙት? አቶ ሀብተሥላሴ፡- ምቀኞች ስለሆንን፡፡ ሁሌም ሲጠሩኝ ለአንድ ወቀሳ ነው፡፡ ቤተክህነት ተጠርቼ በቴሌቪዥን ለምን እንዲህ ተናገርህ እባላለሁ፣ የአገር ውስጥ ገቢ ይጠሩኝና እወቀሳለሁ፡፡ ያን ጊዜ ከቀረጥ ነፃ ሱቅ ከፍተን ነበር፡፡ የእኛ ቢሮ ከመንግሥት ቢሮዎች ሁሉ ሀብታም የሚባለው ነበር፡፡ ያን ጊዜ ቱሪዝም በጀት 220 ሺሕ ብር ስለነበር በዚህ በጀት እንዴት አገርን ማሳደግ ይቻላል እያልሁ ከጃንሆይ ጋር እጨቃጨቅ ነበር፡፡ አንድ ጊዜ ቁልፉን ይዤ ሄድኩና ጃንሆይ ይኼንን መሥሪያ ቤት ለሒሳብ ሹም ይስጡት ደመወዝ ከመክፈል ውጪ ሌላ ሥራ መሥራት አልቻልኩም አልኳቸው፡፡ የዲውቱ ፍሪ ፈቃድ ስጡኝ ብዬ ጃንሆይን ጠየቅሁ፡፡ ኋላ ላይ ገንዘብ ሚኒስትሩ መጡና እኛ ኮንትሮባንድ መቆጣጠር አቅቶናል፣ ሀብተሥላሴ ደግሞ አናታችን ላይ ኮንትሮባንድ ለመፍጠር ይፈልጋል አሉኝ፡፡ ንጉሡም ሥራህ መቆጣጠር ነው እንጂ ሥራ አይሥራ ነው የምትለው ወይስ መቆጣጠር አልችልም ነው? ብለው ጠየቋቸውና ተፈቀደልኝ፡፡ ሥራው ሊጀመር ሲል ደግሞ ገንዘብ ስለጠፋ የአባቴን ካርታ ወስጄ ለአንድ እብድ ሰጠሁና 5,000 ዶላር ተበደርኩ፡፡ በሚሊዮን የሚቆጠር ብር ማግኘት ተቻለን፡፡ በአንድ ወቅት ከመላው ኢትዮጵያ የእኛ መሥሪያ ቤት ነበር ሀብታም የነበረው፡፡ አንድ ሚኒስትር ሲሾም በጊዜው እንዲነግድ አይፈቀድለትም ነበር፡፡ ለእኛ ተፈቅዶ ነበርና ብዙ ገንዘብ አስገብተናል፡፡ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ሕንፃ ተሠርቶ ሥራ ሲጀምር የእኛ መኪኖች ነበሩ የሚያገለግሉት፡፡ 46 ያህል ነበሩን፡፡ እኔ እንደ ሾፌር፣ እንደ አስጐብኚ፣ እንደ ፎቶግራፍ አንሺ እየሆንኩ ሠርቻለሁ፡፡ በኋላ ምቀኛ በዛና የዲውቲ ፍሪ ገንዘብ ወደ መንግሥት ይግባ አሉ፡፡ ያ አሠራር ዛሬ ቆይቶ ቢሆን ኖሮ አሥር ሚሊዮን ሰዎች በተሰማሩበት ነበር፡፡ ሪፖርተር፡- በጊዜው ሴቶችን ፎቶግራፍ ያነሱ ነበርና ከንጉሡ ዘንድ የገጠመዎት ጉዳይ አለ ይባላል፤ አቶ ሀብተሥላሴ፡- አዎ፡፡ አንዲት የጋምቤላ ሴት ፎቶግራፍ አንስቼ ነበር፡፡ ሴትየዋ ጡቷ ቆንጆ ነበርና አንስቼ ፖስተሩ ከመታተሙ በፊት ናሙናውን ለንጉሡ አስገብቼ ጠረጴዛ ላይ እደረድር ነበር፡፡ ንጉሡ መጥተው ሲያዩ ይኼ ምንድን ነው አሉና ጠየቁኝ፣ አይ ቱሪስቶች እንዲህ ማየት ይወዳሉ ስላቸው፣ አንተም ትወዳለህ ይባላል አሉኝ፡፡ በኋላ ታትሞ ሲወጣ ሳንሱር ይደረግ ነበር ራቁት እያሳየ ነው ብለው ንጉሡ ጋር መልሰው ይዘው መጡ፡፡ ንጉሡም አይተናል አሉና መለሷቸው፡፡ ከዚያ በኋላ የቱንም ነገር ከመሥራቴ በፊት ቀድሜ ለንጉሡ ስለማሳይ አይተናል እያሉ ሚኒስትሮችን ይመልሷቸው ነበር፡፡ ብዙ መሥራት አንወድም፡፡ ስንሠራ ደግሞ ምቀኛው ወደኋላ የሚጐትት ነው፡፡ ሪፖርተር፡- እርስዎ ለባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር እሰጣለሁ ካሏቸው ፕሮጀክቶች አንዱ አንድ ብር ቢያንስ በአንድ ዶላር መመንዘር የሚያስችል ነው ብለዋል፡፡ ይኼ አስማት አይደለም ሲሉም ሰምተናልና እንዴት ነው ይኼ የሚሆነው? አቶ ሀብተሥላሴ፡- ይኼ አስማት አይደለም፡፡ እንዴት እንደሆን የምንነግረው ግን ለሚኒስትሩ ነው፡፡ እሳቸው ከተስማሙ በኋላ የእሳቸው ፕሮጀክት ይሁን፡፡ አሁን መናገሩ ጊዜው አይደለም፡፡
የካሜራ ሞጁል, እኛ እናውቃለን እንደ ካሜራዎች ወይም ውጫዊ በይነ የተለያዩ ቅርጾች, ነገር ግን የውስጥ ሞጁሎች በመሠረቱ ሌንሶች, ቤዝ, ማጣሪያዎች, ዳሳሾች, DSP (አይኤስፒ ጨምሮ), PCB substrates, ወዘተ ያቀፈ ነው እንደ ውጫዊ በይነ የተለያዩ መሠረት. የምርቱ የትግበራ ሁኔታዎች ፣ የተለያዩ የበይነገጽ ዓይነቶች አሉ።ለ DSP ክፍል ተመሳሳይ ነው.እንደ ተለያዩ የመተግበሪያ ሁኔታዎች፣ የተለያዩ የአጠቃቀም ዘዴዎች እና የተለያዩ የማስኬጃ መስፈርቶች፣ አንዳንዶቹ በቀጥታ በሴንሰሩ ውስጥ የተካተቱ ሲሆን አንዳንዶቹ ደግሞ በቀጥታ ዳሳሹ ውስጥ ይካተታሉ።ለማቀነባበር ውጫዊ የተወሰነ ቺፕ ያስፈልጋል። መነፅርብርሃንን ወደ ምስል ዳሳሽ የሚያፈስ መሳሪያ ነው።ዘመናዊ ሌንሶች ብዙውን ጊዜ የበርካታ ሌንሶች ቡድን ናቸው.ሌንስ በተለያዩ ቁሳቁሶች መሰረት በመስታወት እና በፕላስቲክ የተከፋፈለ ነው የምስል ዳሳሽበተለምዶ ሴንሰር በመባል የሚታወቀው የካሜራ ሞጁል ዋና አካል ነው።በዋናነት ሁለት ዓይነት የCMOS ምስል ዳሳሾች እና የሲሲዲ ምስል ዳሳሾች አሉ።ላይ ላይ በመቶዎች ወይም በአስር ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ፎቲዲዮዮዶች አሉ።የኦፕቲካል ምልክቱ ወደ ኤሌክትሪክ ምልክት ይቀየራል, ጥራቱ በቀጥታ የ CCM አፈፃፀም ላይ ተጽዕኖ ያሳድራል. የ IR ማጣሪያ ተግባር በሰው ዓይን የማይታየውን አልትራቫዮሌት እና ኢንፍራሬድ ብርሃንን በማጣራት ያልተፈለገ ብርሃንን ማንጸባረቅ፣የቀለም ቀረጻ ተጽእኖን ለመከላከል ቆሻሻዎችን ማስወገድ እና የጠፋ ብርሃንን መቀነስ ነው።650NM፣850NM፣940Nm አለን። መሠረት የየካሜራ ሞጁልየካሜራውን ኦፕቲካል ኤለመንቶችን ከዋናው ፕሮሰሰር ጋር የማገናኘት ሃላፊነት ያለው የታተመ የወረዳ ሰሌዳ (ፒሲቢ) ወይም ተጣጣፊ የወረዳ ሰሌዳ (ኤፍፒሲ/ኤፍሲቢ) ነው። ሮንጉዋ፣ እ.ኤ.አአምራችበ R&D ፣ በማበጀት ፣ በማምረት ፣ በካሜራ ሞጁሎች ፣ በዩኤስቢ ካሜራ ሞጁሎች ፣ ሌንሶች እና ሌሎች ምርቶች ሽያጭ እና አገልግሎት ላይ ያተኮረ ። እኛን ለማግኘት ከፈለጉ እባክዎን
በየትግራይ ክልል ያለውን ሁኔታ “አሰቃቂ” ነው በማለት የገለጹት ዶ/ር ቴድሮስ፤ “6 ሚልየን የሚሆነው የክልሉ ህዝብ ለ500 ቀናት ያክል ከውጭው ዓለም ጋር እንዳይገናኝ ተደርጎ እንደተዘጋበት ነው” ብለዋል። “ከታህሳስ ወር አጋማሽ ጀምሮ ምንም አይነት እርዳታ አልደረሰም” ያሉት ዋና ዳይሬክተሩ ፤ በዓለም ጤና ድርጅት በተደረገ ግምገማ መሰረት የክልሉ ሶስት አራተኛ የጤና ተቋማት መውደማቸውም በሰጡት መግለጫ ተናግረዋል። ባለፈው የካቲት ወር ለ300 ሺህ ሰዎች የሚበቃ 33.3 ሜትሪክ ቶን መድሃኒት እና የህክምና ቁሳቁሶች ወደ ትግራይ ማስገባት ቢቻልም፤ ይህ በክልሉ ላለው ችግር ምላሽ ለመስጠት ከሚያስፈልገው 2 ሺህ 200 ሜትሪክ ቶን እንጻር እጅግ ዝቅተኛ ነው ብለዋል። እስካሁን ወደ ክልሉ የገባው አጠቃላይ የህክምና እርዳታ መጠን 117 ሜትሪክ ቶን (ከ1 በመቶ ያነሰ) ብቻ መሆኑንም ጭምር ዋና ዳይሬክተሩ አስታውቀዋል። አሁን ባለው ሁኔታ 46 ሺህ የሚሆኑ በደማቸው ኤች.አይ.ቪ ያላቸው ሰዎች እንዲሁም የካንሰር፣ስኳር፣ቲቢ እና ተጓዳኝ በሽታ ታማሚዎች ህክምና ማግኘት የሚችሉበት ሁኔታ የለም ብለዋል። ዶ/ር ቴድሮስ በንግግራው አክለውም፤ “አዎ፣ እኔ የትግራይ ተወላጅ ነኝ፤ ይህ ችግር እኔን፣ ቤተሰቤን እና ጓደኞቼን በግል ይነካል” ነገር ግን እኔ የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር በመሆኔ ጤና አደጋ ላይ በወደቀበት ቦታ ሁሉ ጤናን የመጠበቅ እና የማስተዋወቅ ግዴታ አለብኝ ፤እናም በዓለም ላይ እጅግ የከፋ የጤና ቀውስ ያለው በትግራይ ነው” ሲሉም ተደምጧል። ዶ/ር ቴድሮስ በዓፋር እና አማራ ክልል ያለው የሰብዓዊ ቀውስ ሁኔታ ከጊዜ ወደ እየተባባሰ መምጣቱንም ተናግረዋል። በሁለቱም ክልሎች የመጠሊያ፣ ምግብ እና ህክምና ድጋፍ የሚሹ በ10 ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች መኖራቸውን የገለጹት ዋና ዳይሬክተሩ፤ ተፈናቃዮች ለመርዳት የተለያዩ ስራዎች ሲከናወኑ መቆየታቸውንም አስታውቀዋል። የሰሜን ኢትዮጵያው ትግራይ ክልል "ስልታዊ" እገዳ ተጥሎበት ነበር-ዶ/ር ቴድሮስ ሆኖም ግን በአማራ ክልል እና በአፋር ክልል በነበረው ጦርነት ስለወደሙ የጤና ተቋማት ከመናገር ተቆጥበዋል። የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ዛሬ በሰጡት መግለጫቸው የዶ/ር ቴድሮስ መግለጫን በማስመለከት ምላሽ ሰጥተዋል። በምላሻቸውም “ዋና ዳይሬክተሩ እንደ ትግራይ ሁሉ በህወሐት ምክንያት በአማራና በአፋር የወደሙትን የጤና ተቋማት ጉዳይ ሊያሳስባቸው ይገባል” ብለዋል። የኢትዮጵያ መንግስት ከዚህ ቀደም ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖም ከተጣለባቸው ሃላፊነት ውጪ በሽብርተኝነት ለተፈረጀው ህወሃት ያደላ የፖለቲካ ውግንና አሳይተዋል በሚል፤ ለዓለም ጤና ድርጅት መርማሪ ቦርድ የ‘ይመርመርልኝ’ ጥያቄ እስከማቅረብ ደርሷል። የድርጅቱ መርማሪ ቦርድ “ይህ እጅግ ውስብስብና ፖለቲካዊ መልክ ያለው እና ከኮሚቴው የአሰራር ሂደት ውጭ የሆነም ጉዳይ ነው” የሚል ምላሽ እንደሰጠም የሚታወስ ነው።
የናሙና ጊዜ ከ5-7 ቀናት አካባቢ / የጅምላ ማዘዣ ጊዜ ከ10-25 ቀናት አካባቢ በተለያዩ ምርቶች እና ቴክኒኮች (ዝርዝሮች እባክዎን ያነጋግሩን እኛ የበለጠ ለመጋራት እንረዳለን) / በተለያዩ ቻናል ላይ የተመሠረተ የማጓጓዣ ጊዜ (የተለመደ ብሔራዊ ፈጣን ከ5-7 ቀናት አካባቢ ፣ በፍላጎትዎ መሰረት እዚህ ብዙ ወጪ ለመቆጠብ የተሻለውን እንዲመርጡ ተጨማሪ ቻናል እናካፍልዎታለን) ለዋና ሸማችዎ ስለመላክ በተለምዶፓኬጁን ወደ ደንበኞቻችን አድራሻ እንልካለን እና ጥቅሉን ወደ ደንበኛ ደንበኛዎ እንድንልክ ከፈለጉ ለመላክ እንረዳዎታለን።ወይም ከእርስዎ እና ከጓደኞችዎ የተሰበሰበው ትዕዛዝ፣እኛ እንዲሁ ለእያንዳንዱ ሰው ለመላክ እና የማጓጓዣ ወጪን በተናጠል ለማስላት ልንረዳዎ እንችላለን። ስለ ታክስ ወጪ ብዙውን ጊዜ የ EXW ዋጋን ያለግብር ወጪ ወይም በደንበኛ የመርከብ ጥያቄ መሰረት እንጠቅሳለን ፣ከታክስ ወጪ ጋር የመርከብ አማራጭን እናቀርባለን።ነገር ግን የ EXW ዋጋን ለአንዳንድ ደንበኞች ስንጠቅስ በምክንያት የታክስ ወጪን የምንቆጣጠርበት መንገድ የለንም::የተለያዩ ሀገር ፕሮሊሲሲ፣ ነገር ግን ማጓጓዣን ስናዘጋጅ ብጁ እሴት ስራ በዚህ ክፍል ላይ ያለውን ወጪ ለመቆጠብ በተቻለ መጠን ዝቅተኛ ለመስራት መርዳት እንችላለን። ከእኛ ጋር መስራት ይፈልጋሉ? አግኙን OEM & ODM ማተሚያ አምራች, በደንበኞች ተግዳሮቶች እና ግፊቶች ላይ እናተኩራለን, ለደንበኞች በጣም ተወዳዳሪ የሆነ የህትመት ምርት መፍትሄዎችን መስጠቱን እንቀጥላለን.በደንበኞች የሚታመን አቅራቢ እና በሠራተኞች የሚታወቅ የሥራ ልማት ቦታ ይሁኑ።
አዲስ አበባ፣ ሚያዚያ 6፣ 2012 (ኤፍ.ቢ.ሲ) የኮሮናቫይረስ (ኮቪድ 19) ወረርሽኝ ስርጭትን ለመከላከል፣ ለመቆጣጠርና የሚያስከትለውን ጉዳት ለመቀነስ የወጣውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተፈጻሚነት ለማረጋገጥ ዝግጁ መሆናቸውን ፍርድ ቤቶች ገለጹ። መንግስት የኮቪድ 19 ወረርሽኝ ስርጭትን ለመከላከል፣ ለመቆጣጠርና የሚያስከትለውን ጉዳት ለመቀነስ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ወደ ስራ ገብቷል። አዋጁን ተከትሎ የወጣው የማስፈፀሚያ ደንቡ በአራት ዋና ዋና ከፍሎች ክልከላን በማስቀመጥ፤ ግደታዎችን […] Source: ፍርድ ቤቶች የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተፈጻሚነት ለማረጋገጥ ዝግጁ መሆናቸውን ገለጹ – Welcome to Fana Broadcasting Corporate S.C ፍርድ ቤቶች የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ተፈጻሚነት ለማረጋገጥ ዝግጁ መሆናቸውን ገለጹ አዲስ አበባ፣ ሚያዚያ 6፣ 2012 (ኤፍ.ቢ.ሲ) የኮሮናቫይረስ (ኮቪድ 19) ወረርሽኝ ስርጭትን ለመከላከል፣ ለመቆጣጠርና የሚያስከትለውን ጉዳት ለመቀነስ የወጣውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተፈጻሚነት ለማረጋገጥ ዝግጁ መሆናቸውን ፍርድ ቤቶች ገለጹ። መንግስት የኮቪድ 19 ወረርሽኝ ስርጭትን ለመከላከል፣ ለመቆጣጠርና የሚያስከትለውን ጉዳት ለመቀነስ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ወደ ስራ ገብቷል። አዋጁን ተከትሎ የወጣው የማስፈፀሚያ ደንቡ በአራት ዋና ዋና ከፍሎች ክልከላን በማስቀመጥ፤ ግደታዎችን በመጣል፤ የአስፈፃሚ አካላትን ክንውን በመዘርዘር ልዩ ልዩ ድንጋጌዎችን አስቀምጧል፡፡ በዚህም የፌደራል ከፍተኛ እና የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤቶችም መደበኛ የወንጀል ዳኝነት አስራር ስርዓትን ለጊዜው በማቆም በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መሰረት ስራቸውን እንዲያከናውኑም ተደንግጓል። በተለይም በአስቸካይ ጊዜ አዋጁ ድንጋጌዎች በተቋማትና ድርጅቶች ሲጣሱ ግለሰቦችም አዋጁን ሲተላለፉ ፍርድ ቤቶቹ በህግ ተጠያቂ ያደርጋሉ። የአስቸካይ ጊዜ አዋጁ አስፈጻሚ ከሆኑት መካከል ፍርድ ቤቶች ለአዋጁ ተፈጻሚነት ያላቸውን ዝግጁነት ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ገልጸዋል። የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት አቶ ብርሃነ መስቀል፥ መንግስት የዜጎቹን ህልውና ለመጠበቅ ያወጣው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተፈጻሚ እንዲሆን በቅድሚያ ሁሉም ዜጋ የበኩሉን ድርሻ ሊወጣ ይገባል ብለዋል። ይሁንና ይህ አዋጅ ተፈጻሚ እንዳይሆን የሚቀሳቀሱ በተለይም አዋጁን ተላልፈው የተገኙ ሰዎችን በህግ በተቀመጠው የቅጣት አወሳሰን መሰረት በዳኝነት አካሉ ፈጣን እልባት ለመስጠት በፍርድ ቤቶች በኩል ዝግጁነት እንዳለ አረጋግጠዋል። በተለይም የአስቸካይ ጊዜ አዋጁን ተከትሎ በፍርድ ቤቶች ተረኛ ችሎቶችን በአጭር ጊዜ ውስጥ እንዲደራጁ በማድረግ በአዋጁ አተገባበር ዙሪያ የሚገጥሙ መተላለፎችን በህግ መሰረተ ተፈፃሚ ለማድረግ በትኩረት ይሰራል ብለዋል። የፌዴራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት አቶ ፉአድ ኪያር አህመድ በበኩላቸው፥ የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን ለመከላከል ፍርድ ቤቶች ከመጋቢት 10 ጀምሮ በከፊል የተዘጉና በተረኛ ችሎት ለውሳኔ የደረሱ እና ውዝፍ መዛግብት ላይ ውሳኔዎችን እየሰጡ እንደሚገኙ ተናግረዋል። ለአስቸኳይ አዋጁ ተፈጻሚነት ግን ፍርድ ቤቱ ዝግጁ ነው ያሉት አቶ ፉአድ፥ የህግ እልባት የሚሹ ጉዳዮች ሲያጋጥሙም በተረኛ ችሎት በመመልከት አፋጣኝ እልባት ለመስጠት ቁርጠኝነት መኖሩንም ተናግረዋል።
የ1960ዎቹ የኢትዮጵያ አብዮት ንቅናቄ አንዱ ፍንካች፣ በትግራይ እና በኤርትራ የሽምቅ ወታደራዊ ባህሪ ይዞ የቀጠለው ትግል መሆኑ እሙን ነው። በርግጥ የትግራይ ዐመጽና ተቃውሞ መሪዎቹ ከሚሉትም ባለፈ፤ የመነሻ ምክንያቱ ሰፊና መዋቅራዊ ፍላጎት እንደነበረው አይዘነጋም። በዚህ ዐውድ፣ የዛሬዎቹ የወያኔ መሪዎችን እና የትግራይ ልሂቃንን ተጣራሽ አቋምና ፖሊሲዎች በአጭሩ እንመለከታለን። በትብብርና የቅራኔ ታሪክ የቆመው የወያኔ ፖሊሲ ወያኔ አንድን አጋር ድርጅት ወይም ስብስብ ለወታደራዊም ሆነ ለፖለቲካዊ ፍላጎቱ ተጠቅሞ መጣልን ‹መርህ› በሚል የዳቦ ስም እንደሚያቆላምጠው ልብ ይሏል። እንዲህ ዐይነቱን ኀቡዕ ምንፍቅና የተጫነው “ግንኙነት”ም፣ ከበርካታ ድርጅቶች ጋር እንዳደረገው ሁሉ፤ ከኤርትራ ዐማጺያንም ጋር ሲዳከም ትብብርን፣ ሲጠናከር ቅራኔን የተከተለ “ወዳጅነት” ፈጥሮ ነበር። በተለይ በትግሉ መጀመሪያ አካባቢ በአስመራ ዩኒቨርሲቲ የነበሩ የትግራይ ተወላጆች፣ ከኤርትራው ነፃ አውጪ ጀብሓ የድጋፍ ቃል እንዲገባላቸው ብዙ ጥረዋል። በኋላ ምንም እንኳ ጀብሓን ጥለው ሻዕቢያ ላይ ቢንጠላጠሉም። ይህን በተመለከተ ጆን ያንግ “The Tigray and Eritrean Peoples Liberation Fronts;- A History of Tensions and Pragmatism” (1996) የሚል ርዕስ በሰጠው ጽሑፉ ሻዕቢያ፣ ለወያኔ ድጋፍ የማድረግና የማጠናከር ውሳኔ ላይ የደረሰው፣ የነፃነት ጥያቄውን መቀበሉን መሰረት በማድረግ እንደነበረ አስረግጧል። በቀጣይነትም የወያኔ የጦር አዛዥ ስዬ አብርሃን ጨምሮ፤ ዘጠኝ አባላት ያሉት የአመራር ቡድን፣ በኤርትራ ለሦስት ወራት ስልጠናዎችን ወስዶ ተመልሷል። አስመራ በነበሩ የትግራይ ተማሪዎች የድጋፍ ቃል ሲጠየቅ የነበረው ጀብሓም፣ ትግራይ በነበረው የመንግሥት ወታደራዊ ማዕከላት ላይ ከሰነዘራቸው ጥቃቶች፣ ወያኔ የውጊያ ልምድ ማግኘቱ አይካድም። ይህም፣ በጀብሓ እና ወያኔ መሃል በጎ ወታደራዊ ትብብር እንዲፈጥር ያስቻለ ነበር። በተለይ ደርግ በ1968 ዓ.ም (በፈረንጆቹ 1976) የኤርትራ ዐማጺያኖችን ለመምታት “ራዛ ኦፕሬሽን” የተሰኘ ዘመቻ ባወጀበት ወቅት፣ ወታደራዊ ትብብሩን ሻዕቢያም ተቀላቅሎት፣ ዘመቻውን አክሸፈውታል።
እግዚአብሒር ንኣዳም ንሔዋንን ካብ ኣርባዕተ ባሕርያት ፈጢሩ ብመንፈስ ቅዱስ ቀዲሱ ኣኽቢሩ ብዘይካ ሓንቲ ኦም በለሰ ኵሉ ወንኑ ብልዑ ስተዩ ኢሉ ኣብ ገነት ኣቐመጦም፡ ነታ ኦም እቲኣ’ውን ነፊግሎም ኣይኰነን እንታይ ደኣ ናቱ ገዛእነትን ናታቶም ተገዛኢነትን ንኽፈልጡ ንመጻኢ’ውን ሥርዕት ጾም ንኽምህሮም እዩ።(ዘፍ.2፡6-7) ሸውዓተ ዓመት ትእዛዙ ሓሊዎም ብውሉድነት ጸኒዖም ክነብሩ ኸለዉ ብድሕሪኡ ግን ናይ ከይሲ ምኽሪ ሰሚዖም ፤ ኣምላኽነት ተመንዮም ትእዛዙ ኣፍረሱ፤ ካብ’ታ ኣይትብልዑ ዝበሎም ኦም በሊዖም፤ ኣብ ልዕሊ ሞተ ሥጋ ሞተ ነፍስ ተፈርዶም፤ “ሞት ግን ካብ ኣዳም ክሳብ ሙሴ ኣብኣቶም ከም’ቲ ናይ ኣዳም ትእዛዝ ብምጥሓስ ኃጢኣት ኣብ ዝገብሩን ዘይገብሩን ነጊሡ ነበረ’’። (ሮሜ .5፡14) ብድኅሪ’ዚ ጽቡቕን፤ ክፉእን ፤ ነዊሕን ፤ ሐጺርን ፤ ቀይሕን ፤ ጸሊምን፤ ምግቡ እንተ በላዕካዮ ደዌ ሥጋ ፍልጸት ፤ቅርጸት ፤ መንፋሕቲ ፤ ቅርጥማት፡ ደዌ ነፍሲ ኸኣ ዝሙት፤ ኃጢኣት ኣብ ዝነግሠሉ ናብ’ዚ ዓለም’ዚ ሰደዶም “ወተሰዱ ውስተ ምድረ ሕማም ወኣራያ ሕሱም ወኃሣር ወሲሳየ ኃዘን” ከም ዘበለ። (መቅ.ወንጌል) ነገር ግን ኣብ ጐድኒ ቁጥዓኡ ምሕረቱ ከም ዘሎ ፈሊጦም ተጣዒሶም ሚእቲ ዓመት ንስሓ ኣትዮም በኸዩ፤ “ወኮኑ ውስተ ኃዘን ምእተ ዓመት”፡ ብፍጥረቱ ጨኪኑ ዘይጭክን ጐይታ ንስሓኦም ርእዩ ተቐቢሉ ብኽያትቶም ሰሚዑ። “በሐሙስ ዕለት ወበመንፈቃ ለዕለት እትወለድ እምወለተ ወለትከ፤ ወእከውን ሕፃን በእንቲኣከ፤ ወእድህከ ውስተ ምርህብከ፤ ወእትቤዘወከ በመስቀልየ፡” ድሕሪ ሓሙሽተ መዓልትን ፈረቓ መዓልትን ካብ ጓል ጓልካ ተወሊደ ምእንታኻ ሕፃን ኰይነ ኣብ ጐላጒልካ ፍሑኽ ፍሑኽ ኢለ ብመስቀለይ ክብጀወካ እየ ክምዝበለ።(ቀሌምንጦስ) እቲ ተስፋ ንደቁ ነጊርዎም ነበረ፣ ደቁ ኸኣ ትንቢት እናተነበዩ ሱባዔ እናቘጸሩ ከም’ቲ ዳዊት ዝበሎ። “አንሥእ ኃይለከ ፈኑ እዴከ” ኃይልኻ ዝተባህለ ወልድ ብሥጋ ሰዲድካ ኣድሕነና። (መዝ.144፡7)እናበሉ እቲ ተስፋ እቲ እናተጸበዩ በብተራ ሓለፉ፡ ሓሙሽተ መዓልቲ ፈረቓን ዝበሎ ግን ብእግዚአብሔር ኣቋጻጽራ ሰዓት 5500(ሐሙሽተ ሽሐን ሓሙሽተ ምእቲን ዓመት) እዩ ዝነበረ። (መዝ.90፡4 ፡ 2ይጴጥ.3፡8) እቲ ዝተባህለ ዓመት ምስ ኣኸለ። ዝተዛረቦ ዘይርስዕ ዝህቦ ተስፋ ዘይከልእ እግዚአብሔር ሓደ ሰዓት ወይ ደቒቕ ከየሕለፈ ካብ ቅድስት ድንግል ማርያም፤ ካብ ሥጋኣ ሥጋ፤ ካብ ነፍሳ ነፍሲ ወሲዱ፤ ብዘመነ ዮሐንስ ብዕሥራን ትሽዓተን መጋቢት፤ ብሣልሳይ ሰዓት ፤ ብዕለተ እሁድ ተፀንሰ፡ ድሕሪ ትሽዓተ ወርሕን ሓሙሽተ መዓልትን ብዘመን ማቴዎስ ዕሥራን ትሽዕተን ታሕሣስ ሠሉስ መዓልቲ፤ ፍርቂ ለይቲ ተወልደ። ብዳሕራይ ዘመን ካብ ሠለስተ ኣካላት ሓደ መጀመርታ ዘይብሉ ናይ እግዚአብሔር ቃል ማንም ከየገደዶ ብናቱን ብናይ ኣብኡን ብመንፈስ ቅዱስን ፍቓድ ሰብ ኮነ፤ ኣብ ሰማይ ካብ ዘለው መላእኽቲ ሰብ ከም ዝኾነ ምንም ኣይፈለጡን፤ ካብ ኣቦን ካብ ኣደን ዝተወልደት ካብ ቅድስት ድንግል ማርያም ሐደረ፤ ሥጋ ዘይብሉ ንሱ ሥጋ ተዋሒዱ ከም ሰብ ትሽዓተ ወርኂን ሓሙሽተ መዓልትን ብጐይትነቱ ኰሎ ኣብ ማኅፀና ተወሰነ፤ ትሽዓተ ወርኂን ሓሙሽተ መዓልትን ምስ ተፈጸመ፣ ዝውለደሉ መዓልቲ ምስኣኸለ ክምርመር ብዘይከኣል ተግባር ብሕቱም ድንግልና ተወልደ፤ ማኅተመ ድንግልናኣ’ውን ኣይተለወጠን ማኅተመ ድንግልናኣ ከይተለወጠ ደኣ ተወልደ። (ጎርጎርዮስ ዘእንዚናዙ ሃይማኖተ ኣበው 212 ገጽ) ክሳብ እዛ መዓልቲ እዚኣ ጽቡቕ ተግባር ዝገበሩ ቅዱሳን ሓዋርያት ሰማዕታት ኵሎም ከም ዘኣመንዎም እምነት ከምኡ ኢና ንኣምን፤ “ቃል ሥጋ ኮነ” መናፍቃን ከም ዝብልዎ ኣብ (ዕሩቅ ብእሲ) ተራ ሰብ ኣይሓደረን። ብናቱ ፍቓድ፤ ብናይ ኣብኡን፤ ብናይ መንፈስ ቅዱስን ድልየት ካብ ቅድስት ድንግል ማርያም ሥጋ ወሲዱ ተዋሃሃደ፤ ከም’ቲ ዝተጻሕፈ ኵሉ ዝፈጠረ ኣምላኽ ናይ ኣብ ኣካልዊ ቓል ፍጹም ሰብ ኰይነ ተወልደ።(ገላ.4፡4) ዝተባህለ ነስተውዕል እግዚኣብሔር ካባና ባሕርይ ዝተዋሃሃዶ ተዋሕዶ ንእሽቶ ክብሪ ኣይምሰለና፤ እዚ ንመላእኽቲ እኳ ኣይተገብረን፤ ናይ መላእኽቲ ባሕርይ ኣይተወሓሃደቶን ዝተዋሃሃደቶስ ናትና ባሕርይ እያ ንሱ’ውን ንባሕርይና ደኣ ተውሃዳ ንምንታየይ ኣይበለን። (ቅዱስ ዮሐንስ ኣፈወርቂ ሃይማኖተ ኣበው ገጽ 219፡21) ካብ ሠለስተ ኣካላት መን እዩ ዝተወልደልና እንተ ተባህለ እግዚአብሔር ወልድ እዩ፤ ስለምንታይ አብን ፤ መንፈስ ቅዱስን ተወሊዶም እንተ ዝብሃልከ ናይ ባሕርይ ስሞምን ተግባሮምን ምተፋለሰ ነይሩ። ከም’ዚ ከይከውን ግና እግዚኣብሔር ወልድ ብናይ ባሕርይ ስሙን ብናይ ባሕርይ ግብሩን ንምጽዋዕ ብሥምረቱን ድልየቱን ብጀካ ኃጢኣት ፍጹም ሰብ ኰይኑ ተወልደ። “ወአኮ አብ ዘኃደረ ውስተ ከርሠ ድንግል ለተሰብአ፤ ከመ ኢይበል መኑሂ ይትፋለሰ ስመ አብ ወመንፈስ ቅዱስ ለከዊነ ስመ ወልድ፤ ኣላ ውእቱ ወልድ በፈቃደ አቡሁ ወበሥምረተ መንፈስ ቅዱስ ተሠገወ እስመ አሐቲ ፈቃደ ዘሥሉስ ቅዱስ” ። ማንም ሰብ ስም አብን መንፈስ ቅዱስን፤ ናብ ስም ወልድ ንምዃን ተቐያሪ እዩ ንኸይበሃል፤ ኣቦ፥ ሰብ ንምዃን ኣብ ማኅፀን ድንግል ኣይሐደረን፤ እንታይ ደኣ ፍቓድ ቅድስት ሥላሴ ሓደ ስለ ዝኾነ ወልድ ብፍቓድ አብን፤ ብሥምረት መንፈስ ቅዱስን እዩ ሥጋ ዝተወሃሃደ። ይብል። (ቅዱስ ሳዊሮስ ዘአንጾኪያ) ከም’ዚ ሰለ ዝተባህለ ግን አብ ንምጽናዕ፤ ወልድ ሥጋ ንምውህሃድ፣ መንፈስ ቅዱስ ከኣ ንምንጻሕ ፤ ኣብ ከርሢ እግዝእትነ ማርያም ኃደሩ ንብል ነኣምን’ውን። መንፈስ ቅዱስ ንእግዝእትነ ማርያም ኣንጺሕዋ ይብል ካብ ምንታይ ኣንጺሕዋ ማለት እዩ እንተ ተባህለ ካብ ናይ ኣንስቲ ልማድ፤ ካብ ዘርእን፤ ርኳቤን “ውእቱ ንጹሕ እምሠለስቱ ግብራት ዘውእቶሙ ዘርእ፤ ውሩካቤ፤ ወሰስሎተ ድንግልና፤ እለ ሥሩዓን በእጓለ እመ ሕያው ወእሙራን ቦሙ”። ንሱ ኻብ’ቶም ኣብ ደቂ ሰባት ዘለዉ ፍሉጣትን ሥሩዓት ዝኾኑ ሠለስተ ተግባራት ዘርእን ፤ ሩካቤን ንጹሕ እዩ ይብል ። (ስኑትዮ ዝእስክንድርያ) ነገር ግን እዚ ዀሉ ኣብ እግዝእትነ ማርያም ኔሩ ኣይኮነን ንሳስ ናይ ኣዳም ኃጢኣት ዘይረኽባ ንጽሕቲ ባሕርይ እያ፡ “ወኢረኵሰት በምንትኒ እምዘፈጠራ ድንግል ብኅሊናሃ ወድንግል በሥጋሃ” ይብላ፡ (ሃይማኖት ኣበው)። እዚ ዝተብህለ ናይ ደቂ ኣዳም ሥርዓት ንኽይበጽሓ ካብ ትፍጠር ጀሚሩ ቀዲስዋ ኣካላዊ ቃል ጐይታና ኢየሱስ ክርስቶስ ንምውላድ ኣብቂዕዋ ንማለት እዩ፡ “ መንፈስ ቅዱስ አንጽሐ ለማርያም ወረሰያ ድሉተ ለተወክፎ ቃል አብ” ከም ዝበለ፡ (ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ) ቅዱስ ገብርኤል መልኣኸ ክትፀንሲ ኢኺ፤ ወዲ’ውን ክትወልዲ ኢኺ ምስ በላ ንሳ’ውን ከም’ቲ ዝበልካኒ ይኵነለይ ምስ በለቶ፣ ክምርመር ብዘይከኣል ተግባር ብዘይውሱን ኣካል ቅድሚ ዓለም ዝነበረን ዘሎን ንዘልዓለም ዝነብርን ኣካላዊ ቃል ብምልኣትን ብጐይትነትን ካብ አብን መንፈስ ቅዱሱን ሓድነት ከይተፈለየ፤ ብድንግልና ጸኒዓ ካብ ዝነበረትን ዘላን ንዘለዓለም’ውን ትነብርን ካብ ኣዴና ቅድስት ደንግል እግዝእትነ ማርያም ብናይ መንፈስ ቅዱስ ግብሪ ናይ ዕለት ፅንሲ ኾነ፡ “ነሥአ ሥጋ እንዘ ምሉእ በኵለሄ እንዘ ኢየዐርቅ እመንበረ ስብሐቲሁ ፤ ውስተ ማኅፀነ ድንግል ኅደረ ሥጋ ኮነ ወተወልደ” ኣብ ኵሉ ምሉእ ኰሎ ሥጋ ንምልባስ ኣብ ማኅፅን ተወሰነ፤ ካብ ናይ ሥልጣኑ መንበር ከይለቐቐ ኣብ ማኅፀን ድንግል ሓደረ፤ ሥጋ ለቢሱ ኸኣ ተወልደ ይብል፡ (ያሬዳዊ መዝሙር(ድጓ)) ናይ ዕለት ፅንሲ ኮይኑ ዝተቈጽረሉ ምሥጢር ግን ዝፈልጦን ዝምርምሮን የለን፤ ንሱ ብዝፈልጦ እዩ ኣካላዊ ቃል ሰብ ዝኾነ። “ወአሜሃ ሥጋሁ ለእግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ ተሥዕለ በጥንተ ኣካል እንዘ ይትወሐድ ምስለ ቃል”። ሽዑ ሥጋ ጐይታና ኢየሱስ ክርስቶስ ምስ ኣካላዊ ቃል ብምውሕሃድ ብጥንታዊ ኣካል ኣዳም ተፈጥረ ይብል ። (ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቒ) በቲ ጊዜ እቲ ሥጋ ምስ ቃል ተወሃሃደ ሓደ ኣካል ሓደ ባሕርይ ኾነ “ወረሰዮ ምስሌሁ አሐደ ህላዌ ወአሕደ ሥምረተ ወአሐደ አካለ ዘእግዚአብሔር ቃል’’ (ቅዱስ ጎርርዮስ ዘኑሲሰ)። ስለ’ዚ መለኮት ምስ ሥጋ ብምውህሃድ ሰብ ኣምላኽ ኮነ ፤ ሥጋ ምስ መለኮት ብምውህሃድ ከኣ ኣምላኽ ሰብ ኮነ፤ ረቂቕ ዝነበረ መለኮት ምስ ሥጋ ብምውህሃድ ግዙፍ ዝድህሰስ ኾነ፤ ግዙፍ ሥጋ ምስ መለኮት ብምውህሃድ ረቂቕ ኮነ ፤ ወሰን ዘይነብሮ መለኮት ብሥጋ ውሱን ኮነ፤ ውሱን ዝነበረ ሥጋ ብመለኮት ዘይውሱን ኣብ ኵሉ ምሉእ ኮነ ፡ ወልድ አብ ብመለኮቱ ወልደ ማርያም ብትስብእቱ፥፡ ክልተ ልደት ብምውህሃድ ኸበረ፤ ሥጋ ምስ መለኮት ብምውህሃድ ባሕርያዊ ወዲ እግዚአብሔር ኮነ። “ወይደልወነ ንእመን ከም ቦቱ ለወልደ እግዚአብሔር ክልኤቱ ልደታት ቀዳሜ ልደት እምእግዚአብሔር አብ ፤ እምቅድመ ኵሉ መዋዕል ፤ ወዳግም ልደት እምእግዝእትነ ድንግል ማርያም በድኃሪ መዋዕል”፡ ንወዲ እግዚአብሔር ክልተ ልደት ከም ዘለዎ ክንኣምን ይግበኣና እዩ፤ ቀዳማይ ልደት ቅድሚ ዓለም ወዲ እግዚአብሔር አብ ምዃኑ፤ ካልኣይ ልደት ከኣ ዳሕራይ ጊዜ ካብ እግዚእትነ ማርያም ምውላዱ ከም ዝበለ። (ቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሳርያ) “ወለእመኒ ቃል ሥጋ ኮነ ፤ እመቦ ዘሰገደ ለቃል ናሁ ሰገደ ለሥጋ፤ ወዘሂ ሰገደ ለሥጋ ሰገደ ለእግዚአብሔር ቃል፤ ወከማሁ መላእክትኒ ይትለኣኩ ለአርአያ ሥጋ፤ ወየአምሩ ከመ እግዚኦሙ ውእቱ ወይሰግዱ ሎቱ፡”። ቃል ምስ ሥጋ ብምውህሃዱ ንቓል ዝሰገደ እነሆ ንሥጋ ሰገደ’ውን ንእግዚአብሔር ቃል ሰገደ፤ መላኣኽቲ’ውን ከምኡ ንብሥጋ ዝተገልጸ ይለኣኹ፤ ጐይትኦም ምዃኑ ፈሊጦም ከኣ ይሰግድሉ ይብል። (ሃይማኖተ ኣበው) “ወሶቦሂ ሰቀሉ ኣይሁድ ሥጋሁ ፤ ሰቀሉ ኪያሁ፤ ወአልቦ እም ውስተ መጻሕፍት ፍልጠት ማእከለ ቃል ወሥጋሁ አላ አሐዱ ህላዌ ፤ ወአሐዱ ገጽ ፤ ወአሐዱ ግብር ውእቱ ፤ ኵለንታሁ አምላክ ወውእቱ ኵለንታሁ ብእሲ ወአሐዱ ግብር ዘመለኮት ወዘትስብእት ኅብሩ”። ኣይሁድ ንሥጋኡ ምስ ሰቐሉ ፤ ንቓል’ውን ሰቀሉ፤ ብመጻሕፍቲ ወገን ኣብ ማእከል ቃልን ሥጋኡን ፍልልይ የለን፤ እንታይ ደኣ ሓደ ባሕርይ ፤ ሓደ ግብርን፤ ብዅለንተናኡ ፍጹም ኣምላኽ ፍጹም ሰብን እዩ ይብል። (ሃይማኖተ ኣበው) ቃል ሥጋ ኮነ ብኸመይ ነገር ወላዲተ ኣምላኽ ተባሂላ፤ ሥጋ ድማ ቃል ከይኮነ ብኸመይ ነገር ናብ ባሕርያዊ ወዱ ኾነ፤ ንመላእኽቲ’ውን ጎይትኦም ንምንታይ ተባህለ፡ ወላዲተ ኣምላኽ ኢልና እናምን እምበር ብኸም’ዚ ዝበለ ተዋህዶ እዩ። ኣምላኽ ሰብ ከይኮነ ወዲ ኣዳም ድኂኑ ክብሃል ኣይከኣልን፤ ሰብ’ውን ኣምላኽ ከይኮነ ምእንቲ ደቂ ኣዳም ሓሚሙ ፤ ተሰቒሉ ሞይቱ ክብሃል ኣይከኣልን፤ ዓርቢ መዓልቲ ተሰቒሉ መሥዋዕቲ ዝኾነ ናይ ጐይታና ሥጋን ደምን እዩ፤ ማለት ናይ ኣምላኽ ሥጋን ደምን እንተ ዘይኮይኑ ናይ መን ጻድቕ ፤ ወይ ሰማዕት ሥጋን ደምን እዩ መሥዋዕት ኮይኑ ንዘልዓለም ክሳብ ዕለተ ምጽኣት ወሀቢ ሕይወትን ድኅነትን ኮይኑ ዝነብር። ብኸም’ዚ ዝበለ ናይ ተዋህዶ ምሥጢር ናይ እሳት ብሐይን ኣካልን ተለዊጡ ኃፂን ከይኮነ ፤ ከምኡ ኸኣ ናይ ብርሃን ባሕርይ ተለዊጡ ዕንቍ ከይኮነ፤ በተዕቅቦ ሓደ ኣካል ሓደ ባሕርይ ከም ዝኸውን ከምኡ ድማ መለኮት ምስ ትስብእት፤ ትስብእት ምስ መለኮት ብምውህሃድ ፤ ካብ ክልተ ኣካል ፤ ሓደ ኣካል ፤ ካብ ክልተ ባሕርይ ሓደ ባሕርይ ኮነ። “ወይትሜሰል ወልድ በዕንቈ ባሕርይ እንተ ይእቲ በአማን ኵለንታሃ ብርሃን ፣ ወይትሜሰል ሥጋሁ በሥጋሃ ፤ ወብርሃና በመለኮቱ። ባስልዮስ”፡ በአይ ኣምሳል ይትሜሰል መለኮት በትስብእት ፤ ይቤ ይመስል እሳተ በሕፂን ብንያሚ” ወልድ በታ ብዅለትናኣ ብርሃን ዝዀነት ዕንቈ ባሕርይ ይምሰል ፤ ሥጋኡ ብሥጋኡ ብርሃና ብመለኮቱ ይምሰል ይብል፡ (ቅዱስ ባስልዩስ ዘኣንጾኪያ) ሓፂን ጸሊም ከሎ ምስ እሳት ብምውህሃዱ ይበርህ ደኣ እምበር ኣይጽልምን፤ እቲ ሓፂን ዝፍለ እንተ ኮነ ፤ መለኮት ግን ካብ ትስብእት ተፈልዩ ኣይብሃልን ይብል። “ናሁ ድንግል ትፅንስ ወትወልድ ወልደ” እንሆ ድንግል ክትፅንስ ወዲ’ውን ክትወልድ እያ።(ኢሳ።7፡14) ጐይታና ኢየሱስ ክርስቶስ ካብ እግዚእትነ ማርያም ብኅቱም ድንግልና ምውላዱ ብኸመይ እዩ፧ ንዝብል ንምሳሌ ካብ ዐይኒ ብርሃን ካብ ግንባር ድማ ረሓጽ ብኅቱሙ ከም ዝርከብ፤ ከምኡ ኸኣ ጎይታና ኢየሱስ ክርስቶስ ማኅተመ ድንግልናኣ ከይፈትሐ ብኅቱም ድንግልና ተወልደ። “ተወልደ እም ድንግል እንዘ ኅቱም ድንግልናሃ፤ ከመ ልደተ ንጻሬ አዕይንት፤ ወከመ ልደተ ሐፍ እም ገጽ፤ ወከመ ልደተ መልክዕ እመጽሔት” ከም ዝበለ። (ቅዱስ ያዕቆብ ዘእልበረዲ) ከምኡ ድማ ናይ ፀሐይ ነጸብራቕ ምስ ማይ ተዋሀሂዱ ዕንቈ ባሐርይ ከም ዝወልድ፤ ኣካላዊ ቃል ክርስቶስ ከኣ ምስ ደም ድንግልናኣ ተዋሃሂዱ ብዘይ ዘርኢ ተፀኒሱ ብኅቱም ድንግልናኣ ተወልደ፡ “ወዝኩ ዕንቈ ባሕርይ አኮ በተራክቦ ዘይፀነስ ወይትወልድ፤ ባሕቱ ይትወልድ በተዋሕዶተ መብረቅ ወማይ፡ ወከማሁ እግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ ተፅንሰ ዘእንበለ ትድምርተ ሥጋ፤ ወኮነ እመንፈስ ቅዱስ ተፅንሶቱ ለእግዚአብሔር ቃል ሥጋ ኮነ” ከም ዝበለ። (ቅዱስ ኤፍሬም.ኣፍ.በረከት) ካብ አብን መንፈስ ቅዱስን ሓድነት ከይተፈለየ፤ ኣብ ኵሉ ምሉእ ከሎ ሥጋ ምዃኑ ከመይ እዩ፧ እንተ ተባሀለ ናይ ዐይኒ ብርሃን ካብ ክበብ ዓይኑ ከይተፈለየ ፤ ምስ ብርሃነ ፅሐይ ተዋሃሂዱ ምሉእ ኰይኑ ከም ዝርኢ፤ ከምኡ ድማ ጐይታና ብመለኮታዊ ባህርዩ ኣብ ኵሉ ምሉእ ከሎ ኽምርምር ብዘይከኣል ምሥጢር ከም ቅጽበት ዓይኒ ሰብ ኮነ ፤ ዘይፍለን ዘይምርመርን ዘይፍለጥን ተዋህዶ ኮነ። “ወመጽአ እንዘ ኢይትፈልጥ እምሕፅነ አቡሁ፤ ሰማያትኒ ወምድር ምሉአን እምኔሁ”። ካብ ናይ ባሕርይ ኣቡኡ ካብ አብ፤ ካብ ናይ ባሕርይ ሕይወቱ ካብ መንፈስ ቅዱስ ሓድነት ከይተፈለ ፤ ሰብ ኮነ ፤ ሰብ ድኅሪ ምዃኑ ድማ ሰማይን ምድርን ብእኡ ምሉኣት እዮም ማለት ኣብኣቶም ብምልኣት ህልዊ እዩ። ( ቅዱስ ዮሓንስ. ዘኣንጾኪያ) “አንተ ውእቱ አምላክ ዘበአማን ፤ ወአንተ ሰብእ ፍጹም ዝእንበለ ሕፅት፤ ወአንተ ውእቱ ዘትነብር ዲበ መንበረ ስብሐቲከ ፤ ወአንተ ዲበ ዕፀ መስቀል” ሓቀኛ ባሕርያዊ ኣምላኽ ንስኻ ኢኻ፤ (ሕፀፅ) ጉድለት ዘይብልካ’ውን ፍጹም ሰብ ኢኻ፡ ኣብ ልዕሊ መስቀል ምእንቲ ኃጢኣትና ዝተሰቐል ካ’ውን ንስኻ ኢኻ። ኣብ ናይ ጐይትነትካ መንበር እትነብር’ውን ንስኻ ኢኻ። (ቅዱስ ዮሓንስ ኣፈወርቒ ብድርሳነ ቶማስ) ካብ ብዝኅ ብውኅዱ ምሥጢረ ሥጋዌ እዚ እዩ፡
አጋር ሀገሮች የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትረምፕ የኢኮኖሚ ፖሊሲን የሚንቅፉ ቢሆንም ፕሬዚዳንቱ በመጪው የቡድን ሰባት ጉባዔ ላይ በአቋማቸው እንደሚፀኑ ከዋና የኢኮኖሚ አማካሪዎቻቸው አንዱ ትላንት ለጋዜጠኞች ተናግረዋል። ዋሺንግተን ዲሲ — አጋር ሀገሮች የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትረምፕ የኢኮኖሚ ፖሊሲን የሚንቅፉ ቢሆንም ፕሬዚዳንቱ በመጪው የቡድን ሰባት ጉባዔ ላይ በአቋማቸው እንደሚፀኑ ከዋና የኢኮኖሚ አማካሪዎቻቸው አንዱ ትላንት ለጋዜጠኞች ተናግረዋል። “ፕሬዚዳንቱ እነዚህ ከባድ ጉዳዮች አያስጨቋቸውም። ምን ጊዜም ቢሆን በዩናይትድ ስቴትስና በቡድን ሰባት አባል ሀገሮች መካከል ስለሆነ ነገር ውጥረት አለና” ሲሉ የብሄራዊ ኢኮኖሚ ካውንስል ሥራ አስኪያጅ ላሪ ኩድሎው አስገንዝበዋል። ኩድሎው በዋይት ኃውስ ቤተመንግሥት በተደረገው ጋዜጣዊ ጉባዔ ይህን ያሉት የቡድን ሰባት ጉባዔን የሚያስተናግዱት የካናዳ ጠቅላይ ሚኒስትር ጃስቲን ትሩዶና የጀርመን ቻንስለር አንጌላ መርከል ነገና ቅዳሜ በማካሄደው ጉባዔ ላይ ከባድ ውይይት እንደሚደረግ ከገለፁ በኋላ ነው።
ድርጅቱ ጥሪውን ያቀረበው ድርጊቱን የፈጸሙት በክልሉ የሚገኙና ራሳቸውን የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት ብለው የሚጠሩ፣ መንግስት ደግሞ “ሸኔ” ብሎ የሚገልጻቸው ታጣቂዎች ናቸው ሲሉ የተናገሩትን በአካባቢው የሚገኙ የዓይን እማኞችን ጠቅሶ ነው። ሁከት እየተባባሰ በመጣበት የምዕራብ ወለጋ አካባቢ ሰኔ አስራ አንድ ቀን በአማራ ተወላጆች ላይ ለተፈጸመው ጭፍጨፋ መንግስት “ሸኔ” ብሎ የሚጠራውና ራሱን ደግሞ የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት ብሎ የሚገልጸውን ቡድን ተጠያቂ ሲያደርግ፥ ታጣቂው በበኩሉ ከመንግስት ጋር ያበሩ ሚሊሺያዎችን ተጠያቂ ያደርጋል። አምነስቲ ኢንተርናሽናል ያነጋገራቸው ዘጠኝ የዓይን እማኞች እንደሚሉት የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት በቶሌ ቀበሌ ላይ ጥቃት መሰንዘር የጀመረው ከጠዋቱ 3 ሰዓት ጀምሮ ነበር። ገና የመጀመሪያው ጥይት እንደተተኮሰ ነዋሪዎቹ ለአካባቢው ባለስልጣናት ቢያሳውቁም፣ የመንግስት ሃይሎች የደረሱት ጥቃቱ ከተጠናቀቀ ከሰዓታት በኋላ መሆኑን እማኞቹ ለአምነስቲ ተናግረዋል። አጥቂዎቹ የአማራ ተወላጆችን በጅምላ እንደጨፈጨፉ፣ ንብረት እንደዘረፋና ቤቶችን እንዳቃጠሉ ተናግረዋል። የሰብዓዊ መብት ድርጅቱ ይህንን ድርጊት በሳተላይት ምስሎች ማረጋገጡን ገልጿል። ምስሎቹ እሳት በአካባቢው እንደነበር ያሳያሉ ብሏል አምነስቲ። ዲፕሮሰ ሙቼና የአምነስቲ ኢንተርናሽናል የምስራቅና ደቡባዊ አፍሪካ ሃላፊ ሲሆኑ፣ “ይህ በቶሌ በተጠርጣሪው የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት የተፈጸመው ሰቅጣጭ ግድያ ፈጻሚዎቹ ለሰው ህይወት ግድ እንደሌላቸው ማሳያ ነው። ይህ የሴቶችንንና የህጻናትን ህይወት የቀጠፈ ጭቃኔ የተሞላበት ጭፍጨፋ በገለልተኛ ወገን በሚገባ መመርመር አለበት” ብለዋል። የአምነስቲ መግለጫ የወጣው ባለፈው ወር የተመድ የሰብዓዊ መብት ኮሚሽነር ምሼል ባቼሌት የኢትዮጵያ መንግስት በቶሌ የተፈጸመውን ግድያ በተመለከተ “ፈጣን፣ ገለልተኛና ጥልቀት ያለው” ምርመራ እንዲያደርግ ጥሪ ማድረጋቸውን ተከትሎ ነው። የ64 ዓመቱ ሁሴን ለአምነስቲ እንደተናገሩት 22 ልጆችና የልጅ ልጃቸውን በጥቃቱ ተነጥቀዋል። “በአንድ ቦታ ብቻ 42 ሰዎች ገደሉ። ከነዚህ ውስጥ አንድ ወንድ አዋቂ ብቻ ነው የነበረው፣ ሌሎቹ ሴቶችና ህጻናት ናቸው” ናቸው ብለዋል ሁሴን። ሌላኛው የዓይን እማኝ ደግሞ፣ “የአንድ ጎረቤቴን ቤት፣ ቤተሰቡ ልጆቹና የልጅ ልጆቹ ውስጡ እያሉ በእሳት አጋይተውታል። አንዷ የሰባት ወር እርጉዝ ስትሆን ከሁለት ልጆቿ ጋር ነበረች። ከሰል እስኪሆኑ ስለተቃጠሉ እዛው ግቢ ውስጥ ቀበርናቸው” ሲሉ ለአምነስቲ ተናግረዋል። የዓይን እማኞቹን ከበቀል ለመከላከል አምነስቲ እውነተኛ ስማቸውን በሚስጥር ይዟል። የሟቾቹን ቁጥር በተመለከተ እስከአሁን ኦፊሴላዊ ቁጥር ባይቀመጥም፣ የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ቃል አቀባይ ቢልለሌ ስዩም ባለፈው ወር በሰጡት መግለጫ 338 ሰለባዎች መለየታቸውን ተናግረዋል። አንድ የአካባቢው ባለስልጣን ቢያንስ 450 ሰዎች መገደላቸውን ለአምነስቲ ተናግረዋል። የዓይን እማኞቹ እንዳሉት አጥቂዎቹ በለበሱት መለዮ፣ በተሰሩት “ለየት ያለ ረጅም ሹሩባ” እና በሚጠቀሙት የኦሮምኛ ቋንቋ መሰረት የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት አባል መሆናቸውን መለየት እንደቻሉ ተናግረዋል። አጥቂዎቹ በተጨማሪም ቤቶችን ሲያቃጥሉ፥ ከብቶችን፣ ግንዘብና ሌሎች ንብረቶችን ከመንደርተኛው ዘርፈዋል። ባለስልጣናት “መንገድ በመዘጋቱ መድረስ አልቻልንም” ማለታቸውን የአምነስቲ መግለጫ ጠቅሷል። ባለስልጣናት በተጨማሪም በአማራ ተወላጆች ላይ ለተፈጸሙት በርካታ ጥቃቶች “ሸኔ” ብለው የሚጠሩት የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊትን ተጠያቂ ያደርጋሉ። ከ2010 ጀምሮ ከፌዴራል መንግስቱ ጋር ሲዋጋ የሰነበተው የኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት፥ በሰሜን ኢትዮጵያ ከመንግስትና ሌሎች ሃይሎች ጋር ጦርነት ውስጥ ከነበረው ህወሃት ጋር ባለፈው ዓመት የትግል አጋርነት በማወጁ ትኩረት አግኝቷል።
ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲና የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ (አብን) በሀገሪቱ ፍትህና ዴሞክራሲ እንዲሰፍን በጥምረት ለመስራት ያስችላል ያሉትን የትብብር ስምምነት ተፈራርመዋል። ትብብሩ በቀጣይ በአገሪቱ እንዲፈጠርና እንዲጎለብት የሚፈለገው የአገራዊ በጎ ሀይሎች ጥምረት መሰረት እንዲሆን ያለመ መሆኑም ተገልጿል። በመጪው አገራዊ ምርጫ የመራጮች የጋራ ፍላጎትና ራዕይ ለማሳካት ፓርቲዎቹ በጋራ ለመስራት በማሰብ የተመሰረ የፖለቲካ ትብብር መሆኑንም ነው ፓርቲዎቹ የገለፁት። በአገሪቱም ሆነ በዜጎች ላይ የተጋረጡ ፈተናዎች እንዳሉ የገለጹት ፓርቲዎቹ፣ ይህንን ከመቼውም ጊዜ በላይ በትብብር ለመታገል በቁርጠኝነት እንደሚሰሩና ትብብሩ ከምርጫው በኋላም እንደሚቀጥል አስታውቀዋል። (ኢቢሲ) የባልደራስ መሪና በአሁኑ ጊዜ በእሥር ላይ የሚገኙት አቶ እስክንድር ነጋ ከአማራ ድርጅቶች በተለይ ከአብን ጋር ምሥጢራዊ ግንኙነት አላቸው እየተባ ሲነገር ቆይቷል። እርሳቸው ግን በጎጥ እንደማያምኑ የተናገሩ ቢሆንም በሕብረብሔራዊነት ነው የተደራጀሁት ከሚለው መአህድ ጋር ይሠሩ እንደነበር ራሳቸው መናገራቸው ይታወሳል። የባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ እና የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ ትብብርን አስመልክቶ የተሰጠ መግለጫ የሀገራችን ህዝብ ለዘመናት በተጫኑበት ኢዲሞክራሲያዊና አምባገነን አገዛዞች የተነሳ፣ በነጻነት እጦት፣በስቃይ እና በመከራ ኑሮውን እንዲገፋ ተደርጓል። ጭቆናን አስወግዶ የሚፈልገውን ፍትህ እና እኩልነት እውን ለማድረግ ከፍትኛ ዋጋ መክፈሉም እሙን ነው። ይሁንና የሃገራችን የለውጥ ፍላጎት እና እንቅስቃሴ ጅማሮው ሳይሳካ፣ ለቀጣዩ ዴሞክራሲያዊ ትግል ተስፋ ሊሆን የሚችል መሰረታዊ የትርክትና የመዋቅር ክለሳ እንኳ ሳይደረግ አምባገነንነትና ዘረኝነት የእጅ ለውጥ ብቻ እያደረጉ የሚፈራረቁባት ሆናለች። በዚህ ሁሉ ፈተና ውስጥ ያለፈው ህዝባችን አሁንም ዲሞክራሲን፣ እኩልነትንና ዘላቂ ሰላምን በመሻት ለነጻነት የሚያደርገውን ትግል አጠንክሮ እንደቀጠለ ይገኛል። የዚህ አይነት መልክና ይዘት ተላብሶ የተደራጀው የተፎካካሪ ሀይል ለሰርጎ ገቦች የተጋለጠ፣ በተፈጥሮው ደካማና ተሰባሪ ከመሆኑም በላይ የአምባገነኑን ስርአት ራዕይ አቀንቃኝ እስከመሆን ደርሶ እንደነበር ይታወሳል። በተጨማሪ የተቃውሞው ጎራ እርስ በርሱ በፍረጃና በሴራ መጠላለፍ ምክንያት በቁርሾ እንዲሞላ በማድረግ የጋራ ሀገራዊ ስምሪት መውሰድ እንዳይችል አድርጎት ቆይቷል። በዚህ ሂደት ውስጥ አምባገነኖችን በጋራ መታገል ጥረት ከማድረግ ወርደው በመናኛ ፍላጎቶችና በጥቃቅን ልዩነቶች ዙሪያ ታጥረው ሲሻኮቱ በመካከል የባከነው ጊዜ እና የሰው ህይወት የሚያስቆጭ ነው። የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ (አብን) ሀገራችንን ለድሜ ልክ ዝቅታ የዳረጋት የጥላቻ ትርክት፣ ትርክቱን መሰረት አድርገው የተደነገጉ ህግጋትና የተዘረጉ መዋቅሮች ተከልሰው መላ ኢትዬጵያውያን በእኩልነት፣ በወንድማማችነት፣ በፍትህና በሰላም የሚተዳደሩነት ዘላቂ ስርአት በማስፈን በተለምዶ “መንታ ቅኝት” ያለው የትግል እንቅስቃሴ እያደረገ ይገኛል። የአብን ስትራቴጂክ ግብ መላውን ኢትዬጵያዊ የፍትሀዊ አማካኝ ተጠቃሚ በማድረግ ሁሉንም አሸናፊ የሚያደርግ የፖለቲካ ማእቀፍ እንዲፈጠር ሲሆን የድርሻውን ለማበርከት አበክሮ እየሰራ ያለ ንቅናቄ ነው። ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ /ባልደራስ/ ደግሞ የኢትዬጵያዊ ህብር አይነተኛ መገለጫ የሆነችውን የአድስ አበባ ከተማ ህዝብ ከከፋፋይና ከጥላቻ ፖለቲካ ነፃ ለማድረግና ህዝቡ ራሱን በራሱ የማስተዳደር መብቱ እንዲረጋገጥ ለማስቻል በሚል የተደራጀ ስለመሆኑ በሰፊው የሚታወቅ ነው። አዲስ አበባ ከተማ የኗሪዎቿ መሆኗን ለማረጋገጥ የሚያደርጉት የጋራ ትግል መነሻ ዴሞክራሲን፣ ነፃነትን፣ ፍትህንና እኩልነትን በማስፈን ላይ የተመሰረተ ሲሆን አንዳች ቅቡልነት ያለው መርህ ወይም ምክንያት ማጣቀስ የማይችሉ ሀይሎች ከተማዋ የአንድ ንጥል ብሄር ንብረት መሆኗን በይፋ በመግለፅ የማታገያ አጀንዳ በማድረግ ህዝቡ በነሱ ፍቃድና ይሁንታ መኖር እንዳለበት አድርገው ያወጁት ያልተገራ ፍላጎት የጋረጠበትን የህልውና ስጋት መቀረፍ እንዳለበት አብንና ባልደራስ የጋራ ፖለቲካዊ አቋም ወሰደዋል። የሀገራችን ኢትዬጵያ መድናና የመላ ህዝቧ ሰላማዊ መኖሪያ ሆና ዘመናትን የተሻገረችው አዲስ አበባ መደበኛና ነባር ምልከታ ሊቸራት ሲገባ ከልቦለድ የመነጨ የዘረኞች “የልዩ ጥቅም”ቀንበር ጊዜ በረዘመ ቁጥር የህግና የፖለቲካ ቋጠሮው እየጠበቀ መምጣቱና ይዘቱ “በኦሮሚያ ክልል አስተዳደርና በአዲስ አበባ መስተዳደር ስምምነት” እንደሚወሰን በተሻሻለው ቻርተር መደንገጉ ከተማዋንና ህዝቧን ከአንድ ወገን በተሰባሰበ የፖለቲካ ሀይል ይሁንታ፣ ፍፁም ቁጥጥርና ጥበቃ ስር ለማዋል የተወሰነ መሆኑን ያሳያል። አብንና ባልደራስ ይሄን አምባገነናዊ፣ ፍትህ አልቦ፣ ዘረኛ፣ አግላይና በመጨረሻም የግጭትና የብሄራዊ ደህንነት አደጋ የሆነ አፍራሽ እንቅስቃሴ በጋራ ተሰልፈው ለመታገል ከስምምነት ላይ ደርሰዋል። ትብብሩ በቀጣይ እንዲፈጠርና እንዲጎለብት ለምንፈልገው የሀገራዊ በጎ ሀይሎች ጥምረት እርሾ ሆኖ እንዲያገለግል የታለመ ነው። አስቻይነት የሌለውና በህግ የተደነገገው የጊዜ ገደብ ጉዳይ በነባራዊ ተግዳሮቶች ምክንያት የተፈጠረ መሆኑን በማረጋገጥ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ተመሳሳይ አንድምታ ያላቸውን ጉዳዬች ባስተናገደበት ሁኔታ ትብብሩ ለህጋዊ እውቅና ሲቀርብ በመፍቀድና በመመዝገብ እንዲያፀድቀው የሚቀርብ ይሆናል። በዚህ መነሻነት ዴሞክራሲያዊ ስርዓትን እውን ለማድረግ ለሚደረገው ትግል በመጪው ሃገራዊ ምርጫ የመራጮችን የጋራ ፍላጎትና ራዕይ ለማሳካት የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ/አብን/ እና ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ /ባልደራስ/ በጋራ የምንሰራበት የፖለቲካ ትብብር ፈጥረን ለመስራት መወሰናችንን ለመላው ሀገር ወዳድ ኢትዬጵያውያን፣ ለመላው አማራ ህዝብና ለአድስ አበባ ህዝብ ስናበስር በታላቅ ደስታ ነው። ሌሎች ፓርቲዎችን ጨምሮ በሁለቱ ፓርቲ አመራሮች መሃከል ለወራት ሲካሄድ የነበረው ረጂምና አድካሚ ድርድር ፍሬ አፍርቶ መጪውን ሀገራዊና ክልላዊ ምርጫ የአብን እና የባልደራስ ትብብር አሸናፊ ሆኖ መውጣት የሚያስችላቸውን የጋራ ስልቶች ቀይሰው በይፋ መንቀሳቀስ ጀምረዋል። የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ/አብን/ እና ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ/ባልደራስ/ አጠቃላይ የኢትዬጵያ ህዝብ፣ የአማራ ህዝብ እና የአዲስ አበባ ከተማ ኗሪ ህዝብ በበደል ውስጥ አምጠው የወለዷቸው የቁርጥ ቀን ልጆቹ እንደመሆናቸው መጠን በተባባረ ክንድ በህዝባችን ላይ የተጫነውን የመከራ ቀንበር እንዲወርድ ከመቸውም ግዜ በላይ በጋራ ትብብር ለመታገል በቁርጠኝነት ተሰልፈዋል፡፡ አብን በጽንፈኞች የተሳሳተ ትርክት መነሻነት በአማራ ህዝብ ላይ በተከታታይ የሚደርሰው ግፍ ድምጽ በመሆን በመጀመሪያው ረድፍ ሆኖ ትግሉን እየመራ ይገኛል። አብን የሀገራችን ኢትዬጵያን ደህንነት ለማረጋገጥና ህልውናዋን ለማስቀጠል አንድ ወሳኝ አምድ የሆነው የአማራ ህዝብ በልዩ ሁኔታ ተፈርጆ የሚጠቃበትን የፅንፈኞች ስሁት ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ ለመግታት የሚያስችል ልዩ ማዕቀፍ ሆኖ የተደራጀ ሲሆን ታሪካዊ፣ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ስሪቱ በኢትዬጵያዊነት፣ ምልከታውም በወንድማማችነት፣ በፍትህና በዴሞክራሲ የተቃኘ ስለመሆኑ ውሎ ያደረ ጉዳይ ነው። ከላይ በሰፊው እንደተመላከተው ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ በአዲስ አበባ ከተማ ህዝብ ላይ የተጋረጡ የህልውና አደጋዎችን ለመከላከል፣ የከተማዋ ህዝብም ራሱ በዴሞክራሲያዊ መንገድ በመረጣቸው እንደራሴዎቹ የመተዳደር መብቱን ለማስከበር ባሚያደርገው እልህ አስጨራሽ ትግል ውስጥ በብቃትና በንቃት በነሳተፍ አያሌ መስዋዕትነቶችን በመክፈል የቀጠለ መሆኑን ራሱ ህዝቡ በተግባር ኖሮ ያረጋገጠው ሀቅ ነው። ከላይ በተጠቀሱት መሰረታዊ ሰብዓዊ እና ዴሞክራሲያዊ ግቦች ዙሪያ ሁለቱ ድርጅቶች በፅኑ የሚጋሯቸውን አቋሞች መሰረት በማድረግ ቀጣይ ለሚደረገው ጠንካራና የተቀናጀ የህዝብ ትግል ወሳኝ የማታገያ አጀንዳ እንዲሆኑ ስምምነት ላይ ደርሰዋል። በሃገር አቀፍ ደረጃ ይካሄዳል ተብሎ በሚጠበቀው ምርጫ መላው የሀገራችን ህዝብ፣ በተለይም የአማራ ህዝብና የአዲስ አበባ ህዝብ የተደቀነባቸውን የህልውና አደጋ በትብብር ከመታገል ውጭ ሌላ ተጨባጭ የመፍትሄ አማራጭ እንደሌለ መተማመን ላይ ደርሰዋል። ከዚህ ቀደም በጋራ አብረውን ለመስራት ንግግር ጀምረው ሳለ በተለያዩ ምክንያቶች በትብብሩ ለመዝለቅ ያልቻሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች አሁንም ጊዜው አለመርፈዱን ተገንዝበው በጎ ፍላጎት ካሳዩን ከግማሽ መንገድ ባላይ ተጉዘን ለመቀበል ዝግጁ መሆናችንን በዚህ አጋጣሚ ለማረጋገጥ እንወዳለን። የፈጠርነው ትብብር አርአያ መሆን የሚችልና ከትላንት ለተሻለ አዲስ የፖለቲካ ባህል ማሳያ ፈር ቀዳጅ እንደመሆኑ ከምርጫ በኃላም ትብብሩ ጎልብቶ፤ የሀገራችንን ህዝብ ለዘመናት የቆየ የፍትህ ትግል ዳር ለማድረስ እንዲሁም የመላው ኢትዬጵያዊ የሆነችውን የአዲስ አበባ ከተማን ዓለም አቀፍነት የሚመጥን አመራር ለመስጠት ለመፍጠር ከወዲሁ አብረን መቆም ጀምረናል። አብንና ባልደራስ የአዲስ አበባ ህዝብ ራስን በራስ የማስተዳደር ዴሞክራሲያዊ መብት አክብረው ከሚቀበሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር ትብብር በመፍጠር የከተማዋ ህዝብ በፌደራል መንግስቱ ውስጥ ተወክሎ እንደሁሉም ህዝብ ጥቅሙን ለማስጠበቅ የሚያደርገውን ትግል የማሳለጥ ሚና እንደሚኖረው ለማሳወቅ እንወዳለን። አዲስ አበባ በሁሉም ኢትዮጵያውያን ጥረት የተገነባች፣የአፍሪካ የዲፕሎማሲ ዋና ከተማ ብትሆንም፣ ከቅርብ ግዜ ወዲህ የተነሱ ተረኞች ከተማይቷን በልዩ ጥቅም ስም የአንድ ቋንቋ ተናጋሪ ብቸኛ ንብረት ለማድረግ የሚደረገው እንቅስቃሴ በጋራ አጥብቀን እናወግዛለን። በከተማይቱ እና ነዋሪዎቿ ላይ የተደቀነውን ይህ አደጋ ለመከላከል ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ/ ባልደራስ/ በዋነኛነት እያካሄደ ያለውን ትግል አብን የሚያድንቅ እና በሙሉ ልብ ከጎኑ እንደሚሰለፍ ቃል ይገባል። በአንጻሩም ባልደራስ ፓርቲ በጽንፈኞች ሴራ ኢላማ እንዲሆን በተደረገው የአማራ ህዝብ ላይ የሚደርሰውን ግፍ እና በደል ለማስቀረት በቁርጠኝነት አብን ለሚያደርገው ትግል ክብርና እውቅና እንደሚሰጥ ለመግለፅ እንወዳለን፡፡ ከላይ ለመግለጽ እንደተሞከረው ስምምነታችን የተበላሸውን የሀገራችንን ፖለቲካ ባሕል በማስተካከል፣ በውይይትና በሰጥቶ መቀበል መርህ ለሕዝብ ጥቅም ሲባል አብሮ መቆም እንደሚገባ ከማሳየት ባሻገር፣ ሌሎች ለተመሳሳይ አላማ ያነገቡ ፓርቲዎችም ይህን ፈለግ ተከትለው የትብብሩ አካል እንዲሆኑ ፅኑ ፍላጎት አለን። በመጨረሻም በሀገራችን በተለያዩ አካባቢዎች ጽንፈኛ ሃይሎች በሚፈጽሟቸው የሽብር ድርጊቶች ምክንያት እየደረሰ ያለውን ሞት፣የአካል ጉዳት፣መፈናቀል እና የንብረት ውድመት ለማስቆም በየእርከኑ ያሉ የፌደራል እና የክልል መንግስታት ሃላፊዎች ተግተው እንዲሰሩ ጥሪ እናቀርባለን። በተለይ ችግሩ ተባብሶ በሚገኝባቸው የኦሮሚያ፣ የቤንሻንጉል እና አንዳንድ የደቡብ ክልል አካባቢዎች የሚገኙ የመንግስት አስተዳደርና የፀጥታ አካላት ችግሩን የሚመጥን ሀላፊነት በመውሰድ ንፁሀንን ከጥቃት እንዲከላከሉና ወንጀለኞችን ለህግ እንዲያቅርቡ በአፅንኦት እንጠይቃለን። መሰረተ ቢስ በሆነ ክስ ተወንጅለው ለእስር የተዳረጉትንና የመምረጥና መመረጥ መብታቸውን የተነፈጉ የባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ አመራሮች በአስቸኳይ እንዲፈቱ እናሳስባለን። ትህነግ በለኮሰው ጦርነት በትግራይ ክልል ህግ ለማስከበር እየተካሄደ ባለው ዘመቻ የንጹሃን ዜጎቻችንን ደህንነት እና የሰብዓዊ መብት እንዳይጣስ ልዩ ትኩረት እንዲደረግና የሰብአዊ ድጋፍ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ለማሳሰብ እንወዳለን።
ናይ ዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ ኣውሮፓ ካብ ናይ ናዚ ወራር ነፃ ንምውፃእ ኣሽሓት ሓይልታት ጥምረት ኣብ ወሰን ማይ ኖርማንዲ ብውግእ ዝተሰውእሉን D-Day ብዝብል ስም ኣብ ዝፍለጥን ዝኽሪ ኵናት መበል 70 ዓመት ተሳቲፎም። ሎማዕንቲ ዓርቢ 29 ግንቦት 2006 ዓ/ም ወይ 6 ሰነ 2014 ሰማያት ብጡሽ ተሸፊኑ ነፈርቲ ውግእ ኣብ ሰማይ እናተገለባበጣ መሬት የንቅጥቅጣ።እንተኾነ እቲ ናይ ሎማዕንቲ ጡሽ ንኽብሪ እቶም ስውኣት ዝተተኮሱ 21 መዳፍዕ ዝፈጠርዎ እዩ።እተን ዝበራ ዘለዋ ነፈርቲ እውን F-15 ዝዓይነተን ነፈርቲ ውግእ ኮይነን ንዝኽሪ መስዋእቲ ኣሽሓት ወታደራት ዩናይትድ ስቴትስን ሓይልታት ጥምረትን እየን ምርኢት ዘርእያ ዘለዋ። ፕሬዝዳንት ኦባማ ብርክት ዝበሉ ካብ ናይ ኵናት D-Day ዝተረፉ ወታደራት ነበርን ካልኦትን ኣብዝተሳተፉሉ ስነስርዓት ኣብ ዘስዕዎ መደረ ድፋዕ ዴሞክራሲ ክብሉ ፀዊዖምዎ።ኣሜሪካ ዝወነነቶ ሓርነት፣ማዕርነት፣ነፃነትን ተፈጥራዊ ክብሪ ኩሎም ደቂ ሰባትን ኣብዚ ወሰን ባሕሪ ብደም ተፃሒፉ፤ንዘልኣለም እውን ክነብር እዩ ኢሎም። ብዛዕባ ሰላም ንኽንፈልጥ ምእንታ እዞም ወታደራት እዚኦም ኵናት ተዋጎኦም ዝበሉ ንሶም ብምስዓብ ‘’ንሕና ብነፃነት ንኽንነብርን ብድሕሪኦም ክንዋግእ ከምዘይብልና ተስፋ ብምግባርን ንሳቶም ተዋጊኦም።ክብርን ምስጋናን ይብፅሓዮም ‘’ኢሎም። ልዕሊ 160 ሽሕ ሓይልታት ጥምረት ካብዚኦም እቶም 73 ሽሕ ኣሜሪካዊያን እዮም፤ሓይልታት ናዚ ጀርመን ብኸቢድ ዓሪዶምሉ ንዝበሩ መስመር ድፋዕ ወሰን ማይ ንምስባር ግዙፍ መጥቓዕቲ ፈኒዮም።ድሕሪ ክልተ ኣዋርሕ ሓይልታት ጥምረት ንፓሪስ ሓራ ብምውፃእ ከም ውፅኢት ኣብ ምሉእ ኣውሮፓ ንናዚ ስዒሮምዎ። ፕሬዝዳንት ኦባማ ድሕሪ እቲ መደረ ናይ ብሪታኒያ ንግስቲ ኤልሳቤትን መራሕቲ ኣውሮፓን ኣብ ተሳተፍሉ ካሊእ ስነስርዓት ተኻፊሎም።ናይ ሩሲያ ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን እውን ካብቶም መራሕቲ ሓደ ነይሮም። ፕሬዝዳንት ኦባማ ሩሲያ ኣብ ልዕሊ ዩክሬይን ብዝወሰደቶ ስጉምትታት ንፕሬዝዳንት ፑቲን ንምግላል ብዙሕ ሓይሎም ዘጥፍእሉ ናይ ኣውሮፓ መገሽኦም ናብ ምጥቕላል ገፁ እዩ።ክልቲኦም መራሕቲ ኣብ ኖርማንዲ ንምርኻብ ዝኾነ ይኹን ወግዓዊ መደብ ኣይነበሮምን።ግን ኣካል እቲ ስነስርዓት ዝኾነ ብናይ ፈረንሳይ ፕሬዝዳንት ኣብዝተዳለወ እንግዶት ድራድ ንብርክት ዝበሉ ደቓይቕ ጎናዊ ዝርርብ ንምክክያድ ዕድል ረኺቦም።
የአቡዳቢ ልዑል አልጋ ወራሽ እና የአረብ ኤሚሬቶች ጦር ኃይል ምክትል ጠቅላይ አዛዥ ሼክ መሃመድ ቢን ዛይድ አል ናህያን ከአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አንቶኒዮ ብሊንከን ጋር ተወያዩ፡፡ ልዑል አልጋ ወራሹ እና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ በሞሮኮ ራባት ነው የተወያዩት፡፡ የሩሲያ እና ዩክሬን ጦርነትን ጨምሮ በየመን ስለሚንቀሳቀሱት የሃውሲ አማጽያን እንዲሁም በተለያዩ ቀጣናዊ የጸጥታና ደህንነት ጉዳዮች ላይ መወያየታቸውን የኤሚሬት ዜና አገልግሎት (ዋም) ዘግቧል፡፡ በውይይቱ የኤሚሬት የውጭ እና ዓለም አቀፍ ትብብር ሚኒስትር ሼክ አብዱላህ ቢን ዛይድ አል ናህያንን ጨምሮ ሌሎች ባለስልጣናት ተገኝተዋል፡፡ ብሊንከን የሃገራቱን ትብብር የበለጠ ያጠነክራል ያሉትን ፍሬያማ ውይይት ከሼክ መሃመድ ጋር ማድጋቸውን በይፋዊ የማህበረሰብ ትስስር ገጻቸው አስታውቀዋል፡፡ ውይይቱን አስመልክቶ ማብራሪያ የሰጡት የብሊንከን ቃል አቀባይ ኔድ ፕራይስም ኤሚሬት የሃውሲ አማጽያን ከየመን ከሚፈጽሙባት ጥቃት ራሷን ለመከላከል የምታደርገውን ጥረት አሜሪካ በቁርጠኝነት እንደምትደግፍ ተናግረዋል፡፡ ኤሚሬት የየመን ችግር በዲፕሎማሲያዊ መንገዶች ብቻ ሰላማዊ መፍትሔዎችን ሊያገኝ ይገባል ማለቷንም አድንቀዋል፡፡ ብሊንከን እና ሼክ አብዱላህ ቢን ዛይድ ከሰሞኑ እስራኤል ነበሩ፡፡ ወደ ራባት ከማቅናታቸውም በፊት እስራኤል ከአራት የአረብ ሃገራት ጎረቤቶቿ ጋር ባዘጋጀችው የኔጌቭ ጉባዔ ላይ ተሳትፈዋል፡፡ ኤሚሬት እና እስራኤል የአብርሃም ስምምነትን በመፈረም ለዓመታት ሻክሮ የቆየ የሁለትዮሽ ግንኙነታቸውን ለማለስለስ መስማማታቸው ይታወሳል፡፡ በዚህም ሃገራቱ ኤምባሲዎቻቸውን ከፍተው ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ማድረግ ጀምረዋል፡፡
እንዲህ ያለ ኑፋቄ ይዞ ለሚነሣ ሰው አዲስ ነገረ ሃይማኖታዊ ውይይትና ውሳኔ አያስፈልገውም፡፡ የአርዮስን ኑፋቄ ይዞ ለሚነሣ ግለሰብም ሆነ ቡድን የኒቅያ ጉባኤ በየጊዜው ሲሰበሰብ አይኖርም፤ የንስጥሮስን ኑፋቄ ይዞ ለሚነሣም እንዲሁ የኤፌሶን ጉባኤ በየጊዜው አይሰበሰብም፡፡ በቀደመው ውግዘት እስከ ዕለተ ምጽአት የሚነሡት ሁሉ ተወግዘዋል፡፡ ከቤተ ክርስቲያን ትምህርት ግልጽ ተቃርኖ የያዘ ኑፋቄ ሁሉ በአጠቃላይ የተወገዘ ነው፡፡ ለእንዲህ ዓይነቱ ኑፋቄ የሚያስፈልገው አንድ ነገር ብቻ ነው፤ እርሱም ያን ኑፋቄ የሚያራምደው ግለሰብ በትክክል ያን ኑፋቄ መያዝ አለመያዙን፣ የሚመለስ መሆን አለመሆኑን ማረጋገጥ ብቻ ነው፡፡ ከተረጋገጠ በኋላ ያ ሰው ከቤተ ክርስቲያን መለየቱ (ማውገዙ) በአጥቢያ ሰበካ ጉባኤ ወይም በአገረ ስብከት ደረጃ ሊፈጸም ይችላል፡፡ እንግዳ ዓይነት ኑፋቄ ሲባል ደግሞ በግልጽ ስህተቱ ይህ ነው ለማለት ቀላል ያልሆነና ጉዳዩን ከቤተ ክርስቲያን እምነት አንጻር በጥንቃቄ መመዘን የሚያስፈልገው ማለት ነው፡፡ እንዲህ ሲሆን የኑፋቄውን ምንነት፣ ነገረ ሃይማኖታዊ አንድምታውን፣ ጥልቀቱንና ስፋቱን በጥንቃቄ መመርመር ያስፈልጋል፡፡ ይህን የሚያደርጉትም በሳል የሆነ ነገረ ሃይማኖታዊ እውቀት ያላቸው ሊቃውንት መሆን ይኖርባቸዋል፡፡ የመጨረሻ ውሳኔውን የሚሰጠው የቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ነው፡፡ ፰. መናፍቃን እንዴት ይመለሱ? ከቤተ ክርስቲያን በኑፋቄ ተወግዘው (ይፋዊ በሆነ ውግዘትም ሆነ ራሳቸውን በኑፋቄ በመለየታቸው) የተለዩ ሰዎች እንዲመለሱ የቤተ ክርስቲያን ናፍቆቷና ምኞቷ ነው፡፡ እንዲወገዙ የሚደረገውም ከላይ እንዳየነው ለራሳቸው ለሰዎቹ ጥቅም ሲባል፣ ነፍሳቸው በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ቀን እንድትድን ለመርዳት ሲባል እንጂ እንዲጠፉ አይደለም፡፡ ስለሆነም የመመለሳቸው ዜና ታላቅ የምሥራች ነው፣ ከዚህ የበለጠ ደስታም የለም፡፡ ጌታችን በትምህርቱ የጠፋው ልጅ ሲመለስ ስለሆነው ነገር ሲናገር እንዲህ አለ፡- “አባቱ ለአገልጋዮቹ ፈጥናችሁ ከሁሉ የተሻለ ልብስ አምጡና አልብሱት፣ ለእጁ ቀለበት ለእግሩም ጫማ ስጡ፤ የሰባውን ፊሪዳ አምጥታችሁ እረዱት፥ እንብላም ደስም ይበለን፤ ይህ ልጄ ሞቶ ነበርና ደግሞም ሕያው ሆኖአል፤ ጠፍቶም ነበር ተገኝቶአልም። ደስም ይላቸው ጀመር፡፡” ሉቃ. 15፡22-24 ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድ የጠፋ ልጇ ሲመጣ እንዲህ ደስ ይላታል፡፡ ቅዱሳን መላእክትም በሰማይ ንስሐ ስለሚገባ አንድ ኃጥእ ደስ ይሰኛሉ፡፡ ይህ እንዳለ ሆኖ፣ በሌላ በኩል ደግሞ ሊደረጉ የሚገባቸው ጥንቃቄዎችና ተግባሮችም አሉ፡፡ ይህም ቤተ ክርስቲያንን ከመጠበቅ አንጻር አስፈላጊ በመሆኑ ነው፡፡ መናፍቃን የነበሩ ሰዎች ወደ ቤተ ክርስቲያን እንመለሳለን ሲሉ ሊደረጉ የሚገባቸው ዋና ዋና ጥንቃቄዎችና ተግባራት የሚከተሉት ናቸው፡- 1. መመለሳቸው (ተመልሰናል ማለታቸው) የእውነት ነው? ከልብ ነው? ወይስ ለስልትና ለዘዴ ነው? ቤተ ክርስቲያን እስካሁን በተጓዘችባቸው ዘመናት ሁለቱም ዓይነት ሰዎች በየጊዜው ሲገጥሟት ነበር፤ እነዚህም በአንድ በኩል በእውነት ተጸጽተው የሚመለሱ ሲሆኑ በሌላ በኩል ደግሞ ከልባቸው ሳይመለሱ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ተመልሰው በመግባት ብዙ ምእመናንን ለመበረዝና ለማታለል ያመቻቸው ዘንድ በተንኮል ተመልሰናልና ተቀበሉን የሚሉ ናቸው፡፡ ስለዚህ ተመልሰናል ስላሉ ብቻ ዝም ብሎ መቀበል የዋህነት ሳይሆን ጅልነት ስለሆነ በሚገባ ማጣራትና መጠንቀቅ በእጅጉ አስፈላጊ ነው፡፡ በኒቅያ ጉባኤ በቅዱሳን አባቶች ተወግዞ የተለየው አርዮስና የኑፋቄ ጓደኞቹ የተለያዩ ሰዎችን በመላክና በውስጥ ለውስጥ በሠሩት የፕሮፓጋንዳ ሥራ በመጨረሻ ላይ ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ አርዮስን ከፈረደበት ከግዞቱ እንዲወጣና ወደ ቤተ መንግሥቱ እንዲመጣ አደረገው፡፡ ንጉሥ ቆስጠንጢኖስም እምነቱን በጽሑፍ እንዲያቀርብ አዘዘው፡፡ አርዮስም በፊት የፈጠራቸውን የኑፋቄ ቃላትና ሐረጎች ሁሉ፣ እንዲሁም የተወገዘባቸውን የክህደት አንቀጾች ሁሉ ለጊዜው ወደ ጎን ትቶ ከመጽሐፍ ቅዱስ በቀጥታ ያሉና ማንም ሰው ሊቀበላቸው የሚችላቸውን ነገሮች ብቻ ጽፎ “በፊትም ቢሆን ከዚህ የተለየ ሃሳብም ሆነ እምነት አልነበረኝ፣ አሁንም የማምነው ይህን ነው” በማለት ፈርሞ፣ በመሐላ አጽንቶ ሰጠው፡፡ ያ አርዮስ ጽፎ የሰጠው አንቀጸ እምነት እነርሱ (አርዮሳውያን) በፈለጉት መንገድ ሊተረጉሙትና የያዙትን አርዮሳዊ እብደት በቀላሉ በማያጋልጥ መልኩ በፈሊጥ ተሸፍኖ የቀረበ ማታለያ ነበር፡፡ ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ ግን እንዲያ ሲያደርግ ሲያየው አርዮስ በእውነት የተመለሰና ኦርቶዶክሳዊ የሆነ መሰለው፡፡ ይህን አጋጣሚ በመጠቀም አርዮሳውያን የነበሩ ጳጳሳት አርዮስ በይፋ መጀመሪያ በተወገዘበት በእስክንድርያ ወደ ቤተ ክርስቲያን እንዲገባና ከምሥጢራት እንዲካፈል የሚል ደብዳቤ ንጉሡ እንዲጽፍላቸው አደረጉና ያን ደብዳቤ ከዛቻና ከማስፈራሪያ ጋር ወደ ቅዱስ አትናቴዎስ ወደ እስክንድርያ እንዲላክ አደረጉ፡፡ ለየአብያተ ክርስቲያናቱም አርዮስና ጓደኞቹ ኦርቶዶክሳውያን መሆናቸውን ንጉሡ ቆስጠንጢኖስ የመሰከረላቸው ስለሆነ፣ በሲኖዶስም የተወሰነ በመሆኑ ወደ ቤተ ክርስቲያን አንድነትና ወደ ሱታፌ ምሥጢራት ይቀበሏቸው ዘንድ በጥብቅ የሚያሳስብ ደብዳቤ በፍጥነት ላኩ፡፡ የአርዮስ ቀኝ እጅ የነበረው አውሳብዮስ ዘኒቆምድያ ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ በደብዳቤው ላይ ቅዱስ አትናቴዎስን “ወደ ቤተ ክርስቲያን ሊመለሱ የሚፈልጉትን ሁሉ የማትቀበል ከሆነ እኔ ራሴ ሰው ልኬ ከመንበርህ አወርድሃለሁ” የሚል ዛቻ እንዲላክበት አደረገ፡፡ ብዙ ጊዜ ከታሪክ ስናይ መናፍቃን የፖለቲካ ሰዎችንና ባለ ሥልጣናትን በመዘወርና ከጎናቸው በማሰለፍ በኩል ጠንካሮችና የተሳካላቸው ናቸው፡፡ ቅዱስ አትናቴዎስ ግን “የክርስቶስ ጠላት የሆነው አርዮስና ኑፋቄው ከኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ጋር ምንም ኅብረት የላቸውም” በማለት በጉባኤ የተወገዘውን አርዮስን በንጉሥ ቀላጤ አልቀበልም አለ፡፡ የቅዱስ አትናቴዎስ ስለ ኦርቶዶክሳዊት ሃይማኖት ከአርዮሳዊ ክህደት አቀንቃኞችና ደጋፊዎች ጋር የገባው እልህ አስጨራሽ ትግል በዚህ ሁኔታ እየጠነከረ ሄደ፡፡ ከመንበሩ ስድስት ጊዜ እንዲሳደድና ከአርባ አምስት ዓመት ዘመነ ፕትርክናው አሥራ ሰባት ዓመቱን ያህል በስደትና በእንግልት እንዲያሳልፍ ያደረገው ይህ የአርዮሳውያን ተንኮልና ዘመቻ ነበር፡፡ በአጠቃላይ አርዮሳውያን ያን ንጉሡ ከግዞት መመለሱን እንደ መልካም ካርድ በመጠቀም ከዚያ ቀጥሎ በነበሩት ሃምሳ ዓመታት ያህል ቤተ ክርስቲያንን በእጅጉ ሲያውኳትና ሲፈትኗት ኖረዋል፡፡ ነገሥታትን ሳይቀር ከጎናቸው እያሰለፉ ኦርቶዶክሳውያን ጳጳሳትንና ካህናትን ከየመናብርታቸውና አብያተ መቃድሳቸው እያሳደዱ እነርሱ ሲፈነጩባቸው ኖረዋል፡፡ ነገሩ የማታ የማታ እውነት ይረታ ሆነ እንጂ፡፡ ስለዚህ ዛሬም እንመለሳን የሚሉት ሰዎች በትክክል ከልባቸው ነው? ወይስ እንደ ግብር አባቶቻቸው እንደ አርዮሳውያን ውስጥ ገብተው ለመበጥበጥ ነው? የሚለውን በሚገባ ማጤን ያስፈልጋል፡፡ “ታሪክ የሚያስተምረው ሰዎች ከታሪክ አለመማራቸውን ነው” የተባለው እንዳይደርስብን ማሰብ ይገባል፡፡ “በሬ ሆይ፣ ሣሩን አየህ እንጂ ገደሉን ሳታይ” እንደ ተባለውም እንዳይሆን እያንዳንዱ ምእመን፣ እስከ ቅዱስ ሲኖዶስ ድረስ ሊያስቡበትና ተገቢውን ነገር ሊያደርጉበት የሚገባ ጉዳይ ነው፡፡ 2. ጉዳዮችን በቡድን ወይም በጅምላ ሳይሆን በእያንዳንዱ ሰው ደረጃ መመልከትና መለየት፣ እንመለሳለን የሚሉትን ወገኖቻችንን ጉዳያቸውን በእያንዳንዳቸው ማየትና ማጥናት ይገባል እንጂ በጅምላ ከዚህ ወዲያ ወይም ከዚያ መለስ ብሎ ማድረግ አይገባም፡፡ እግዚአብሔር የሚፈርደው በእያንዳንዱ ሰው እንጂ በቡድን ወይም በጅምላ አይደለም፤ “እስመ አንተ ትፈድዮ ለኩሉ በከመ ምግባሩ - አንተ ለእያንዳንዱ እንደ ሥራው ታስረክበዋለህና” እንደ ተባለ፡፡ መዝ. 61፡ እንዲሁም “እንግዲያስ እያንዳንዳችን ስለ ራሳችን ለእግዚአብሔር መልስ እንሰጣለን” ተብሏልና። ሮሜ 14፡12 ስለሆነም እያንዳንዱን በየግለሰቡ ጥፋቱ ምን አንደ ነበር፣ ለምን እመለሳለሁ እንዳለ፣ ወዘተ በዝርዝር ማጥናትና መወሰን ይገባል እንጂ “እነ እገሌ” በሚል የጅምላ ንስሐ የለምና ይህን ማስታወሱም ተገቢ ነው፡፡ 3. ከቤተ ክርስቲያን እንዲወጡ (እንዲያፈነግጡ) ያደረጓቸውን ምክንያቶች በሙሉ እንዲዘረዝሩ ማድረግና መመዝገብ፣ አንድ ሰው ዳነ ሲባል ታምሞ የነበረ መሆኑ፣ ተመለሰ ሲባል ደግሞ ወጥቶ ወደ ሌላ ሄዶ የነበረ መሆኑን ያጠይቃልና እንመለሳለን የሚሉት ሰዎች እያንዳንዳቸው ቀድሞ እንዲወጡ ያደረጋቸው ምክንያት ምን እንደ ነበረ በግልጽ መታወቅ ይኖርበታል፡፡ አለበለዚያ በሽታውን ደብቆ እንዲሁ አክሙኝ እንደሚል ሰው መምሰል ይሆናል፡፡ ይህን ማድረግ ግን እንመለሳለን ለሚሉት ሰዎችም፣ ለማኅበረ ምእመናኑም ጠቃሚና አስፈላጊ ነው፡፡ ያን ኑፋቄ እንደገና ሲያስተምሩ ቢገኙ ማንነታቸውን በግልጽ ለመለየት ይጠቅማል፤ አለበለዚያ “ሞኝን እባብ ሁለት ጊዜ ነከሰው” (መጀመሪያ ሲያይ፣ ሁለተኛ ደግሞ ሲያሳይ) እንደ ተባለው ይሆናል፡፡ 4. መመለሳቸውን፣ እንዲሁም ከምን ዓይነት ስህተት እንደ ተመለሱ ለሕዝቡ በይፋ መነገር ይኖርበታል፡፡ መናፍቃን ሲመለሱ በጓዳና ለሌሎች በማይታወቅ ሁኔታ ሳይሆን በግልጽ፣ ምእመናን ሁሉ በሚሰሙበትና በሚያውቁበት መድረክ በይፋ መሆን አለበት፡፡ በፊት የካዱትና ቤተ ክርስቲያንን ያሳጡትና የነቀፉት በይፋ እንደ ነበር ሁሉ ሲመለሱም በይፋ መሆን ይኖርበታል፡፡ ቅዱስ ባስልዮስ ስለ መናፍቃን አመላለስ በጻፈው ቀኖና ላይ እንዲህ ይላል፡- “በማንኛውም መንገድ ቢሆን ከኑፋቄ ወደ ቤተ ክርስቲያን የሚመለሱ ሰዎች ምእመናን ባሉበት መሆን አለበት፤ ወደ ምሥጢራት ሊቀርቡ የሚገባቸውም እንዲህ ባለ ይፋዊ ሁኔታ ካለፉ በኋላ ብቻ ነው፡፡” ቀኖና ዘቅዱስ ባስልዮስ፣ ቁ. 1 እንዲህ ካልሆነ ብዙ ችግር ያስከትላል፡፡ እንዲህ ማድረግ ለአጭበርባሪዎችና ለተንኮለኞች መጠቀሚያ ሰፊ በር ይከፍታል፡፡ ነገ ተመልሰው ያንኑ ዓይነት ችግር እንዳይፈጥሩ በይፋ መነገሩ በእጅጉ ይጠቅማል፡፡ አለበለዚያ ውስጥ ውስጡን ምእመናንን እየበከሉ ላለመቀጠላቸው ዋስትና አይኖርም፡፡ መመለሳቸው በይፋ ከተደረገ ግን የቀድሞ ኑፋቄያቸውን እናስተምራለን ቢሉ እንኳ “ተመልሰናል ብላችሁ አልነበረምን? የቀድሞ ስህተታችንን ትተናል ብላችሁ አልነበረምን?” ብሎ ለመጠየቅና በቶሎ ማንነታቸውን ለማወቅ ይረዳል፡፡ 5. ከጥንት ጀምሮ የተነሡ የተለያዩ የኑፋቄ መሪዎችንና ዋና ዋና መናፍቃንን በጥንቃቄ ከተዘረዘሩ በኋላ ማውገዝ ይገባቸዋል፣ የሚመለሱ መናፍቃን በእውነት ከመናፍቃን የተለዩና ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ጋር የተዋሐዱ ስለ መሆናቸው አንዱ ምስክር የሚሆነው ከቀድሞ ጀምሮ የተነሡ ዋና ዋና የኑፋቄ አመንጪዎችን በይፋ ማውገዝ ነው፡፡ ስለሆነም በጥንቃቄ በተዘጋጀ የመናፍቃን ዝርዝር ላይ እነዚያን መናፍቃን ማውገዝና ለዚህም መፈረም ይኖርባቸዋል፡፡ 6. እስከ ዛሬ ድረስ በስብከቶቻቸውና በመጻሕፍት ያስተማሯቸውንና የጻፏቸውን የኑፋቄ ትምህርቶች ሁሉ ቀድሞ ኑፋቄው ከተላለፈበት ልሳን ጋር ተመጣጣኝ በሆነ መንገድ እንዲያወግዙና ስህተት መፈጸማቸውን ተቀብለው ከአሁን በኋላ እንደዚያ ዓይነት የስህተት ትምህርት እንደማያስተምሩ በጽሑፍ ቃል መግባት ይኖርባቸዋል፡፡ የስህተት ትምህርቱን በመጽሐፍ ወይም በቪሲዲ ወይም በካሴት እና በመሳሰለው ያስተላለፈ ሰው ስህተቱን ሲያምንና ወደ እውነት ሲመለስ የቀደመውን አስተምህሮውን ስህተትነት መግለጽ የሚገባው በዚያው የስህተት ትምህርቱን ባስተላለፈበት መንገድ (ልሳን - ሚዲያ) ነው፡፡ አለበለዚያ ተደራሽነቱ ተመጣጣኝ አይሆንም፡፡ የስህተት ትምህርቱን በመጽሐፍ የጻፈ ሰው በቃሉ “አጥፍቼ ነበር፣ አሁን ተመልሻለሁ” ቢል መመለሱንና የቀድሞውን አስተምህሮውን ስህተትነት ማመኑን የሰሙት በተናገረበት ጊዜና ቦታ የሚገኙት ሰዎች ብቻ ናቸው፤ ሌሎቹ ግን በመጻሕፍት የተጻፈውን ኑፋቄውን እንጂ በቃል የተናገረውን የሚያውቁበት መንገድ የለም፡፡ እንዲሁም በቃሉ ብቻ “ያ ቀድሞ ያልሁት ስህተት ነው” ብሎ ቢናገር ያ ነገር ከአንድ ትውልድ ያለፈ ሊታወስና አስተማማኝ በሆነ ሁኔታ ሊጠቀስ አይቻልም፣ መጽሐፉ ግን ለዘመናት ትውልድን እየተሻገረ ሊጠቀስ የሚችል ነው፡፡ ስለሆነም በእነዚህና በሌሎችም ምክንያቶች አንድ ወደ ቤተ ክርስቲያን የሚመለስ ሰው ቀድሞ የስህተት ትምህርቱን ካስተማረበት የሚዲያ ዓይነትና ተደራሽነት ጋር ተመጣጣኝ በሆነ መንገድ መግለጽ ይኖርበታል፡፡ አለበለዚያ ቀድሞ በቤተ ክርስቲያን ላይ ለብዙዎች መሰናከያ አድርጎ ያስተማረው እንክርዳድ መበከሉን እየቀጠለና ትውልድ እየተሻገረ ስለሚሄድ ስለ አንዱ ሰው መመለስ እንደምንጨነቀው ሁሉ ይህ ሰው በኑፋቄ ትምህርቱ ስላጠፋቸው ስለ ብዙዎቹም ማሰብ የግድ ይላል፡፡ አለበለዚያ ያ ሰው ያጠፋቸውን የብዙዎቹን ሰዎች ነፍሳት ረስተን ለአንዱ ብቻ የተጨነቅን መስሎን የምናደርገው ነገር ውስጡ ወይ አለመረዳት ወይም ደግሞ ሌላ ነገር እንዳይሆን ማሰብ ይገባል፡፡ 7. በእርሱ የኑፋቄ ትምህርት ምክንያት ከቤተ ክርስቲያን የወጡትን ወደ ቤተ ክርስቲያን መመለስ ይኖርበታል፡፡ ኑፋቄውን በማስተማሩ ምክንያት ለብዙዎች ከቤተ ክርስቲያን መውጣት ምክንያት የሆነና በነፍሳቸው እንዲሞቱ ያደረገ ሰው ሲመለስ በመጀመሪያ እነዚያ ያጠፋቸውን ወደ ቤተ ክርስቲያን መመለስ ይኖርበታል፡፡ መርቅያን የተባለው መናፍቅ ብዙ ሰዎችን ካጠፋና የራሱን አንጃ መሥርቶ ከኖረ በኋላ በሕይወቱ መጨረሻ አካባቢ በኑፋቄው ተጸጽቶ ወደ ቤተ ክርስቲያን ልመለስ ብሎ ጠይቆ ነበር፡፡ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ከሁሉም አስቀድሞ በመጀመሪያ ማድረግ እንዳለበት የነገሩት ነገር ቢኖር ወደ ስህተት የመራቸውን ሁሉ ወደ ቤተ ክርስቲያን እንዲመልስ ነበር፡፡ ያን ለማድረግ በመሯሯጥ ላይ እያለ ታመመና ሞተ፡፡ ይህ በየዘመናቱ እንመለስ ሲሉ በነበሩ ሰዎች ላይ ሲፈጸም የኖረ ቀኖና ነው፡፡ ሽዎችን አጥፍቶ አንድ እርሱ ብቻ ቢመለስ እግዚአብሔር ስለ ጠፉት ስለ ብዙዎቹ ግድ የለውምን? እንዲህ የሚያደርጉትንስ ዝም ብሎ ይመለከታቸዋልን? ስለዚህ ይህን ጉዳይ መዘንጋት አይገባም፣ ለመጥፋታቸው ምክንያት የሆኗቸውን ሰዎች (በእነርሱ ምክንያት የጠፉትን ሁሉንም ለይቶ ማወቅ ባይቻልም እንኳ) ለመመለስ ከፍተኛ ጥረት ማድረግና መመለስ ይኖርባቸዋል፡፡ 8. እያንዳንዳቸውን በኦርቶዶክሳዊ መንገድ የሚመራቸው በነገረ ሃይማኖት በሳል የሆኑ አባቶችን መመደብ፣ ኦርቶዶክሳዊነት ከሁሉም በላይ እሳቤው፣ መንፈሱ እንዲገባቸውና እንዲሠርጻቸው ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱን ትምህርቷን ሳያውቁ፤ ከሁሉም በላይ ደግሞ ኦርቶዶክሳዊ እሳቤና እይታ እንዲሁም መንፈስ ሳይኖራቸው በሌላ ቅኝት መንፈስ የኖሩ ሰዎች እንደ መሆናቸው እንመለስ ስላሉ ብቻ አብሯቸው የኖረውና የሠረጻቸው የኑፋቄ ትምህርትና መንፈስና እንዲሁ በአንድ ጊዜ ውልቅ ብሎ የሚወድቅ አይደለም፡፡ የያዛቸው የኑፋቄ መንፈስ እንዲለቃቸው፣ እርሾው ጭልጥ ብሎ እንዲጨለጥላቸው ማድረግ ይገባል፡፡ ይህ ደግሞ በአንድ ጀምበር የሚፈጸም አይደለም፡፡ ጌታችን “ዝንቱ ዘመድ ኢይወጽእ ዘእንበለ በጾም ወበጸሎት - ይህ ዓይነት አብሮ አደግ ክፉ መንፈስ ያለ ጾምና ጸሎት አይወጣም” እንዳለ፡፡ ስለዚህ ኦርቶዶክሳዊ ነገረ ሃይማኖታዊ መንፈስንና እይታን፣ ኦርዶክሳዊ አስተምህሮንና በአጠቃላይ ኦርቶዶክሳዊ ክርስትና ምን እንደሆነ በበሰለ እውቀት፣ በእውቀት ብቻም ሳይሆን በሕይወት የሚያስተምራቸው በሳል አባት ያስፈልጋቸዋል፡፡ ቆዳ በማውለቅና ልብስ በመቀየር ብቻ ከኑፋቄ ወደ ኦርቶዶክሳዊነት መመለስ አይቻልም፡፡ ባለፉት የቅርብ ጊዜያት (በ1990ዎቹ ዓመታት) በሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ ከፍተኛ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት ተፈጥሮ በነበረው ችግር ምክንያት ቅዱስ ሲኖዶስ ካጣራ በኋላ በሃይማኖት ችግር (በተሐድሶነት) የተጠረጠሩትን ወደ አንዳንድ ቦታዎች ሄደው የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት እንዲማሩ ተብሎ ነበር፡፡ ከእነዚያ ለቀኖና ተብለው ከተላኩት መካከል ግን አጋጣሚውን ሌላ ጥፋት ለመሥራት እንደ ምቹ አጋጣሚ የተጠቀሙበት ነበሩ፡፡ ከዚህም የተነሣ እየተማሩ ይቆዩ ተብለው ከተላኩት መካከል ሌሎችን የቤተ ክርስቲያን አባቶች አስክደው ወደ እነርሱ የጥፋት መንገድ ለማስገባት የተጠቀሙበት ነበሩ፡፡ ሌሎች ደግሞ የፕሮቴስታንታዊ ትምህርቶችን በተለያዩ መንገዶች ለማስፋፋት ሲሞክሩ የተደረሰባቸው ነበሩ፡፡ ስለዚህ ያን ጊዜ እንደ ተደረገው እንዲሁ ሁለት ሁለት እያደረጉ ወደ ሆነ ገዳም ወይም ቦታ መላክ ብቻውን ሰዎቹን አይለውጣቸውም፡፡ ስለዚህ በዚህም ከፍተኛ ሥራና ጥንቃቄ ያስፈልጋል፡፡ “ከሞኝ ደጅ ሞፈር ይቆረጣል” እንደሚባለው እንዳይሆን፡፡ 9. የቤተ ክርስቲያኒቱን አስተምህሮ የሚቀበሉ ስለ መሆናቸው ግልጽና ጠንቃቃ የሆነ ቃለ ጉባኤ አዘጋጅቶ እንዲፈርሙ ማድረግ ይህም አስፈላጊ ነው፡፡ የሰው ነገር ነገ የሚሆነው ስለማይታወቅ ለወደፊቱም ጥሩ መሠረትና ማስረጃ፣ ምስክርም ይሆን ዘንድ የቤተ ክርስቲያኒቱን አስተምህሮና ሥርዓት ያለ አንዳች ቅሬታ የሚቀበሉ ስለመሆናቸው ቃለ ጉባኤ ተይዞ በሚዘጋጅ ወረቀት ላይ መፈረም ይኖርባቸዋል፡፡ 10. ቀኖና መስጠት - (በመድረክ ላይ ይቀጥላሉ ወይስ አይቀጥሉም?) ይህ ለአባቶች የሚተው ጉዳይ ቢሆንም እዚህ ላይ ያነሣነው እንዲሁ ለትምህርት ያህል ግን አስፈላጊነቱን ሳይጠቅሱ ማለፍ አይገባም በሚል ነው፡፡ እንዲያውም ፍትሐ ነገሥታችን ለሌላው ሰው ክህደት ምክንያት የሚሆን ሰው ሲመለስ ቀኖናው ከበድ ያለ እንዲሆን ያዝዛል፡- “ወለዘኢአከሎ ክሕደቱ ባሕቲቱ እስከ ያወጽኦ ለካልኡ እምሃይማኖቱ ወኮነ ምክንያተ ለክህደቱ ይኩን ንስሓሁ ፈድፋደ - የራሱ ክህደት ብቻ አልበቃው ብሎ ባልንጀራውን ከሃይማኖቱ እስኪያወጣው ድረስ ለመካድ ምክንያት ቢሆን ንስሓው ጽኑዕ ይሁን፡፡” አንቀጽ ፳ ቁ. ፯፻፷ ከዚሁም ጋር ገና ተመለስን እንዳሉ “በዚያው በለመድነው ማስተማራችንን እንቀጥላለን፣ ከመድረክ አንወርድም የሚሉ ከሆነም ሌላ መታየት ያለበት ጉዳይ ነው፡፡ በመጀመሪያ አንድ ሰው ቀኖናውን ሳይጨርስ እንዲያ ማድረግ ተገቢ መሆን አለመሆኑን ማየት ያስፈልጋል፡፡ ከዚህም በላይ ደግሞ አንድ በኑፋቄ የነበረ ሰው እንዲሁ “ተመልሻለሁ” ስላለ ብቻ በውስጡ የነበረው ኑፋቄ በአንድ ጊዜ በተአምራት በኦርቶዶክሳዊ ትምህርት አይሞላም፡፡ ስለዚህ በመድረክ እቀጥላለሁ ካለ የሚያስተምረው ያንኑ ከመመለሱ በፊት ሲያስተምረው የነበረውን የቀድሞ የስህተት ትምህርት ካልሆነ በስተቀር ሌላ ከየት ያመጣል? ጌታችን “ኄር ብእሲ እምሠናይ መዝገበ ልቡ ያወጽኣ ለሠናይት ወእኩይሰ ብእሲ እምእኩይ መዝገበ ልቡ ያወጽኣ ለእኪት እስመ እምተረፈ ልብ ይነበብ አፍ - በልብ ሞልቶ ከተረፈው አፉ ይናገራልና፣ መልካም ሰው ከልብ መልካም መዝገብ መልካሙን ያወጣል፥ ክፉ ሰውም ከልብ ክፉ መዝገብ ክፉውን ያወጣል” እንዳለ፡፡ ሉቃ. 6፡45 ታዲያ በኑፋቄ የኖረና ልቡ በዚያ ተሞልቶ፣ ከዚያ ውስጡን ከሞላው ኑፋቄ ለሌሎችም ሲናገር የኖረ ሰው ተመልሻለሁ ስላለ ብቻ ኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮና መንፈስ በአንድ ጊዜ ውስጡ ይመላበታልን? ይኽ ጌታችን ካስተማረው ትምህርት ጋር የማይሄድ ስለሆነ በሚገባ ሊጤን ይገባዋል፡፡ ተመልሰናል የሚሉት ሰዎች መመለሳቸውና ንስሐቸው የእውነት መሆን አለመሆኑ የሚገለጥበትና የሚፈተንበት አንዱ መንገድም ይኽ ነው፤ የተመለሱት በእውነት ከሆነ ግድ እናስተምር፣ በመድረክ እንቀጥል አይሉም፤ ነገር ግን የተንኮልና የስልት ከሆነ መድረኩ ላይ ካልቀጠልን ብለው የሙጥኝ ይላሉ፡፡ በዚህም ላይ አንድ በእውነተኛ መንፈስ ንስሐ የሚገባ ሰው በመጀመሪያ የሚያሳስበው ነገር እግዚአብሔርን በመበደሉ ይቅር እንዲለው፣ በደሉና ንስሓው እንጂ አሁንም መድረክ ላይ የመቀጠሉ ጉዳይ ሊሆን አይገባውም፡፡ እንመለስ የሚሉ ሰዎች ጭንቀታቸው መድረክ ላይ ስለ መዘመራቸውና ስለ መስበካቸው ከሆነ ጉዳዩ ዓላማን በውጭ ሆኖ ማስፈጸም ስለማይመች ወደ ውስጥ ገብቶ ተሐድሷዊውን ዓላማ ለማስፈጸም የአስገቡኝ ጥያቄ እንጂ የመመለስና የንስሐ ጥያቄ አይደለም ማለት ነው፡፡ ይኼ የድርድር እንጂ የንስሓ መንገድ አይደለም፡፡ የእንመለሳለን ጥያቄው ትኩረቱ በመድረክ ላይ ስለ መዘመርና ስለ መስበክ ከሆነ ጉዳዩ በእውነትም የእድሜ ማራዘሚያና የተንኮል ስልት እንጂ በቅንነት የተደረገ የእንመለሳለን አካሄድ ሆኖ አይታይም፡፡ 11. የሚደረጉትን እያዳንዳቸውን ነገሮች ሁሉ በከፍተኛ ጥንቃቄና ማስተዋል ማድረግ የጠፉትን መቀበል ተገቢና መልካም ቢሆንም በሌላ በኩል ደግሞ በዚህ ሂደት የሚደረጉት እያንዳንዳቸው ነገሮች ሁሉ ቤተ ክርስቲያኒቷ ለኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ እምነት ያላት ቁርጠኝነትና ድርጊቶቹ በኅብረተሰቡ ሥነ ልቡናዊና ሃይማኖታዊ አረዳድና መንፈስ ላይ ሸርሻሪ መሆን አለመሆናቸውን መጠየቅና በጥንቃቄ መመርመር ያስፈልጋል፡፡ በአንዳንዶች ዘንድ መናፍቃን የነበሩትን መቀበል የቤተ ክርስቲያንን እምነት መሸርሸር ተደርጎ እንዳይታይ መጠንቀቅ ይገባል፡፡ አለበለዚያ አንዱን እገነባለሁ ሲሉ ሌላውን ማፍረስ እንዳይሆን፡፡ እነዚህ ነገሮች በሚሆኑበት ጊዜ የሕዝቡን አረዳድና ሊያስከትል የሚችለውን ተጽእኖ በሚገባ ማጤን ያስፈልጋል፡፡ ገና ለገና ለወደፊቱ ይጠቅማል በማለት በጊዜው ያለውን ተጨባጭ ሁኔታ ያላገናዘበ ውሳኔና ድርጊት ውስጥ መግባት አደገኛ ነው፡፡ ሊያስከትል የሚችለውን አደጋ አርቆ ማየት ያስፈልጋል፣ ጭምብሎቻቸውን ገልጦ ትክክለኛ ማንነታቸውንና አደጋውን መረዳትና መለየት ያስፈልጋል፡፡ “ሰላም ሰላም” በሚል ቃል ብቻ እውነተኛ የቤተ ክርስቲያንን ውሳጣዊ ሰላም፣ እንዲሁም ጊዜያዊ ችግር የፈታንና ያቃለልን ሲመስለን ለወደፊቱ ችግር እያወሳሰብንና እያቆላለፍን እንዳይሆን መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡ ለዚህ ደግሞ በቅርብ ጊዜ በዘመናችን ከስድስቱ አኃት አብያተ ክርስቲያናት መካከል አንዷ በሆነችው በሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን የሆነውን አሳዛኝ ነገር ልንረሳው አይገባንም፡፡ በዋናነት በአንግሊካን ፕሮቴስታንት ቸርች (በእንግሊዝ ቤ/ክ) ቀያሽነትና አስፈጻሚነት በውስጣቸው ተፈልፍለው ያደጉት ተሐድሶዎች ገና ከመጀመሪያው ጉዳዩን የተረዱ አባቶችና ምእመናን ለይተው የማውገዝና የማጥራት ሥራ ሊሠሩ ሲሉ ተሐድሶዎቹ የእንመለሳን፣ የአስታርቁን ሽምግልና በተለያዩ ሰዎች በኩል ይልኩባቸው ነበር፡፡ በሽምግልናው ይሳተፉ የነበሩት ሰዎች አንዳንዶቹ እንዲሁ በሽፍኑ እርቅ ማን ይጠላል፣ ሰላም ምን ክፋት አለው በሚሉ መሸፈኛዎች የተታለሉና ምን እያደረጉ እንደሆኑ የማያውቁ ነበሩ፡፡ አንዳንዶቹ ደግሞ አስታረቁ ተብለው ስም ለማሰርና ጀብድ እንደ ሠሩ ለመቆጠር ነበር፡፡ አንዳንዶቹ ደግሞ ራሳቸውን በአስታራቂነት ጎራ ሲመድቡ እነርሱ ከሌሎቹ የተሻሉ አስተዋዮችና ያላከረሩ ብልሆች እንደሆኑ አድርገው ራሳቸውን ይቆጥሩ ነበር፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ዋናዎቹ ከጀርባ ሽማግሌዎቹን የሚልኳቸውና በሽምግልናውም ውስጥ ዋናውን ሥራ ይሠሩ የነበሩት ጥቂቶቹ ግን ዓላማው ገብቷቸው ተሐድሶዎቹ በደንብ ሳይጠነክሩና ሳይጎለምሱ፣ ብዙዎችን ወደ እነርሱ ጎራ ሳይለውጡ እንዳይወጡ እንደ እድሜ ማራዘሚያ ስልት ለመጠቀም ነበር፡፡ በዚህ ምክንያት ሳይወገዙ “እርቅ”፣ “ይቅርታ፣ “ንስሐ” እየተባለ ውስጥ ውስጡን ብዙ ካህናትንና ምእመናንን ከመለመሉና ከቀሰጡ በኋላ ራሳችንን የቻልንበት ደረጃ ላይ ደርሰናል ብለው ሲያስቡ መላዋን ቤተ ክርስቲያን መቆጣጠር ስላልቻሉ በይገባኛል የቤተ ክርስቲያኒቱን ነገር ሁሉ በፍርድ ቤት ተካፍለው ከሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ውስጡን ተሐድሶ ያደረጓቸውን ካህናትና ምእመናን ይዘው በመውጣት የራሳቸውን የተሐድሶ ቤተ እምነት መሥርተዋል፡፡ እነዚህም “ማር ቶማ ቸርች” ይባላሉ፡፡ ምሥራቃዊ ፕሮቴስታንትም (Oriental Protestant) ይሏቸዋል፡፡ እርቁንና ሽምግልናውን እየተቀበሉ ተወግዘው እንዳይለዩ ሲደግፉና ሓሳብ ሲሰጡ፣ በጊዜው ጊዜ ተወግዘው እንዲለዩና ምእመናን እንዲያውቋቸው ለማድረግ ይጥሩ የነበሩ ጳጳሳትንና ምእመናንን እየለመኑና እያግባቡ “እርቅ፣ ሰላም፣ አንድነት” በሚሉ ቃላት ተታለው ሲያታልሉ የነበሩት ጳጳሳትና ምእመናን ግን የኋላ ኋላ ጥቅም የሌው ጸጸት ብቻ ነበር ያተረፉት፡፡ ነገሩ ጅብ ከሄደ ሆነባቸው፡፡ ስለሆነም ይህ ጉዳይ አንድ ጊዜ ከመቁረጥ በፊት አሥር ጊዜ፣ ካስፈለገም ከዚያም በላይ፣ መለካት የሚያስፈልገው ጠንካራ ጉዳይ ነው፡፡ እንዲሁ በይሁን ይሁን፣ በምናለበት፣ ያለ ማስተዋልና ያለ አርቆ ማሰብ የሚደረግ ነገር በኋላ በእግዚአብሔርም ዘንድ፣ በትውልድም ዘንድ ያስጠይቃልና መጠንቀቅ ይገባል፡፡ ይኼው የሕንድ ቤተ ክርስቲያን የደረሰባትን አሳዛኝ ነገር እኛ እያዘንን እንደምንጠቅሰው፣ ሌላውም ዛሬም ወደፊትም እንደ አሳዛኝ ታሪክ ማሳያ እያደረገ እንደሚጠቅሰው ሁሉ የእኛ ቤተ ክርስቲያን አባቶችና ምእመናን በዚህ ጉዳይ ላይ ከፊታችን የሚሠሩት ሥራም በበጎም ሆነ በክፉ ተጠቃሽ ነው፡፡ ግን በአስተዋይነት የተሠራ መልካም ሥራ ሆኖ በበጎ ታሪክነትና በአስተማሪነቱ የሚጠቀስ ይሆን? ወይስ በስህተትና “በእነርሱ የደረሰ እንዳይደርስባችሁ” በሚል ማስፈራሪያነት? ውጤቱን ወደፊት የምናየው ይሆናል፡፡ ግን ከአፍንጫ ሥር ያለውንና ከፊት የቀረበውን ብቻ አሽትቶና አይቶ የሚወሰን ሳይሆን ወደ ኋላ ከዘመነ ሐዋርያት አንሥቶ የነበረው ታሪከ ቤተ ክርስቲያንና አስተምህሮን፣ አሁን ደግሞ ያለንበትን ጠቅላላና ዝርዝር ተጨባጭ ሁኔታ፣ ወደፊትም በእግዚአብሔርና በትውልድ ያለብንን ኃላፊነት ታሳቢ ያደረገ ቀኖናዊ ሂደት ይኖራል ብለን ተስፋ እናደርጋለን፣ እንዲኖርም እንፈልጋለን፡፡ ቤተ ክርስቲያን የሁላችንም ናትና እያንዳንዳችንም ችላ ሳንል፣ “እንዳረጉ ያድርጉት፣ እኔ ምን አገባኝ” ሳንል የቤተ ክርስቲያንን አንድነትና ቀኖናዊነት በጠበቀና ባገናዘበ መልኩ የየድርሻችንን እንወጣ፡፡ “ከወዳጆችህ ጋር ብቻ ሳይሆን ከጠላቶችህም ጋር እንኳ ሳይቀር በሰላም ኑር፤ ነገር ግን እንዲህ የምልህ ካንተ ከግል ጠላቶችህ ጋር እንጂ ከእግዚአብሔርና ከቤተ ክርስቲያን ጠላቶች ጋር አይደለም፡፡”አንድ ገዳማዊ አባት ለአንድ በቤተ ክርስቲያን ኃላፊነት ላይ ለነበረ ሌላ አባት ከጻፈው መልእክት ላይ የተወሰደ “ሰውን ከእግዚአብሔር ከሚለየው አጉል ሰላም ይልቅ ከእግዚአብሔር የማይለየው ጦርነት ይሻላል፤ ስሜታዊ ከሆነና ለቤተ ክርስቲያን ዘለቄታዊ ጉዳት ከሚኖረው ስምምነትና አንድነት ይልቅ ስለ ሃይማኖት መጠበቅ ዘለቄታዊ ጠቀሜታ የሚኖረውና ለዚህ ሲባል የሚሆን አለመስማማት ይሻላል፡፡” ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ፣ ትምህርት 2፡82 ላይ ኦገስት 15, 2013 ምንም አስተያየቶች የሉም: ይህን ኢሜል አድርግጦማር አድርግ!Twitter ላይ አጋራFacebook ላይ አጋራለPinterest አጋራ 2013 ኦገስት 8, ሐሙስ ሃይማኖት ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን የወጡ (ያፈነገጡ) ሰዎች የሚመለሱት እንዴት ነው? መስከረም 22 ቀን 2006 ዓ.ም. ዲ/ን ያረጋል አበጋዝ ፩. የቤተ ክርስቲያን ምንነት፣ ዓላማና ተልእኮዎች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የምትባለው በአጭር ቃል የኢየሱስ ክርስቶስ አካል ስትሆን፣ አማንያን ደግሞ የተለያዩ የአካል ክፍሎቿ ናቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ባለቤቷና መሥራቿ እግዚአብሔር ሲሆን ከእግዚአብሔር ጋር መንፈሳዊ ኅብረትና ግንኙነት ያላቸው መንፈሳውያን አንድነት (ጉባኤ) ናት፡፡ አንድ ሰው በሃይማኖትና በምሥጢራት አማካይነት ወደዚህች ጉባኤ ሲገባ የዚህ ጉባኤ (ኅብረት) አካል ሆኖ ይሠራል፡፡ ሐዋርያው “ወደ ልጁ ወደ ጌታችን ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ኅብረት የጠራችሁ እግዚአብሔር የታመነ ነው” በማለት ያስረዳው ይህን ነው፡፡ 1 ቆሮ. 1፡9 እንዲሁም “ከእንግዲህ ወዲህ ከቅዱሳን ጋር ባላገሮችና የእግዚአብሔር ቤተ ሰዎች ናችሁ እንጂ እንግዶችና መጻተኞች አይደላችሁም” የሚለው ቃል ይህን የቤተ ክርስቲያንን መንፈሳዊ እሳቤ ያሳያል። ኤፌ. 2፡19-22 ይህች እግዚአብሔር የመሠረታት ጉባኤ (ማኅበር) ቀዳማዊት ናት፤ “ተዘከር ማኅበረከ ዘአቅደምከ ፈጢረ - አስቀድመህ የፈጠርሃትን ማኅበርህን አስብ” ያለው ለዚህ ነው፡፡ መዝ. 73፡2 የቤተ ክርስቲያን የአንድነቷ መሠረት ሃይማኖት ነው፡፡ ይህ ሃይማኖት ደግሞ ከእግዚአብሔር የተሰጠ አንድና ብቸኛ እውነት ነው፡፡ ሐዋርያው “ብዘገይ ግን፥ በእግዚአብሔር ማደሪያ ቤት እንዴት መኖር እንደሚገባ ታውቅ ዘንድ እጽፍልሃለሁ፤ ቤቱም የእውነት ዓምድና መሠረት፥ የሕያው እግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን ነው” ያለው ለዚህ ነው፡፡ 1 ጢሞ. 3፡15 ይህ የቤተ ክርስቲያን አምዷ (ምሰሶዋ) የሆነው እውነትና ሃይማኖት ካልተጠበቀ ወይም ችላ ከተባለና እግዚአብሔር ከገለጠው እውነት ጋር እንሸቃቅጠው ከተባለ ቤተ ክርስቲያን ባሕርይዋ ስለማይፈቅድላት እንዲህ ያለ ነገር መቀበል አትችልም፡፡ የቤተ ክርስቲያን መሠረቷ እና ዓምዷ እውነት ነውና፡፡ ፪. የቤተ ክርስቲያን መሠረታዊ ባሕርያት ወልድ ዋሕድ ኢየሱስ ክርስቶስ የመሠረታት ቤተ ክርስቲያን እርሷነቷን ለመግለጽ የሚያገለግሉ አራት መሠረታዊ ባሕርያት አሏት፡፡ እነዚህም ቅድስት፣ አሐቲ (አንዲት)፣ ሐዋርያዊት እና ኩላዊት (ጉባኤያዊት) ናት የሚሉት ናቸው፡፡ የቤተ ክርስቲያን ዓላማዎችና ተልእኮዎች የሚመነጩትና የሚቀዱት ከዚህ መሠረታዊ ባሕርይዋ ነው፡፡ ሆኖም በዚህ ጽሑፍ በርእሱ ወደ ተነሣው ጉዳይ ላይ ለማተኮር ስንል የቤተ ክርስቲያን ባሕርያት የሚለውን መሠረታዊ ጉዳይ አሁን አንዳስሰውም፡፡ ፫. የቤተ ክርስቲያን ዓላማና ተግባር ቅድስት፣ አሐቲ፣ ሐዋርያዊትና ኩላዊት የሆነችው የልዑል እግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን ዓላማዎችና ተልእኮዎች በዋናነት የሚከተሉት ናቸው፡፡ 1. ቅዱስ እግዚአብሔር ለሰዎች የሰጠውን የመዳን ምሥጢር መግለጥ፣ ሰዎችን ማዳን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እግዚአብሔር ለሰው ልጆች ሁሉ የሰጠውን የመዳን ጸጋ ሰዎች አውቀውና ተረድተው ይጠቀሙበት ዘንድ የምሥራቹን ለዓለም (ለሰዎች) ሁሉ የምትናገር ናት፡፡ የቤተ ክርስቲያን ዋናው ተልእኮዋም ጌታችን “እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው፥ ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው” ብሎ የሰጣት ታላቅ አምላካዊ ትእዛዝ ነው፡፡ ማቴ. 28፡19-20 ሰዎች ይህን የወንጌል ጥሪ ተቀብለው ለመዳን የሚያስፈልጋቸውን ነገር እንዲያደርጉ ታስተምራለች፣ ያመኑትን ደግሞ አስፈላጊ የሆኑ ቅዱሳት ምሥጢራትን ትፈጽምላቸዋለች፡፡ በዚህም ከእግዚአብሔር ጋር አንድ ይሆናሉ፣ እንዲሁም የእግዚአብሔር ከሆኑት ሁሉ ጋር ኅብረት ይኖራቸዋል፡፡ “ . . . ስለ ክርስቶስ መልክተኞች ነን፤ ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ ብለን ስለ ክርስቶስ እንለምናለን” እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ 2 ቆሮ. 5፡20፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ደጉ ሳምራዊ በመንገድ ላይ ቆስሎ ወድቆ ለተገኘው ሰው ያደረገለት ነገሮች - ማዘኑ፣ ዘይትና ወይን በቁስሉ ላይ ማፍሰሱና ከዚያም በራሱ አህያ ላይ አስቀምጦት ወደ እንግዶች ማረፊያ ስፍራ ካደረሰውና ከጠበቀው በኋላ በዚያ አሳድሮ በማግሥቱ ሁለት ዲናር አውጥቶ ለባለቤቱ ሰጠና “ጠብቀው፣ ከዚህም በላይ የምትከስረውን ሁሉ እኔ ስመለስ እከፍልሃለሁ” አለው ተብሎ የተገለጸውን አገልግሎት - በዚህ ዓለም በኃጢአትና በክህደት ለቆሰሉ ሁሉ ታደርግ ዘንድ የተሰጠች ሐኪም ቤት ናት። ሉቃ. 10፡30-35 በአጠቃላይ የቤተ ክርስቲያን ዋና ተልእኮዋ ሰዎች እንዲድኑ መርዳት (ማስተማር፣ ማጥመቅ፣ ማቁረብ . . . ) ነው፡፡ ሌላው ተግባሯና ድርጊቷ ሁሉ ከዚህ የሚመነጭና የዚህ አጋዥና ደጋፊ ነው፡፡ 2. ምእመናንን፣ ሃይማኖትን፣ እና ምሥጢራትን መጠበቅ ገና ያላመኑትን ማስተማሯና መስበኳ እንዳለ ሆኖ በዚህ ላይ ወደ ድኅነት መስመር የገቡትን፣ በመዳን መንገድ ላይ ጉዞ የጀመሩትን ደግሞ ትጠብቃለች፡፡ ጌታችን ቅዱስ ጴጥሮስን “ጠቦቶቼን ጠብቅ” እንዳለው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ይህን ሲያስረዳ የመንፈስ ልጁን ጢሞቴዎስን “አንድን እንኳ በአድልዎ ሳታደርግ፥ እነዚህን ያለ መዘንበል እንድትጠብቅ በእግዚአብሔርና በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ በተመረጡትም መላእክት ፊት እመክርሃለሁ” ይላል፡፡ 1 ጢሞ. 5፡21 በድጋሜም “ዕቀብ ማኅፀንተከ ሠናየ በመንፈስ ቅዱስ ዘኅዱር ላዕሌከ - መልካሙን አደራ በእኛ በሚኖረው በመንፈስ ቅዱስ ጠብቅ” ይላል 2 ጢሞ. 1፡14፡፡ እንዲሁም ቤተ ክርስቲያን ከእግዚአብሔር ለሰዎች የተሰጠውን የመዳኛና መቀደሻ መንገድ የሆነውን ሃይማኖትና እውነት፣ እንዲሁም እነዚህ የሚፈጸሙበትንና የሚገለጡበትን ምሥጢራትን (Mysteries) መጠበቅ ተግባሯና ተልእኮዋ ነው፡፡ 3. የጠፉትን መፈለግ ልጆቿ የሆኑ ምእመናን የሚሰማሩት ተኩላ በበዛበት ዓለም በመሆኑ ከመንጋው መካከል በግልጽ ተኩላ የሆኑም፣ የበግ ለምድ የለበሱ ተኩላዎችም የሚያስቀሯቸው በጎች አይጠፉም፡፡ በራሳቸው ስንፍናና ድካም የሚጠፉም ይኖራሉ፡፡ ስለዚህ በምንም ምክንያት ይሁን የጠፉባትን ልጆቿን ትፈልጋለች፡፡ እስኪመለሱላት ድረስም ዕረፍት አይኖራትም፡፡ ፈሪሳውያንና ጻፎች በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ “ይህስ ኃጢአተኞችን ይቀበላል፣ ከእነርሱም ጋር ይበላል” ብለው እርስ በርሳቸው ባንጐራጐሩ ጊዜ እንዲህ ሲል በምሳሌ ነገራቸው፡- “መቶ በግ ያለው ከእነርሱም አንዱ ቢጠፋ፥ ዘጠና ዘጠኙን በበረሃ ትቶ የጠፋውን እስኪያገኘው ድረስ ሊፈልገው የማይሄድ ከእናንተ ማን ነው?” ሉቃ. 15፡2-4፡፡ እንዲሁም ከዚሁ ጋር በተያያዘ ምሳሌ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የጠፉ ልጆቿን መልሳ እስክታገኛቸው ድረስ ዕረፍት እንደማይኖራትና አጥብቃ ከመፈለግ እንደማትቦዝን ሲያስተምረን እንዲህ አለ፡- “ወይም አሥር ድሪም ያላት አንድ ድሪም ቢጠፋባት፥ መብራት አብርታ ቤቷንም ጠርጋ እስክታገኘው ድረስ አጥብቃ የማትፈልግ ሴት ማን ናት? ባገኘችውም ጊዜ ወዳጆቿንና ጐረቤቶቿን በአንድነት ጠርታ፡- የጠፋውን ድሪሜን አግኝቼዋለሁና ከእኔ ጋር ደስ ይበላችሁ ትላቸዋለች። እላችኋለሁ፣ እንዲሁ ንስሐ በሚገባ በአንድ ኃጢአተኛ በእግዚአብሔር መላእክት ፊት ደስታ ይሆናል።” ሉቃ. 15፡8-10 ይህን ሁሉ አጠቃልሎ “የሰው ልጅ የጠፋውን ሊፈልግና ሊያድን መጥቷልና” በማለት ነግሮናል፡፡ ሉቃ. 19፡10 የክርስቶስ አካሉ የሆነችው ቤተ ክርስቲያንም አንዱ ተልእኮዋ የጠፉትን መፈለግና ሕይወት ወደ ሆነው ወደ እግዚአብሔር እንዲመለሱ የምትችለውን ሁሉ ማድረግ ነው፡፡ 4. ስለ ሁሉም ጸሎትና ምልጃ ማቅረብ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በሰውና በእግዚአብሔር መካከል የምትገኝ ድልድይ እንደ መሆኗ ሌላው ተግባሯ ስለ ፍጥረታት ሁሉ ወደ እግዚአብሔር ጸሎትና ምልጃ ማቅረብ ነው፡፡ ይህም “እንግዲህ እግዚአብሔርን በመምሰልና በጭምትነት ሁሉ ጸጥና ዝግ ብለን እንድንኖር፥ ልመናና ጸሎት ምልጃም ምስጋናም ስለ ሰዎች ሁሉ ስለ ነገሥታትና ስለ መኳንንትም ሁሉ እንዲደረጉ ከሁሉ በፊት እመክራለሁ። ሰዎች ሁሉ ሊድኑና እውነቱን ወደ ማወቅ ሊደርሱ በሚወድ በእግዚአብሔር በመድኃኒታችን ፊት መልካምና ደስ የሚያሰኝ ይህ ነው” ተብሎ የተሰጣት ተግባር ነው፡፡ 1 ጢሞ. 2፡1-4 ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በሊጦኑ፣ በዘይነግሡ፣ በመስተብቁዑ፣ በእንተ ቅድሳቱ፣ በመሳሰለው ጸሎት ሁሉ ስለ ዝናማት፣ ስለ ወንዞች፣ ስለ ነፋሳት፣ ስለ ፍሬ ምድር፣ ስለ ሰላም፣ ስለ መንገደኞች፣ ስለ ተማረኩ ሰዎች፣ ስለ ታመሙ ሰዎች፣ ወዘተ ወደ እግዚአብሔር የምትማልደው ስለዚህ ነው፡፡ ፬. ማውገዝ ለምን አስፈለገ? በመጀመሪያ ማውገዝ ምንድን ነው? ማውገዝ ማለት አንድ ሰው በሃይማኖትና በምሥጢራት አማካይነት የቤተ ክርስቲያንን ጸጋ ከተቀበለና አካል መሆን ከጀመረ በኋላ ቀድሞ ያመነውን ሲክድ፣ የቤተ ክርስቲያን አካላትን አንድ ከሚያደርገው ከሃይማኖትና ከእውነት ዐምድ ሲያፈነግጥ ያን ጊዜ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን “ከአሁን በኋላ የእኔ አካል አይደለህምና ወደፈለግኸው ሂድ፣ ከእኔ ጋር ግን ኅብረትና አንድነት የለህም” ብላ የምታሰናብተው ማሰናበት ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን እሥራትም ሆነ ግርፋት አትፈርድም፣ ይህ የምድራውያን ፍርድ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ግን ሰማያዊና መንፈሳዊ የእግዚአብሔር ጉባኤ እንደ መሆኗ የአንድነቷ መሠረት ከሆነው ከሃይማኖት የወጣውን እርሱ ራሱ ክዶ የወጣ ስለሆነ ያንኑ በግልጽ በመግለጥ ልጇና አባሏ አለመሆኑን በይፋ ለሁሉም ታሳውቃለች፡፡ ውግዘት የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ፍላጎቷም፣ ዓላማዋም አይደለም፤ ማውገዝ የግድ በሁኔታዎች አስገዳጅነት የሚመጣ ነገር ነው፡፡ ቅዱስ አግናጥዮስ “ሰዎችን መጥራት፣ መመገብና መጠበቅ እንጂ መፍረድ የቤተ ክርስቲያን ድርሻ አይደለም” ይላል፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ፍላጎቷና ምኞቷ እንኳን ወደ ውስጧ የገቡት ቀርቶ ገና ያልቀረቡትም እንዲቀርቡና እንዲድኑ ነው፡፡ ሆኖም ግን በተግባራዊ ዓለም ሲታይ ከገቡ በኋላ የሚወጡ፣ ካመኑ በኋላ የሚክዱ፣ ከቀረቡ በኋላ የሚርቁ አልጠፉም፡፡ ስለዚህ ማውገዝ ከሰውነት አካላት መካከል የታመመና ሌላውን የሚበክል አካል ቢኖር ያ አካል የሰውነት ክፍል ሆኖ መቀጠሉ ለሰውዬው ሕይወት አደጋ የሚሆን ሲሆን ይቆረጥ እንደሚባለው ዓይነት ነው፡፡ አንዱን የጠፋውን በግ - የሰውን ልጅ - ለመፈለግ እስከ መስቀል ሞት ድረስ የተቀበለው መድኃኔ ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ የቤተ ክርስቲያን አካል ከሆኑ በኋላ ከእምነቷና ከሥርዓቷ ስለሚያፈነግጡ ሰዎች ምን ማድረግ እንደሚገባ እንዲህ በማለት በግልጽ አስተምሮናል፡- “ወንድምህም ቢበድልህ፥ ሄደህ አንተና እርሱ ብቻችሁን ሆናችሁ ውቀሰው። ቢሰማህ፥ ወንድምህን ገንዘብ አደረግኸው፤ ባይሰማህ ግን፥ በሁለት ወይም በሦስት ምስክር አፍ ነገር ሁሉ እንዲጸና፥ ዳግመኛ አንድ ወይም ሁለት ከአንተ ጋር ውሰድ፤ እነርሱንም ባይሰማ፥ ለቤተ ክርስቲያን ንገራት፤ ደግሞም ቤተ ክርስቲያንን ባይሰማት፥ እንደ አረመኔና እንደ ቀራጭ ይሁንልህ” ማቴ. 18፡15-17፡፡ ተመክሮ የማይሰማና የማይመለስ ከሆነ፣ ለቤተ ክርስቲያንም ተነግሮ አሁንም የማይመለስ ከሆነ፣ በመጨረሻ ያለው አማራጭ “ደግሞም ቤተ ክርስቲያንን ባይሰማት፥ እንደ አረመኔና እንደ ቀራጭ” እንዲሆን ማድረግ ነው፡፡ ይህም ማለት አረመኔና ቀራጭ በቤተ ክርስቲያን ከምሥጢራቷና ከጸጋዋ ሱታፌ እንደሌላቸው ሁሉ እርሱም እንደዚያ ይሆናል፣ ክርስቲያን ከተባለ በኋላ አረመኔ ይባላል፣ ከቤተ ክርስቲያን የወጣ፣ ከጸጋዋና ከሁሉ ነገሯ የተለየ ይሆናል ማለት ነው፡፡ እንደዚሁም በቆሮንቶስ ቤተ ክርስቲያን ከባድ ኃጢአት ሠርቶ የነበረውን ሰው ቀኖና ሊሰጡትና ከመካከላቸው ሊለዩት ሲገባ እነርሱ ግን ምንም ያልሆነ ይመስል ዝም ብለው ሰውዬውን በመካከላቸውይዘው፣ ከዚያም አልፎ እንዲያ ያደረገው ሰው በመጸጸት ፋንታ ዝም ሲሉት ጊዜ የተወደደለት መስሎት የራሱን ደጋፊዎችና አንጃዎች ወደ ማሰባሰብና ወደ ማደራጀት ደረጃ ደርሶ ስለ ነበር ቅዱስ ጳውሎስ ጠንከር ያለ መልእክት ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች ልኮላቸዋል፡፡ ይህን የተመለከተው ቃል እንዲህ ይላል፡- “በአጭር ቃል በእናንተ መካከል ዝሙት እንዳለ ይወራል፣ የዚያም ዓይነት ዝሙት በአሕዛብስ እንኳ የማይገኝ ነው፣ የአባቱን ሚስት ያገባ ሰው ይኖራልና። እናንተም ታብያችኋል፤ ይልቅስ እንድታዝኑ አይገባችሁምን? ይህን ሥራ የሠራው ከመካከላችሁ ይወገድ። እኔ ምንም እንኳ በሥጋ ከእናንተ ጋር ባልሆን፥ በመንፈስ ከእናንተ ጋር ነኝ፥ ከእናንተም ጋር እንዳለሁ ሆኜ ይህን እንደዚህ በሠራው ላይ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አሁን ፈርጄበታለሁ፤ እናንተና መንፈሴም ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል ጋር ተሰብስበን መንፈሱ በጌታ በኢየሱስ ቀን ትድን ዘንድ እንደዚህ ያለው ለሥጋው ጥፋት ለሰይጣን እንዲሰጥ ፍርዴ ነው። መመካታችሁ መልካም አይደለም። ጥቂት እርሾ ሊጡን ሁሉ እንዲያቦካ አታውቁምን? እንግዲህ ያለ እርሾ እንዳላችሁ አዲሱን ሊጥ ትሆኑ ዘንድ አሮጌውን እርሾ አስወግዱ” 1 ቆሮ. 5፡1-7፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊም በሃይማኖታዊ ጉዳይ ላይ ምን ያህል ጠንቃቆች መሆን እንደሚገባን ሲናገር “ለሚወጣ ሁሉ በክርስቶስም ትምህርት ለማይኖር ሰው አምላክ የለውም፤ በክርስቶስ ትምህርት ለሚኖር አብና ወልድ አሉት። ማንም ወደ እናንተ ቢመጣ ይህንም ትምህርት ባያመጣ በቤታችሁ አትቀበሉት ሰላምም አትበሉት፤ ሰላም የሚለው ሰው በክፉ ሥራው ይካፈላልና።” በማለት አርቀን እንድናጥርና እንድንጠነቀቅ አስተምሮናል፡፡ 2ኛ ዮሐ. 9-11 ቅዱስ ጳውሎስም “ነገር ግን፥ ወንድሞች ሆይ፥ እናንተ የተማራችሁትን ትምህርት የሚቃወሙትን፣ መለያየትንና ማሰናከያን የሚያደርጉትን ሰዎች እንድትመለከቱ እለምናችኋለሁ፣ ከእነርሱ ዘንድ ፈቀቅ በሉ፤ እንዲህ ያሉት ለገዛ ሆዳቸው እንጂ ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ አይገዙምና፣ በመልካምና በሚያቆላምጥ ንግግርም ተንኮል የሌለባቸውን ሰዎች ልብ ያታልላሉ” በማለት ነግሮናል ሮሜ 16፡18፡፡ ፭. የማውገዝ ምክንያቶች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን መናፍቃንን የምታወግዝባቸው ዋና ዋና ምክንያቶች የሚከተሉት ናቸው፡፡ 1. ምእመናንን እንዳይበክሉ ለመጠበቅ ኑፋቄ ደዌ ነው፣ በሽታ ነው፡፡ ስለዚህ በኑፋቄ በሽታ የተለከፈውና የታመመው ሰው “ታምመሃል፣ ታከምና ዳን” ሲሉት “አይ፣ እኔ ጤነኛ ነኝ፣ ምንም ችግር የለብኝም” የሚል ከሆነ የሃይማኖት በሽታውን ወደ ሌሎች እንዳያዛምትና አንዲቷን ጉባኤ (ቤተ ክርስቲያንን) እንዳይበክል ለመከላከል ሲባል ከማኅበረ ምእመናን እንዲለይ (እንዲወገዝ) ይደረጋል፡፡ አንድ ሰው ከአካሉ ውስጥ በጠና የታመመና የማይድን መሆኑ የተረጋገጠ አካል ቢኖረው፣ አለመዳኑ ብቻ ሳይሆን የዚያ አካል በሽታ ወደ ሌላው የሰውነት ክፍል የሚዛመትና የሰውዬውን ሕይወት አደጋ ላይ የሚጥለው ከሆነ ሐኪሞች ብቸኛው መፍትሔ ያን አካል መቁረጥና ማውጣት መሆኑን ይነግሩታል፡፡ ሐኪሞች እንዲያ የሚሉት የሰውዬውን አካል ጠልተውት ወይም ሰውዬውን ለመጉዳት ብለው ሳይሆን የሰውዬውን ሕይወት ለመታደግ፣ ሌላው አካሉ እንዳይመረዝ ለማዳን ሲሉ የሚያደርጉት የርኅራኄ ሥራ ነው፡፡ በሽተኛውም ገንዘቡን አፍስሶና ይደረግ ዘንድ ፈቃደኛነቱን በፈርማው አረጋግጦ አካሉን ወደ ማስቆረጥ የሚሄደው ሕይወቱን ለማቆየት ካለው ጽኑ ምኞት የተነሣ መሆኑ የታወቀ ነው፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም በኑፋቄ በሽታ ላይድኑ የታመሙ ሰዎች ዝም ቢባሉ የቤተ ክርስቲያን አካላት ምእመናንን ስለሚበክሉ የግድ እያዘኑ እንደሚቆረጠው አካል ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም እያዘነች አውግዛ ትለያቸዋለች፡፡ እስራኤላውያን ከግብጽ ወጥተው ወደ ምድረ ርስት ከነዓን ሊገቡ ዮርዳኖስን ተሻግረው ኢያሪኮን በተአምራት በእጃቸው አሳልፎ ሲሰጣቸው በኢያሪኮ ካለው ሀብትና ንብረት ምንም ዓይነት ነገር እንዳይወስዱ “እርም ነው” ብሎ እግዚአብሔር ነግሯቸው ነበር፡፡ ሆኖም ግን ከመካከላቸው አንድ አካን የተባለ ሰው እርም የሆነውን ነገር በመንካቱ ምክንያት እግዚአብሔር ከሕዝቡ ተለያቸው፡፡ በአሕዛብ ፊትም ድል ተነሡ፣ ብዙ ሰዎችም ተገደሉባቸው፣ ከዚህም የተነሣ ብዙ ሐዘን ደረሰባቸው፡፡ በዚያን ጊዜ ኢያሱ ከእስራኤል ሽማግሌዎች ጋር ስላደረገው ነገር ቅዱስ መጽሐፍ እንዲህ ይናገራል፡- “. . . ኢያሱም ልብሱን ቀደደ፥ እርሱና የእስራኤልም ሽማግሌዎች በእግዚአብሔር ታቦት ፊት እስከ ማታ ድረስ በግምባራቸው ተደፉ በራሳቸውም ላይ ትቢያ ነሰነሱ። ኢያሱም አለ። ዋይ! ጌታ እግዚአብሔር ሆይ፥ በአሞራውያን እጅ አሳልፈህ ትሰጠን ታጠፋንም ዘንድ ይህን ሕዝብ ዮርዳኖስን ለምን አሻገርኸው? በዮርዳኖስ ማዶ መቀመጥን በወደድን ነበር እኮ! ጌታ ሆይ፥ እስራኤል በጠላቶቻቸው ፊት ከሸሹ ምን እላለሁ? ከነዓናውያንም በምድሪቱ የሚኖሩ ሁሉ ሰምተው ይከብቡናል፥ ስማችንንም ከምድር ያጠፋሉ ለታላቁ ስምህም የምታደርገው ምንድር ነው? እግዚአብሔርም ኢያሱን አለው፡-ለምን በግምባርህ ተደፍተሃል? ቁም እስራኤል በድሎአል፣ ያዘዝኋቸውንም ቃል ኪዳኔን አፍርሰዋል እርም የሆነውንም ነገር ወሰዱ፣ ሰረቁም፥ ዋሹም፥ በዕቃቸውም ውስጥ ሸሸጉት። ስለዚህም የእስራኤል ልጆች በጠላቶቻቸው ፊት መቆም አይችሉም የተረገሙ ስለ ሆኑ በጠላቶቻቸው ፊት ይሸሻሉ እርም የሆነውንም ነገር ከመካከላችሁ ካላጠፋችሁ ከዚህ በኋላ ከእናንተ ጋር አልሆንም።” ችግሩንና የችግሩን ምክንያት እንዲህ ከነገራቸው በኋላ ምን ማድረግ እንዳለባቸው ደግሞ እንዲህ ሲል አዘዛቸው፡- “ተነሣና ሕዝቡን ቀድስ፥ እንዲህም በላቸው፣ እስራኤል ሆይ፣ እርም የሆነ ነገር በመካከልህ አለ፣ እርምም የሆነውን ነገር ከመካከላችሁ እስክታጠፉ ድረስ በጠላቶቻችሁ ፊት መቆም አትችሉም ብሎ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ተናግሯልና እስከ ነገ ተቀደሱ። . . .” ኢያሱና ሕዝቡ ስለዳረጉት ደግሞ እንዲህ ይላል፡- “ኢያሱና እስራኤል ሁሉ የዛራን ልጅ አካንን፣ ብሩንም፣ ካባውንም፣ ወርቁንም፣ ወንዶችና ሴቶች ልጆቹንም፣ በሬዎቹንም፣ አህያዎቹንም፣ በጎቹንም፣ ድንኳኑንም፣ ያለውንም ሁሉ ወስደው ወደ አኮር ሸለቆ አመጧቸው። ኢያሱም፡- ለምን አስጨነቅኸን? እግዚአብሔር ዛሬ ያስጨንቅሃል አለው፡፡ እስራኤልም ሁሉ በድንጋይ ወገሩት፣ በእሳትም አቃጠሏቸው፥ በድንጋይም ወገሯቸው። በላዩም እስከ ዛሬ ድረስ ያለ ታላቅ የድንጋይ ክምር ከመሩ፣ እግዚአብሔርም ከቍጣው ትኵሳት ተመለሰ። ስለዚህም የዚያ ስፍራ ስም እስከ ዛሬ ድረስ የአኮር ሸለቆ ተብሎ ተጠራ” ኢያ. 7፡1-26፡፡ እንግዲህ ይህ የሚያስተምረን ነገር በአንድ ሰው በአካን እርም የሆነውን ነገር መንካት ምክንያት መላው ሕዝብ መጨነቁንና እግዚአብሔርም ከማኅበረ እስራኤል መለየቱን ነው፡፡ አካን ሲወገድ ደግሞ ተለይቷቸው የነበረው አምላካቸው እንደገና አብሯቸው ሆነ፡፡ በሃይማኖት ላይ የሚጨምርም ሆነ የሚቀንስ ሰው ከባድ እርም መንካቱ ስለሆነ ቤተ ክርስቲያን እንዲህ ያለውን ሰው አብራ ይዛ ጸጋ እግዚአብሔርንም ልትሰጥና ልትጠብቅ አትችልም፤ ስለዚህ እንዲህ ያሉትን ሰዎች ካጣራች በኋላ ትለያቸዋለች፡፡ ይህም ማኅበረ ምእመኑ እግዚአብሔር እንዳይለየውና ጸጋ እግዚአብሔር እንዳይርቀው ያደርጋል፡፡ ገንዘባቸውን ከሸጡ በኋላ ሰርቀው አስቀርተው ወደ ምእመናን አንድነት እንገባለን ብለው የነበሩት ሐናንያና ሰጲራ የተባሉት ባልና ሚስቶች በመንፈስ ቅዱስ የተቀሰፉትም ለዚህ ነበር፡፡ የሐዋ. 5፡1-11 ድርጊታቸው ያላቸውን ሁሉ እየሸጡ በሐዋርያት እግር ሥር እየጣሉ “ይህ የእኔ ነው” ይህ የአንተ ነው” ሳይባባሉ በአንድነት ይኖሩ ለነበሩት ምእመናን መጥፎ አብነት እንዳይሆኑ ገና ከበሩ ላይ ሐናንያና ሰጲራን ቀስፏቸዋል፡፡ እንዲህ ያለው መጥፎ እርሾ ጥቂትም እንኳ ቢሆን ብዙውን ሊጥ ሊያቦካ ይችላልና፤ ጌታችን ደቀ መዛሙርቱን “ከፈሪሳውያንና ከሰዱቃውያን እርሾ ተጠንቀቁና ተጠበቁ” ያላቸው ለዚህ ነበር። ማቴ. 16፡5 በእርሾ እየተለወሰ የማይቦካ ዱቄት የለምና፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ “የአንዳንዶች ሰዎች ኃጢአት የተገለጠ ነው፣ ፍርድንም ያመለክታል” በማለት እንዲህ ኑፋቄያቸው ግልጽ የሆነውና የታወቀውን ሰዎች ዝም ማለት እንደማይገባና መፍረድ (ማውገዝ) እንደሚገባ ይናገራል፡፡ 1 ጢሞ. 5፡24-25 ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እውነቱን እውነት፣ ሐሰቱን ሐሰት ማለት ስለሚገባት፣ ብርሃንን ከጨለማ መለየት ስላለባት በራሳቸው ጊዜ እውነትንና ብርሃንን የተውትን ትለያቸዋለች፡፡ ይህም ክፉዎች መናፍቃን ቤተ ክርስቲያንን እንዳይውጧት ለመጠበቅ አስፈላጊ ነው፡፡ በአራተኛው መቶ ዓመት መጨረሻና በአምስተኛው የመጀመሪያ አጋማሽ የነበረው የሰሜን አፍሪቃው አውግስጢኖስ የተለያየ ዓይነት በሆኑ በብዙ መናፍቃን ተከብቦ ነበር፡፡ እርሱም ይመለሱ እንደ ሆነ በማለት ከእነርሱ ጋር ውይይትን ደጋግሞ ሞከረ፣ ሆኖም ግን ውጤት እንደ ሌለው ተመለከተ፡፡ ከሂደቱም የምእመናን እምነት ለመጠበቅ መናፍቃንን አውግዞ ከመለየት ውጭ ሌላ መፍትሔ የለም አለ፡፡ ይህንም ሲያስረዳ እንዲህ አለ፡- “የማይስማማ ነገር ወደ ሰውነታችን ሲገባ ያ ነገር በትውኪያ ካልወጣ በስተቀር ውስጣችን ሰላምና ጤና እንደማያገኘው ሁሉ፣ መናፍቃንም እስካልተተፉ ድረስ ቤተ ክርስቲያን ጤና አታገኝም፡፡ ከሕይወታዊ ባሕርዩ ጋር ከማይሄድ ከማንኛውም ባእድ ነገር ጋር አለመስማማትና እስኪወጣለት ድረስ ዕረፍት ማጣት የሕይወት ባሕርይ መሆኑ የታወቀ ነው፡፡ ውስጣችን ወደ ራሱ ሊያዋሕደው የማይችለው ማንኛውም ነገር ጋር ይጋጫል፣ ያ ባእድ ነገር እስከሚወጣ ድረስም ይታወካል፣ ይታመማል፡፡ መናፍቃንም ለቤተ ክርስቲያን እንዲሁ ናቸው፡፡” ቅ. አውግስጢኖስ፣ 1ኛ ዮሐ. 2፡19 (ከእኛ ዘንድ ወጡ፥ ዳሩ ግን ከእኛ ወገን አልነበሩም፤ ከእኛ ወገንስ ቢሆኑ ከእኛ ጋር ጸንተው በኖሩ ነበር፤ ነገር ግን ሁሉ ከእኛ ወገን እንዳልሆኑ ይገለጡ ዘንድ ወጡ) የሚለውን ሲተረጉም ኑፋቄን ዝም ብለን እንታገሠው፣ አብሮ ይኑር ማለት ኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮ እና ኑፋቄ አንድ ናቸው ወደ ማለት ይወስዳል፤ ወይም ደግሞ ጥንቱንም በመካከላቸው ያን ያህልም የጎላና መሠረታዊ የሆነ ልዩነት የለም ማለት ይመስላል፡፡ ስለሆነም ሐዋርያዊና መጽሐፍ ቅዱሳዊ የሆነው ኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮ እንዲጠበቅ ብቻም ሳይሆን ከኑፋቄ ጋር ምንም ዓይነት ኅብረትና አንድነት የሌለው መሆኑ ይገለጥና ይታወቅ ዘንድ የተለየ አስተሳሰብ ይዘው ብቅ የሚሉ ወገኖችን ወደሚመስሏቸው እንዲሄዱ እንጂ በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የእነርሱ አስተሳሰብ ተቀባይነትና ቦታ እንደ ሌለው መግለጫና ማሳወቂያ መንገድም ነው፡፡ “ከማያምኑ ጋር በማይመች አካሄድ አትጠመዱ፤ ጽድቅ ከዓመፅ ጋር ምን ተካፋይነት አለውና? ብርሃንም ከጨለማ ጋር ምን ኅብረት አለው? ክርስቶስስ ከቤልሆር ጋር ምን መስማማት አለው? ወይስ የሚያምን ከማያምን ጋር ምን ክፍል አለው?” ተብሏልና፡፡ 2 ቆሮ. 6፡14-15 ስለዚህ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ምእመናን ልጆቿ በኑፋቄ በሽታ እንዳይያዙባት ስትል የኑፋቄ ተሐዋስያን የያዙትን መናፍቃንን በውግዘት እንዲለዩ ታደርጋቸዋለች፡፡ ከተለዩ (ከተወገዙ) በኋላም እናት ቤተ ክርስቲያን እግዚአብሔር ልብ እንዲሰጣቸውና ወደ ሕይወት እንዲመለሱ ትጸልይላቸዋለች፡፡ በመውጣታቸውም ታዝናለች፡፡ ምንም እንኳ ከቤተ ክርስቲያን አንድነት ቢለዩም እንደ ሰብአዊ ፍጡርነታቸውና እንደ ሰውነታቸው ክፉ እንዳያገኛቸው የምትችለውን ለማድረግ ፈቃዷ ነው፡፡ 2. ለራሱ ለሰውዬው ጥቅም ሲባል ቤተ ክርስቲያን መናፍቃንን የምታወግዛቸው ለራሳቸው ለመናፍቃኑ ጠቀሜታ ስትልም ነው፡፡ መወገዝ ለሚወገዘው ሰው ቢያንስ ሁለት መሠረታዊ ጠቀሜታዎች አሉት፡፡ አንደኛው፡- ሰውዬው ራሱን የሚያይበት እድል ለመስጠት ነው፡፡ የያዘውን ኑፋቄ በማሰራጨት ላይ ተጠምዶ ያለ ሰው ምን እያደረገ እንደሆነ ቆም ብሎ ራሱን የሚያይበት ዕድል ላያገኝ ይችላል፡፡ ነገር ግን ቤተ ክርስቲያን “ይሄ አስተምህሮህና ድርጊትህ ትክክል አይደለም፣ ተመለስ፣ ተስተካከል” ስትለው ልብ ከገዛ መልካም፣ ተጠቀመ ማለት ነው፡፡ ያ ካልሆነም በመጨረሻ ሲወገዝ አሁንም ድርጊቱ ስህተት መሆኑ በይፋ እየተነገረው በመሆኑ እልከኝነት ካላሸነፈው በስተቀር የድርጊቱን ስህተትነት ለመረዳትና ራሱን ለማየት ሰፊ ዕድል ይሰጠዋል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ተወግዞ እንዲለይ የወሰነበትን የቆሮንቶስ ሰው ስለ ውግዘቱ ምክንያት (ለምን እንደዚያ እንደ ወሰነበት ሲናገር) እንዲህ ያለው ለዚህ ነበር፡- “እኔ ምንም እንኳ በሥጋ ከእናንተ ጋር ባልሆን፥ በመንፈስ ከእናንተ ጋር ነኝ፥ ከእናንተም ጋር እንዳለሁ ሆኜ ይህን እንደዚህ በሠራው ላይ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አሁን ፈርጄበታለሁ፤ እናንተና መንፈሴም ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል ጋር ተሰብስበን፥ መንፈሱ በጌታ በኢየሱስ ቀን ትድን ዘንድ እንደዚህ ያለው ለሥጋው ጥፋት ለሰይጣን እንዲሰጥ ፍርዴ ነው” 1 ቆሮ. 5፡5፡፡ ስለዚህ የውግዘቱ ዓላማ ማጥፋት ሳይሆን ማዳን ነበር ማለት ነው፤ “መንፈሱ በጌታ በኢየሱስ ቀን ትድን ዘንድ እንደዚህ ያለው ለሥጋው ጥፋት ለሰይጣን እንዲሰጥ ፍርዴ ነው” በማለት ዓላማውን ተናገረ፡፡ እንዲሁም “በዚህ መልእክት ለተላከ ቃላችን የማይታዘዝ ማንም ቢኖር፥ ይህን ተመልከቱት፥ ያፍርም ዘንድ ከእርሱ ጋር አትተባበሩ። ነገር ግን እንደ ወንድም ገሥጹት እንጂ እንደ ጠላት አትቍጠሩት” አለ፡፡ 2 ተሰ. 3፡14-15 የሚወገዘው (የተወገዘው) ሰው እንደ ጠላት ሊቆጠር አይገባውም፣ ሆኖም ደግሞ ከቤተ ክርስቲያን የወጣና የተለየ መሆኑንና ያም ማለት ምን ማለት እንደ ሆነ እንዲገነዘብ ማድረግ ደግሞ ያስፈልጋል፡፡ መናፍቃንን ዝም ማለትና “ተዋቸው” በማለት በኑፋቄ ሲበላሹ እያዩ ዝም ማለት ፍቅር ሳይሆን ጥላቻ ነው፣ እነዚያን ሰዎች መጥቀም ሳይሆን መጉዳት ነው፤ ያውም በሥጋ ሳይሆን በነፍስ መጉዳት ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ አዳም በበደለ ጊዜ ከዕፀ ሕይወት እንዳይበላ ከልክሎታል፣ እንዲህ በማለት፡- “እግዚአብሔር አምላክም አለ፡- እነሆ አዳም መልካምንና ክፉን ለማወቅ ከእኛ እንደ አንዱ ሆነ፤ አሁንም እጁን እንዳይዘረጋ፣ ደግሞም ከሕይወት ዛፍ ወስዶ እንዳይበላ፣ ለዘላለምም ሕያው ሆኖ እንዳይኖር፣ ስለዚህ እግዚአብሔር አምላክ ከዔድን ገነት አስወጣው፣ የተገኘባትን መሬት ያርስ ዘንድ። አዳምንም አስወጣው፣ ወደ ሕይወት ዛፍ የሚወስደውንም መንገድ ለመጠበቅ ኪሩቤልንና የምትገለባበጥ የነበልባል ሰይፍን በዔድን ገነት ምሥራቅ አስቀመጠ” ዘፍ. 3፡22-24፡፡ እግዚአብሔር አምላክ አዳምን ከሃይማኖት ወጥቶ ከፈጣሪው ተጣልቶ ባለበት ሁኔታ የተቀደሰ ከሆነው ነገር ሁሉ (ከዕፀ ሕይወት፣ ከገነት፣ ወዘተ) የከለከለውና ወደዚያም እንዳይደርስ ዘግቶ ያስጠበቀበት አዳምን ስለ ጠላው አልነበረም፡፡ ከእግዚአብሔር በላይ ሰውን የሚወድድ ማን አለ ሊባል ነው? አዳምን የከለከለው ከፍጹም ፍቅሩና ከቸርነቱ የተነሣ ነበር እንጂ ከክፋት አልነበረም፡፡ ስለሆነም ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ከሃይማኖት የወጡ ከሥርዓት ያፈነገጡ ሰዎችን እስኪመለሱ ድረስ ከምሥጢራቷና ከአንድነቷ የምትለያቸው ከእናትነት ፍቅሯ የተነሣ ነው፡፡ ይልቁንም ጭካኔና ፍቅር የለሽነት የሚሆነው ኑፋቄያቸውን እያዩ በግድ የለሽነት ዝም ማለት ነው፡፡ መናፍቅነት የእግዚአብሔርን መንግሥት ከማያስወርሱ ታላላቅ ኃጢአቶች አንዱ ነውና፣ “. . . መናፍቅነት . . . አስቀድሜም እንዳልሁ፥ እንደዚህ ያሉትን የሚያደርጉ የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም” ገላ. 5፡21፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ስለዚህ ሲናገር እንዲህ አለ፡- “እምነትና በጎ ሕሊና ይኑርህ፣ አንዳንዶች ሕሊናን ጥለው መርከብ አለ መሪ እንደሚጠፋ በእምነት ነገር ጠፍተዋልና፤ ከእነዚያም እንዳይሳደቡ ይማሩ ዘንድ ለሰይጣን አሳልፌ የሰጠኋቸው፥ ሄሜኔዎስና እስክንድሮስ ናቸው።” 1 ጢሞ. 1፡19-20 ለሰይጣን አሳልፎ የሰጣቸው “እንዳይሳደቡ ይማሩ ዘንድ ነው” አለ፡፡ የጠፋው ልጅም ለዚህ ጥሩ ምሳሌ ነው፡፡ በተወለደበትና ባደገበት በአባቱ ቤት ያለው መልካም ነገር ሁሉ ስልችት ባለውና ከዚያ ወጥቶ መሄድ በፈለገ ጊዜ አባቱ አልከለከለውም፡፡ ነገር ግን ወደ ሌላ አገር ከሄደ በኋላ የደረሰበት ረሃብና መከራ ሌላው ቢቀር ቢያንስ በአባቴ ቤት እንጀራ ጠግበውና ተርፏቸው ከሚያድሩት ከባሮቹ እንደ አንዱ ልሁን ብሎ ወደ ልቡ ተመለሰ፤ ከዚያም ወደ አባቱ በንስሐ ተመለሰ፡፡ አባቱ ከመጀመሪያውኑ እንዳይሄድ ከልክሎት ቢሆኖ ኖሮ ምናልባት የአባቱ ቤት መልካም ነገር ከተሰደደ በኋላ እንደ ታየው ሆኖ ላይታየው ይችል ነበር፡፡ መውጣቱና መቸገሩ ግን በአባቱ ቤት ያለውን መልካም ነገር በንጸጽር እንዲመለከት አድርጎታል፡፡ መናፍቃንም በቤቷ ሲኖሩ የጸጋዋ ጣዕም ካልገባቸው ተወግዘው ሲወጡና በባዕድ አገር (በሌላ ሁኔታ) ሲባዝኑ ያጡት ጸጋ ምንነት በፊታቸው ወለል ብሎ ሊታያቸው ይችላል፡፡ ይህ ባይሆንም ችግሩ የራሳቸው የሰዎቹ ነው፡፡ ሆኖም ግን እንዲህ ራሳቸውን የሚያዩበትን ዕድል መስጠቱ ከራሳቸው እልከኝነትና ስንፍና የተነሣ ሁሉም ላይጠቀምበት ቢችልም ምን ጊዜም ቢሆን በተሰጠው ነገር የሚጠቀመው ፈሪሃ እግዚአብሔር ያለው እና ወደ ልቡ የሚመለስ ሰው ስለሆነ እንደዚህ ላሉት ሰዎች ዕድሉን ማግኘቱ ይጠቅማቸዋል፤ ሌሎቹ ደግሞ የሚያመካኙበት ሰበብ ያጣሉ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅም እንዲህ ይላል፡- “ኩላዊት የሆነችው ቤተ ክርስቲያን ታላቅና ገነት ናት . . . እናም ማንም ቢሆን በዚች ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በዲያብሎስ የኑፋቄ ትምህርት ተበክሎና ታሞ ከተገኘ . . . አዳም ከጥንቷ ገነት እንደ ተባረረ ሁሉ እርሱም ከዚህችኛዋ ገነት - ከቤተ ክርስቲያን ይባረራል፡፡” ሁለተኛው ጠቀሜታ ብዙዎችን በማጥፋት ባለ ብዙ ዕዳ እንዳይሆን ስለሚከለክለውና ስለሚረዳው፣ ኃጢአቱና ዕዳው እንዳይጨምር በግድም ቢሆን ስለሚጠቅመው ነው፡፡ “እስመ ዘሞተሰ ድኅነ እምገቢረ ኃጢአት - የሞተ ሰው ኃጢአት ከመሥራት ድኗል” በማለት እንደ ገለጸው የሞተ ሰው ቢያንስ ከዚያ በኋላ ኃጢአት ከመሥራት ነጻ ወጥቷል፡፡ ሮሜ 6፡7 እንደዚሁም በኑፋቄው ምክንያት ከቤተ ክርስቲያን አንድነት የተወገዘ (የተለየ) ሰው ሌሎችን በኑፋቄው መርዝ እየበከለ በማቁሰልና በመግደል በብዙዎች ደም ተጠያቂና ባለ ዕዳ እንዳይሆን ይረዳዋል፡፡ ሰዎችን መግደል ማለት ቁሳዊ በሆነ ነገር መምታትና የማይቀረውን ሞት ማምጣት ብቻ ሳይሆን ይልቁንም ከዚህም በላይ ሊቀር ይችል የነበረውን ሞተ ነፍስን በኑፋቄ ምክንያት ሰዎችን ከእግዚአብሔር እንዲለዩ ማድረግ እጅግ በጣም ከባድ ዕዳ ነው፡፡ ስለዚህ ተወግዞ ሲለይ ስለሚታወቅበትና ለብሶት የነበረው የበግ ለምድ ስለሚገፈፍ ምእመናን ስለሚያውቁት ይጠነቀቃሉ፣ ይርቁታል፡፡ በዚህም በኃጢአት ላይ ኃጢአት እንዳይጨምርና ዕዳው እንዳይበዛበት ይረዳዋል፡፡ 3. ለሌሎችም ትምህርት እንዲሆን በሃይማኖት ላይ የሚጨምርም ሆነ የሚቀንስ መናፍቅ በተገቢው ጊዜ ትክክለኛ የሆነ እርማት ካልተሰጠውና ዝም የሚባል ከሆነ ሌላውም እንደዚያ እያደረገ ላለመቀጠሉ ምንም ዓይነት ዋስትና አይኖርም፡፡ ስለዚህ ችግሩ በዚያ በአንዱ መናፍቅ ብቻ ተወስኖ አይቀርም፣ እርሱ ምንም ሳይባል ዝም ሲባል ያዩ ሌሎችም እንደ እርሱ ኑፋቄያቸውን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንደ ልባቸው መትከልና ማሳደግ ይጀምራሉ፡፡ የመጀመሪያው ዝም ሲባል ያዩት ሌሎቹም “እገሌ ምን ተደረገ?” እያሉ ልባቸው እየደነደነ፣ በኃጢአት ላይ ኃጢአት እየጨመሩ ይሄዳሉ፡፡ ስለዚህ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንዲህ ወዳለ የተወሳሰበ ችግር ውስጥ እንዳትገባ ከመጀመሪያው በሃይማኖት ላይ ባእድ ነገር (ኑፋቄ) የሚያመጣውን ሰው የሚመለስ ከሆነ በምክርና በቀኖና፣ አልመለስም ካለ ደግሞ በውግዘት መለየት የግድ ይሆናል፡፡ ይህም ለሌሎች መገሠጫና መጠንቀቂያም ይሆናል፡፡ እንዲህ ካልተደረገ ቤተ ክርስቲያን የመናፍቃንና የግዴለሾች መሰባሰቢያ የምትመስላቸው፣ ትዕግሥቷንና ዝምታዋን እንደ አለማወቅ ወይም ከእነርሱ ጋር እንደ መስማማት የሚቆጥሩና በክፋት ላይ ክፋት እየጨመሩ የሚሄዱ ሰነፎች ሊበዙ ይችላሉ፡፡ ከላይ ያነሳነው የሐናንያና የሰጲራ ቅጣት በዚህ አንጻርም የሚታይ ነው፡፡ በእነርሱ ላይ መንፈስ ቅዱስ ስላደረገው ቅጣት ሲናገር “ጴጥሮስም፦ የጌታን መንፈስ ትፈታተኑ ዘንድ ስለ ምን ተስማማችሁ? እነሆ፣ ባልሽን የቀበሩት ሰዎች እግር በደጅ ነው፣ አንቺንም ያወጡሻል አላት። ያን ጊዜም በእግሩ አጠገብ ወደቀች፣ ሞተችም፤ ጐበዞችም ሲገቡ ሞታ አገኟት፣ አውጥተውም በባሏ አጠገብ ቀበሯት” ይልና የዚያ ቅጣት ውጤት ምን እንደ ነበር ሲናገር “በቤተ ክርስቲያን ሁሉና ይህንም በሰሙ ሁሉ ላይ ታላቅ ፍርሃት ሆነ” ይላል፡፡ የሐዋ. 5፡9-11 የእነርሱ መቀጣት በሌሎች ዘንድ ተመሳሳይ ጥፋት እንዳይፈጽሙ ተግባራዊ ማስጠንቀቂያ ሆነ፡፡ እንኳን የመንፈሳዊ አሠራር፣ የዚህ ዓለም አሠራርም ቢሆን የሕግና የቅጣት መሠረታዊ ዓላማው ሰዎችን መጉዳት ሳይሆን ማስተማርና ማስጠንቀቅ ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ይህን በተመለከተ እንዲህ ይላል፡- “ትንሽ በሆኑ ነገሮች ላይ በጊዜው ጊዜ ተገቢውን ቁጣ አለመቆጣታችን የደረሱብንና የሚደርሱብን ጥፋቶችና ምስቅልቅሎች ምክንያት ነው፤ ጥቃቅን ስህተቶች በጊዜው ተገቢው የማስተካከያ እርምጃ ሳይደረግባቸው ስለሚታለፉ ታላላቆቹ ስህተቶች እየተንኳተቱ ይመጣሉ፡፡ ሰውነታችን ላይ ቁስል ሲወጣ ዝም ብለን ብንተወው መመረዝንና ሞትን ሊያስከትል እንደሚችለው ሁሉ በነፍስም ችላ የሚባሉ ስህተቶችና ተገቢ ያልሆኑ ነገሮች ለታላላቆቹ ክፉ ነገሮች በር ይከፍቱላቸዋል፡፡ . . . ነገር ግን ከአምላካዊ አስተምህሮ ለማፈንገጥና ትንሽ የሆነ ነገር ለመለወጥ የሚሞክሩት ሰዎች ገና ከመጀመሪያው ተገቢው ተግሣጽ ተሰጥቷቸው ቢሆን ኖሮ እንዲህ ያለው የኑፋቄ ወረርሽኝ አይወለድም ነበር፣ ቤተ ክርስቲያንንም እንዲህ ያለ ማዕበል አይይዛትም ነበር፤ በኦርቶዶክሳዊ እምነት ትንሽ የሆነ ነገር እንኳ የሚለውጥ ሰው በሁሉም ነገረ ሃይማኖት ላይ ጥፋት ያስከትላልና፡፡” (ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ፣ ትርጓሜ መልእክተ ጳውሎስ ኀበ ሰብአ ገላትያ) ለዚህ ነው ሐዋርያው “ሌሎቹ ደግሞ እንዲፈሩ፥ ኃጢአት የሚሠሩትን በሁሉ ፊት ገሥጻቸው” ያለው፡፡ 1 ጢሞ. 5፡20 ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ቅዱሳን ሊሆኑ የተጠሩ ሰዎች ጉባኤ (አንድነት) ናት እንጂ በክህደት ለመኖር፣ በኑፋቄያቸው ለመቀጠል የወሰኑ የተንኮለኞች ዋሻ አይደለችምና፡፡ ስለዚህ የቤተ ክርስቲያን የሃይማኖት አጥርና ቅጥር በኑፋቄ እንዳይፈርስና የመዳን ምሥጢር እንዲጠበቅ ለማድረግ ሲባል ባእድ ነገር ይዘን ካልገባን ሞተን እንገኛለን የሚሉትን ማራቅና መጠበቅ የግድ ይላል፡፡ እንድ ሰው “በራሱ ማንነትና መሠረታዊ ምንነት ዙሪያ ድንበርና ወሰን የማያበጅና እነዚያን ያበጃቸውን ድንበሮችም የማይጠብቅ ማንኛውም ቡድን ማንነቱንና ህልውናውን ለረጂም ጊዜ ጠብቆ መዝለቅና መኖር አይችልም” ያለው ለዚህ ነው፡፡ ከዚህም ጋር ቅድስት ቤተ ክርስቲያን መናፍቃንን የምታወግዘው በነገረ ሃይማኖት በሳል እውቀት ለሌላቸው ልጆቿ ለማስጠንቀቅ፣ “እንዲህ የሚለው . . . ኑፋቄ ነው፣ የእኔ እምነትና ትምህርት አይደለምና ተጠንቀቁ” ለማለት ነው፡፡ የኑፋቄውን ምንነት ለመግለጥ፣ ከቤተ ክርስቲያን ትምህርት የተለየ መሆኑን በይፋ ለመግለጥና ለማሳወቅ ነው፡፡ አንድ የነገረ ሃይማኖት ምሁር “ኑፋቄዎችና መናፍቃን ሊወገዙ የሚገባበት ምክንያት በውስጡ እውነት የሚመስሉ ነገሮች ስላሉትና የዋሃን ክርስቲያኖችን ወደ ስህተት ሊመራ የሚችል ስለሆነ ነው” ብሏል፡፡ ጠርጠሉስ የተባለው ሊቅም “መናፍቃን ደካማዎች የሆኑትን ያሳስታሉ፣ ታናናሾችን ያናውጻሉ፣ የተማሩትን ደግሞ ያታክታሉ፣ ያጭበረብራሉ” ብሏል፡፡ የታላቁ የቅዱስ ቄርሎስ መንፈሳዊ አባትና መካሪው የነበረው የፔሉዚየሙ ቅዱስ ኤስድሮስም ስለ መናፍቃን እንዲህ ይላል፡- “ዓሣ አጥማጆች መንጠቆውን ዓሣዎችን በሚስብ ነገር እንደሚሸፍኑትና ከዚህም የተነሣ ዓሣዎቹን እንደሚይዟቸው፣ መናፍቃንም ከተንኮላቸው የተነሣ ክፉ ትምህርታቸውንና የተበላሸ አረዳዳቸውን በመንፈሳዊነትና በአስመሳይነት በመሸፈን ሞኞችንና የማያስተውሉትን በማጥመድ ወደ መንፈሳዊ ሞት ይወስዷቸዋል፡፡” ስለዚህም ምእመናን ልጆቿ አስመሳዮች በሆኑ መናፍቃን እንዳይታለሉባት ለመጠበቅ መናፍቃን የሆኑትን ትለያቸዋለች፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ጢሞቴዎስን በመልክእቱ እንዲህ ሲል በጽኑ ያሳሰበው ለዚህ ነው፡- “ወደ መቄዶንያ በሄድሁ ጊዜ፣ አንዳንዶች ልዩ ትምህርትን እንዳያስተምሩና ወደ ተረት መጨረሻም ወደሌለው ወደ ትውልዶች ታሪክ እንዳያደምጡ ልታዝዛቸው በኤፌሶን ትቀመጥ ዘንድ ለመንሁህ” 1 ጢሞ. 1፡3-4፡፡ 4. በሰማይ (ኋላ) ላለው (ለሚገለጠው) የኃጥአን ከጻድቃን መለየት ማሳያ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የእግዚአብሔር መንግሥት ወካይና መገለጫ ናት፡፡ ስለዚህ በሰማያዊቷ ኢየሩሳሌም፣ በእግዚአብሔር መንግሥት ተቀላቅሎና ተመሳስሎ መግባት እንደ ሌለ ሁሉ በዚህ ዓለም ያለችው ቤተ ክርስቲያንም የዚያ ወካይና መገለጫ እንደ መሆኗ የእርሷ ወገኖች ያልሆኑትን ትለያቸዋለች፡፡ እግዚአብሔር ስለሚያደርው መለየት በተለያዩ ምሳሌዎችና ሁኔታዎች ተገልጾአል፡፡ ለአብነትም፡- “አሕዛብም ሁሉ በፊቱ ይሰበሰባሉ፤ እረኛም በጎቹን ከፍየሎች እንደሚለይ እርስ በርሳቸው ይለያቸዋል፣ በጎችን በቀኙ ፍየሎችንም በግራው ያቆማቸዋል” ይላል፡፡ ማቴ. 25፡32-33 “መንሹም በእጁ ነው፣ አውድማውንም ፈጽሞ ያጠራል፣ ስንዴውንም በጎተራው ይከታል፣ ገለባውን ግን በማይጠፋ እሳት ያቃጥለዋል።” ማቴ. 3፡12 “የዚያን ጊዜም ከቶ አላወቅኋችሁም፤ እናንተ ዓመፀኞች፥ ከእኔ ራቁ ብዬ እመሰክርባቸዋለሁ። ማቴ. 7፡23 “ንጉሡም የተቀመጡትን ለማየት በገባ ጊዜ በዚያ የሰርግ ልብስ ያለበሰ አንድ ሰው አየና፡- ወዳጄ ሆይ፥ የሰርግ ልብስ ሳትለብስ እንዴት ወደዚህ ገባህ? አለው እርሱም ዝም አለ። በዚያን ጊዜ ንጉሡ አገልጋዮቹን እጁንና እግሩን አስራችሁ በውጭ ወዳለው ጨለማ አውጡት፤ በዚያ ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ይሆናል አለ” ማቴ. 22፡11-13፡፡ በተጨማሪም በአንድ ማሳ ላይ በነበሩት በእንክርዳዱና በስንዴው መለየት መስሎም አስተምሯል፡፡ ስለሆነም ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በየጊዜው ጉባኤያትን እያደረገች መናፍቃንን የምታወግዘው ለዚህ ነው፡፡ 5. የሰጠችውን ሀብት ለመንሣት መናፍቃን የሆኑትን ቀድሞ ስትቀበላቸውና ልጆቿ ስታደርጋቸው፣ ከዚያም ባለፈ በአገልግሎት ስታሰማራቸውና ዲያቆናት ካህናት አድርጋቸው ከነበረ በዚያ ጊዜ የሰጠቻቸውን ስጦታና የፈጸመችውን ለማጠፍና ከዚያ በኋላ ልጆቿ አለመሆናቸውንና እነርሱ የሚያደርጉት ማንኛውም ነገራቸው እርሷን እንደማይመለከታት በዐዋጅ ለማሳወቅ ነው፡፡ በዚህም ሰጥታቸው የነበረውን መብትና ጸጋ ሁሉ በአደባባይ ታነሳለች፡፡ ይህ በዚህ ዓለም ባሉ እንደ ወታደራዊ ባሉ ተቋማትም ይፈጸማል፡፡ አንድ የጦር ሠራዊት አባል ወይም ባለ ሥልጣን ከተሰጠው አደራና ኃላፊነት ጋር የማይሄድ፣ አገርንና ሕዝብ የሚጎዳ ድርጊት ከፈጸመ በይፋ መዓርጉና ክብሩ ይገፈፋል፡፡ ፮. መናፍቃን ከቤተ ክርስቲያን የሚለዩት መቼ ነው? አንድ ምእመን በቤተ ክርስቲያን የሚኖረው በእውነትና በሃይማኖት እስካለ ድረስ ብቻ ነው፡፡ ያን እምነትና እውነት ሲክድና ሌላ ባእድ ነገር ውስጥ ሲገባ ግን ያን ጊዜውኑ ከቤተ ክርስቲያን ራሱን በራሱ ያወጣል፤ በራሱ ድርጊት ራሱን ከድኅነት ውጭ ያደርጋል፡፡ ሐዋርያው “ቤቱም የእውነት ዓምድና መሠረት ነው” ያለው ለዚህ ነው፡፡ ያን የእውነት ዓምድ የማይይዝ ሰው በራሱ ይለያል፡፡ ባለቤቱ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “በልጁ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፤ በልጁ የማያምን ግን የእግዚአብሔር ቍጣ በእርሱ ላይ ይኖራል እንጂ ሕይወትን አያይም” ብሎ ያስተማረን ይኸው ነው፡፡ ዮሐ. 3፡36 ያላመነ ሰው ያን ጊዜውኑ የራሱ አለማመን ፈርዶበታል፡፡ እንዲሁም “መለያየትን የሚያነሣ ሰው ጠማማ እንዲሆን በራሱም ላይ ፈርዶ ኃጢአትን እንዲያደርግ አውቀህ፥ አንድ ጊዜ ሁለት ጊዜም ከገሠጽኸው በኋላ እንዲህ ከሚመስል ሰው ራቅ” ሲል ይህን ያመለክታል፡፡ ቲቶ 3፡10-11 ኑፋቄን (መለያየትን) የሚያነሣ ሰው በራሱ ላይ የፈረደው ያን ጊዜ ነው፡፡ አዳም ከእግዚአብሔር የተለየውና ራቁቱን የሆነው ከገነት እንዲወጣ በተፈረደበት ጊዜ ሳይሆን ከዚያ አስቀድሞ በእግዚአብሔር ላይ የነበረውን ንጹሕ እምነት በዲያብሎስ ስብከት በለወጠና ባበላሸ ጊዜ ነበር፡፡ ለዚህ ነበር እግዚአብሔር ወደ እነርሱ ከመምጣቱ በፊት አስቀድሞ ራቁታቸውን እንደሆኑ በማወቃቸው የበለስ ቅጠል ሰፍተው ያገለደሙት፡፡ ስለሆነም ማንም ሰው ከቤተ ክርስቲያን የሚለየውን ነገር የሚያደርገው ራሱ ነው፡፡ ራሱን ከእግዚአብሔርና ከቤተ ክርስቲያን ያልለየን ሰው ማንም ሊለየው አይችልም፡፡ ራሱን የለየን ሰው ደግሞ የቤተ ክርስቲያን ውሳኔ ሰጪ አካላት በተለያዩ ምክንያቶች (መናፍቅነቱን ባለማወቅ፣ ወይም ሰውዬው ኑፋቄውን ሰውሮ እያጭበረበረ በመኖሩ፣ ወይም በሌሎች ሰብአዊ ምክንያቶች) ከቤተ ክርስቲያን በውግዘት ሳይለይ ቢቀር እንኳ እርሱ አስቀድሞ ራሱን የለየ ስለሆነ ከሰዎች ፍርድ ማምለጡ ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከመለየት አያድነውም፡፡ እንዲህ በማድረግ ከሰዎች ፍርድ ማምለጥ ለሰማያዊ ሕይወቱ አንድም የሚጠቅመው ነገር የለም፣ ይልቁንም ከላይ እንዳየነው ይጎዳዋል እንጂ፡፡ በመሆኑም በዚህ ዓለም ያለችው ቤተ ክርስቲያን አውግዛ የምትለየው ቀድሞውንም ራሱን በኑፋቄው የለየውን ሰው ነው፡፡ እንደ አንድ ማሳያ የተፍጻሜተ ሰማዕት ቅዱስ ጴጥሮስን እና የአርዮስን ሁኔታ በአጭሩ ማስታወስ እንችላለን፡፡ ፲፯ኛው የእስክንድርያ ፓትርያርክ የነበረው ተፍጻሜተ ሰማዕት ቅዱስ ጴጥሮስ በሰማዕትነት ከማረፉ በፊት (ያረፈው በ፫፻፲፩ ዓ. ም. ነው) ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተቀደደ ልብስ ለብሶ በራእይ ታየው፡፡ ያን ጊዜ ተፍጻሜተ ሰማዕት ቅዱስ ጴጥሮስ “አንተ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ አይደለህምን? ልብስህን ማን ቀደደው? አለው፡፡ ጌታችንም “አርዮስ ሰጠጣ ለልብስየ ወፈለጠኒ አምአቡየ ወእምእመናን ዘአጥረይክዎሙ በደምየ - አርዮስ ከባሕርይ አባቴ ከአብ ለየኝ፣ በደሜ ከቤዠኋቸው ከምእመናንም ለየኝ” አለው፡፡ ከዚያም ጌታችን ተፍጻሜተ ሰማዕት ቅዱስ ጴጥሮስን አርዮስ የማይመለስ መናፍቅ ስለሆነ ወደ ቤተ ክርስቲያን እንዳይቀበለውና አውግዞ እንዲለየው ነገረው፡፡ እንግዲህ አርዮስ ከእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን ራሱ ባመነጨው ኑፋቄው የተለየው ከዚያ አስቀድሞ ነበር ማለት ነው፡፡ ይህም ከቅዱስ ጴጥሮስ ዕረፍት በፊት ማለት ነው፡፡ ሆኖም አርዮስ በጉባኤ የተወገዘው ግን ከተፍጻሜተ ሰማዕት ከቅዱስ ጴጥሮስ ዕረፍት ከአሥር ዓመት በኋላ በእስክድርያው ፓትርያርክ በቅዱስ እለእስክንድሮስ ሰብሳቢነት በ፫፻፳፩ ዓ. ም. በእስክንድርያ በተካሄደ ጉባኤ ነበር፡፡ ሆኖም ምንም እንኳ አርዮስ በጉባኤ ሳይወገዝ ከአሥር ዓመት በላይ ቢቆይም እርሱ ግን ራሱን ከቤተ ክርስቲያን ከለየና የወይን ግንድ ከሆነው ከጌታ ራሱን ቆርጦ ከጣለ ቆይቷል፡፡ ስለዚህ በእምነት ያፈነገጠና የወጣ ሰው በጉባኤ ቢወገዝም ባይወገዝም ራሱን በራሱ የቆረጠና የለየ፣ በራሱ የተወገዘ ነው፡፡ ልዩነቱ እንደ ታወቀበትና ያልታወቀበት ሌባ ወይም ወንጀለኛ ነው፡፡ ወንጀልን የፈጸመ ሰው ፖሊስ ቢይዘውም ባይይዘውም፣ ፍርድ ቤት ቢፈርድበትም ባይፈርድበትም ወንጀለኛነቱ አይለወጥም፡፡ ሆኖም ሲያዝና ሰፈረድበት ለራሱም ለኅብረተሰቡም ጠቀሜታው የጎላ ነው፤ ከዚያ ባለፈ የሰውዬውን ጥፈተኛነት ግን አይለውጠውም፡፡ ፯. መናፍቃን የሚወገዙት እንዴት ነው? የመናፍቃን አወጋገዝ ሂደት እንደ ኑፋቄው ዓይነት ነው፡፡ የኑፋቄው ዓይነት ምንድን ነው? የሚለውን ማጤን ይገባል፡፡ ይህም:- የታወቀ ኑፋቄ፣ እና እንግዳ ዓይነት ኑፋቄ የታወቀ ኑፋቄ - ስንል ሀ. ከመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርትና ከቤተ ክርስቲያን ትውፊት ጋር ተቃርኖው ግልጽና የማያሻማ የሆነ ኑፋቄ፣ እና ለ. ከዚያ በፊት በአካባቢያዊም ሆነ በዓለም አቀፋዊ ጉባኤ የተወገዘ ኑፋቄ ማለታችን ነው፡፡ እንዲህ ያለ ኑፋቄ ይዞ ለሚነሣ ሰው አዲስ ነገረ ሃይማኖታዊ ውይይትና ውሳኔ አያስፈልገውም፡፡ የአርዮስን ኑፋቄ ይዞ ለሚነሣ ግለሰብም ሆነ ቡድን የኒቅያ ጉባኤ በየጊዜው ሲሰበሰብ አይኖርም፤ የንስጥሮስን ኑፋቄ ይዞ ለሚነሣም እንዲሁ የኤፌሶን ጉባኤ በየጊዜው አይሰበሰብም፡፡ በቀደመው ውግዘት እስከ ዕለተ ምጽአት የሚነሡት ሁሉ ተወግዘዋል፡፡ ከቤተ ክርስቲያን ትምህርት ግልጽ ተቃርኖ የያዘ ኑፋቄ ሁሉ በአጠቃላይ የተወገዘ ነው፡፡ ለእንዲህ ዓይነቱ ኑፋቄ የሚያስፈልገው አንድ ነገር ብቻ ነው፤ እርሱም ያን ኑፋቄ የሚያራምደው ግለሰብ በትክክል ያን ኑፋቄ መያዝ አለመያዙን፣ የሚመለስ መሆን አለመሆኑን ማረጋገጥ ብቻ ነው፡፡ ከተረጋገጠ በኋላ ያ ሰው ከቤተ ክርስቲያን መለየቱ (ማውገዙ) በአጥቢያ ሰበካ ጉባኤ ወይም በአገረ ስብከት ደረጃ ሊፈጸም ይችላል፡፡ እንግዳ ዓይነት ኑፋቄ ሲባል ደግሞ በግልጽ ስህተቱ ይህ ነው ለማለት ቀላል ያልሆነና ጉዳዩን ከቤተ ክርስቲያን እምነት አንጻር በጥንቃቄ መመዘን የሚያስፈልገው ማለት ነው፡፡ እንዲህ ሲሆን የኑፋቄውን ምንነት፣ ነገረ ሃይማኖታዊ አንድምታውን፣ ጥልቀቱንና ስፋቱን በጥንቃቄ መመርመር ያስፈልጋል፡፡ ይህን የሚያደርጉትም በሳል የሆነ ነገረ ሃይማኖታዊ እውቀት ያላቸው ሊቃውንት መሆን ይኖርባቸዋል፡፡ የመጨረሻ ውሳኔውን የሚሰጠው የቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ነው፡፡ ፰. መናፍቃን እንዴት ይመለሱ? ከቤተ ክርስቲያን በኑፋቄ ተወግዘው (ይፋዊ በሆነ ውግዘትም ሆነ ራሳቸውን በኑፋቄ በመለየታቸው) የተለዩ ሰዎች እንዲመለሱ የቤተ ክርስቲያን ናፍቆቷና ምኞቷ ነው፡፡ እንዲወገዙ የሚደረገውም ከላይ እንዳየነው ለራሳቸው ለሰዎቹ ጥቅም ሲባል፣ ነፍሳቸው በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ቀን እንድትድን ለመርዳት ሲባል እንጂ እንዲጠፉ አይደለም፡፡ ስለሆነም የመመለሳቸው ዜና ታላቅ የምሥራች ነው፣ ከዚህ የበለጠ ደስታም የለም፡፡ ጌታችን በትምህርቱ የጠፋው ልጅ ሲመለስ ስለሆነው ነገር ሲናገር እንዲህ አለ፡- “አባቱ ለአገልጋዮቹ ፈጥናችሁ ከሁሉ የተሻለ ልብስ አምጡና አልብሱት፣ ለእጁ ቀለበት ለእግሩም ጫማ ስጡ፤ የሰባውን ፊሪዳ አምጥታችሁ እረዱት፥ እንብላም ደስም ይበለን፤ ይህ ልጄ ሞቶ ነበርና ደግሞም ሕያው ሆኖአል፤ ጠፍቶም ነበር ተገኝቶአልም። ደስም ይላቸው ጀመር፡፡” ሉቃ. 15፡22-24 ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድ የጠፋ ልጇ ሲመጣ እንዲህ ደስ ይላታል፡፡ ቅዱሳን መላእክትም በሰማይ ንስሐ ስለሚገባ አንድ ኃጥእ ደስ ይሰኛሉ፡፡ ይህ እንዳለ ሆኖ፣ በሌላ በኩል ደግሞ ሊደረጉ የሚገባቸው ጥንቃቄዎችና ተግባሮችም አሉ፡፡ ይህም ቤተ ክርስቲያንን ከመጠበቅ አንጻር አስፈላጊ በመሆኑ ነው፡፡ መናፍቃን የነበሩ ሰዎች ወደ ቤተ ክርስቲያን እንመለሳለን ሲሉ ሊደረጉ የሚገባቸው ዋና ዋና ጥንቃቄዎችና ተግባራት የሚከተሉት ናቸው፡- 1. መመለሳቸው (ተመልሰናል ማለታቸው) የእውነት ነው? ከልብ ነው? ወይስ ለስልትና ለዘዴ ነው? ቤተ ክርስቲያን እስካሁን በተጓዘችባቸው ዘመናት ሁለቱም ዓይነት ሰዎች በየጊዜው ሲገጥሟት ነበር፤ እነዚህም በአንድ በኩል በእውነት ተጸጽተው የሚመለሱ ሲሆኑ በሌላ በኩል ደግሞ ከልባቸው ሳይመለሱ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ተመልሰው በመግባት ብዙ ምእመናንን ለመበረዝና ለማታለል ያመቻቸው ዘንድ በተንኮል ተመልሰናልና ተቀበሉን የሚሉ ናቸው፡፡ ስለዚህ ተመልሰናል ስላሉ ብቻ ዝም ብሎ መቀበል የዋህነት ሳይሆን ጅልነት ስለሆነ በሚገባ ማጣራትና መጠንቀቅ በእጅጉ አስፈላጊ ነው፡፡ በኒቅያ ጉባኤ በቅዱሳን አባቶች ተወግዞ የተለየው አርዮስና የኑፋቄ ጓደኞቹ የተለያዩ ሰዎችን በመላክና በውስጥ ለውስጥ በሠሩት የፕሮፓጋንዳ ሥራ በመጨረሻ ላይ ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ አርዮስን ከፈረደበት ከግዞቱ እንዲወጣና ወደ ቤተ መንግሥቱ እንዲመጣ አደረገው፡፡ ንጉሥ ቆስጠንጢኖስም እምነቱን በጽሑፍ እንዲያቀርብ አዘዘው፡፡ አርዮስም በፊት የፈጠራቸውን የኑፋቄ ቃላትና ሐረጎች ሁሉ፣ እንዲሁም የተወገዘባቸውን የክህደት አንቀጾች ሁሉ ለጊዜው ወደ ጎን ትቶ ከመጽሐፍ ቅዱስ በቀጥታ ያሉና ማንም ሰው ሊቀበላቸው የሚችላቸውን ነገሮች ብቻ ጽፎ “በፊትም ቢሆን ከዚህ የተለየ ሃሳብም ሆነ እምነት አልነበረኝ፣ አሁንም የማምነው ይህን ነው” በማለት ፈርሞ፣ በመሐላ አጽንቶ ሰጠው፡፡ ያ አርዮስ ጽፎ የሰጠው አንቀጸ እምነት እነርሱ (አርዮሳውያን) በፈለጉት መንገድ ሊተረጉሙትና የያዙትን አርዮሳዊ እብደት በቀላሉ በማያጋልጥ መልኩ በፈሊጥ ተሸፍኖ የቀረበ ማታለያ ነበር፡፡ ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ ግን እንዲያ ሲያደርግ ሲያየው አርዮስ በእውነት የተመለሰና ኦርቶዶክሳዊ የሆነ መሰለው፡፡ ይህን አጋጣሚ በመጠቀም አርዮሳውያን የነበሩ ጳጳሳት አርዮስ በይፋ መጀመሪያ በተወገዘበት በእስክንድርያ ወደ ቤተ ክርስቲያን እንዲገባና ከምሥጢራት እንዲካፈል የሚል ደብዳቤ ንጉሡ እንዲጽፍላቸው አደረጉና ያን ደብዳቤ ከዛቻና ከማስፈራሪያ ጋር ወደ ቅዱስ አትናቴዎስ ወደ እስክንድርያ እንዲላክ አደረጉ፡፡ ለየአብያተ ክርስቲያናቱም አርዮስና ጓደኞቹ ኦርቶዶክሳውያን መሆናቸውን ንጉሡ ቆስጠንጢኖስ የመሰከረላቸው ስለሆነ፣ በሲኖዶስም የተወሰነ በመሆኑ ወደ ቤተ ክርስቲያን አንድነትና ወደ ሱታፌ ምሥጢራት ይቀበሏቸው ዘንድ በጥብቅ የሚያሳስብ ደብዳቤ በፍጥነት ላኩ፡፡ የአርዮስ ቀኝ እጅ የነበረው አውሳብዮስ ዘኒቆምድያ ንጉሥ ቆስጠንጢኖስ በደብዳቤው ላይ ቅዱስ አትናቴዎስን “ወደ ቤተ ክርስቲያን ሊመለሱ የሚፈልጉትን ሁሉ የማትቀበል ከሆነ እኔ ራሴ ሰው ልኬ ከመንበርህ አወርድሃለሁ” የሚል ዛቻ እንዲላክበት አደረገ፡፡ ብዙ ጊዜ ከታሪክ ስናይ መናፍቃን የፖለቲካ ሰዎችንና ባለ ሥልጣናትን በመዘወርና ከጎናቸው በማሰለፍ በኩል ጠንካሮችና የተሳካላቸው ናቸው፡፡ ቅዱስ አትናቴዎስ ግን “የክርስቶስ ጠላት የሆነው አርዮስና ኑፋቄው ከኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ጋር ምንም ኅብረት የላቸውም” በማለት በጉባኤ የተወገዘውን አርዮስን በንጉሥ ቀላጤ አልቀበልም አለ፡፡ የቅዱስ አትናቴዎስ ስለ ኦርቶዶክሳዊት ሃይማኖት ከአርዮሳዊ ክህደት አቀንቃኞችና ደጋፊዎች ጋር የገባው እልህ አስጨራሽ ትግል በዚህ ሁኔታ እየጠነከረ ሄደ፡፡ ከመንበሩ ስድስት ጊዜ እንዲሳደድና ከአርባ አምስት ዓመት ዘመነ ፕትርክናው አሥራ ሰባት ዓመቱን ያህል በስደትና በእንግልት እንዲያሳልፍ ያደረገው ይህ የአርዮሳውያን ተንኮልና ዘመቻ ነበር፡፡ በአጠቃላይ አርዮሳውያን ያን ንጉሡ ከግዞት መመለሱን እንደ መልካም ካርድ በመጠቀም ከዚያ ቀጥሎ በነበሩት ሃምሳ ዓመታት ያህል ቤተ ክርስቲያንን በእጅጉ ሲያውኳትና ሲፈትኗት ኖረዋል፡፡ ነገሥታትን ሳይቀር ከጎናቸው እያሰለፉ ኦርቶዶክሳውያን ጳጳሳትንና ካህናትን ከየመናብርታቸውና አብያተ መቃድሳቸው እያሳደዱ እነርሱ ሲፈነጩባቸው ኖረዋል፡፡ ነገሩ የማታ የማታ እውነት ይረታ ሆነ እንጂ፡፡ ስለዚህ ዛሬም እንመለሳን የሚሉት ሰዎች በትክክል ከልባቸው ነው? ወይስ እንደ ግብር አባቶቻቸው እንደ አርዮሳውያን ውስጥ ገብተው ለመበጥበጥ ነው? የሚለውን በሚገባ ማጤን ያስፈልጋል፡፡ “ታሪክ የሚያስተምረው ሰዎች ከታሪክ አለመማራቸውን ነው” የተባለው እንዳይደርስብን ማሰብ ይገባል፡፡ “በሬ ሆይ፣ ሣሩን አየህ እንጂ ገደሉን ሳታይ” እንደ ተባለውም እንዳይሆን እያንዳንዱ ምእመን፣ እስከ ቅዱስ ሲኖዶስ ድረስ ሊያስቡበትና ተገቢውን ነገር ሊያደርጉበት የሚገባ ጉዳይ ነው፡፡ 2. ጉዳዮችን በቡድን ወይም በጅምላ ሳይሆን በእያንዳንዱ ሰው ደረጃ መመልከትና መለየት፣ እንመለሳለን የሚሉትን ወገኖቻችንን ጉዳያቸውን በእያንዳንዳቸው ማየትና ማጥናት ይገባል እንጂ በጅምላ ከዚህ ወዲያ ወይም ከዚያ መለስ ብሎ ማድረግ አይገባም፡፡ እግዚአብሔር የሚፈርደው በእያንዳንዱ ሰው እንጂ በቡድን ወይም በጅምላ አይደለም፤ “እስመ አንተ ትፈድዮ ለኩሉ በከመ ምግባሩ - አንተ ለእያንዳንዱ እንደ ሥራው ታስረክበዋለህና” እንደ ተባለ፡፡ መዝ. 61፡ እንዲሁም “እንግዲያስ እያንዳንዳችን ስለ ራሳችን ለእግዚአብሔር መልስ እንሰጣለን” ተብሏልና። ሮሜ 14፡12 ስለሆነም እያንዳንዱን በየግለሰቡ ጥፋቱ ምን አንደ ነበር፣ ለምን እመለሳለሁ እንዳለ፣ ወዘተ በዝርዝር ማጥናትና መወሰን ይገባል እንጂ “እነ እገሌ” በሚል የጅምላ ንስሐ የለምና ይህን ማስታወሱም ተገቢ ነው፡፡ 3. ከቤተ ክርስቲያን እንዲወጡ (እንዲያፈነግጡ) ያደረጓቸውን ምክንያቶች በሙሉ እንዲዘረዝሩ ማድረግና መመዝገብ፣ አንድ ሰው ዳነ ሲባል ታምሞ የነበረ መሆኑ፣ ተመለሰ ሲባል ደግሞ ወጥቶ ወደ ሌላ ሄዶ የነበረ መሆኑን ያጠይቃልና እንመለሳለን የሚሉት ሰዎች እያንዳንዳቸው ቀድሞ እንዲወጡ ያደረጋቸው ምክንያት ምን እንደ ነበረ በግልጽ መታወቅ ይኖርበታል፡፡ አለበለዚያ በሽታውን ደብቆ እንዲሁ አክሙኝ እንደሚል ሰው መምሰል ይሆናል፡፡ ይህን ማድረግ ግን እንመለሳለን ለሚሉት ሰዎችም፣ ለማኅበረ ምእመናኑም ጠቃሚና አስፈላጊ ነው፡፡ ያን ኑፋቄ እንደገና ሲያስተምሩ ቢገኙ ማንነታቸውን በግልጽ ለመለየት ይጠቅማል፤ አለበለዚያ “ሞኝን እባብ ሁለት ጊዜ ነከሰው” (መጀመሪያ ሲያይ፣ ሁለተኛ ደግሞ ሲያሳይ) እንደ ተባለው ይሆናል፡፡ 4. መመለሳቸውን፣ እንዲሁም ከምን ዓይነት ስህተት እንደ ተመለሱ ለሕዝቡ በይፋ መነገር ይኖርበታል፡፡ መናፍቃን ሲመለሱ በጓዳና ለሌሎች በማይታወቅ ሁኔታ ሳይሆን በግልጽ፣ ምእመናን ሁሉ በሚሰሙበትና በሚያውቁበት መድረክ በይፋ መሆን አለበት፡፡ በፊት የካዱትና ቤተ ክርስቲያንን ያሳጡትና የነቀፉት በይፋ እንደ ነበር ሁሉ ሲመለሱም በይፋ መሆን ይኖርበታል፡፡ ቅዱስ ባስልዮስ ስለ መናፍቃን አመላለስ በጻፈው ቀኖና ላይ እንዲህ ይላል፡- “በማንኛውም መንገድ ቢሆን ከኑፋቄ ወደ ቤተ ክርስቲያን የሚመለሱ ሰዎች ምእመናን ባሉበት መሆን አለበት፤ ወደ ምሥጢራት ሊቀርቡ የሚገባቸውም እንዲህ ባለ ይፋዊ ሁኔታ ካለፉ በኋላ ብቻ ነው፡፡” ቀኖና ዘቅዱስ ባስልዮስ፣ ቁ. 1 እንዲህ ካልሆነ ብዙ ችግር ያስከትላል፡፡ እንዲህ ማድረግ ለአጭበርባሪዎችና ለተንኮለኞች መጠቀሚያ ሰፊ በር ይከፍታል፡፡ ነገ ተመልሰው ያንኑ ዓይነት ችግር እንዳይፈጥሩ በይፋ መነገሩ በእጅጉ ይጠቅማል፡፡ አለበለዚያ ውስጥ ውስጡን ምእመናንን እየበከሉ ላለመቀጠላቸው ዋስትና አይኖርም፡፡ መመለሳቸው በይፋ ከተደረገ ግን የቀድሞ ኑፋቄያቸውን እናስተምራለን ቢሉ እንኳ “ተመልሰናል ብላችሁ አልነበረምን? የቀድሞ ስህተታችንን ትተናል ብላችሁ አልነበረምን?” ብሎ ለመጠየቅና በቶሎ ማንነታቸውን ለማወቅ ይረዳል፡፡ 5. ከጥንት ጀምሮ የተነሡ የተለያዩ የኑፋቄ መሪዎችንና ዋና ዋና መናፍቃንን በጥንቃቄ ከተዘረዘሩ በኋላ ማውገዝ ይገባቸዋል፣ የሚመለሱ መናፍቃን በእውነት ከመናፍቃን የተለዩና ከቅድስት ቤተ ክርስቲያን ጋር የተዋሐዱ ስለ መሆናቸው አንዱ ምስክር የሚሆነው ከቀድሞ ጀምሮ የተነሡ ዋና ዋና የኑፋቄ አመንጪዎችን በይፋ ማውገዝ ነው፡፡ ስለሆነም በጥንቃቄ በተዘጋጀ የመናፍቃን ዝርዝር ላይ እነዚያን መናፍቃን ማውገዝና ለዚህም መፈረም ይኖርባቸዋል፡፡ 6. እስከ ዛሬ ድረስ በስብከቶቻቸውና በመጻሕፍት ያስተማሯቸውንና የጻፏቸውን የኑፋቄ ትምህርቶች ሁሉ ቀድሞ ኑፋቄው ከተላለፈበት ልሳን ጋር ተመጣጣኝ በሆነ መንገድ እንዲያወግዙና ስህተት መፈጸማቸውን ተቀብለው ከአሁን በኋላ እንደዚያ ዓይነት የስህተት ትምህርት እንደማያስተምሩ በጽሑፍ ቃል መግባት ይኖርባቸዋል፡፡ የስህተት ትምህርቱን በመጽሐፍ ወይም በቪሲዲ ወይም በካሴት እና በመሳሰለው ያስተላለፈ ሰው ስህተቱን ሲያምንና ወደ እውነት ሲመለስ የቀደመውን አስተምህሮውን ስህተትነት መግለጽ የሚገባው በዚያው የስህተት ትምህርቱን ባስተላለፈበት መንገድ (ልሳን - ሚዲያ) ነው፡፡ አለበለዚያ ተደራሽነቱ ተመጣጣኝ አይሆንም፡፡ የስህተት ትምህርቱን በመጽሐፍ የጻፈ ሰው በቃሉ “አጥፍቼ ነበር፣ አሁን ተመልሻለሁ” ቢል መመለሱንና የቀድሞውን አስተምህሮውን ስህተትነት ማመኑን የሰሙት በተናገረበት ጊዜና ቦታ የሚገኙት ሰዎች ብቻ ናቸው፤ ሌሎቹ ግን በመጻሕፍት የተጻፈውን ኑፋቄውን እንጂ በቃል የተናገረውን የሚያውቁበት መንገድ የለም፡፡ እንዲሁም በቃሉ ብቻ “ያ ቀድሞ ያልሁት ስህተት ነው” ብሎ ቢናገር ያ ነገር ከአንድ ትውልድ ያለፈ ሊታወስና አስተማማኝ በሆነ ሁኔታ ሊጠቀስ አይቻልም፣ መጽሐፉ ግን ለዘመናት ትውልድን እየተሻገረ ሊጠቀስ የሚችል ነው፡፡ ስለሆነም በእነዚህና በሌሎችም ምክንያቶች አንድ ወደ ቤተ ክርስቲያን የሚመለስ ሰው ቀድሞ የስህተት ትምህርቱን ካስተማረበት የሚዲያ ዓይነትና ተደራሽነት ጋር ተመጣጣኝ በሆነ መንገድ መግለጽ ይኖርበታል፡፡ አለበለዚያ ቀድሞ በቤተ ክርስቲያን ላይ ለብዙዎች መሰናከያ አድርጎ ያስተማረው እንክርዳድ መበከሉን እየቀጠለና ትውልድ እየተሻገረ ስለሚሄድ ስለ አንዱ ሰው መመለስ እንደምንጨነቀው ሁሉ ይህ ሰው በኑፋቄ ትምህርቱ ስላጠፋቸው ስለ ብዙዎቹም ማሰብ የግድ ይላል፡፡ አለበለዚያ ያ ሰው ያጠፋቸውን የብዙዎቹን ሰዎች ነፍሳት ረስተን ለአንዱ ብቻ የተጨነቅን መስሎን የምናደርገው ነገር ውስጡ ወይ አለመረዳት ወይም ደግሞ ሌላ ነገር እንዳይሆን ማሰብ ይገባል፡፡ 7. በእርሱ የኑፋቄ ትምህርት ምክንያት ከቤተ ክርስቲያን የወጡትን ወደ ቤተ ክርስቲያን መመለስ ይኖርበታል፡፡ ኑፋቄውን በማስተማሩ ምክንያት ለብዙዎች ከቤተ ክርስቲያን መውጣት ምክንያት የሆነና በነፍሳቸው እንዲሞቱ ያደረገ ሰው ሲመለስ በመጀመሪያ እነዚያ ያጠፋቸውን ወደ ቤተ ክርስቲያን መመለስ ይኖርበታል፡፡ መርቅያን የተባለው መናፍቅ ብዙ ሰዎችን ካጠፋና የራሱን አንጃ መሥርቶ ከኖረ በኋላ በሕይወቱ መጨረሻ አካባቢ በኑፋቄው ተጸጽቶ ወደ ቤተ ክርስቲያን ልመለስ ብሎ ጠይቆ ነበር፡፡ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ከሁሉም አስቀድሞ በመጀመሪያ ማድረግ እንዳለበት የነገሩት ነገር ቢኖር ወደ ስህተት የመራቸውን ሁሉ ወደ ቤተ ክርስቲያን እንዲመልስ ነበር፡፡ ያን ለማድረግ በመሯሯጥ ላይ እያለ ታመመና ሞተ፡፡ ይህ በየዘመናቱ እንመለስ ሲሉ በነበሩ ሰዎች ላይ ሲፈጸም የኖረ ቀኖና ነው፡፡ ሽዎችን አጥፍቶ አንድ እርሱ ብቻ ቢመለስ እግዚአብሔር ስለ ጠፉት ስለ ብዙዎቹ ግድ የለውምን? እንዲህ የሚያደርጉትንስ ዝም ብሎ ይመለከታቸዋልን? ስለዚህ ይህን ጉዳይ መዘንጋት አይገባም፣ ለመጥፋታቸው ምክንያት የሆኗቸውን ሰዎች (በእነርሱ ምክንያት የጠፉትን ሁሉንም ለይቶ ማወቅ ባይቻልም እንኳ) ለመመለስ ከፍተኛ ጥረት ማድረግና መመለስ ይኖርባቸዋል፡፡ 8. እያንዳንዳቸውን በኦርቶዶክሳዊ መንገድ የሚመራቸው በነገረ ሃይማኖት በሳል የሆኑ አባቶችን መመደብ፣ ኦርቶዶክሳዊነት ከሁሉም በላይ እሳቤው፣ መንፈሱ እንዲገባቸውና እንዲሠርጻቸው ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱን ትምህርቷን ሳያውቁ፤ ከሁሉም በላይ ደግሞ ኦርቶዶክሳዊ እሳቤና እይታ እንዲሁም መንፈስ ሳይኖራቸው በሌላ ቅኝት መንፈስ የኖሩ ሰዎች እንደ መሆናቸው እንመለስ ስላሉ ብቻ አብሯቸው የኖረውና የሠረጻቸው የኑፋቄ ትምህርትና መንፈስና እንዲሁ በአንድ ጊዜ ውልቅ ብሎ የሚወድቅ አይደለም፡፡ የያዛቸው የኑፋቄ መንፈስ እንዲለቃቸው፣ እርሾው ጭልጥ ብሎ እንዲጨለጥላቸው ማድረግ ይገባል፡፡ ይህ ደግሞ በአንድ ጀምበር የሚፈጸም አይደለም፡፡ ጌታችን “ዝንቱ ዘመድ ኢይወጽእ ዘእንበለ በጾም ወበጸሎት - ይህ ዓይነት አብሮ አደግ ክፉ መንፈስ ያለ ጾምና ጸሎት አይወጣም” እንዳለ፡፡ ስለዚህ ኦርቶዶክሳዊ ነገረ ሃይማኖታዊ መንፈስንና እይታን፣ ኦርዶክሳዊ አስተምህሮንና በአጠቃላይ ኦርቶዶክሳዊ ክርስትና ምን እንደሆነ በበሰለ እውቀት፣ በእውቀት ብቻም ሳይሆን በሕይወት የሚያስተምራቸው በሳል አባት ያስፈልጋቸዋል፡፡ ቆዳ በማውለቅና ልብስ በመቀየር ብቻ ከኑፋቄ ወደ ኦርቶዶክሳዊነት መመለስ አይቻልም፡፡ ባለፉት የቅርብ ጊዜያት (በ1990ዎቹ ዓመታት) በሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ ከፍተኛ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት ተፈጥሮ በነበረው ችግር ምክንያት ቅዱስ ሲኖዶስ ካጣራ በኋላ በሃይማኖት ችግር (በተሐድሶነት) የተጠረጠሩትን ወደ አንዳንድ ቦታዎች ሄደው የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት እንዲማሩ ተብሎ ነበር፡፡ ከእነዚያ ለቀኖና ተብለው ከተላኩት መካከል ግን አጋጣሚውን ሌላ ጥፋት ለመሥራት እንደ ምቹ አጋጣሚ የተጠቀሙበት ነበሩ፡፡ ከዚህም የተነሣ እየተማሩ ይቆዩ ተብለው ከተላኩት መካከል ሌሎችን የቤተ ክርስቲያን አባቶች አስክደው ወደ እነርሱ የጥፋት መንገድ ለማስገባት የተጠቀሙበት ነበሩ፡፡ ሌሎች ደግሞ የፕሮቴስታንታዊ ትምህርቶችን በተለያዩ መንገዶች ለማስፋፋት ሲሞክሩ የተደረሰባቸው ነበሩ፡፡ ስለዚህ ያን ጊዜ እንደ ተደረገው እንዲሁ ሁለት ሁለት እያደረጉ ወደ ሆነ ገዳም ወይም ቦታ መላክ ብቻውን ሰዎቹን አይለውጣቸውም፡፡ ስለዚህ በዚህም ከፍተኛ ሥራና ጥንቃቄ ያስፈልጋል፡፡ “ከሞኝ ደጅ ሞፈር ይቆረጣል” እንደሚባለው እንዳይሆን፡፡ 9. የቤተ ክርስቲያኒቱን አስተምህሮ የሚቀበሉ ስለ መሆናቸው ግልጽና ጠንቃቃ የሆነ ቃለ ጉባኤ አዘጋጅቶ እንዲፈርሙ ማድረግ ይህም አስፈላጊ ነው፡፡ የሰው ነገር ነገ የሚሆነው ስለማይታወቅ ለወደፊቱም ጥሩ መሠረትና ማስረጃ፣ ምስክርም ይሆን ዘንድ የቤተ ክርስቲያኒቱን አስተምህሮና ሥርዓት ያለ አንዳች ቅሬታ የሚቀበሉ ስለመሆናቸው ቃለ ጉባኤ ተይዞ በሚዘጋጅ ወረቀት ላይ መፈረም ይኖርባቸዋል፡፡ 10. ቀኖና መስጠት - (በመድረክ ላይ ይቀጥላሉ ወይስ አይቀጥሉም?) ይህ ለአባቶች የሚተው ጉዳይ ቢሆንም እዚህ ላይ ያነሣነው እንዲሁ ለትምህርት ያህል ግን አስፈላጊነቱን ሳይጠቅሱ ማለፍ አይገባም በሚል ነው፡፡ እንዲያውም ፍትሐ ነገሥታችን ለሌላው ሰው ክህደት ምክንያት የሚሆን ሰው ሲመለስ ቀኖናው ከበድ ያለ እንዲሆን ያዝዛል፡- “ወለዘኢአከሎ ክሕደቱ ባሕቲቱ እስከ ያወጽኦ ለካልኡ እምሃይማኖቱ ወኮነ ምክንያተ ለክህደቱ ይኩን ንስሓሁ ፈድፋደ - የራሱ ክህደት ብቻ አልበቃው ብሎ ባልንጀራውን ከሃይማኖቱ እስኪያወጣው ድረስ ለመካድ ምክንያት ቢሆን ንስሓው ጽኑዕ ይሁን፡፡” አንቀጽ ፳ ቁ. ፯፻፷ ከዚሁም ጋር ገና ተመለስን እንዳሉ “በዚያው በለመድነው ማስተማራችንን እንቀጥላለን፣ ከመድረክ አንወርድም የሚሉ ከሆነም ሌላ መታየት ያለበት ጉዳይ ነው፡፡ በመጀመሪያ አንድ ሰው ቀኖናውን ሳይጨርስ እንዲያ ማድረግ ተገቢ መሆን አለመሆኑን ማየት ያስፈልጋል፡፡ ከዚህም በላይ ደግሞ አንድ በኑፋቄ የነበረ ሰው እንዲሁ “ተመልሻለሁ” ስላለ ብቻ በውስጡ የነበረው ኑፋቄ በአንድ ጊዜ በተአምራት በኦርቶዶክሳዊ ትምህርት አይሞላም፡፡ ስለዚህ በመድረክ እቀጥላለሁ ካለ የሚያስተምረው ያንኑ ከመመለሱ በፊት ሲያስተምረው የነበረውን የቀድሞ የስህተት ትምህርት ካልሆነ በስተቀር ሌላ ከየት ያመጣል? ጌታችን “ኄር ብእሲ እምሠናይ መዝገበ ልቡ ያወጽኣ ለሠናይት ወእኩይሰ ብእሲ እምእኩይ መዝገበ ልቡ ያወጽኣ ለእኪት እስመ እምተረፈ ልብ ይነበብ አፍ - በልብ ሞልቶ ከተረፈው አፉ ይናገራልና፣ መልካም ሰው ከልብ መልካም መዝገብ መልካሙን ያወጣል፥ ክፉ ሰውም ከልብ ክፉ መዝገብ ክፉውን ያወጣል” እንዳለ፡፡ ሉቃ. 6፡45 ታዲያ በኑፋቄ የኖረና ልቡ በዚያ ተሞልቶ፣ ከዚያ ውስጡን ከሞላው ኑፋቄ ለሌሎችም ሲናገር የኖረ ሰው ተመልሻለሁ ስላለ ብቻ ኦርቶዶክሳዊ አስተምህሮና መንፈስ በአንድ ጊዜ ውስጡ ይመላበታልን? ይኽ ጌታችን ካስተማረው ትምህርት ጋር የማይሄድ ስለሆነ በሚገባ ሊጤን ይገባዋል፡፡ ተመልሰናል የሚሉት ሰዎች መመለሳቸውና ንስሐቸው የእውነት መሆን አለመሆኑ የሚገለጥበትና የሚፈተንበት አንዱ መንገድም ይኽ ነው፤ የተመለሱት በእውነት ከሆነ ግድ እናስተምር፣ በመድረክ እንቀጥል አይሉም፤ ነገር ግን የተንኮልና የስልት ከሆነ መድረኩ ላይ ካልቀጠልን ብለው የሙጥኝ ይላሉ፡፡ በዚህም ላይ አንድ በእውነተኛ መንፈስ ንስሐ የሚገባ ሰው በመጀመሪያ የሚያሳስበው ነገር እግዚአብሔርን በመበደሉ ይቅር እንዲለው፣ በደሉና ንስሓው እንጂ አሁንም መድረክ ላይ የመቀጠሉ ጉዳይ ሊሆን አይገባውም፡፡ እንመለስ የሚሉ ሰዎች ጭንቀታቸው መድረክ ላይ ስለ መዘመራቸውና ስለ መስበካቸው ከሆነ ጉዳዩ ዓላማን በውጭ ሆኖ ማስፈጸም ስለማይመች ወደ ውስጥ ገብቶ ተሐድሷዊውን ዓላማ ለማስፈጸም የአስገቡኝ ጥያቄ እንጂ የመመለስና የንስሐ ጥያቄ አይደለም ማለት ነው፡፡ ይኼ የድርድር እንጂ የንስሓ መንገድ አይደለም፡፡ የእንመለሳለን ጥያቄው ትኩረቱ በመድረክ ላይ ስለ መዘመርና ስለ መስበክ ከሆነ ጉዳዩ በእውነትም የእድሜ ማራዘሚያና የተንኮል ስልት እንጂ በቅንነት የተደረገ የእንመለሳለን አካሄድ ሆኖ አይታይም፡፡ 11. የሚደረጉትን እያዳንዳቸውን ነገሮች ሁሉ በከፍተኛ ጥንቃቄና ማስተዋል ማድረግ የጠፉትን መቀበል ተገቢና መልካም ቢሆንም በሌላ በኩል ደግሞ በዚህ ሂደት የሚደረጉት እያንዳንዳቸው ነገሮች ሁሉ ቤተ ክርስቲያኒቷ ለኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ እምነት ያላት ቁርጠኝነትና ድርጊቶቹ በኅብረተሰቡ ሥነ ልቡናዊና ሃይማኖታዊ አረዳድና መንፈስ ላይ ሸርሻሪ መሆን አለመሆናቸውን መጠየቅና በጥንቃቄ መመርመር ያስፈልጋል፡፡ በአንዳንዶች ዘንድ መናፍቃን የነበሩትን መቀበል የቤተ ክርስቲያንን እምነት መሸርሸር ተደርጎ እንዳይታይ መጠንቀቅ ይገባል፡፡ አለበለዚያ አንዱን እገነባለሁ ሲሉ ሌላውን ማፍረስ እንዳይሆን፡፡ እነዚህ ነገሮች በሚሆኑበት ጊዜ የሕዝቡን አረዳድና ሊያስከትል የሚችለውን ተጽእኖ በሚገባ ማጤን ያስፈልጋል፡፡ ገና ለገና ለወደፊቱ ይጠቅማል በማለት በጊዜው ያለውን ተጨባጭ ሁኔታ ያላገናዘበ ውሳኔና ድርጊት ውስጥ መግባት አደገኛ ነው፡፡ ሊያስከትል የሚችለውን አደጋ አርቆ ማየት ያስፈልጋል፣ ጭምብሎቻቸውን ገልጦ ትክክለኛ ማንነታቸውንና አደጋውን መረዳትና መለየት ያስፈልጋል፡፡ “ሰላም ሰላም” በሚል ቃል ብቻ እውነተኛ የቤተ ክርስቲያንን ውሳጣዊ ሰላም፣ እንዲሁም ጊዜያዊ ችግር የፈታንና ያቃለልን ሲመስለን ለወደፊቱ ችግር እያወሳሰብንና እያቆላለፍን እንዳይሆን መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡ ለዚህ ደግሞ በቅርብ ጊዜ በዘመናችን ከስድስቱ አኃት አብያተ ክርስቲያናት መካከል አንዷ በሆነችው በሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን የሆነውን አሳዛኝ ነገር ልንረሳው አይገባንም፡፡ በዋናነት በአንግሊካን ፕሮቴስታንት ቸርች (በእንግሊዝ ቤ/ክ) ቀያሽነትና አስፈጻሚነት በውስጣቸው ተፈልፍለው ያደጉት ተሐድሶዎች ገና ከመጀመሪያው ጉዳዩን የተረዱ አባቶችና ምእመናን ለይተው የማውገዝና የማጥራት ሥራ ሊሠሩ ሲሉ ተሐድሶዎቹ የእንመለሳን፣ የአስታርቁን ሽምግልና በተለያዩ ሰዎች በኩል ይልኩባቸው ነበር፡፡ በሽምግልናው ይሳተፉ የነበሩት ሰዎች አንዳንዶቹ እንዲሁ በሽፍኑ እርቅ ማን ይጠላል፣ ሰላም ምን ክፋት አለው በሚሉ መሸፈኛዎች የተታለሉና ምን እያደረጉ እንደሆኑ የማያውቁ ነበሩ፡፡ አንዳንዶቹ ደግሞ አስታረቁ ተብለው ስም ለማሰርና ጀብድ እንደ ሠሩ ለመቆጠር ነበር፡፡ አንዳንዶቹ ደግሞ ራሳቸውን በአስታራቂነት ጎራ ሲመድቡ እነርሱ ከሌሎቹ የተሻሉ አስተዋዮችና ያላከረሩ ብልሆች እንደሆኑ አድርገው ራሳቸውን ይቆጥሩ ነበር፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ዋናዎቹ ከጀርባ ሽማግሌዎቹን የሚልኳቸውና በሽምግልናውም ውስጥ ዋናውን ሥራ ይሠሩ የነበሩት ጥቂቶቹ ግን ዓላማው ገብቷቸው ተሐድሶዎቹ በደንብ ሳይጠነክሩና ሳይጎለምሱ፣ ብዙዎችን ወደ እነርሱ ጎራ ሳይለውጡ እንዳይወጡ እንደ እድሜ ማራዘሚያ ስልት ለመጠቀም ነበር፡፡ በዚህ ምክንያት ሳይወገዙ “እርቅ”፣ “ይቅርታ፣ “ንስሐ” እየተባለ ውስጥ ውስጡን ብዙ ካህናትንና ምእመናንን ከመለመሉና ከቀሰጡ በኋላ ራሳችንን የቻልንበት ደረጃ ላይ ደርሰናል ብለው ሲያስቡ መላዋን ቤተ ክርስቲያን መቆጣጠር ስላልቻሉ በይገባኛል የቤተ ክርስቲያኒቱን ነገር ሁሉ በፍርድ ቤት ተካፍለው ከሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ውስጡን ተሐድሶ ያደረጓቸውን ካህናትና ምእመናን ይዘው በመውጣት የራሳቸውን የተሐድሶ ቤተ እምነት መሥርተዋል፡፡ እነዚህም “ማር ቶማ ቸርች” ይባላሉ፡፡ ምሥራቃዊ ፕሮቴስታንትም (Oriental Protestant) ይሏቸዋል፡፡ እርቁንና ሽምግልናውን እየተቀበሉ ተወግዘው እንዳይለዩ ሲደግፉና ሓሳብ ሲሰጡ፣ በጊዜው ጊዜ ተወግዘው እንዲለዩና ምእመናን እንዲያውቋቸው ለማድረግ ይጥሩ የነበሩ ጳጳሳትንና ምእመናንን እየለመኑና እያግባቡ “እርቅ፣ ሰላም፣ አንድነት” በሚሉ ቃላት ተታለው ሲያታልሉ የነበሩት ጳጳሳትና ምእመናን ግን የኋላ ኋላ ጥቅም የሌው ጸጸት ብቻ ነበር ያተረፉት፡፡ ነገሩ ጅብ ከሄደ ሆነባቸው፡፡ ስለሆነም ይህ ጉዳይ አንድ ጊዜ ከመቁረጥ በፊት አሥር ጊዜ፣ ካስፈለገም ከዚያም በላይ፣ መለካት የሚያስፈልገው ጠንካራ ጉዳይ ነው፡፡ እንዲሁ በይሁን ይሁን፣ በምናለበት፣ ያለ ማስተዋልና ያለ አርቆ ማሰብ የሚደረግ ነገር በኋላ በእግዚአብሔርም ዘንድ፣ በትውልድም ዘንድ ያስጠይቃልና መጠንቀቅ ይገባል፡፡ ይኼው የሕንድ ቤተ ክርስቲያን የደረሰባትን አሳዛኝ ነገር እኛ እያዘንን እንደምንጠቅሰው፣ ሌላውም ዛሬም ወደፊትም እንደ አሳዛኝ ታሪክ ማሳያ እያደረገ እንደሚጠቅሰው ሁሉ የእኛ ቤተ ክርስቲያን አባቶችና ምእመናን በዚህ ጉዳይ ላይ ከፊታችን የሚሠሩት ሥራም በበጎም ሆነ በክፉ ተጠቃሽ ነው፡፡ ግን በአስተዋይነት የተሠራ መልካም ሥራ ሆኖ በበጎ ታሪክነትና በአስተማሪነቱ የሚጠቀስ ይሆን? ወይስ በስህተትና “በእነርሱ የደረሰ እንዳይደርስባችሁ” በሚል ማስፈራሪያነት? ውጤቱን ወደፊት የምናየው ይሆናል፡፡ ግን ከአፍንጫ ሥር ያለውንና ከፊት የቀረበውን ብቻ አሽትቶና አይቶ የሚወሰን ሳይሆን ወደ ኋላ ከዘመነ ሐዋርያት አንሥቶ የነበረው ታሪከ ቤተ ክርስቲያንና አስተምህሮን፣ አሁን ደግሞ ያለንበትን ጠቅላላና ዝርዝር ተጨባጭ ሁኔታ፣ ወደፊትም በእግዚአብሔርና በትውልድ ያለብንን ኃላፊነት ታሳቢ ያደረገ ቀኖናዊ ሂደት ይኖራል ብለን ተስፋ እናደርጋለን፣ እንዲኖርም እንፈልጋለን፡፡ ቤተ ክርስቲያን የሁላችንም ናትና እያንዳንዳችንም ችላ ሳንል፣ “እንዳረጉ ያድርጉት፣ እኔ ምን አገባኝ” ሳንል የቤተ ክርስቲያንን አንድነትና ቀኖናዊነት በጠበቀና ባገናዘበ መልኩ የየድርሻችንን እንወጣ፡፡ “ከወዳጆችህ ጋር ብቻ ሳይሆን ከጠላቶችህም ጋር እንኳ ሳይቀር በሰላም ኑር፤ ነገር ግን እንዲህ የምልህ ካንተ ከግል ጠላቶችህ ጋር እንጂ ከእግዚአብሔርና ከቤተ ክርስቲያን ጠላቶች ጋር አይደለም፡፡”አንድ ገዳማዊ አባት ለአንድ በቤተ ክርስቲያን ኃላፊነት ላይ ለነበረ ሌላ አባት ከጻፈው መልእክት ላይ የተወሰደ “ሰውን ከእግዚአብሔር ከሚለየው አጉል ሰላም ይልቅ ከእግዚአብሔር የማይለየው ጦርነት ይሻላል፤ ስሜታዊ ከሆነና ለቤተ ክርስቲያን ዘለቄታዊ ጉዳት ከሚኖረው ስምምነትና አንድነት ይልቅ ስለ ሃይማኖት መጠበቅ ዘለቄታዊ ጠቀሜታ የሚኖረውና ለዚህ ሲባል የሚሆን አለመስማማት ይሻላል፡፡” ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ፣ ትምህርት 2፡82 ላይ ኦገስት 08, 2013 1 አስተያየት: ይህን ኢሜል አድርግጦማር አድርግ!Twitter ላይ አጋራFacebook ላይ አጋራለPinterest አጋራ በጣም አዲስ ልጥፎች መነሻ ደንበኛ ይሁኑ ለ፡ ልጥፎች (Atom) በአውሮጳ የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ የተውጣጡ ካህናት፡” የ... በእንተ ሙኒክ ደብረ ብሥራት ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያንና ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ገብረ ሕይወት ፍስሐ [ጀርመን ] ምእመናን ከአንዱ ሀገር ወደ ሌላው ሀገር በተለያየ ምክንያት መሰደዳቸው አይቀሬ ነው:: ታዲያ ሲሰደዱ በሄዱበት ሀገር ሁሉ ቤተክርስቲያን ያስፈልጋቸዋል :: ምንም አያጠያይቅም የተመቻቹ ሁኔታዎችም አሉ... አስቸኩዋይ ጥሪ ለምእመናን በሙሉ የታላቁ የደብረ ሊባኖስ ገዳምን ለመርዳት ገዳሙ ጥሪ አስተላለፈ ገዳሙ በአሁን ሰዓት በመሬት መንሸራተት ምክንያት ከፍተኛ አደጋ እንደተጋረጠበት ተጠቅሶ ሰኔ 8 ቀን ከ7፡30 ጀምሮ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የስ... ጾመ ፍልሰታ የእመቤታችን ዕረፍት ጾመ ፍልሰታ የእመቤታችን ዕረፍት Written By Hulubante Abebe on Tuesday, August 5, 2014 | 1:02 PM መ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ ...
ቀዳማይ ሚንስትር ኬንያ ዝነበሩን መራሒ ተቃ፟ዋሚ ሰልፊ ዝኾኑ ራይላ ኦዲንጋ ነቲ ብውሑድ ነጥቢ ዝተሳዕርሉ ውፅኢት ኢሎም ኣለው ምርጫ ብምቅዋም ናብ ላዕለዋይ ቤት ፍርዲ እታ ሃገር ክሶም ኣቕሪቦም። ኦዲንጋ ነቲ ሕጋዊ ቃልሲ ነቲ ዕሸል ዴሞክራሲ እታ ሃገር ዝክፈል መስዋእቲ እዩ ኢሎም ኣለው። ኣብ ቀረባ እተዛዘመ ኢሎም ኣለው ምርጫ ኬንያ ዝተሳዕሩ ራይላ ኦዲንጋ ላዕለዋይ ቤት ፍርዲ እታ ሃገር እቲ ንዊልያም ሩቶ ፕረዚደንት ዝገብረ ውፅኢት ክቅ፟ይሮ ትማሊ ሰኑይ ወግዓዊክሶም ኣቅ፟ሪቦም። ኦዲንጋ ንደገፍቶምን ብኣሽሓት ዝቁ፟ፀሩ ሰነዳት ዝተዓጥቁ ጠበቃ፟ታቶምን ኣስዒቦም እዮም ኣብ ማእከል ናይሮቢ ናብ ዝርከብ ላዕለዋይ ቤት ፍርዲ ቐሪቦም። ክሶም ድሕሪ ምቅ፟ራቦም ስርዓት ምርጫ እዛ ሃገር ተበላሽዩ እዩ ክብሉ ተዛሪቦም። “ኬንያውያንን ወፍርታትና ዝከታተሉ ዝነበሩን ኩሎም ከም ዝዝክርዎ ኣንፃር ብልሽውና ምቅላስን ንሓዋሩ ካብ ኬንያ ክጠፍእ ምግባርን ከም ፓርቲ ኣዝሚዮላ ኡሞጃንን ከም ሓደ ናይ ኬንያ ውሁድ ፓርቲን ኣብ ኩሉ ወፍርታትና ቀንዲ ኣጀንዳና ምንባሩ ዝፍለጥ እዩ። ኣብ ዝሓለፈ ሰሙን ዝተኣወጀ ውፅኢት ፕረዚዳንታዊ ምርጫ ዘርእዮ ሓይሊታት ዴሞክራሲን ሰናይ ምምሕዳርን ኣንፃር እቶም ነዛ ሃገርን መንግስትን ንምቁፅፃር ካብ ዝገብርዎ ፈተነታት ዘይድቅሱ ገበነኛታት ብልሽውና ዝግበር ቀፃጻሊ ቃልሲ የመላኽት።" ጠበቃ፟ታት ኦዲንጋ ከምዝብልዎ እቲ ኣብ 9 ነሓሰ ዝተኻየደ ምርጫ ንዊልያም ሩቶ ዝወገነ ምንባሩ ዝሕብሩ ሰነዳት ምስቲ ክሶምም ምትሕሓዞም ይዛረቡ ። ውፅኢት እቲ ምርጫ ሩቶ 7.1 ሚልየን ድምፂ ክረኽቡ ከለዉ ኦዲንጋ ድማ 6.9 ሚልዮን ምርካቦም እዩ ብወግዒ ዝተገልፀ። ጄሚስ ኦረንጎ ካብ ጠበቃ፟ታት ኦዲንጋ ሓደ እዮም ኣብ ቤት ፍርዲ ክረትዑ ምዃኖም እዮም ብርግፀኝነት ይዛረቡ። “ኣብ ብዙሓት ጥርዓናት ተሳቲፈ እየ። ብዛዕባ እዚ ክብለኩም ዝኽእል ግን ጭቡጥ ዝኾነ ኣዝዩ ዘገርም መርተዖ እዩ ዘለና ከምኡ'ውን ብዙሓት ንፁራት ሰነዳትውን ኣለዉና፤ ኣብ መወዳእታ እዚ ክሲ ውሳነ ቤት ፍርዲ ናብ ራይላ ኣሞሎ ኦዲንጋ ዝወገነ ክኸውን እዩ ኢለ እየ ዝሓስብ።” ኦዲንጋ ነቲ ኮምሽን ምርጫ ብገበናት ምርጫን ብልሽው ኣሰራርሓን ይኸስዎ። "ገበነኛታት ብልሽውና ንሰበ-ስልጣን ምርጫ ጉቦ ብምሃብ እቲ ስርዓት ፀጥታ ካልእ መገዲ ክሕዝ ወይውን ፈፂሙ ክመውት ንምግባር ይፅዕሩ ኣለዉ። ኣብ ስልጣን ዝፀንሕሉን ብዘይሕጋዊ መገዲ ዘኻዕበትዎ ሃብቶም ካብ ህዝቢ እናሰረቁ ዝቅ፟ፅልሉ ኩነታት ንምድልዳል ተዳልዮም እዮም። አብዚ እዋን ምርጫ ዘጋጠመ'ውን እዚ እዩ።" ኮምሽን ምርጫን ተዓዋታይ ፕረዚደንታዊ ምርጫ ዊልያም ሩቶን ነቲ ናብኦም ዘነፃፀረ ክሲ መልሲ ንምሃብ ኣርባዕተ መዓልታት ጥራሕ እዩ ዘለዎም። ኣቦ መንበር ኮሚሽን ምርጫ ኬንያ ኣብ ዝሓለፈ ከምዝበልዎ ኮምሽኖም ሕጊ ተከቲሉ ምርጫ 9 ነሓሰ ምክያዱ ገሊፆም ነይሮም። ሩቶ ብወገኖም ኣብ ዝሓለፈ ሰሞን ዝረከብዎ ዓወት አብ ቤትፍርዲ ክጣበቁሉ ምኳኖም ገሊፆም። ኦዲንጋ ኣብ 2017 ንውፅኢት ፕረዚደንታዊ ምርጫ ዝገብርዎ ተቃ፟ውሞ ተዓዊቱ'ዩ። ኣብቲ እዋን ላዕለዋይ ቤት ፍርዲ ንቴክኒካዊ ጥሕሰታት ሕጊ ጠቂ፟ሱ ነቲ ውፅኢት ብምስራዝ ዳግማይ ኦዲንጋክካየድ ወሲኑ እዩ። ኦዲንጋ ካብቲ ኦዲንጋ ንርእሶም ኣግሊሎም ኡሁሩ ኬንያታ ድማ ንኻልኣይ ጊዜ ፕረዚደንት ኮይኖም ምምራፆም ዝዝከር እዩ። ካብ ጠበቃ፟ታት ኦዲንጋ ሓደ ዝኮኑ ኦሬንጎ ሎምዘበን ካብ ጥሕሰታት ሕጊ ዝዛየደ ከምዝፅበዩ እዮም ዝገልፁ። ብፈላመይቲ ጓለንስተይቲ ዳኛ ማርታ ኮሜ ዝምርሑ ሸውዓቲኦም ዳያኑ ላዕለዋይ ቤት ፍርዲ ኣብ 2021 ዝተሾሙ እዮም። እቲ ቤት ፍርዲ ውሳነ ንምሃብ ናይ ክልተ ሰሙን ጊዜ ኣለዎ።
“ጠንካራው፤ ኃላፊነት የተሞላበት እርምጃ በመውሰዱ፤ ደካማ የሚመስልበትና፤ ደካማው ደግሞ በሚወስደው ኃላፊነት የጎደለው እርምጃ ጠንካራ የሚመስለበት አስገራሚ ወቅት ላይ እንገኛለን” የቀድሞው የጀርመን ቻንስለር ኦቶ ቮን ቢስማርክ (Otto von Bismarck). በቀል፤ በኢትዮጵያ ባሕል ውስጥ የተገመደና፤ ለዘመናት አንዱን ከአንዱ ጋር ሲያገዳድል የኖረ አደገኛ ባሕላዊ ክስተት ነው። ሌላው ቀርቶ ልጅ ሲወለድ የሚሰጡ ስሞች እና አንዳንድ ምሳሌያዊ አነጋገሮቻችን በቀልን የሚያወድሱ እና በቀልን የሚያበረታቱ ናቸው። በአንድ አንድ የሃገራችን አካባቢዎች፤ በቀል ከትውልድ ወደ ትውልድ ሲተላለፍ እና በማህበረሰቡ ውስጥ ከፍተኛ ጉዳት ሲያመጣም ለዓመታት አስተውለናል። “ብድሩን የማይመልስ ወንድ ልጅ አይወለድ” የሚል ዓይነት ብሂል እና “ደም-መላሽ” የሚል ዓይነት ሥም፤ በባሕላችን እና በማህበረሰባችን በቀል ያለውን ተቀባይነት ያንፀባርቃል። ይህ የበቀል ባሕል፤ ፖለቲካችንን፤ ሃይማኖታችንን፤ ማህበራዊ ኑሯችንን እና የምጣኔ ሃብታችንን ጨምሮ አቃውሷል። እስካሁንም ትኩረት ተሰጥጦበት በጥናት የተደገፈ መፍትሔ ለማምጣት ብዙ ባይሞከርም፤ የበቀል ባሕልን ከሥሩ ለመንቀል ከመጣር ይልቅ፤ ስለ ሰላምና እርቅ መስበኩ፤ ዋነኛ አጀንዳ ሆኖ ቆይቷል። ይህ ፀሃፍ፤ የበቀል ባሕልን ከሥሩ እስካልነቀልን ድረስ፤ በሃገራችን ሰላም እና እርቅ ይኖራል በሎ ለመገመት ያዳግተዋል። እስካሁን ድረስ ሃገራችን ከቀውስ አዙሪት ያልወጣችው፤ የፖለቲካ ባሕላችን በበቀል አስተሳሰብ የተመረዘ በመሆኑ ነው። ትላንትም ሆነ ዛሬም እየተገዳደልን የምንኖረው፤ ውስጣችን በበቀል ስሜት ስለጨቀየ እና፤ ይህን የበቀል ባሕል ለመቀየር ይህ ነው የሚባል ሥራ ባለመስራታችን ነው። ሃገራችን ብዙ ብርቅዬ ልጆቿን ያጣችው፤ ባልተቋረጠው በቀል በወለደው የግጭት እና የዓመጽ አዙሪት ለመሆኑ፤ ታሪክ ተንታኝ አያስፈልገንም። ለዘመናት ያካሄድናቸው የእርስ በእርስ ግጭቶች፤ መሰረታቸው በቀል ነው። ሌላው ቀርቶ፤ የፈጣሪን ፍቅር ማስተማር የሚገባቸው የሃይማኖት አባቶች፤ በበቀል ስሜት ታውረው፤ የሃይማኖት ተከታዮቻቸውን ለመግራት እንኳን ተነሳሽነት አያሳዩም። ምንም እንኳን በቃል በአደባባይ ስለ-ሰላም ቢሰብኩም፤ ከመጋረጃ ጀርባ ግን፤ በቀልን የሚያራምዱና የጥፋት ሴራ የሚጎነጉኑ ለመሆናቸው የአደባባይ ሚስጥር ነው። ሃይማኖቶች ከአፈጣጠራቸው ጀምረው የፖለቲካ መሳሪያ የነበሩ እና አሁንም የሆኑ ናቸው። ለዚህም ነው ዛሬ መስጊድ ሲቃጠል፤ በአደባባይ ውግዘት፤ ከጀርባ ደግሞ፤ የበቀል እርምጃ ግፊት የምናየው። በስልጤ ዞን፤ ቤተ ክርስቲያን የተቃጠለው፤ መስጊድ ውስጥ ጸሎታቸውን አጠናቀው ከመስጊድ በወጡ ሰዎች መሆኑ፤ መምህራኖቹ፤ ‘በቀል አያዋጣም፤ ከፈጣሪም ያጣላል’ ብለው አጽንተው ባለመምከራቸው ነው። ይህ ባይሆን ኖሮ፤ ከፈጣሪው ጋር በቤተ እምነቱ ተነጋግሮ (ፀልዮ) የወጣ ሰው፤ ምንም ቢሆን ወደ ጥፋት ጎዳና ባልሄደ ነበር። በጎንደርም የተከሰተው ከዚህ የተለየ አይደለም። መጽሐፍ ቅዱስ፤ ስጡ እንጂ ንፉግ ሁኑ ብሎ አያስተምርም። ሕይወታቸው ላለፈው ሙስሊም አባት ቀብር፤ ድንጋይ ከተፈለገ፤ ቤተክርስቲያኗም ሆነ “አማኝ” ነን የሚሉት ሰዎች፤ ድንጋዩን መስጠት ብቻ ሳይሆን፤ ቀብሩ በሥርአት እንዲያልቅ ማገዝ ነበረባቸው። የሃይማኖቱም ትክክለኛ አስተምርሆት ይህ ይመስለኛል። ይህ በሃይማኖት ስም የተሰራ ሸፍጥ እንጂ ከሃይማኖቱ ጋር ምንም ግንኙነት የለውም። የተነሳውንም ግጭት ከማብረድ እና ለችግሩ መንሰኤ የሆኑ ሰዎችን ከመገሰጽ ይልቅ፤ በውስጥ ያለው የበቀል ስሜት ያነሳሳቸው “የሃይማኖት መሪ ነነ” ባዮች፤ ሁኔታዎችን ማባባሳቸው፤ ከክርስቶስ ትምህርት እና ክርስቲያን መርህ ያፈነገጠ ለመሆኑ፤ ፈላስፋ መሆንን አይጠይቅም። ድንጋይ አትርፎ፤ የእግዚአብሔር ፍጡር የሆነውን ክቡሩን የሰው ሕይወት የሚያጠፋስ በየትኛው ሃይማኖታዊ ትምህርት ታንጾ ነው? እኔ እንደሚገባኝ፤ ችግሩ፤ የሃይማኖቶቹ መርህ ሳይሆን፤ ችግሩ፤ የሃይማኖቱን አስተምርሆት ለምእመናን በተሳሳተ መንገድ ከማስጨበጥ የመነጨ ነው። በሰበታ ውስጥ፤ ማርያም ቤተክርስቲያን ባዋጣቸው መሬት እና ከሙስሊሙ ማህበረሰብ በተዋጣ ገንዘብ ትምህርት ቤት መገንባቱ፤ ያኮራንን ያክል፤ በጎንደር፤ በስልጤና በሌሎች አካባቢዎች በሃይማኖት ተቋማት ላይ የተፈፀመው ጥቃት እና፤ ከዛም ጋር ተያይዞ በጠፋው ሕይወት እና በወደመው ንብረት፤ ሁላችንም ልናፍር ይገባናል። ማፈር ብቻ ሳይሆን፤ የበቀል ባሕላችን ከሥሩ ሊበጠስ የሚችልበትንም መንገድ ማቀድ እና መተግበርም ይኖርብናል። እኔ እስከማቀው ድረስ የየትኛውም ሃይማኖት የተቀደሰ መጽሐፍ የሰዉን ሕይወት በከንቱ አጥፋ፤ ንብረት አውድም አይልም። በሁለቱም ወገን ለደረሰው ጥፋት፤ ዋና ተጠያቂዎቹ፤ የሃይማኖቶቹ መሪዎች ናቸው። የሃይማኖት መሪዎች፤ ምእመኖቻቸውን፤ የሚያስተምሩት ምንድነው? ይህ መልስ ማግኘት ያለበት ጥያቄ ነው። ፈጣሪ ሁሉንም የሰው ልጅ የሚያየው እኩል ነው። ሙስሊም፤ ክርስቲያን፤ ወዘተ የሚለውን ክፍፍል የፈጠርነው እኛ ነን። አላህ እና እግዚአብሔር አንድ ናቸው። “አላህ” አረብኛ እንጂ “እስላምኛ” አይደለም። በአማርኛ እግዚአብሔር፤ በእንግሊዝኛ God፤ በፈረንሳይ Dieu፤ በእብራይስጥ elo’ah፤ በአረበኛ ደግሞ አላህ ነው። በአረብ ሃገራት የሚኖሩ ክርስቲያኖች፤ እግዚአብሔርን የሚጠሩት “አላህ” ብለው ነው። የሰው ልጆች ተለያየ ሥም ቢሰጡትም፤ ፈጣሪያችን ግን አንድና አንድ ብቻ ነው። ሁሉም ሃይማኖቶች ክቡሩ የሰው ልጅ፤ የአንድ ፈጣሪ ፍጥረት መሆኑን እንደማስተማርና ፍቅርን እንደመስበክ፤ ለየራሳቸው “የሃይማኖት ችርቻሮ” ሲሉ፤ በሰዎች መካከል ልዩነትን በመፍጠር፤ በማስፋት እና፤ አንዳንድ ተከታዮቻቸው፤ በበቀል እንዲታወሩ በማድረግ፤ ላማያባራ ግጭት እየዳረጉን ለመሆኑ፤ በግልጽ፤ በድፍረት እና በተደጋጋሚ ሊነገር ይገባል። በአንድ ሃገር በሰላም ልንኖር የምንችለው፤ አንዳችን ሌላችንን እንደ ሰው ስናከብር፤ አንዳችን የሌላችንን እምነት ሳንጋፋ፤ ስንከባበር ነው። አባላት ለማብዛት በሚደረግ ፉክክር ውስጥ፤ በዚህም በሚገመድ ተንኮል ማንም አያተርፍም፤ ማንም አይፀድቅም። መጽሐፍ ቅዱስ “እሱ እንዳደረገብኝ እንዲሁ አደርግበታለሁ፤ አጸፋውን እመልሳለሁ አትበል” ይላል (ምሳሌ 24:29)። ቅዱስ ቁርዓን በበኩሉ “ለዲያብሎሳዊ ሥራ የምትሰጠው የበቀል ምላሽ እራሱ ዲያቢሎሳዊ ነው፤ሆኖም ማንም ይቅር የሚል፤ ካሳውን የሚያገኘው ከአላህ ነው።” ይላል (ቁርዓን 42፡40)። የየሃይማኖቶቹ፤ የተቀደሱ መጽሐፍት የሚያስተምሩን፤ ይቅር ባይነትን ነው። ጥያቄው ግን የየሃይማኖቶቹ መሪዎችና አስተማሪዎች ይህንን ያስተምራሉ ወይ ነው። በየሃይማኖቶቹ የተሰገሰጉትንስ ጽንፈኞች እና ሃይማኖትን ለራሳቸው ፖለቲካ መጠቀምያ የሚያደርጉትንስ፤ የየሃይማኖቱ መሪዎች እንዴት ማጽዳት አቃታቸው? የማጽዳትስ ፍላጎት አላቸው ወይ? እነዚህ ጥያቄዎች በጥናት መልስ ሊገኝላቸው ይገባል። አንዱ ከሌላው የበላይ ለመሆን የሚያደርገው ፉክክር እና የአባላቶቻችውን የበቀል ስሜት በመቆስቆስ እየፈጠሩ ያሉት የማያቋርጥ የግጭት አዙሪት፤ መፍትሔው በሃይማኖት መሪዎቹ እንጂ በመንግሥት እጅ ብቻ አይደለም። በተደጋጋሚ እንደምንሰማውም፤ ከተራ “የሕብረተሰብ አንቂ” ጀምሮ፤ እስከ ከፍተኛ የሃይማኖት እና የፖለቲካ መሪዎች፤ ሁሌም የሚሉት አስገራሚ ነገር አለ። “መንግስት ዋና ሃላፊነቱ፤ የዜጎችን ሰላም የማስጠበቅ ነው፤ መንግሥት ሃላፊነቱን ይወጣ” የሚል። የመንግሥት ዋና ሃላፊነት ሰላም ማስጠበቅ ነው ማለት፤ ሁሌም መንግሥት ችግር ከመፈጠሩ በፊት፤ ችግሮችን ማስቆም ይችላል ማለት አይደለም። የሃይማኖት መሪውም፤ የፖለቲካ መሪውም ሆነ አንቂው፤ በየቦታው እሳት እየለኮሰ፤ መንግሥት እሳቱ እናዳይነሳ ማድረግ አልቻለም ብሎ መክሰስ ተገቢ አይደለም። በየትኛውም አለም ያለ መንግሥት፤ ሙሉ ለሙሉ ችግሮች ከመነሳታቸው በፊት ሊያስቆም አይችልም። ችግሮች ከተከሰቱ በኋላ ግን፤ መንግሥት አጥፊዎች ላይ እርምጃ የመውሰድ ግዴታና ሃላፊነት አለበት። ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ፤ ችግሩ ከመከሰቱ በፊት፤ ችግሩ እንዳይነሳ የማድረግ ሃላፊነቱ የማነው? በሃይማኖት መምህራን እና አመራሮች ያልተገራ አጥፊ ለሚያጠፋው ጥፋት፤ ተጠያቂ መሆን ያለበት የሃይማኖት መምህሩ እና አመራሩ ነው። በፖለቲካውም እንዲሁ። የፖለቲካ ድርጅቶች፤ አባላቶቻቸውን በተገቢው ሁኔታ በመግራት፤ በነውጥ እንዳይሳተፉ ከማድረግ ይልቅ፤ ነውጥን እየሰበኩ፤ አባላቶቻቸውና ደጋፊዎቻቸው፤ ጥፋት ሲፈጽሙ፤ መንግሥት ላይ ጣት መጠቆም ተገቢ አይሆንም። ኢትዮጵያ የሁላችንም ነች፤ ሰላሟን የማስጠበቅ ግዴታ የሁላችንም ነው። የመግሥት አካላት ከመሃላችን የወጡ እንጂ ከሰማይ የመጡ ተዓምር ሰሪዎች አይደሉም። ሕወሃት ስልጣን ከተቆናጠጠበት ጊዜ ጀምሮ፤ ከስልጣን እስከተወገደበት ጊዜ ድረስ፤ የሃገሪቱን በሔራዊ ተቋማት ያዳከመ እና በተለይም የፀጥታ መዋቅሩ፤ ለአንድ ፓርቲ ብቻ እንዲቆም ሆኖ የተገነባ እንደነበር መረዳት አለብን። ከለውጡ በኋላ ግንባታው እንደ አዲስ የተጀመረ በመሆኑ ጠንካራ ሆኖ ለመውጣት ብዙ ይቀረዋል። ተቋም መገንባት ጊዜ ወሳጅ ነው። በሃገራችን በተለያዩ አካባቢዎች ሽብር ለመፍጠር፤ የጅምላ ጭፍጨፋዎችን ለማካሄድ እና ሰላም ለመንሳት ቆርጠው የተነሱ የሽብር እና አጥፊ ሃይሎች መኖራቸውም የተዘነጋ ይመስላል። እነዚህን ኃይሎች መንግስት ሊቋቋም እና ሊያጠፋ የሚችለው፤ በህብረተሰቡ ትብብር ነው። እኛስ ችግር ከመፈጠሩ በፊት፤ ችግር እንዳይፈጠር የማድረግ ሃላፊነት የለብንም ወይ? ችግር ከተፈጠረስ በኋላ፤ ችግር ፈጣሪዎችን ለሕግ አካላት አሳልፈን የመስጠት ግዴታ የለብንም ወይ? ፋኖ አጠፋ ሲባል፤ ተከራካሪው አማራ ብቻ ከሆነ፤ ሸኔ አጠፋ ሲባል ተከራካሪው ኦሮሞ ብቻ ከሆነ፤ ይህ አካሄዳችን፤ በእውነት ለሃገራችን ይበጃል ወይ? ለሙስሊሙ ክርስቲያኑ ካልተከራከረ፤ ለክርስቲያኑ ሙስሊሙ ካልተከራከረ፤ የጋራ ሃገር ውስጥ በሰላም መኖር እንችላለን ወይ? መንግሥትን መውቀስ ቀላል ነው፤ እራሳችንንስ በመስተዋት ማየት የለብንም ወይ? ሃላፊነት እንደሚሰማው ዜጋ ሁላችንም ለሃገራችን ዘብ መቆም የለብንም ወይ? ወይስ በበቀል ደዌ ታመን፤ “የእኔ” የማንለውን ሃይል ለመጣል በምናደርገው እኩይ ተግባር ሃገርን በመጉዳት ዘላቂ ሰላም እናመጣለን ብለን እናስባለን? ዛሬ አዲስ አበባ ተቀምጠው ወንበር የሚያሞቁ እና “ጭብጨባ ፍለጋ” በመግለጫ የሚያደነቁሩን የፖለቲካ ሃይሎች ምን እየሰሩ ነው? መንግሥት የተቸገረውን እንዲረዳ የወቀሳ አለንጋቸውን ከመሞረድ ይልቅ፤ ሕዝቡን በማስተባበር፤ ለተቸገረውና ከየቀዬው ለተፈናቀለው ሕብረተሰብ እርዳታ ለምን አያደርሱም? ሕዝብን ለማገልገል፤ ከልብ ለማገልገል፤ የግድ ቤተ መንግሥት መገባት አለበት የሚል አስተሳሰብ ከየት ነው የመጣው? ኢትዮጵያ ውስጥ በጦርነት ሕዝብ ሲፈናቀል ይህ የመጀመሪያው አይደለም። ከሱማሌ ጋር በተደረገ ጦርነት በደረሰው ጉዳትና መፈናቅል፤ በግል አነሳሽነት፤ እርዳታ ስናሰባስብ ለነበርን ሰዎች፤ አሁን በተሻለ ቴክኖሎጂ፤ የተሻለ ጥረት የማይደረግበት ምክንያቱ ግራ አጋብቶናል። በወሎ ረሃብ ጊዜ፤ በወቅቱ የወጣት መሪዎች የነበሩት እነ ረዘነ በየነ ገብረእግዚአብሔር፤ በብሔራዊ ሎተሪ አዳራሽ እርዳታ ያሰባሰቡበት የኢትዮጵያዊነት መንፈስ የተ ገባ? በጋሽ ጳውሎስ ኞኞ አስተባባሪነት፤ አባቴም የተሳተፈበት፤ የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች፤ በራሳቸው አነሳሽነት፤ ለወሎ እና ለትግራይ ረሃብተኞች ያሰባሰቡት እርዳታስ፤ መንፈሱ የታለ? ከእነዚህ ልምዶች እንዴት ትምህርት አልተወሰደም? አንዳንድ የዛሬ “ጋዜጠኞቻችን” ስለተቸገረው ሕዝብ የአዞ እንባ እያፈሰሱ፤ ስህተት ፍለጋ ከማነፍነፍ እና አንዱን ብሔር ከሌላው ጋር ለማጋጨት፤ ተግተው ከመስራት ይልቅ እናስብለታለን ለሚሉት ተፈናቃይ ሕዝብ ምን ሰሩ? እነዚህ ኃይሎች፤ በበቀል ስሜት የታመሙ በመሆናቸው፤ የመገናኛ ብዙሃንን ለራሳቸው ጠባብ ፍላጎት ሲጠቅሙብት እያየን፤ እና እያበረታታን፤ መፍትሔ ማግኘት እንዴት እንችላለን? ለዚህ ሁሉ የሰው ሕይወት መጥፋት፤ ንብረት መውደም፤ ምክንያቱ የበቀል ባሕላችን ነው። ችግሩን ካባባስነው፤ ስለመንግሥት ጥፋት ነጋ ጠባ ካወራን፤ መንግስትን ብቻ ተጠያቂ ካደረግን፤ የማንፈልገው ቡድን ከሥልጣን ይነሳል፤ በሚል የበቀል ስሜት የተገመደ ሃገር አጥፊ የበቀል ባሕል። በመንግሥት በኩል ያሉ ጥፋቶችን ተገቢና ገንቢ በሆነ መንገድ ከማረም ይልቅ፤ “ልጁንም፤ የታጠበበትንም ቆሻሻ ወኃ” የመድፋት የቂም አስተሳሰብ ሃገራችንን እየጎዳ ነው። አመራር ላይ ያሉ ሰዎችን፤ በአስተሳሰባቸው ወይም በስራቸው ሳይሆን፤ የምንመዝናቸው በሃይማኖታቸው እና በዘራቸው በመሆኑ፤ የእኔ ካልናቸው እንደግፋቸዋለን፤ የእኔ ካላልናቸው ደግሞ አምርረን እንጠላቸዋልን። ስንጠላቸው ደግሞ በሥራቸው ስኬታማ እንዳይሁኑ ግጭት እናራግባለን። መልሰን ስለሰላም የምንጠይቀው ደግሞ እኛው እንሆናለን። “ትኋንን ለማጥፋት ቤትን የማቃጠል” እርምጃ በሃይማኖቱም በፖለቲካውም የምናየው የሃገር ጠንቅ፤ ሊወገድ የሚችለው የበቀል ባሕላችንን ከሥሩ ነቅለን ስንጥል ብቻ ነው። በአንድ ጉንጭ ስለሰላም እየሰበኩ፤ በሌላ ጉንጭ ጥፋትን ማስተማር የሚያጠፋው ሁላችንንም መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል። እንደዚህ ፀሃፍ እምነት፤ የወደፊት አብሮነታችንን እና ዘላቂ ሰላም ልናሰፍን የምንችለው፤ አደገኛውን የበቀል ባሕል ለመቀየር፤ በጥናት የተደገፈ መሰረታዊ ለውጥ የሚያመጣ ሥራ ስንሰራ ብቻ ነው። በተለይም የተቋቋመው የሰላምና የእርቅ ኮምሺን፤ የበቀል ባሕላችንን ለመለወጥ ተግቶ ካልሰራ፤ ስበሰባው ብቻውን፤ ለውጥ ያመጣል ብሎ ማመን አስቸጋሪ ነው። ገና ከጅምሩ፤ በርካታ የፖለቲካ ኃይሎች እንቅፋት ሲፈጥሩ የምናየው፤ ውስጣቸው ባለው የበቀል ስሜት ነው። ዛሬም ዓላማቸው የሃገር ፅናት ሳይሆን፤ በአቋራጭ ሥልጣን መያዝ ነው። ሃሳብ አቅርበው፤ በሃሳብ ተሟግተው የሕዝብን ልብ ለማሸነፍ አቅም የሌላቸው፤ ገና ክ70ዎቹ የበቀል የፖለቲካ አስተሳሰብ ያልተላቀቁ እና የሙሾ ፖለቲካ ላይ የተቸነከሩ ፖለቲከኞች፤ አርቀው የሚያዩት እስከ ሥልጣናቸው እንጂ፤ ከሥልጣን ባሻገር፤ ለሃገር ዘላቂ ሰላም እና ከትውልድ ወደ ትውልድ የሚሸጋገር ስልተ ሥርዓት የመገንባት አዎንታዊ ሥራ ላይ አይደለም። ይህም የሆነው፤ ውስጣቸው በበቀል የተሞላ በመሆኑ ነው። ለዚህም ነው ሃገራችንን በጥናት በተደገፈ ከፍተኛ ሥራ የበቀል ባሕልን ከሃገራችን ማጽዳት ያለብን። ለዚህም ነው፤ ከበቀል የፀዳ ኅብረተሰብ ስንገነባ ሃገራችን ኢትዮጵያ ከግጭት አዙሪት የምትወጣበት ዕጣ ፈንታ የሚሆነው። ሰላም ለኢትዮጵያ፤ ኢትዮጵያንና ሕዝቧን እግዚአብሔር ይጠብቅ፤ ይባርክ። __ በነጻ አስተያየት መድረክ የሚቀርቡ ሃሳቦች የጸሃፊውን እንጂ የግድ የቦርከናን ድረገጽ ሃሳብ ላያንጸባርቁ ይችላሉ፡፡ በዚህ ድረ ገጽ ላይ መጣጥፍ ለማውጣት ከፈለጉ ጽሁፍዎትን በሚከተለው አድራሻ በኢሜይል ይላኩልን info@borkena.com
የሰበር ዜና ልክፍት የተጠናወተው የዘመኑ “ሚዲያ” የአባዱላን ከአፈጉባኤነት መልቀቅ በሰበር ዜናነት ማናፈሱ ቆም ብሎ ላየው ራስን ትዝብት ላይ የሚጥል ነው። የአባዱላ መልቀቂያ ማስገባት “ምስጢር” በቅርቡ የሚለይለት ቢሆንም በህወሓት ተለክቶና ተጠፍጥፎ የተሠራ ድርጅትና ስብዕና ያለው ለዚህ ዓይነት የሞራል ልዕልና ይደርሳል ብሎ መገመት ህወሓትን ካለማወቅ ወይም ራስን ከመሳት የሚመነጭ ነው ቢባል ማጋነን አይሆንም። በበርካታ የሙስና ተግባራትና ህይወት ማጥፋት አለበት እየተባለ የሚነገርለት አባዱላ ከቀድሞው የኢትዮጵያ ሠራዊት ተማርኮ በሻዕቢያ ፈቃድና በህወሓት ፈጣሪነት አዲስ ስብዕና ተሰጥቶት ኦህዴድ የሚባል የጀመረ መሆኑ የሚዘነጋ አይደለም። ይህ ስብዕናው ህወሓት በህንፍሽፍሽ ልትበታተን ስትል የኦሮሞውን ክንፍ ይዞ መለስን የታደገ በመሆኑ ባለውለታነቱ ለማን እንደሆነ በድጋሚ ያስመሰከረ ሆኗል። በሌላው አንጻር አባዱላ የኦሮሚያ ዋና ኃላፊ በነበረበት ጊዜ ጁነዲን ሳዶ በኦሮሚያ የፈጠረውን ካቢኔ እና አደረጃጀት በማፍረስ አዲስ ለመለመላቸው የኦህዴድ አባላት “አትደግፉን ነገር ግን የክልሉን ልማት አታደናቅፉ” በማለት እስከ ቀበሌ የደረሰ አዲስ የካድሬ አደረጃጀት አዋቅሮ ነበር። አባዱላ ይህንን ተፈጻሚ ሲያደርግ የሄደበት የአደረጃጀት መንገድ የኦነግም ሆነ የተቀናቃኝ ፓርቲ አባላትን የኦህዴድ ጭምብል በማልበስ ነበር። ለዚህ ድፍረት ያበቃውም በህንፍሽፍሹ የነ ስዬና ተወልደን ውህዳን ቡድን በመቃወም ከመለስ ጋር በመወገን ኦህዴድን ለህወሓት በማዳኑ ከመለስ በተሰጠው “በኦሮሚያ ያሻህን አድርግ” ፈቃድ ነበር። ለካድሬው “ነጻነት” በመስጠት የተወዳጀው አባዱላ ባንድ ወገን ይህ ድርጊቱ የካድሬውን ፍቅር ሲቸረውና “ጃርሳው” ሲያስብለው በሌላው ግን ከአላሙዲ ጋር በግብር ጉዳይ፤ ከመለስ ጋር ደግሞ በተወዳጅነት ቅንዓት ጥርስ ውስጥ አስገባው። እንደ ሰይጣን ወዳጅ የሌለው ህወሓትም አባዱላን አፈጉባኤ በማለት አከሸፈው። አንድ የማይካድ ሐቅ ቢኖር አባዱላ ኦሮሚያን ከለቀቀ ወዲህ ኦሮሚያ እንደቀድሞው መሆን አቅቷታል። የጁነዲን አርሲ ተኮር ኦህዴድ በጃርሳው ከተናደ በኋላ ኦህአዴድም እንደ ድርጅት የህወሓት ሎሌነቱን በበላይ አመራሩ ብቻ ወስኖ የመካከለኛውና የበታቹ ከከዳ ሰንብቷል። በሙክታር ከዲር የሥልጣን ዘመን ከመለስ ሞት ጋር ተዳምሮ ህልውና ያጣውን ኦህዴድን ወደነበረበት የመመለስ ሥራ የለማ መገርሳ ትከሻ የማይሸከመው ሆኗል። የመናገር፣ የመጻፍ፣ ሃሳብን የመግለጽ፣ ወዘተ መብቶች በማይታሰቡባት ኢትዮጵያ እንደ ብአዴን በህወሓት ተጠፍጥፎ የተሠራው ኦህዴድና ከስም እስከ ስብዕና ተለክቶ የተሰጠው አባዱላ በቴሌቪዥን ቀርቦ “ሥልጣኔን እለቃለሁ” ብሎ በነጻነት መናገሩ አእምሮ ላለው “እንዴት” ብሎ እንዲጠይቅ የሚያስገድድ ተግባር ነው። በአደባባይ “ስኳር እወዳለሁ፤ ይጣፍጠኛል” አስብሎና አዋርዶ አብሮ የታገለውን ታምራት ላይኔን ያዋረደው ህወሓት፤ በርካታ “በቁምሳጥን ውስጥ የተደበቁ አጽሞች” ያሉበትን አባዱላ ለዚህ “ዕድል” ማብቃቱ ከአባዱላ የመልቀቂ ጥያቄ በላይ በሰበር ዜናነት ሊበሰር የሚገባው ነበር። ለማንኛውም ሁኔታው በቅርቡ ግልጽ ይሆናል። የኦሮሚያ ጉዳይ እጅግ መከራ ውስጥ ያስገባው ህወሓት አባዱላን በጃርሳውነት ወደ ኦሮሚያ (ጨፌ) ይመልሰው ይሆናል (ከአፈጉባኤነት እንጂ ከድርጅቴ አለቀኩም ማለቱን ያጤኗል) ወይም በቅርቡ በሙስና ጉዳይ ተጠርጣሪ ከአገር እንዲስኮበልል አድርጓል፣ አንጃ ሆኗል፣ በሙስና ተጨማልቋል፣ … ብሎ ወደ ሸቤ ይወረውረዋል። አለበለዚያም ፋይሉ እንደ ተዘጋ ጉዳይ በመዝገብ ቤት በኩል ወደ “ዴድ ፋይል” ክፍል ይልከዋል። ከዚህ ይልቅ ኢትዮጵያን እንደ አገር ለመቆየት የሚያሰጋት በርካታ ጉዳይ መኖሩን ሳንዘነጋ ጥይታችንን በእንደዚህ ዓይነት አናሳ ዜና ላይ ከማባከን ይልቅ በህወሓት ላይ ማድረጉ ነጻነታችንን ቅርብ ያደርግልናል።
እርስዎ የድር ጣቢያቸውን የሚገባውን ትራክት ማግኘት የማይችሉ የመስመር ላይ ንግድ ፣ ሥራ ፈጣሪ ወይም ነፃ አውጪ ነዎት? ወደ SEO ዓለም ለመግባት ሞክረዋል ፣ ነገር ግን የንግድ ስራዎን የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴዎችዎን በሚያስተዳድሩበት ጊዜ አእምሮዎን መጠበቁ በጣም ግራ የሚያጋባ እና ከባድ ነው? ብቻሕን አይደለህም. ድር ጣቢያዎ በ Google በጥሩ ሁኔታ እንዲመዘገብ እና ለጣቢያዎ ኦርጋኒክ ትራፊክን የሚስብ ይዘት ለመፍጠር ፣ የ SEO ቴክኒኮችን በብቃት እና በብቃት መተግበር አለብዎት። እና እነዚህን ስልቶች እራስዎ ለመጠቀም ሊሞክሩ ቢችሉም ፣ ሊያሳጡዎት የሚችሉ ስህተቶች ሊያደርጉ ይችላሉ ፡፡ ያስታውሱ-ከመጥፎው SEO የተሻለ የለም ፡፡ ጣቶችዎ በ SEO ውስጥ ከእርስዎ ይልቅ ረዘም ላለ ጊዜ የሾሙ ሰዎችን በመወከል እና ጥሩ የድር ጣቢያዎችን በማግኘት የተረጋገጠ የትራክ ሪኮርድን ለማግኘት የ SEO ሥራን በመወጣት ፈጣን ውጤቶችን ማግኘት ይችላሉ ፡፡ ሴሚል ብዙ ንግዶች የመስመር ላይ መገኘታቸውን እንዲያጠናክሩ የረዳ በጣም የታወቀ SEO እና ዲጂታል ግብይት ኤጀንሲ ነው። ልምድ ካላቸው የፀሐፊዎች ቡድን እና የ SEO መሐንዲሶች ጋር ፣ ሴሚል ትራፊክ እና ደረጃን ከፍ ለማድረግ ጥሩ ጥራት ያለው ይዘት እና ውጤታማ የ SEO ዘመቻዎችን ይሰጣል ፡፡ እውነት ለመሆን በጣም ጥሩ ይመስላል የበለጠ ለማወቅ ማንበብዎን ይቀጥሉ። AutoSEO: ከቁልፍ ቃል ምርምር እስከ ገጽ-ማሻሻል ድረስ የመስመር ላይ ሽያጮችን ማሳደግ ከፈለጉ ነገር ግን ሊኖሩ የሚችሉ ውጤቶችን ሳያውቁ በ SEO ብዙ ቶን ገንዘብ ለማውጣት ዝግጁ ካልሆኑ ፣ AutoSEO በመሰረታዊ ዋጋ ጥሩ ውጤቶችን የሚሰጥዎ መሳሪያ ነው ፡፡ በ AutoSEO በራስ-ሰር የእርስዎ SEO ዘመቻ ሊሻሻል የሚችልባቸው ሁሉም መንገዶች እዚህ አሉ የድር ጣቢያዎን ታይነት ያሻሽላል ድር ጣቢያዎ መስመር ላይ ለእነሱ የማይታይ ከሆነ ደንበኞች ምርቶችዎን ወይም አገልግሎቶችዎን ማየት አይችሉም። በመስመር ላይ ወደ ምርቶችዎ በትክክል መድረስ የሚችሉት ብቸኛው መንገድ ድር ጣቢያዎ ደረጃ እንዲይዝ ማድረግ ነው ፡፡ በተመሳሳይም የድር ጣቢያዎን ታይነት ማሻሻል አቋራጮችን መውሰድ የሚችሉበት ሂደት አይደለም ፣ ጊዜ እና ቁርጠኝነት ይጠይቃል ፣ የአጭር ጊዜ መፍትሄዎችን የሚሰጥዎ ማንኛውም ሰው ድር ጣቢያዎ በ Google ልክ በተሰየመው እና በ Google ቅጣት ይፈርዳል። በ AutoSEO አማካኝነት ድር ጣቢያዎ ለብዙ ንግዶች ጥሩ ውጤቶችን ለማምጣት በተሞከሩ በነጭ ባርኔጣ ቴክኒኮች አማካይነት እንደሚቀመጥ እርግጠኛ መሆን ይችላሉ ፡፡ የድር ጣቢያዎን ታይነት ማሻሻል የሽያጭ መሪዎችን ለመጨመር እና ኦርጋኒክ ትራፊክ ለማመንጨት የመጀመሪያው እርምጃ ነው ፣ ለዚህ ነው AutoSEO የጥቃት መከላከያ ስትራቴጂ በተገቢው ጊዜ በሚፈለጉ ቁልፍ ቃላት አማካኝነት ድር ጣቢያዎ በ Google ከፍተኛ ደረጃ የተሰጠው። በገጽ ላይ ማመቻቸት ሁሉም የተወሰደ እንክብካቤ ስለ ድርጣቢያ ታይነት እና ደንበኞች ምርቶችዎን ማየት ምን ያህል አስፈላጊ እንደሆነ ተነጋግረዋል። በገጽ ላይ ይዘት እንዲሁ የድር ጣቢያዎን ታይነት ላይም በእጅጉ ይነካል። ገጽ ማመቻቸት ላይ ብዙ ብዙ አለ-ይዘትዎ ምን ያህል በጥሩ ሁኔታ እንደተጻፈ ፣ በተፈጥሮ ቁልፍ የ LSI ቁልፍ ቃላት ጋር የተካተቱ ናቸው ፣ የኋላ አገናኞችን ፈጥረዋል ፣ ለሜታዳታ የተመቻቹ እና ጥሩ UX / UI ዲዛይን ያለው ድር ጣቢያ ሠርተዋል? ገጽ ላይ SEO የጎብኝዎች ድርሰቶች ትርጉም Google ን በተሻለ ሁኔታ እንዲገነዘቡት የድርጣቢያዎችን ትርጉም ትርጉም ለማሻሻል ይዛመዳል። የድር ተንከባካቢዎች እንዴት እንደሚቀርብ በመረዳት በመስመር ላይ የይዘት ቁሶችን አውድ የሚረዱ ሮቦቶች ናቸው ፡፡ ይህ የአንድ ድር ጣቢያ የኤች.ቲ.ኤም.ኤል ኤ.ዲ.አር. መመርመሪያ የትርጓሜ ትንታኔ እና የይዘት ዐውደ-ጽሑፍ ለመወሰን ሁለቱንም የውስጠ እና የወጪ አገናኞችን በመጠቀም ያካትታል። በገጽ ላይ ማመቻቸት ለመተግበር ከባድ እና አድካሚ ሊመስል ይችላል ግን ለዛ ነው AutoSEO ሕይወት አድን ነው! የእርስዎን የ SEO ደረጃ አሰጣጥን ለማሻሻል እና ትንታኔዎችዎን ከፍ ለማድረግ የሚያስፈልጉዎትን ሁሉንም ተስፋዎች ይንከባከባል። አንዴ በ AutoSEO ዘመቻ ከጀመሩ ፣ ለተሻለ ደረጃ መሻሻል መሻሻል ስለሚፈልጉ የድር ጣቢያዎ የተለያዩ ገጽታዎች ዝርዝር ዘገባ ይኖርዎታል ፡፡ ቁልፍ ቃል ጥናት ለእርስዎ ጎጆ ምርቶችዎን ወይም አገልግሎቶችዎን በመስመር ላይ ማስቀመጥ እና ጎብ toው ወደ ድር ጣቢያዎ እንደሚመጣ ማሰቡ ብቻ በቂ አይደለም። ደንበኞችዎ እርስዎን እንዲያገኙ የዳቦ ፍርፋሪዎችን መተው ያስፈልግዎታል ፡፡ እነዚያ የዳቦ ፍርግርግ ቁልፍ ቃላት ናቸው እና በሚገባ የተመረመረ የቁልፍ ቃል ስትራቴጂ እንደማንኛውም ደረጃዎን ከፍ ያደርጋሉ ፡፡ ቁልፍ ቃል ጥናት ሥነጥበብ ነው ፡፡ ከፍተኛ ድምፅ ያላቸውን ብቻ ሳይሆን ንግድዎ ለሚሠራበት ጎራ የሚጠቅሙ ቁልፍ ቃላትን ማከል የፈጠራ ጥረት ይጠይቃል ፡፡ ከጎራዎ ጋር ተዛመጅ መሆናቸውን በማረጋገጥ የረጅም-ጭራ ቁልፍ ቃላትን ከአጫጭር ጅራት ጋር ሲጠቀሙ ጥምረት እጅግ በጣም አስፈላጊ ነው ፡፡ ሰልፈር ትራፊክን ብቻ ሳይሆን ነገር ግን ወደ ሽያጭ ሊያደርጋቸው የሚችሏቸውን ቁልፍ ቃላት መፈለግ አስፈላጊነትን ተረድቷል ፡፡ የመስመር ላይ ንግድዎ በጥሩ ሁኔታ ላይ እንዳለ በቀላሉ ማወቅ ይችላሉ። ከ AutoSEO ዘመቻ ጋር ፣ የሰሜል የ SEO መሐንዲሶች ለአገርዎ ብቻ ብቻ ሳይሆን ጥሩ ትራፊክ እና ሽያጮችንም ያመነጫሉ ቁልፍ ቃላት ያመጣሉ። አፈፃፀምዎን ለመገምገም የትንታኔ ሪፖርቶች እንዲሁም በራስ-ሰር ትንታኔዎችዎ ውስጥ በራስ-ሰር ብዙ ሊታወቁ የሚችሉ እንቅስቃሴዎችን ይፈጥራል ፡፡ Semalt በውጤቶች የሚያም እና የእነሱ ባለቤት መሆን ሙሉ-ሙሉ የቁጥር ዲጂታል ግብይት ኤጀንሲ ነው ፡፡ AutoSEO የድር ጣቢያዎን ደረጃን የሚያሻሽሉባቸው መንገዶች ሁሉ ፣ ትንታኔዎቹ በአሁኑ ጊዜ ገንዘብዎ በጥሩ ሁኔታ እየተጠቀመበት መሆኑን እንዲያውቁ በአሁኑ ጊዜ እየተዋወቁ ያሉትን የቁልፍ ቃላት ቁልፍ ደረጃዎችን ይሰጣሉ ፡፡ ሀብታቸው ምንም ይሁን ምን ፣ ለሁሉም ድርጣቢያ በሚሠራበት የ SEO ቴክኒኮችን መሠረት በእያንዳንዱ ድርጣቢያ ለሁሉም ንግድ ስኬታማነት ዋስትና የሚሰጥ አንድ ዘዴ የለም ፡፡ እነዚህ ስልቶች ምን ያህሉ እየሰሩ እንደሆኑ ለማሳየት ትንታኔዎች ማካሄድ የተሻሉ ውሳኔዎችን ለማድረግ እና ተጨማሪ እገዛ በሚያስፈልጋቸው አካባቢዎች ለማሻሻል ይረዳዎታል። የግል ሴሚል ሥራ አስኪያጅ - በማንኛውም ጊዜ የሚገኝ - በኢሜል እና በቀጣይነት ዘመቻዎች እርስዎን ለማሳወቅ በኢሜል ትንታኔያዊ ሪፖርቶችን ያቀርባል ፡፡ FullSEO ከ ‹በይዘት› ፅሁፍ ውስጥ ገቢን እና ከዚያ በላይን ለማገናኘት Semalt እንዲሁም ድር ጣቢያዎን በ SEO ደረጃዎች መሠረት ሙሉ በሙሉ ለማክበር እየፈለጉ ከሆነ ሴሜል ሙሉውን ያቀርባል- እንከን የለሽ ይዘት ጽሑፍ እና የድር ጣቢያ ቅጂ በጣም ውጤታማ የሆኑ ቁልፍ ቃላት ተፈልገዋል ሊኖሩት ይችላሉ ነገር ግን እርስዎ ያስቀመጡት ይዘት ለአንባቢዎ ዋጋ የማይሰጥ ከሆነ እርስዎ ደረጃ አይሆኑም ወይም ትራፊክን አያስገኙም ፡፡ የሚስብ ብቻ ሳይሆን ፣ ነገር ግን ችግር ፈቺ እና መረጃ ሰጭ አንባቢዎቹን ለማቆየት ቁልፍ ነገር ነው ፡፡ ሴሚል የድር ጣቢያዎን ትራፊክ እና ሽያጭ እንዲሁ ምን አይነት ይዘት እንደሚጨምር በትክክል የሚያውቅ የቅጂ ጸሐፊዎች ቡድን አለው። አገናኝ ግንባታ እና ከዚያ በላይ ከ ቁልፍ ቃል ምርምር በተጨማሪ ወደ ውጤታማ SEO ዘመቻ የሚገቡ ብዙ ነገሮች አሉ። ውጤታማ የአገናኝ ግንባታ - ከገጽ ውጭ (ቴክኒካዊ SEO) አንድ አካል ነው ፡፡ መጥፎ ወይም ውጤታማ ያልሆኑ አገናኞችን በማስወገድ ድር ጣቢያዎ ከውስጡ እና ከውጭ አገናኞች በተሻለ እንደተሻሻለ ማረጋገጥ በጣም አስፈላጊ ነው ፡፡ የሴሚል ሙሉው የ ‹SEOO› መሣሪያ ለድር ጣቢያዎ ጥራት ያለው የውስጥ የውስጥ አገናኞች ብዛት እንዲሁ እንዲጨምር ለድር ጣቢያዎ ምጣኔ ከፍ እንዲል ሴሜል ሙሉ አገናኝ አገናኝን ከድር ገጽዎ ጋር በአግባቡ መያዙን ያረጋግጣል ፡፡ ከፍተኛ ዩ.አር.ኤል. ያላቸው ድር ጣቢያዎ ላይ ከፍተኛ ዋጋ ያላቸውን የኋላ አገናኞችን ማከልን ያካትታል። የድርጣቢያ ስህተቶችን ማስተካከል ብዙውን ጊዜ ድር ጣቢያዎች እንደ ኤችቲኤምኤል ካሉ ከድር ቴክኖሎጂዎች ጋር በደንብ ካልተላበሱ ሳይስተዋል ሊተላለፉ የሚችሉ ብዙ ስህተቶች ወይም የተሳሳቱ አገናኞች አሏቸው። መሰረታዊ የ Google ፍለጋ ፕሮግራም መመዘኛዎች መሟላታቸውን ለማረጋገጥ እያንዳንዱ እና እያንዳንዱ ኖክ እንክብካቤ በሚደረግበት ድር ጣቢያዎ ላይ አጠቃላይ ትንታኔ ይደረጋል። በትርጉም ትንተና አማካኝነት የሁሉም ስህተቶች ዝርዝር በሴሚል ቤት በ SEO የምህንድስና ቡድን ተስተካክሎ ይቀመጣል ፡፡ ሁሉም አስፈላጊ ለውጦች በሴልታል SEO በኩል ይነገርዎታል። ድር-አዋቂዎች በተሻለ እንዲገነዘቡት እና በተነጣጠረ የፍለጋ ቦታዎ ውስጥ ከፍ እንዲል ድር ጣቢያዎ የተመቻቸ ነው። በእያንዳንዱ መሻሻል እንዲዘምን የሚያደርግልዎ አስተዳዳሪ ለእርስዎ ተመድቧል። ምክክር እና ድጋፍ እኛ ቀደም ብለን እንደጠቀስነው ፣ ከ FullSEO ጋር በተሻለ ሁኔታ ለእርስዎ የሚጠቅመውን የ SEO ስትራቴጂ ለማቋቋም ከባለሙያዎች ቡድናችን ጋር ምክክር ያገኛሉ ፡፡ ቡድኑ ሊኖርዎት ለሚችለው ማንኛውም ጥያቄ እና ቡድን የግንኙነት መስመሮች ሁል ጊዜ ክፍት ናቸው ፡፡ የእራስዎ አቀናባሪ የ ‹የ‹ ‹‹ ‹›››››››››››› ን ን የዕለት ተዕለት ዕለታዊ እንቅስቃሴን ይከታተላል እና ዘመቻዎቹ እንዴት እየሆኑ እንደሆኑ በዝርዝር ትንታኔ አፈፃፀም ሪፖርቶች አማካኝነት በሪፖርት ማዕከሉ በኩል ያዘምኑዎታል ፡፡ የድጋፍ ቡድኑ እና የግልዎ SEO አስተዳዳሪ እርስዎ ድር ጣቢያዎን ደረጃ ለመያዝ እና የትራፊክ መጨመሩን ለማሳደግ ጠንክረው በሚሰሩበት ጊዜ ጥሩውን አገልግሎት እንዲያገኙ ዝግጁ ናቸው። የመጨረሻ ሀሳብ ሴሚል ድር ጣቢያዎን ደረጃዎችን እና ትንታኔዎችን ወደ አዲስ የስኬት ቁመት የሚወስደው አንድ-ማቆሚያ ዲጂታል ኤጀንሲ ነው። ከ AutoSEO ወይም ከ ‹FullSEO› ዘመቻ ጋር አብረው ለመሄድ ቢመርጡ በ SEO እና በድር ልማት መስክ ውስጥ ከፍተኛ ብቃት ካላቸው ባለሙያዎች ቡድን የባለሙያ ድጋፍ ያገኛሉ ፡፡ በመስመር ላይ ተገኝነትዎ ሊያምኗቸው የሚችሉት ብዙ ንግዶች እንዲበለጽጉ እና ድር ጣቢያቸው በ Google ከፍ እንዲል በረዳው በሴልታል እጅ መሆኑን ማመን ይችላሉ።
● ጎማ-የታሸገ ሄክስ ዱምቤል: በዚህ የጎማ-የታሸገ አስራስድስትዮሽ ዱብቤል ወደ ስፖርታዊ እንቅስቃሴዎ የጥንካሬ እና የመቋቋም ስልጠና ያምጡ።ሸጫጫታ ለመቀነስ እና በመሳሪያው እና በፎቅ ላይ የሚደርሰውን ጉዳት ለመቀነስ ቀላል ተረኛ የጎማ ጭንቅላት።ለቤትዎ ወይም ለቢሮዎ ጂም ፣ ካርዲዮ ፣ HIIT ስፖርታዊ እንቅስቃሴ ወይም ክብደትን ለመቋቋም የአካል ብቃት እንቅስቃሴ ለማድረግ ፍጹም። ●ጠንካራ Cast-Iron Core: ክብደቱ ከፍተኛ ጥራት ላለው ጥንካሬ እና ከአንዱ ስፖርታዊ እንቅስቃሴ ወደ ቀጣዩ አስተማማኝ መረጋጋት ጠንካራ የብረት-ብረት ኮርን ያሳያል። ጥያቄዝርዝር የሚስተካከለው ዱምቤል፣ 10.3/25 ኪ.ግ የእጅ ክብደት ለወንዶች እና ለሴቶች፣ ዱምቤል ክብደት ለቤት ጂም ● ክብደቶች በ1-ሰከንድ ውስጥ ይለዋወጣሉ: dumbbell ከ 5 ኪ.ግ ወደ 25 ኪ.ግ ሳይበታተኑ ያስተካክላል;አንድ-እጅ ኦፕሬሽን ዲዛይን፣ በ 5kg ጭማሪ (5kg/10kg/15kg/20kg/25kg) ለፈጣን ለውጥ ቀላል። ● Super 5 in 1 Structure: በ 1 dumbbell 5 የሚስተካከለው ሲሆን እነዚህም ከአምስት ባህላዊ ዱብብልሎች ጋር እኩል ናቸው፣ ይህም ገንዘብ ይቆጥብልዎታል እንዲሁም የተሻለ የስልጠና ግብ ማሳካት ይችላል። ● የኢኖቬሽን ባዮኒክስ ቴክኖሎጂ፡ መያዣው ከፍተኛ ጥንካሬ ካለው የኒሎን ቁሳቁስ እና ከሲሊኮን ብረት የተሰራ ነው።በማይንሸራተት በረዶ ህክምና፣ የእጅ ክብደት በሁሉም አቅጣጫዎች ግጭትን ያሻሽላል። ጥያቄዝርዝር የሄክስ ቅርጽ ኒዮፕሪን ዱምቤል እና ቪኒል ዲፕንግ ዱምቤል ● የበለጠ ሂደት ፍፁም ነው፡ የፍሬም ዲዛይኑ ከበርካታ ንብርብር ሂደት በኋላ፣ በፀረ-ግጭት ደህንነት ቁሶች የታጀበ፣ እና የተፅዕኖው የመሳብ አንግል መዋቅር ከባድ ተፅእኖዎችን ሊበታተን ይችላል። ● የበለጠ ኤርጎኖሚክ፡ እጀታው ለመያዝ የበለጠ ምቹ ነው፣ እና የማያንሸራተት መያዣ ንድፍ ተሻሽሏል።ከፍተኛ ጥራት ያለው የቁሳቁስ ሽፋን ገርን ለመያዝ እና ንክኪዎችን ይከላከላል ፣ በሚጠቀሙበት ጊዜ በላብ ምክንያት ምቾት አይሰማዎትም ፣ ስለሆነም በስፖርት ማራኪነት ይደሰቱ። ጥያቄዝርዝር ከ 12 ዓመታት በላይ የኢንዱስትሪ ልምድ ፣ ጥልቅ የአቅርቦት ሰንሰለት ውህደት ፣ የጁላይ ስፖርት የራሱ አስተማማኝ እና የተረጋጋ የጥሬ ዕቃ አቅራቢዎች እና የመጀመሪያ ደረጃ የምርት መሠረት አለው።
አንድ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ባለስልጣን እንደሚሉት የሚያንማር የጸጥት ሃይሎች በሰሜን ምዕራብ ራኺን ክፍለ-ግዛት የቀሩትን ሮሂንጋ ሙስሊሞች ሰብአዊ መብት መርገጡን ቀጥለዋል። ዋሺንግተን ዲሲ — አንድ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ባለስልጣን እንደሚሉት የሚያንማር የጸጥት ሃይሎች በሰሜን ምዕራብ ራኺን ክፍለ-ግዛት የቀሩትን ሮሂንጋ ሙስሊሞች ሰብአዊ መብት መርገጡን ቀጥለዋል። ሚያንማር ውስጥ በሮሂንጋዎች ላይ የሚፈጸመው የዘር ማጽዳት ተግባር እየቀጠለ ነው ይላሉ በተባበሩት መርንግስታት ድርጅች የሰብአዊ መብት ጉዳይ ዋና ጸሀፊ አንድሪው ጊልሞር።ጊልሞር ዛሬ ባወጡት መግለጫ ይህና ያሉት በቅርቡ በጎረቤት ሀገር ባንግላደሸ በተፋፈጉ የሰደተኛ ሰፈሮች ከተጠለሉ ሮሂንጋዎች ባገኙት ምመረጃ መሰረት ነው። ወደ 700,000 የሚጠጉ ሮሂንጋዎች የሚንያማ የጸጥታ ሀይሎች ከሚያደርሱባቸው ስቃይ በመሸሽ ካለፈው ነሃሴ ወር አንስቶ ባንግላደሽ ገብተዋል። የሮሂንጋ እማኞችና የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች እንደሚሉት የሀገሪቱ ወታደራዊ ሃይል በሮሂንጋዎች ላይ ግድያ አስገድዶ መድፈርና በእሳት የማጋየት ተግባር ይፈጽማል
የግብፅ ፕሬዝዳንት አብደል ፈታህ አልሲሲ በግብፅ አለመረጋጋትና ትርምስ ለመፍጠር ጥረት የሚያደርጉ ሁሉ ከድርጊታቸው ቢታቀቡ ይሻላቸዋል ሲሉ ማስጠንቀቃቸውን አልጀዚራ ዘግቧል። ተቃዋሚዎች አልሲሲ ስልጣን እንዲለቁ ይፈልጋሉ፤ እንደ ዋና ምክያት የሚያነሱት ደግሞ ሙሰኝነታቸውን ነው። ሲሲ ለአመታት ከጦር ኃይሉ ጋር በመሆን ለፕሬዝዳንቱ ቤተሰብ እና ጓደኞች ይሆኑ ዘንድ ከተገነቡ ቅንጡ ቤቶችና ከሌሎች በርካታ የግንባታ ፕሮጀክቶች ጋር በተያያዘ የሙስና ወንጀል ፈፅመዋል እያሉ ነው። ተቃውሞው ቁጣቸው እየጨመረ በሚመጣ አመፀኞች ተቀጣጥሏል። በተለይ በገጠርና ዝቅተኛ ገቢ ባላቸው አካባቢዎች በርትቷል። ህገ ወጥ ግንባታዎች ይቁሙ የመሰሉ መፈክሮች እየተሰሙ ነው። እየወጡ እንዳሉ ዘገባዎች በመላው ግብፅ 40 መንደሮች ላይ የተቀሰቀሰው አመፅ የፖሊስ የኃይል እርምጃ ሊገታው አልቻለም። ኤል ሲሲ ለአመፅ የተጠሩትን ጥሪዎች ግብፃውያን ባለመስማታችሁ አመሰግናለሁ ብለዋል። በህዝቡ እየተነሱ ያሉ ጥያቄዎችን የሪፎርሙ አካል አድርጎ መንግስት እንደሚተገብራቸውም ገልፀዋል።በስደት ላይ በሚገኘው በግብፃዊው የንግድ ሰው ሞሀመድ አሊ በተደረገው ጥሪ ተቃዋሚዎች በአልሲሲ መንግስት ላይ በማመፅ ጎዳናዎችን እንደ አውሮፓውያኑ ከ መስከረም 20 ጀምሮ እያጥለቀለቁ ነው። ፖሊስ አመፆቹን ለመበተን አስለቃሽ ጭሶችን ተጠቅሟል። እንደ ሚድል ኢስት ሞኒተር ዘገባ የግብፅ የፀጥታ ሀይሎች 400 ሰዎችን ሲያስሩ 3 ሰዎች ደግሞ ተገድሏል። አመጹ ከተጀመረ ጀምሮ የተያዙ እድሜያቸው ያልደረሰ 60 ህፃናትም ከእስር እንዲፈቱ እየተጠየቀ ነው።ህፃናቱ ከ 10 እስከ 15 ዕድሜ ሲሆኑ ሁሉም አመፁ በብዛት ከሚደረግበት ላይኛው ግብፅ ናቸው። አብዛኞቹ አመፆች በመንደሮችና በገጠራማ አካባቢዎች እየተደረጉ ያሉት ካይሮንና አሌክሳንድርያን በመሰሉ ከተሞች የፀጥታ ሀይሉ ጥብቅ ጥበቃ እያደረገ ስለሆነ ነው። ባለፈው አመት መስከረም መጨረሻ ላይ ስደት ላይ ያለው ሞሀመድ አሊ ስፋት ያለው አመፅ በጠራ ወቅት በሺዎች የሚቆጠሩ ግብፃውያን በተለያዩ ትላልቅ የግብፅ ከተማ ጎዳናዎች በመውጣት የሲሲ መንግስት ስልጣኑን እንዲለቅ ጠይቀው ነበር። በስፔን በስደት ላይ የሚገኘው ሞሀመድ አሊ፤ ሲሲ በአሁኑም አመት በአገዛዙ ላይ ግብፃውያን እንዲያምፁ ጥሪ በማድረጉ ግብፅ በአመፅ ታምሳለች። በጥሪው ሰልፈኞች በተለያዩ ግዛቶች በመውጣት ያለፉትን አመታት አመፆችንም አስታውሰዋል። አል ሲሲ በሐምሌ 2013 ነበር በወታደራዊ መፈንቅለ መንግስት የሀገሪቱን የመጀመርያ በዲሞክራሲያዊ መንገድ የተመረጡትን ሞሀመድ ሙርሲን አስወግደው ስልጣን ላይ የወጡት። (በሔኖክ አስራት፤ Ethio Fm 107.8)
ካብ ኩሉ ኩርንዓት ዓለም ዝተኣኻኸቡ ስነ ጥበበኛታት ኤርትራ ኣብ ሃገረ-ስዊዘርላንድ ከተማ ግሪንከን ካንቶን ሶሎቶርን ድሕሪ ዘካየድዎ ቀዳማይን መስራቲን ዋዕላ ትማሊ 21 ለካቲት 2020 ‘ማሕበር ስነ ጥበባውያን ኤርትራውያን ደለይቲ ፍትሒ’ ከምዝመስረቱ ኣቐዲሙ ተገሊዑ ኔሩ። ኣብቲ ገዳይምን መንእሰያትን ስነ ጥበበኛታት ዝተሳተፍዎ ፈለሚ ዋዕላ፡ ክልተ ዓንዲ ሕጊን ራእን ዕላማታትን ዝሓዘለ መወከሲ ሰነዳት ክቐርብ እንከሎ ተሳተፍቲ ኣብ ዲሞክራስያዊ መትከላት ዝተሃንጸ ሰፊሕ ዘተ ክተዓትን ልዝብን ብምክያድ ኣብቲ ሰነዳት ምምሕያሻትን ብምግባር ቅዋም ኣጽዲቑ። በቲ ዝጸደቐ ዓንዲ ሕጊ መሰረት ድማ፡ እቲ ጉባኤ 7 ዝኣባላታ ፈጻሚት ሽማግለን 4 ተጠባበቕትን ብምምራጽ። እዚ ጉባኤ’ዚ ዕውት ንኽኸውን፡ ብዝተፈላለየ ዓቕምን ኣበርክቶን፡ ተርኦም ንዝተዋጽኡ ኩላቶም ኣካላት፡ ምስጋንኡ ኣቕሪቡ። እቶም ተመሪጾም ዘለዉ ፈዓሚት ሽማግለን ተጠባበቕትን መርሃዊት ኪዳነ፡ ዓንዲት ዑቕባይ፡ ፍጹም በራኺ፡ ሰናይት ሓድሽ፡ ሮሞዳን ሺፋ፡ ክፍሎም ይከኣሎ፡ ሃይለ ገዙ፡ ተመስገን ያሬድ፡ ግርማይ ተኽለማርያም፡ መሓመድ ኣቡበከርን ኣማን ብርሃነን እዮም። ኣብ ነንሕድሕዶም ኣኼባ ብምግባር ድማ ኣቦ/ኣደ ወንበርን ካልእ ሓላፍነታትን ክመቓርሑ እዮም። ኣብ መኽፈቲ እቲ ዋዕላ ኣባል ኣወሃሃዲት ኮሚቴ መርሃዊት ኪዳነ ኣብ ዘስመዓቶ ቃል፡ ዋዕለኛታት እቲ ኣኼባ ክውን ክኸውንን ኣብቲ ኣኼባ ክሳተፉ ዝገበርዎ ውልቃዊ ተበግሶን ብምምስጋን ስነ ጥበበኛታት ሕድሕዳዊ ምውድዳርን ህልኽን ኣወጊዶም ንርሑቕ ብምጥማት ንህዝቦም ፍቕርን ሓልዮትን ፍትሕን ንኽነግሱ ክጽዕሩ ተላብያ። ከምቲ ርሑቕ መገዲ ብሓደ ስጉምቲ ዝጅመር ስነ ጥበበኛታት ድማ ካብ ሎሚ ጀሚሮም ነቲ ፍትሓዊ ዝኾነ ጉዕዞ ለውጢ ብሓባር ክጅምርዎ ነቲ ብዙሕ ነገር ዝጽበ ህዝቢ ኣርኣያ ክኾንዎን ድማ ጸዊዓ። ኣብቲ ኣኼባ ብሃራት ስነ ጥበበኛታት ናይ ክብሪ ዕዱማትን ተወልደ ረዳ፡ ኣብራር ዑስማን፡ መምህር ንጉሰ ሃይለ ተረኺቦም ኔሮም። መምህር ንጉሰ ኣብ ዝሃብዎ ቃል ከምዚ ዓይነት ኣኼባ ከካይዱ ካብ ነዊሕ እዋን ይሓስብዎ ከምዝነበሩ ሕጂ ግን ሳላ ደቆም ክዉን ኮይኑ ኣብ ተግባር ብምውዓሉ ከምዘሐጉሶም ገሊጹ። ስነ ጥበባዊ ተወልደ ረዳ ብወገኑ ብዛዕባ እቲ ዋዕላ ምስ ሰምዐ ኣዝዩ ከምዘሐጎሶን መንእሰያት ኣቦታት ኣለዉና ዘማኽሩ ኢሎም ምሕሳቦም ብምምስጋን እታ ተበጊሳ ዘላ ማሕበር ቀጻልነታ ክረጋገጽ ኣብ ጎና ደው ከምዝብሉ ገሊኡ። ስነ ጥበባዊ ኣብራር ዑስማን ብወገኑ ስነ ጥበብ ማለት ፍቕሪ ውህደትን ምትእስሳርን ማለት ከምዝኾነ ብምግላጽ ስነ ጥበበኛታት ድማ ነዚ ብግብሪ ንህዝቦም ከርእይዎ ተላብዩ። ዕላማ ማሕበር ስነ ጥበባውያን ኤርትራውያን ደለይቲ ፍትሒ ምዕቃብ ባህልን ክብረታትን መላእ ሕብረተሰብ ኤርትራ፡ ምምዕባል ስነ ጥበብን ምሕላው መሰላት ስነ ጥበበኛን፤ ምህናጽ ስነ ጥበባዊ ትካላትን ክለባትን ኣብ ውሽጢ ዓድን ደገን፤ ኣብ ሓቅነት ምምርኳስን ወገን ህዝቢ ምሓዝን፤ ጎስጓስ ሕብረተሰብ ኣብ ህሉው ኩነታት ሃገር፤ መሰል ድርሰት ኤርትራዊ ስነ ጥበብ ምዕቃብ፤ ምምዕባል ዓቕሚ ስነ ጥበበኛታት እዩ። ማሕበር ስነ ጥበባውያን ኤርትራውያን ደለይቲ ፍትሒ ካብ ሃይማኖት፡ ብሄር፡ ዓሌት፡ ጾታን ካልእ ፈላላይ ነገራትን ነጻ ኮይኑ ብኣንጻሩ ፍልልያት ብምውጋድ ንምዕባለ ስነ ጥበብ መላእ ሕብረተሰብ ክሰርሑ ተሰማሚዖም። እቲ ማሕበር ኣብ ኩሉ ዓውዲ ዝነጥፉ ስነ ጥበበኛታት፡ ደረፍቲ፡ ሙዚቀኛታት፡ ጸሓፍቲ፡ ተዋሳእቲ፡ ቀባእቲ፡ ሰኣልቲ፡ ገጠምቲን ካልእን ኮታስ ኣብ ኩሉ ስነ ጥበብ ዝዋስኡ ኤርትራውያን ሰብ ሞያ ዘሳትፍ እዩ። ብሕጋጋት እቲ ማሕበር ዝቕየድ ኩሉ ኤርትራዊ ስነ ጥበባዊ ኣባል ክኸውን ይኽእል።
ለከት ያጣው የወያኔ ጭካኔ እና የማይነጥፈው የሕዝብ ትእግስት ኢትዮጵያን ወዴት እየወሰዷት እንደሆነ አገሪቱ ዛሬ ያለችበት ውጥንቅጥ ሁኔታ በግላጭ ያሳያል። በመግደል አባዜ የተለከፉት የወያኔ ተጋዳላዮች ዛሬም መግደላቸውን ቀጥለዋል። ለይስሙላ በወረቀት ላይ የሰፈረው ሕገ-መንግስት እና በውስጥ የያዛቸው መሰረታዊ የሆኑ የሰብአዊ መብቶችና ነጻነቶች ለወያኔ ተጋዳላዮች ምናቸውም እንዳልሆነ በተደጋጋሚ እያሳዩን ነው። በአገሪቱ ውስጥ ያለው የሕግ ማእቀፍ (አንዳንዶቹ ሕጎች በራሳቸው የማፈኛ መሳሪያ ተደርገው የተቀረጹ መሆኑ ሳይረሳ) ለወያኔ ተጋዳላዮችና ተራ ካድሬዎች ሳይቀር ምናቸውም አይደለም። ሲሻቸው ይገድላሉ፣ ያፍናሉ፣ ይሰውራሉ፣ ባደባባይ ይደበድባሉ፣ ሺዎችን በየማጎሪያው ያሰቃያሉ፣ ያዋርዳሉ፣ ቅጥ ባጣ መልኩ ይሞስናሉ፣ ይሰርቃሉ፣ ይዘርፋሉ፣ ያስፈራራሉ፣ ሴቶችን ይደፍራሉ፣ ህዝብን ያሸብራሉ፣ ምኑ ቅጡ። እንግዲህ የሕግ አምላኩ ሲሞት ሥርዓት አልበኝነት ይነግሳል፤ ዘራፊዎች ይበራከታሉ፣ ገዳዮች ባደባባይ ገድል ይጥላሉ፣ ሙሰኞች አገርን እና ሕዝብ ይቆጣጠራሉ፣ የአገር ሃብት ያሸሻሉ፣ በድሆች ጉሮሮ ላይ ቆመው በሃብት ይጨማለቃሉ። በዚህ ላይ ጎጠኝነት ሲታከልበት መላ ቅጡ ይጠፋል። ብዙዎቹ እየከሰሙ ያሉ አገሮች (failed states) እየተባሉ በየጊዜው የሚጠቀሱ አገሮች በእነዚህ ችግሮች ውስጥ የሚማቅቁ ናቸው። ወያኔም ለኢትዮጵያ የዋለላት አንዱ ትልቁ ነገር ከእነዚህ አገሮች ተርታ እንድትሰለፍ ማድረጉ ነው። እንደ ታላቅ ስኬት የሚቦተለክለት የዛሬዋ የኢትዮጵያ ልማት ውስጡ ሲገባ ላዩ አሮ ውስጡ ሊጥ እንደሆነ ዳቦ ስለመሆኑ ምንም ጥናትና የተለየ ምርምር ሳይጠይቅ 95% የሚሆነውን የአገሪቷን ሕዝብ ኑሮ ማየት በቂ ነው። አንጻራዊ በሆነ መልኩ በወያኔ ዘመን የመጀመሪያዎቹ አሥር አመት ውስጥ እንኳን የኢትዮጵያ ሕዝብ ያገኛቸው የነበሩትን እንደ መብራት፣ ውኃ፣ የጤና አገልግሎትና ሌሎች መሰረታዊ ፍላጎቶቹ ዛሬ ተነፍጓል። የደብል ዲጂት ልማታዊነት ነጠላ ዜማዎች በወያኔ እና ባጫፋሪዎቹ የአለም አቀፍ ‘የልማት’ ተቋማት ጆሮዋችን እሲደነቁር በሚዘፈንበት በዚህ ወቅት የኢትዮጵያ ሕዝብ አስከፊ በሆነ የኑሮ ዋስትና ማጣት ውስጥ ሆኖ የመከራ እንቆቆውን እየተጋተ ይገኛል። የእነዚህ የመሰረታዊ አቅርቦቶች በዚህ ደረጃ ላይ አቆልቁሎ መገኘት አንኳን የቀለም አብዮት፤ ሌላም መገለጫ የሌላቸው አመጾችንና እልቂትን ቢወልድና በአገሪቱን ወደ ከፋ ብጥብጥ ቢከት የሚገርም አይደለም። ይሁንና እንደ ወያኔ ያለ ክፉ፣ መረን የማያውቅ እና ጨካኝ ሥርዓት እድለኛ ሆኖ ሆደ ሰፊ፣ የማይቻለውን ሁሉ የሚችል፣ ጨዋና ታጋሽ ሕዝብ ሲጋጥመው ጭካኔውን እያበረታ፣ የአፈና ሰንሰለቱን እያጠበቀ፣ አባላቱን በአሃብት እያሞሰንነና እያጎለበተ ይንሰራፋል። የአገር መፍረስ ወይም አደጋ ላይ መወደቅ የራሳቸውን ጥቅም አደጋ ላይ እስካልጣለ ድርስ ግድ የማይሰጣቸው ጎጠኛ ፖለቲከኞችም በደሃው ሕዝብ ላይ ይሰለጥኑበታል፤ ይሰይጥኑበታልም። ሰሞኑን በአገሪቱ ውስጥ የሚስተዋለው የፖለቲካ ድባብ ወያኔ ከመቼውም ጊዜ በከፋ ሁኔታ አገሪቱን የሚዘውርበት መሪ ከቁጥጥሩ ውጭ እንዳይወጣ እየተውተረተረ ያለ መሆኑን ነው። ለዚህም ይመስላል ሰላማዊ ሰልፍ ለማካሄድ ባንዲራና መፈክር ይዘው በተንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲ አባላት፤ በተለይም የሰማያዊ ፓርቲ አባላትን አስሮ እያሰቃየ ያለው። ለዚህም ነው በማኅበራዊ ድኅረ ገጾች በተለያዩ አገራዊ ጉዳዮች ላይ የውይይት መነሻ ሃሳቦችን እያጫሩ ሕዝቡ እንዲወያይ ይጋብዙ የነበሩ የዞን 9 አባላትን ለቃቅሞ አጉሮ እያሰቃያቸው የሚገኘው። ይህም አልበቃ ብሎ ባለፉት ሦስት እና አራት ቀናት ውስጥ ሰላማዊ በሆነ መንገድ ጥያቄ (ጥያቄያቸው ምንም ይሁን ምን) እያቀረቡ ያሉ የኦሮሚኛ ቋንቋ ተናጋሪ ዩንቨርሲቲ ተማሪች ላይ የተለመደውን የጭካኔ እርምጃ እየወሰደ ያለው። ከተለያዩ መገናኛ ብዙሃን እንደተገለጸው ከሆነ በርካታ ተማሪዎች በታጠቁ ሃይሎች የጭካኔ እርምጃ ለከባድና ቀላል የአካል ጉዳት ተዳርገዋል። በተለይም በአንቦ ከተማ ተማሪዎች በግፍ ተገድለዋል። የወያኔ መንግሥት ሥልጣን ከያዘበት ጊዜ አንስቶ በተማሪዎች ላይ ተደጋጋሚ የጭካኔ እርምጃዎችን ወስዷል። በመላ አገሪቷ በወያኔ እርምጃዎች ከተጠቁት ተማሪዎች ውስጥ ግን ትልቁን ግፍ የተቀበሉት በኦሮሚያ ክልል ውስጥ የሚገኙ ተማሪዎች ስለመሆናቸው የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን የሚመለከቱ ሪፖርቶች ይመሰክራሉ። በሥራዬ አጋጣሚ እኔም ይህን አረጋግጫለሁ። ዛሬ ላለንበት ጠቅላላ አገራዊ ክሽፈት፣ ውርደት እና የመከራ ሕይወት ከላይ እንደጠቀስኩት ለከት ያጣው የወያኔ ጭካኔ እና አፈና፤ እንዲሁም የአለማችን ተጭባጭ ሁኔታ ብቻ ሳይሆን የማይነጥፈው የሕዝብ ትእግስት እና ዝምታም ትልቁን አስተዋጾ አድርጓል። በኦሮሚያ ክልል በሚገኙ ተማሪዎች ላይ፣ በጋዜጠኞች ላይ፣ በሰብአዊ መብት ተሟጋቾች ላይ፣ በተቃዋሚ ፓርቲዎች አባላትና ደጋፊዎች ላይ፤ እንዲሁም በኃይማኖት መሪዎች ላይ እየደረሰ ያለውን ግፍና በደል በጋራ ልናወግዘው እና ልንታገለውም ይገባል። በፍትሕ እና በኢ-ፍትሐዊነት፣ በጭቆና እና በነፃነት መካከል ገለልተኛ ሆነው የሚንጠለጠሉበት ገመድ ወይም የሚቆዩበት ደሴት የለም። ፍትሕ ሲጓደል እያዩ እንዳላዩ መሆን በራሱ ኢ-ፍትሐዊነት ነው። መብት ሲጣስ እያዩ እንዳላዩ መምሰል በራሱ የጣሹ ግራ እጅ መሆን ነው። ንጹሃን ዜጎች በግፍ ሲገደሉ፣ ሲደበደቡ፣ ሲታሰሩ እና በሃሰት ክስ እየተፈረደባቸው በእስር ሲማቅቁ እያዩ ገለልተኛ መሆን አይቻልም። የፖለቲካ ገለልተኝነትን እና ለፍትሕ፣ ነጻነት እና ለህሊና መቆምን ባናምታታቸው ጥሩ ነው።
ትላንት በፌስቡክ ገፄ ላይ የትእምት (EFFORT) ድርጅቶች በመንግስት መወረስ እንዳለባቸው ለመጠቆም ሞክሬ ነበር። ለዚህ ያቀረብኳቸው ምክንያቶችና ማስረጃዎች እንዳሉ ሆነው እነዚህን ድርጅቶች መውረስና ወደ ግል እንዲዛወሩ ማድረግ ምን ፋይዳ አለው? በሀገሪቱ ፖለቲካና ኢኮኖሚ ላይ ምን ዓይነት አሉታዊ ሆነ አዎንታዊ ተፅዕኖ ሊፈጥር ይችላል? እና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮችን በዝርዝር መመልከት ያስፈልጋል። በቅድሚያ ግን ስለ ትእምት (EFFORT) ድርጅቶች አጠቃላይ ባህሪ የተወሰነ ግንዛቤ ሊኖረን ይገባል። ለዚህ ደግሞ ከትእምት (EFFORT) ድርጅቶች የመሰቦ ሲሚንቶ ፋብሪካን እንደ ማሳያ በመውሰድ እንመልከት። በመቐለ ዩኒቨርሲቲ በቢዝነስ አመራር ሙያ (Business Administration) የሁለተኛ ዲግሪ ትምህርት በምማርበት ወቅት “Operation Management” የሚባለውን ኮርስ ያስተማረኝ አንድ የውቅሮ ተወላጅ የሆነ መምህር ነው። ይህ ስሙን የማልጠቅሰው መምህር የመሰቦ ሲሚንቶ የገበያ ስትራቴጂን እንደ ምሳሌ በመጥቀስ የተናገረው ነገር መቼም ከአዕምሮዬ አይጠፋም። ነገሩ እንዲህ ነው፤ የመሰቦ ሲሚንቶ በመቐለ ከተማ የሚሸጥበት ዋጋ በአዲስ አበባ ከሚሸጥበት ዋጋ በሁለት ብር ይበልጣል። በዚህ መሰረት የመሰቦ ሲሚንቶ መቐለ ላይ 300 ብር የሚሸጥ ከሆነ ከፋብሪካው 700 ኪ.ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው አዲስ አበባ ደግሞ 298 ብር ይሸጣል። ይህ “dumping” እንደሚባልና ሕገ-ወጥ ተግባር መሆኑን ስናገር መምህሩና የአካባቢው ተወላጅ የሆኑ ተማሪዎች በሙሉ “No” በማለት በአንድ ድምፅ ተቃወሙኝ። ቀጠልኩና “እሺ.. የመቐለ ከተማ ሲሚንቶ ተጠቃሚዎች ያለ አግባብ በድርጅቱ እየተበዘበዙ ነው” ስላቸው አሁንም በአንድ ተቃወሙኝ። በመጨረሻም መምህሩ ያነሳሁትን ጥያቄ ሆነ ሃሳብ በሚያጣጥል መልኩ “ይህ የመሰቦ ሲሚንቶ የገበያ ስልት (Market Strategy) ነው” በማለት በተግሳፅ ተናገረኝ። በመሰረቱ የሲሚንቶ ፋብሪካ ምርቱን የሚሸጥበት ገበያ ከ300 ከ.ሜትር በላይ የሚርቅ መሆን እንደሌለበት የዘርፉ ምሁራን ይገልፃሉ። ምክንያቱም ሲሚንቶ በባህሪው ከባድ (Bulky) ምርት ስለሆነ ከ300 ኪ.ሜ በላይ በትራንስፖርት አጓጉዞ መሸጥ ለከፍተኛ የትራንስፖርት ወጪ ይዳርጋል። መሰቦ ሲሚንቶ ግን ምርቱን በመኪና 700 ኪ.ሜ ርቀት ላይ ወደምትገኘው አዲስ አበባ አምጥቶ መቐለ ላይ ከሚሸጥበት ዋጋ የሁለት ቅናሽ አድርጎ ይሸጣል። በዚህ መሰረት፣ አንደኛ፡- መሰቦ ሲሚንቶ ምርቱን አዲስ አበባ ድረስ ወስዶ የትራንስፖርት ወጪውን ሳይጨምር በሁለት ብር ቅናሽ መሸጡ በሕገ-ወጥ ተግባር እንደተሰማራ ያሳያል፣ ሁለተኛ፡- መቐለ ላይ ያለው የመሰቦ ሲሚንቶ መሸጫ ዋጋ ከአዲስ አበባው የመሸጫ ዋጋ በሁለት ብር የሚበልጥ ከሆነ ድርጅቱ የከተማዋን ነዋሪዎች ያለአግባብ እየበዘበዘ መሆኑን ያሳያል። ከላይ በተጠቀሰው መሰረት፣ መሰቦ ሲሚንቶ የሚከተለው የገበያ ስልት (Market Strategy) ከሕግም ሆነ ከቢዝነስ አንፃር ፍፁም የተሳሳተ ነው። ከሕግ አንፃር የመሰቦ የገበያ ስልት ሌሎች የሲሚንቶ ፋብሪካዎችን ቀስ በቀስ ከገበያ በማስወጣት የምርቱን ገበያ በበላይነት ለመቆጣጠር ያለመ ነው። ከዚህ በተጨማሪ፣ በአካባቢው ማህብረሰብ ላይ ያልተገባ የዋጋ ጭማሪ በማድረግ ይበዘብዛል። እንዲህ ያለ የገበያ ስልት የድርጅቱን ተወዳዳሪነት ከማሳደግ ይልቅ ለኪሳራ ይዳርገዋል። ይሁን እንጂ ነባር የሲሚንቶ ፋብሪካዎች ከገበያ ከመውጣት ይልቅ ብዛት ያላቸው አዳዲስ ፋብሪካዎች ተከፈቱ። የመሰቦ ሲሚንቶ ፋብሪካም በሚፈለገው ደረጃ ተወዳዳሪ ባይሆንም እንኳን በኪሳራ ምክንያት ከገበያ አልወጣም። ለምን? አስታውሳለሁ… ደርባ ሲሚንቶ ወደ ገበያ በገባበት ወቅት በሀገራችን ከፍተኛ የሆነ የሲሚንቶ ምርት እጥረት ተከስቶ ነበር። በተመሳሳይ በመቐለ ከተማ ነዋሪዎች የሲሚንቶ ምርት ለመግዛት ለብዙ ቀናት ወረፋ የሚጠብቁበት ወቅት ነበር። በዚህ ወቅት ነው እንግዲህ ደርባ ሲሚንቶ ምርቱን በራሱ ትራንስፖርት ለመቐለ ከተማ ተጠቃሚዎች እንደሚያቀርብ ያስታወቀው። ይህን ተከትሎ አብዛኞቹ ሲሚንቶ ፈላጊዎች ከደርባ ሲሚንቶ ጋር የግዢ ስምምነት ማድረግ የጀመሩት። በዚህ ምክንያት በወረፋና በሰልፍ ሲንያንገላታቸው የነበረውን መሰቦ ሲሚንቶ ፋብሪካ ዞር ብሎ የሚያየው ጠፋ። መሰቦ የትእምት (EFFORT) አባል ድርጅት እንደመሆኑ መጠን ዋና ስራ አስኪያጁ ከፍተኛ የህወሓት ባለስልጣን ነው። ይህ ባለስልጣን ለኢትዮጵያ ንግድ ባንክ መቐለ ቅርጫፍ ዋና ስራ አስኪያጅ ቀጭን ትዕዛዝ አስተላለፈ። ትዕዛዙም “በመሰቦ ሲሚንቶ ላይ ፊታቸውን በማዞር ከደርባ ሲሚንቶ የግዢ ውል ለሚገቡ የመቐለ ከተማ ነዋሪዎች የባንክ ሲፒኦ (CPO) እንዳይሰጣቸው” የሚል ነበር። በዚህ መልኩ በህወሓት ከፍተኛ ባለስልጣናት ጣልቃ-ገብነት ምክንያት መሰቦ ሲሚንቶ የተሳሳተና ሕገ ወጥ የሆነ የገበያ ስልቱን ይዞ እንዲቀጥል ያደርጉታል። ስለዚህ እንደ መሰቦ ሲሚንቶ ያሉ የትእምት (EFFORT) ድርጅቶችን መውረስና ወደ ግል እንዲዘዋወሩ ማድረግ ምን ፋይዳ አለው? 1ኛ፡- የትእምት (EFFORT) ድርጅቶች የሀገሪቱን ኢኮኖሚ በበላይነት ለመቆጣጠር በሚከተሉት ስልት ምክንያት በተለያዩ የቢዝነስ ዘርፎች የሚያሳድሩትን አሉታዊ ተፅዕኖ ማስወገድ ይቻላል። በዘርፉ የሚታየውን የፖለቲካ ጣልቃ ገብነት ያስቀራል። በመሆኑም በዘርፉ አዳዲስ የቢዝነስ ተቋማት እንዲሰማሩ ያስችላል። እንዲሁም የሀገር ውስጥና የውጪ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ ምቹ ሁኔታ ይፈጠራል። 2ኛ፡- ድርጅቶቹ ወደ ግል ሲዘዋወሩ በምርት ዋጋና ጥራት ተወዳዳሪ የሚያደርጋቸውን የገበያ ስልት ይቀይሳሉ። በመሆኑም ምርቶቻቸውን ለአካባቢው ማህብረሰብ በተመጣጣኝ ዋጋ ያቀርባሉ። ከዚህ በተጨማሪ፣ በገበያው ውስጥ ተወዳዳሪና ትርፋማ ስለሚሆኑ ለአካባቢው ማህብረሰብ ሆነ ለሀገሪቱ አሁን ካለው በተሻለ ሁኔታ ተጨማሪ የሥራ እድል ይፈጥራሉ። 3ኛ፡- የትእምት (EFFORT) ድርጅቶችን ወደ ግል በማዘዋወር መንግስት ገንዘብ ያገኛል። በዚህ መሰረት፣ በመሰረተ-ልማት ግንባታ አስተዋፅዖ ከማበርከቱ በተጨማሪ ፍትሃዊ የሃብት ክፍፍልን ከማረጋገጥ አንፃር የራሱ የሆነ ሚና ይኖረዋል። ከላይ በተገለፀው መሰረት፣ መንግስት የትእምት (EFFORT) ድርጅቶችን በመውረስ ወደ ግል ባለሃብቶች ማዘዋወሩ የህወሓት ባለስልጣኖች እያገኙት ያለውን ያልተገባ ጥቅም ያስቀራል። እነዚህ ድርጅቶች ቢወረሱ የሚጎዱት የተወሰኑ የህወሓት አመራሮች እና አባላት ናቸው። ከዚያ በተረፈ ግን እንደ ክልል የትግራይ ሕዝብ ይጠቀማል። እንደ ሀገር ደግሞ ለኢትዮጵያ የተሻለ ነገር ይዞ ይመጣል። ሌላው ቢቀር የህወሓትን አድሏዊ ድጋፍ፥ ማጭበርበርና ኪራይ ሰብሳቢነት ያስቀራል። በአጠቃላይ “EFFORTን” መውረስ ከሀገሪቱ ኢንዱስትሪ ውስጥ ጥገኛ ተውሳክን እንደማስወገድ ነው። እነዚህ ድርጅቶች እስካሁን ባሉበት ሁኔታ በኢኮኖሚው ውስጥ ከጥገኛ ተውሳክ የተለየ ሚና የላቸውም። በመጨረሻም፣ አንዳንድ የትግራይ ልሂቃን “የትእምት (EFFORT) ድርጅቶች የሚወረሱት በእኛ መቃብር ላይ ነው” የሚል አቋም የሚያራምዱበትን በተመለከተ ቀደም ሲል የጠቀስኩትን መምህርና ተማሪዎች ማስታወስ ይበቃል። እንኳን የትግራይ ሕዝብን ጥቅምና ተጠቃሚነት የሚማሩትን ሆነ የሚያስተምሩትን ፅንሰ-ሃሳብ መገንዘብ የተሳናቸው ስለመሆናቸው ጥርጥር የለውም።
የሩስያው ፕሬዚዳንት ቭላዲሚር ፑቲንና የዩናይትድ ስቴትሱ አቻቸው ዶናልድ ትረምፕ በአንድ፣ ሶስተኝ ሀገር ተገናኝተው የመነጋገር ሥምምነት እንዳለ የሩስያ ባለስልጣኖች ጠቁመዋል። ዋሺንግተን ዲሲ — የሩስያው ፕሬዚዳንት ቭላዲሚር ፑቲንና የዩናይትድ ስቴትሱ አቻቸው ዶናልድ ትረምፕ በአንድ፣ ሶስተኝ ሀገር ተገናኝተው የመነጋገር ሥምምነት እንዳለ የሩስያ ባለስልጣኖች ጠቁመዋል። ስለጉብኝቱ ዛሬ ይፋ የተደረገው የዩናይትስድ ስቴትስ ብሄራዊ የጸጥታ አማካሪ ጆን ቦልተን ከፑቲንና ከሌሎች ከፍተኛ የሀገሪቱ ባለልስጣኖች ጋር ለመነጋገር ሞስኮ በሚገኙበት ወቅት ነው። የክረምሊን የውጭ ፖሊሲ ረዳት ዩሪ ኡሻኮቭ ስለትረምፕና ፑቲን ተገንኝቶ መነጋገር ጉዳይ ነገ ሀሙስ በዝርዝር ይገለፃል ብለዋል። ትረምፕ እአአ በመጪው ሀምሌ 11 እና 12 ቀናት በኔቶ /በሰሜን አትላንቲክ ቃል ኪዳን ሀገሮች ድርጅት/ ጉባዔ ከተሳተፉና ብሪታንያን ከጎበኙ በኋላ ቪየና ወይም ሄሲንኪ ከሩስያው መሪ ጋር ሊገናኙ እንደሚችሉ ተገልጿል።
ትናንት ታስቦ የዋለውን የዓለም የኤድስ ቀን አስታክኮ የተባበሩት መንግሥታት ፀረ-ኤድስ መርሃግብር ባወጣው ሪፖርት ባለፉት ሰላሣ ዓመታት በኤድስ ምክንያት ከሃያ አምስት ሚሊየን በላይ ሰው በመላው ዓለም ሕይወቱ ማለፉን ገልጿል፡፡ አፍሪካና ኤድስ በሌላ በኩል ግን ኤድስን በመዋጋት የተሣካ ሥራ አከናውነዋል ከሚባሉት ሃገሮች አንዷ በሆነችውና በወረርሽኙ ክፉኛ በተጎዳችው ኢትዮጵያ የሥርጭቱ መጠን ከአሥርና አሥራ አምስት ዓመታት በፊት እንደነበረ ከሚነገረው ሰባት ከመቶ ዛሬ ወደ 1.3 ከመቶ መውረዱ ተነግሯል፡፡ ኢትዮጵያ የእናቶችንና የሕፃናትን ሞት በመቀነስ በኩል ሰፊ ሥራ እያከናወነች መሆኑን በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የሕዝብ ግንኙነት ምክትል ኃላፊው አቶ ተገኔ ረጋሣ ለቪኦኤ ገልፀዋል፡፡ ለዝርዝሩ ከላይ የተያያዘውን የድምፅ ፋይል ያዳምጡ፡፡ Obama World AIDS Day በሌላ በኩል ደግሞ የዩናይትድ ስቴትስ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ኅዳር 22ን የዓለም የኤድስ ቀን ሆኖ በመላ የዩናይትድ ስቴትስ ግዛቶች ታስቦ እንዲውል ሰሞኑን በፊርማቸው ባወጡት አዋጅ ጦርነቱ ዓለምአቀፍ ጦርነት መሆኑን አመልክተው በጦርነቱ ውስጥ አሜሪካ በመሪነቷ እንደምትቀጥል አረጋግጠዋል፡፡ (የፕሬዚዳንታዊውን አዋጅ ሙሉ ቃል ለማንበብ ከታች ያለውን ማገናኛ ተጭነው ይከተሉ)http://www.whitehouse.gov/the-press-office/2013/11/27/world-aids-day-2013
176 ሰዎችን አሳፍሮ ሲጓዝ የነበረው የዩክሬን ዓለማቀፍ አየር መንገድ ንብረት የሆነው ቦይንግ 737 ፕሌን ዛሬ ረቡዕ ታህሳስ 29 ቀን 2012 ዓ.ም ማለዳ ላይ ከቴህራን አየር ማረፊያ በተነሳ በጥቂት ደቂቃዎች ውስጥ ተከስክሶ ያሳፈራቸው ሰዎች በሙሉ በአደጋው ሞተዋል፡፡ በፕሌኑ ላይ ከነበሩ ተጓዦች ዘጠኑ የበረራ ሰራተኞች ናቸው፡፡ የዩክሬን ሚዲያዎች ቀደም ብለው ባወጡት ሪፖርት ተሳፋሪዎቹ 180 እንደነበሩ ዘግበው ነበር፡፡ ፕሌኑ ከኢራን ተነስቶ ወደ ዩክሬን፣ ኬቭ በመብረር ላይ ነበር፡፡ በአሁኑ ወቅት የአደጋ ጊዜ ሰራተኞች ፐሌኑ ወደተከሰከሰበት ስፍራ አምርተው ስራ ቢጀምሩም የአካባቢው ነበልባል ግን በፍጥነት ወደ ተግባር ለመግባት እንዳላስቻላቸው የሲኤንኤን መረጃ ያመለክታል፡፡ የተከሰከሰው ፕሌን አራት ዓመት ተኩል የአገልግሎት እድሜ ያለው ነው፡፡ የመከስከሱ ምክኒያት የቴክኒክ ችግር እንደነ የኢራን ሚያዎች ዘግበዋል፡፡ ይሁን እንጂ የቦይንግ ቃል አቀባይ ኩባንያው መረጃዎችን ገና በማሰባሰብ ላይ እንደሚገኝ ነው የተናገሩት፡፡ አደጋው የተከሰተው ከሳምንታት በፊት ከኃላፊነት የተነሱትን የቦይንግ ዋና ስራ አስፈጻሚ ዴኒስ ሙሊንበርግን በመተካት የተሰየሙት ዴቪድ ካልሆን ስራቸውን በይፋ ለመጀመር በመንደርደር ላይ ባሉበት ወቅት ነው፡፡ ግዙፉ የአሜሪካ አቪዬሽን ኩባንያ-ቦይንግ 346 ሰዎች የሞቱበት ሁለት የ737 ማክስ አይሮፕላኖች አደጋ ከተከሰተ ወዲህ ፈተና ውስጥ መግባቱ ይታወቃል፡፡ በኢንዶኔዢያው ላዮን ኤይር እና በኢትዮጵያ አየር መንገድ ላይ ከተከሰቱት ከነዚህ አደጋዎች በኋላ በመላው ዓለም የ737 ማክስ አይሮፕላኖች ከስራ ውጭ መደረጋቸው ይታወሳል፡፡
ከጃንዋሪ 24 እስከ 27 ቀን 2022 ሜድላብ መካከለኛው ምስራቅ በዱባይ የዓለም ንግድ ማእከል በታቀደለት መርሃ ግብር ተካሂዶ ነበር ፣ የሲኖኬር ዓለም አቀፍ የሽያጭ ቡድን እና የሕንድ ንዑስ ቡድን ወረርሽኙን በማሸነፍ ለመሳተፍ ወደ ዱባይ ሄደ ። የአረብ አለም አቀፍ የህክምና መሳሪያዎች ኤግዚቢሽን አስፈላጊ አካል እንደመሆኑ፣ ከ50 በላይ ሀገራት ጎብኚዎችን የሚያስተናግድ የሜድላብ ህዝብ ብዛት። ሲኖኬር 36 ካሬ ሜትር ቦታ ያለው ጥሬ የጠፈር ዳስ አዘጋጅቷል "በዓለም ግንባር ቀደም የሜታቦሊክ በሽታን ለይቶ ማወቅ ባለሙያ" በሚል መሪ ቃል እና ተከታታይ የኢንዱስትሪ መሪ ምርቶችን ወደ ኤግዚቢሽኑ አምጥቷል, እንደ የቤት ውስጥ ጥቅም ላይ የሚውሉ ባለብዙ-ተግባር ማወቂያ ምርቶች ለ ሥር የሰደዱ በሽታዎች እንደ የደም ግሉኮስ መቆጣጠሪያ፣ የደም ቅባት መቆጣጠሪያ፣ ዩሪክ አሲድ መቆጣጠሪያ፣ ወዘተ፣ እንዲሁም ሙያዊ ሥር የሰደደ በሽታ መመርመሪያ መሣሪያዎች፣ iCARE-2100፣ ተንቀሳቃሽ አውቶማቲክ ባለብዙ ተግባር ተንታኝ ነው። የቅርብ ጊዜዎቹ የ HPALC ተከታታይ ምርቶች እና ግንባር ቀደም የደም ግሉኮስ እና ዩሪክ አሲድ መመርመሪያ SPUG እንዲሁ በዚህ ኤግዚቢሽን ላይ አስገራሚ ታይተዋል። የሲኖኬር ባለብዙ-ተከታታይ ፣ ባለብዙ-ተግባር እና ባለብዙ-ሁኔታ ሥር የሰደዱ በሽታዎች አያያዝ ምርቶች በቻይና እና በዓለም ላይም ለህክምናው አስተዋፅኦ ያደርጋሉ። በጤና አጠባበቅ ኢንደስትሪ ውስጥ ያለው ትብብር እንደ የስኳር በሽታ ያሉ ሥር የሰደዱ በሽታዎች ራስን በራስ ማስተዳደር ላይ ያግዛል. አሁን ያለው ወረርሽኝ የፕሮፌሽናል ታዳሚዎችን ጉጉት በጭራሽ አይጎዳውም ። የሲኖኬር ቡድን ከአፍሪካ፣ ከመካከለኛው ምስራቅ እና ከላቲን አሜሪካ የመጡ ብዙ ደንበኞችን ለጉብኝት ተቀብሏል ፣ለእኛ ባለብዙ-ተግባር ስር የሰደደ በሽታን የመመርመሪያ ምርቶች ፣ ለቤት አገልግሎትም ምቹ ለሆኑ ምርቶች ከፍተኛ ምስጋና ሰጡ ። analyzer iCARE-2100 ብዙ ትኩረት ስቧል. ብዙ ደንበኞች በኤግዚቢሽኑ ወቅት የሙከራ ትዕዛዞችን ከተለማመዱ በኋላ ፈርመዋል። በአሁኑ ጊዜ የሲኖኬር ምርቶች በዓለም ዙሪያ ወደ 136 አገሮች እና ክልሎች ተልከዋል, እና የባህር ማዶ ንግድ በቅርብ ዓመታት ውስጥ እያደገ በመምጣቱ ቀስ በቀስ "Sinocare" በባህር ማዶ ገበያዎች ውስጥ ያለውን መልካም ስም እያሳደገ ነው. በ Medlab 2023 እንደገና እንገናኝ! የቀድሞው ወደ ዜና ተመለስ ቀጣይ የስኳር ህመም እና ሌሎች ሥር የሰደደ በሽታ ላለባቸው ሰዎች ከፍተኛ ጥራት ያላቸውን ምርቶች እና አገልግሎቶችን በማቅረብ የህይወታቸውን ጥራት ለማሻሻል ይረዱታል ፡፡
በኦሮምያ ክልል፣ ቄለም ወለጋ ዞን ውስጥ ወረዳና ቀበሌውን ባልጠቀሱት አካባቢ በተፈፀመ ጥቃት “ንፁሃን ዜጎች ተገድለዋል” ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ዛሬ ማምሻውን በማኅበራዊ ትስስር ገፆቻቸው ላይ ባወጡት ፅሁፍ አስታውቀዋል። "በኦሮምያ ክልል፣ ቄለም ወለጋ ዞን ውስጥ የሚገኙ ዜጎች ጭፍጨፋ ተፈፅሞባቸዋል" የሚለው የጠቅላይ ሚኒስትሩ ፅሁፍ የተገደለውን ሰው ብዛት አልገለፀም። በሌላ በኩል ጥቃቱ የተፈፀመው በቄለም ወለጋ ዞን፣ ሐዋ ገላን ወረዳ ውስጥ በሚገኝ መንደር ሃያ ተብሎ የሚጠራ አካባቢ መሆኑንና ቢያንስ ሰባ ሰው ሳይገደል እንዳልቀረ ከተገደሉት መካከል “ቤተሰቦቼ ይገኙባቸዋል” ያሉ አንድ የምዕራብ ወለጋ ነዋሪ ለቪኦኤ ተናግረዋል። የጠፋውን ህይወት ብዛት በሚመለከት ከአካባቢው ባለሥጣናትም ሆነ ከሌላ አካል የወጣ ማረጋገጫ ወይም የተለየ ቁጥር የለም። በሰላማዊ ሰዎቹ ላይ ግድያውን የፈፀመው መንግሥቱ በሽብር የፈረጀውና ባለሥልጣናቱ “ሸኔ” እያሉ የሚጠሩት፤ “የኦሮሞ ነፃነት ሠራዊት” እንደሚባል የሚናገረው ታጣቂ ቡድን መሆኑ ከዘመዶቻቸው እንደተነገራቸው እኝሁ የሟች ቤተሰብ አመልክተዋል። መንግሥት በቡድኑ ላይ “እየወሰደ ነው” ያሉትን እርምጃ “አጠናክሮ እንደሚቀጥል” ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባያያዙት የኀዘን መልዕክታቸው ላይ ተናግረዋል። ከሁለት ሣምንታት በፊት፤ ሰኔ 11 / 2014 ዓ.ም በምዕራብ ወለጋ ዞን፣ ጊምቢ ወረዳ፣ ቶሌ ቀበሌ ውስጥ በተፈፀመ የብሄር ማንነት ላይ ያነጣጠረ ጥቃት 338 ሰላማዊ አማርኛ ተናጋሪ ነዋሪዎች መገደላቸውን መንግሥት ማስታወቁ ይታወሳል። ክስ የሚሰማበት “የኦሮሞ ነፃነት ሠራዊት” እንደሆነ የሚናገረው ታጣቂ ቡድን በመንግሥትም ሆነ በተጠቂ ቤተሰቦች የሚቀርቡበትን ውንጀላዎች በየወቅቱ እያስተባበለ ይገኛል።
መጀመሪያ የተፈጠረው እንደ ፈጣን የፕሮቶታይፕ ዘዴ ፣3D ማተምተጨማሪ ማኑፋክቸሪንግ በመባልም ይታወቃል፣ ወደ እውነተኛ የማምረት ሂደት ተቀይሯል።3D አታሚዎች መሐንዲሶች እና ኩባንያዎች ሁለቱንም ፕሮቶታይፕ እና የመጨረሻ ጥቅም ላይ የሚውሉ ምርቶችን በአንድ ጊዜ እንዲያመርቱ ያስችላቸዋል፣ ይህም ከባህላዊ የማምረቻ ሂደቶች የላቀ ጠቀሜታ አለው።እነዚህ ጥቅሞች የጅምላ ማበጀትን ማንቃት, የንድፍ ነፃነትን ማሳደግ, የተቀነሰ ስብሰባን መፍቀድ እና ለአነስተኛ ባች ምርት እንደ ወጪ ቆጣቢ ሂደት ሊያገለግሉ ይችላሉ. ስለዚህ በ 3-ል ማተሚያ ቴክኖሎጂ እና አሁን ባለው የተቋቋመ ባህላዊ መካከል ያለው ልዩነት ምንድን ነውየ CNC ሂደቶች? 1 - የቁሳቁሶች ልዩነት ለ 3 ዲ ማተሚያ ዋና ቁሳቁሶች ፈሳሽ ሬንጅ (ኤስኤልኤ), ናይሎን ዱቄት (SLS), የብረት ዱቄት (ኤስኤልኤም) እና ሽቦ (ኤፍዲኤም) ናቸው.ለኢንዱስትሪ 3-ል ማተሚያ አብዛኛው የገበያውን የፈሳሽ ሙጫ፣ የናይሎን ዱቄት እና የብረት ዱቄቶች ይሸፍናሉ። ለሲኤንሲ ማሽነሪነት የሚያገለግሉት ቁሶች በሙሉ አንድ ቁራጭ ብረቶች ናቸው ፣በክፍሉ ርዝመት ፣ወርድ ፣ቁመት እና መልበስ ይለካሉ ፣ከዚያም ለሂደቱ በሚስማማው መጠን ይቁረጡ ፣የ CNC የማሽን ቁሳቁሶች ምርጫ ከ 3D ህትመት ፣ አጠቃላይ ሃርድዌር እና ፕላስቲክ ሉህ ብረት CNC ማሽን ሊሆን ይችላል, እና የተቋቋመው ክፍሎች ጥግግት ከ 3D ማተም የተሻለ ነው. 2 - በመቅረጽ መርሆዎች ምክንያት በክፍሎች ውስጥ ያሉ ልዩነቶች 3D ህትመት አንድን ሞዴል ወደ N ንብርብሮች/N ነጥቦች የመቁረጥ ሂደት እና በመቀጠል በቅደም ተከተል በመደርደር / ቢት በቢት ልክ እንደ ግንባታ ብሎኮች።የ3ዲ ህትመት ውስብስብ መዋቅራዊ ክፍሎችን እንደ አጽም የተሰሩ ክፍሎችን በማቀነባበር ረገድ ውጤታማ ሲሆን የ CNC ማሽነሪ ግን አፅም ያላቸው ክፍሎችን ማግኘት አስቸጋሪ ነው። የ CNC ማሽነሪ የማምረቻ ዘዴ ሲሆን በከፍተኛ ፍጥነት የሚሰሩ የተለያዩ መሳሪያዎች በፕሮግራም በተዘጋጀ የመሳሪያ መንገድ መሰረት የሚፈለጉትን ክፍሎች የሚቆርጡበት ነው።ስለዚህ, CNC ማሽነሪ ብቻ የተጠጋጋ ማዕዘኖች, ውጫዊ ቀኝ አንግል CNC ማሽነሪ ምንም ችግር ነው, ነገር ግን የሽቦ መቁረጥ በኩል ማሳካት, በቀጥታ የውስጥ ቀኝ ማዕዘን ውጭ machined አይችልም, ብቻ የተጠጋጋ ማዕዘኖች መካከል ኩርባ በተወሰነ ደረጃ ጋር ሊሰራ ይችላል / EDM. እና ሌሎች ሂደቶች.በተጨማሪም፣ ለተጠማዘዘ ንጣፎች፣ የCNC ማሽነሪ ጠመዝማዛ ቦታዎች ጊዜ የሚወስድ እና የፕሮግራም አወጣጥ እና ኦፕሬቲንግ ሰራተኞቹ በቂ ልምድ ከሌላቸው በቀላሉ የሚታዩ መስመሮችን በቀላሉ ሊተው ይችላል።ውስጣዊ የቀኝ ማዕዘኖች ወይም የበለጠ ጠመዝማዛ ቦታዎች ላላቸው ክፍሎች፣ 3D ህትመት ለማሽን አስቸጋሪ አይደለም። 3 - የአሠራር ሶፍትዌር ልዩነቶች አብዛኛው የሶፍትዌር መቆራረጥ ሶፍትዌሮች ለ 3D ህትመት ለመስራት ቀላል ናቸው እና በአሁኑ ጊዜ በጣም ቀላል እና ድጋፍ በራስ-ሰር ሊፈጠሩ የሚችሉ ናቸው ፣ለዚህም ነው 3D ህትመት በግለሰብ ተጠቃሚዎች ዘንድ ታዋቂ ሊሆን የሚችለው። የCNC ፕሮግራሚንግ ሶፍትዌሮች የበለጠ ውስብስብ እና ባለሙያዎች እንዲሰሩት ይፈልጋል፣ በተጨማሪም የCNC ኦፕሬተር የCNC ማሽንን ለመስራት ይፈልጋል። 4 - የ CNC ፕሮግራሚንግ ኦፕሬሽን ገጽ አንድ ክፍል ብዙ የ CNC ማሽነሪ አማራጮች ሊኖሩት ይችላል እና ለማቀድ በጣም የተወሳሰበ ነው።በሌላ በኩል የ3-ል ማተም የክፍሉ አቀማመጥ በማቀነባበሪያው ጊዜ እና በፍጆታ ላይ ትንሽ ተፅእኖ ስላለው በአንጻራዊነት ቀላል ነው። 5 - በድህረ-ሂደት ውስጥ ያሉ ልዩነቶች ለ 3D የታተሙ ክፍሎች ከድህረ-ሂደት በኋላ ጥቂት አማራጮች አሉ, በአጠቃላይ ማሽኮርመም, ማፈንዳት, ማረም, ማቅለም, ወዘተ. ከአሸዋ, ከዘይት ፍንዳታ እና ማረም በተጨማሪ ኤሌክትሮፕላቲንግ, የሐር-ማጣራት, የፓድ ማተሚያ, የብረት ኦክሳይድ, ሌዘር መቅረጽም አሉ. , የአሸዋ ፍንዳታ እና የመሳሰሉት.
የሱዳንና መንግስት የቆመው ለግብፅ ጥቅም እንጅ ለሱዳን ጥቅም አይደለም። ትክክለኛ የሱዳን ህዝብ ጥቅም ያለው #ኢትዮጵያ ከምትገነባው፣ የህዳሴ ግድብ ጋር ነው!!! የሱዳን መንግስት አቋሙ የኛ የሱዳን ህዝቦች አቋም አይደለም!!! ለግብፅ ጥቅም መከበር ነው የቆመው። ግብፅ ስትመኘው የነበረውን አይነት መንግስት በሱዳን በቅሎላታል። ይሄ መንግስት የግብፅን ጥቅም ለማስከበር #አጎብድዶ እየሰራ ነው። እንጅማ፣ በህዳሴ ግድቡ ዙሪያ የሱዳን አቋም ከግብፅ ጋር እንዴት አንድ አይነት ሊሆን ቻለ? ሲል ፕሮፌሰሩ ይጠይቃል። የግብፅ ፍላጎት ከአባይ ወንዝ 50 % መውሰድ ነው። ኢትዮጵያ 30% ትወሰድ ሱዳን 20% ይበቃታል፣ እኔ እሱዳን መሬት ላይ እየመጣ አልምቼ የግብፅ ምርት ብየ እሸጣለሁ የሚል አቋም ነው ያላት። አሁን የኛ መንግስት ይሄን አቋም ደግፎ ነው የሱዳንና የግብፅ ፍላጎት እየተባለ በሚዲያ የሚነገረን፣ ፕሮፌሰሩ ንግግሩን አላቆመም፣ ግብፅ የህዳሴ ግድብን የምትፈራው ለሱዳን ጥቅም ስለሚውል ነው፡፡ ምክኒያቱም ግድቡ ከተጠናቀቀ ግብፅ እንደፈለገች የሱዳንን ድርሻ መውሰድ አትችልም። በተረፈው ድርሻዋን ለፈለገችው ልማት ማዋል ትችላለች። የህዳሴው ግድቡ ሲጠናቀቅ የሚፈልገውን ሁሉንም ሀይል ያቀርባል ፣ የሱዳን የኢንዱስትሪ መጠን ይጨምራል፡፡ ንግድና ኢንቨስትመንቶች ይጨምራሉ። ያማለት የሱዳን ኢኮኖሚ ተነቃቃ ማለት ነው። ሱዳን አምራች ግብፅ ሻጭ የምትሆንበት የዘመናዊ ቅኝ ግዛት (የ Modern Colonialism) ህልሟ አከተመ ማለት ነው። እናም ግብፅ የምትፈራው የአባይን ግድብ መገደብ ብቻ ሳይሆን፣ በግድቡ ሱዳን ተጠቃሚ ሆና ትነቃብኛለች፣ እኔ እንደፈለኩ የሱዳንን ምርት እየሰበሰብከ አልቸበችብም ወይም ዘመናዊ የቀኝ አገዛዝ ህልሜ ይቋረጥብኛል ብላ ስለምታስብ ነው። ብሏል ሱዳናዊው ፕሮፌሰር!!!!
የፌደራል መንግስት የትግራይ ክልልን ይመራ ከነበረው ህወሓት ጋር በተፈጠረው አለመግባባት ወደ ውጊያ ያመራ ሲሆን ኦነግ ሸኔ ደግሞ በተለያዩ የኢትዮጵያ ክልሎች ለተፈጠሙ ግድያዎች ተጠያቂ ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ መንግስት በመግለጫው በሁለቱ ድርጅቶች “ የበርካታ ዜጎች ሕይወት ጠፍቷል፣ አካላቸው ጎድሏል፤ እንዲሁም ንብረታቸው ወድሟል፤ ከቀዬአቸውም ተፈናቅለዋል። እነኚህ ጥቃቶች ኅብረተሰቡ ቀጣይነት ባለው ሥጋት እና ፍርሐት ውስጥ እንዲኖር በማድረግ በመንግሥት ላይ እምነት እንዲያጣ፣ ዜጎች እርስ በእርስ እንዳይተማመኑ አድርጓል።” መንግስት ለኢቢሲ እንደላከው መግለጫ ከሆነ የህወሃትና ሸኔ “ የሀገረ መንግሥቱን ህልውና አደጋ ላይ ለመጣል” ተንቀሳቅሰዋል ብሏል፡፡ ህወሃትና ሸኔ “ሲፈጸሙና ሲያስፈጽሙ የቆዩዋቸው የጥፋት ተግባራት የሽብር ወንጀል ተግባራት ናቸው። እነዚህ ተግባራት የሽብር ወንጀልን ለመከላከል እና ለመቆጣጠር በወጣው ዐወጅ 1176/2012 አንቀጽ 3 ሥር ስለሽብር የወንጀል ድርጊት የተሰጠውን ትርጓሜ ሙሉ ለሙሉ የሚያሟሉ ተግባራት እንደሆኑ በቀላሉ ለመገንዘብ ይቻላል።” መንግስት ግለስቦችን በሽብር ከመጠየቅ ይልቅ ድርጅቶችን በሽብር መፈረጅ “አግባብ የሽብር ወንጀል ድርጊትን በተሻለ ሁኔታ ለመቆጣጠር እና ለመከላከል ይችላል” ብሏል፡፡
በአዲስ አበባ በተደጋጋሚ ማስክ ሳያደርጉ የሚንቀሳቀሱ ሰዎችን በመለየት ፍርድ ቤት ማቅረብ ሊጀምር መሆኑን የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን አስታወቀ። – Ethio FM 107.8 Skip to content በአዲስ አበባ በተደጋጋሚ ማስክ ሳያደርጉ የሚንቀሳቀሱ ሰዎችን በመለየት ፍርድ ቤት ማቅረብ ሊጀምር መሆኑን የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን አስታወቀ። By Ethio Admin August 5, 2020 August 5, 2020 የሀገር ውስጥ ዜና ኮሚሽኑ ህብረተሰቡ ለኮቪድ 19 የሚያደርገው ጥንቃቄ ላይ መዘናጋት በመታየቱ ጠንከር ያለ ቁጥጥር ጀምሪያለሁ ብሏል፡፡ ጣቢያችን በአንዳንድ አካባቢዎች ላይ እንደተመለከተው ማስክ ሳያደርጉ ሲንቀሳቀሱ የተገኙ ሰዎች ተይዘው ስማቸው፣ የመኖሪያ አድራሻቸው እንዲሁም ስልካቸውን በፖሊስ እየተመዘገበ መሆኑን እና እንዲሁም መታወቂያ ሲጠየቁ አስተውሏል፡፡ ኢትዮ ኤፍ ኤምም ይህ የሰዎችን የስም ዝርዝር መመዝገብ ሂደት ቫይረሱን ከመከላከል አንፃር የሚኖረው አስተዋፆ ምን ያህል ነው ሲል ጠይቋል፡፡ በኮሚሽኑ ዋና ኢንስፔክተር ማርቆስ ታደሰ እንደነገሩን በሀገራችን በኮሮና ቫይረስ የሚያዙ ሰዎች ቁጥር በየእለቱ እየጨመረ ቢሆንም በህብረተሰቡ ዘንድ የሚታየው መዘናጋት ግን ዋጋ ያስከፍለናልና ይህ ከመሆኑ ሰዎች በቂ ጥንቃቄ እንዲያደርጉ እየሰራን ነው ብሏል፡፡ የኮሮና ቫይረስ መከላከያ ተብለው የተቀመጡትን በተለይ ማስክ አድረገው የማይንቀሳቀሱ ሰዎችን በመመዝገብ ደጋጋሚ የሆኑትን በመከታተል በአስቸኳይ አዋጁ የተቀመጠውን ቅጣት እንደሚጣልባቸውም ነው ዋና ኢንስፔክተሩ የተናገሩት፡፡ ከዚህ ቀደም ማስክ ሳያደርጉ የሚንቃቀሱ ሰዎችን ወደ ፖሊስ ጣቢያ ተወስደው እንዲታሰሩ ይደረግ የነበረ ቢሆንም አሁን ባለው ሁኔታ ሰዎችን ማሰር ስለማይቻል የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎች እየተሰሩ አዋጁን በተደጋጋሚ በሚጥሱት ላይ ግን እርምጃ ለመወስድ አሰራሩ መዘርጋቱን ተናግረዋል፡፡ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የተደነገጉ የመብት እገዳዎችን፣ እርምጃዎችን፣ የተሰጠ መመሪያ ወይም ትዕዛዝን ሆን ብሎ የጣሰ ማንኛውም ሰው እስከ ሦስት ዓመት በሚደርስ ቀላል እስራት ወይም ከአንድ ሺህ ብር እስከ ሁለት መቶ ሺህ ብር የሚደርስ የገንዘብ መቀጮ ሊቀጣ እንደሚችል በአዋጁ መቀመጡ አይዘነጋም።
የእግዚአብሔር ልጆች መሆናችንን ከምናሳይባቸው መንገዶች አንዱ ከሌሎች አማኞች ጋር ያለን ግንኙነት ነው። በቤተሰብ ውስጥ የሁለት ልጆች መጣላት የተቀሩትን የቤተሰብ አባላት እንደሚነካ ሁሉ፥ በአማኞች መካከል የሚካሄድ ጸብ ከእግዚአብሔር ጋር ያላቸውን ግንኙነት ይጎዳዋል። ዮሐንስ በአማኞች መካከል ያለውን ግንኙነት «ፍቅር» በሚል ቃል ይገልጸዋል። ዮሐንስ ይህን ሲል ስለ ስሜታዊ ፍቅር መናገሩ ብቻ አይደለም፥ ወይም በአማኞች መካከል ሊኖር ስለሚገባ መልካም ስሜት ብቻ መናገሩ አይደለም። ይልቁንም ከፍቅር የሚመነጩትን ተግባራት ለማመልከት ይፈልጋል። እነዚህም ተግባራት በአሳብ ወይም በተግባር የተከናወኑትን በደሎች ይቅር ማለት ሊያካትቱ ይችላሉ፥ ወይም ደግሞ በችግር ውስጥ ያሉትን መርዳትን ሊያመለክቱ ይችላሉ። ዮሐንስ በዚህ መልእክት ውስጥ ወደዚሁ ማዕከላዊ ትምህርት ብዙ ጊዜ ደጋግሞ ይመለሳል። እርስ በርሳችሁ ተዋደዱ የሚለው ትእዛዝ በአንድ በኩል በጣም ያረጀ ነው። ይህ ትእዛዝ ብሉይ ኪዳን ውስጥ ይገኛል (ዘሌዋ. 19፡18 አንብብ)። በተጨማሪም ይህ ትእዛዝ አዲስ የሆነው በብዙ መንገዶች ነው። በመጀመሪያ፥ የብሉይ ኪዳን የፍቅር ትእዛዝ የተመሠረተው በጎሰኝነት ላይ መሆኑ፥ ይህ እርስ በርስ ተዋደዱ የሚለው ትእዛዝ አዲስ ነው። አይሁዳውያን ወገኖቻቸውን እንዲወዱ ነበር የተጠየቁት። ነገር ግን አይሁዳውያን ያልሆኑትን እንዲወዱ የታዘዙበት ስፍራ አልተጠቀሰም። አሁን ግን እግዚአብሔር ሰዎችን ሁሉ እንድንወድ አዞናል (ማቴ. 22፡39-40)፡፡ ሁለተኛ፥ በስፋቱም አዲስ ነው። ብሉይ ኪዳን አይሁዶች ድሆችን እንዲረዱ ሲያዛቸው፥ ወዘተ… ፥ ከሰዎች የሚጠበቀውን ነገር ይወስነዋል። በመጀመሪያ: የብሉይ ኪዳን ፍቅር በተለይም ለአይሁዶች መልካም ከሆኑት ሰዎች ጋር ግንኙነት ማድረግን ያበረታታል። አዲስ ኪዳን ግን በመሥዋዕትነት ፍቅር ላይ ያተኩራል። ይህም ለእኛ ጥሩዎች ያልሆኑትን (ጠላቶቻችንን ጨምሮ) መውደድን ያካትታል (ማቴ. 5፡43-47)። የአዲስ ኪዳን ፍቅር ሕይወታችንን ሳይቀር ለሌላ ሰው ፍቅር በመሥዋዕትነት እንድናቀርብ ይጠይቀናል (1ኛ ዮሐ. 3፡16)። ዮሐንስ አንድ ሰው የክርስቶስ ተከታይ ነኝ እያለና ከእግዚአብሔር አብ ጋር መልካም ኅብረት እንዳለው እየተናገረ ዳሩ ግን ፍቅርን ሳይሆን ጥላቻን የሚያሳይ ከሆነ፥ ድነትን (ደኅንነትን) ያላገኘ የጨለማ ውስጥ ተጓዥ መሆኑን ይናገራል። አሁንም ዮሐንስ «ጥላቻ» የሚለውን ቃል የሚጠቀመው እንደ ስሜታዊ አለመውደድ ሳይሆን፥ ሌሎችን ለመርዳት አለመፈለግን ለማሳየት ነው። አንድ አማኝ በችግር ውስጥ እያለ ልንረዳው ካልፈለግን ጠልተነዋል ማለት ነው። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) በቤተ ክርስቲያንህ ውስጥ ያሉት አብዛኞቹ ግንኙነቶች ተለይተው የሚታወቁት በፍቅር ነው ወይስ በጥላቻ? ለ) የኮሚኒስት መንግሥት ከወደቀ በኋላ በአማኞች መካከል መከፋፈል የበረከተው ለምን ይመስልሃል ? ሐ) ይህ በክርስቶስ ላይ ስላለን እምነት ምን ያሳያል? በ1ኛ ዮሐንስ 2፡12-14፤ ጸሐፊው በአማኞች ሕይወት ውስጥ የተመለከተውን ነገር ያስታውሳል። ይህም የእግዚአብሔር ልጆች መሆናቸውን የሚያረጋግጥ ነበር። ምሁራን ልጆች፥ ጎበዞችና አባቶች የሚለው ማንን እንደሚያመለክት ይጠራጠራሉ? ይህ ቅደም ተከተላዊ የዕድሜ መግለጫ ነው? ወይስ የመንፈሳዊ ብስለት መግለጫ ? በአመዛኙ ዮሐንስ መንፈሳዊ ብስለትን የሚያመለክት ይመስላል። ዮሐንስ እነዚህን የተለያዩ ነገሮች ከተለያዩ የዕድሜ ቡድኖች ጋር የሚያዛምደው ለምንድን ነው? አናውቅም። ዮሐንስ አማኞች ሁሉ ሊያስታውሷቸውና ሊያድጉባቸው የሚገባቸውን ሦስት ባሕርያት ለማሳየት የሚፈልግ ይመስላል። ሀ) ኃጢአታችን እንደ ተሰረየ እናውቃለን። አዳዲስ እማኞች፣ ሊያውቋቸው ከሚገቡ ነገሮች አንዱ ከክርስቶስ ደም የተነሣ ለቀድሞዎቹ፣ ለአሁኖቹና ወደፊት ለሚያደርጓቸው ኃጢአቶች ሁሉ ዋጋ እንደ ተከፈለ ነው። እግዚአብሔር ሙሉ በሙሉ ይቅር ብሏቸዋል። ሰይጣን በቀድሞው ኃጢአታቸው ሳቢያ ልባቸውን እንዳያዝልባቸው፥ ይህን ማወቁ ጠቃሚ ነው። በክርስቶስ ከማመናችን በፊትና ካመንን በኋላ ለበደለኛነት ስሜት የሚያጋልጡንን ኃጢአቶች ልንፈጽም እንችላለን። ዮሐንስ ግን እነዚህን ኃጢአቶች ለእግዚአብሔር ከተናዘዝን ይቅርታ እንደሚደረግልን ይናገራል፡፡ ለፈጸምናቸው ኃጢአቶች ዋጋ መክፈላችንን ልንቀጥል እንችላለን (ለምሳሌ: አንዲት ሴት ከጋብቻ ውጭ ዝሙት ፈጽማ ብታረግዝ፣ እግዚአብሔር እርግዝናውን አያስወግድላትም)። ነገር ግን እግዚአብሔር ይቅር ስላለን ለዚያ ኃጢአት አይቀጣንም። ኃጢአት እንዳልፈጸምን ያህል ከእርሱ ጋር ግንኙነት ልናደርግ እንችላለን። ለ) አማኞች «ከመጀመሪያው ከነበረው» ወይም ከእግዚአብሔር አብ ጋር ሕያው ግንኙነት አላቸው። ዮሐንስ «ማወቅ» የሚለውን ቃል የተጠቀመው ምሁራዊ እውቀትን ሳይሆን ዝምድናዊ እውቀትን ለማሳየት ነው። በብስለት የሚያድጉ ሰዎች የእግዚአብሔርን ማንነት በማወቅ ይበልጥ ወደ እርሱ እየቀረቡ ይሄዳሉ። ግንኙነቶች ሁሉ በእውቀት ላይ የተመሠረቱ ናቸው። አንድን ሰው የበለጠ ስናውቅና ብዙ ጊዜ አብረነው ስናሳልፍ፥ ግንኙነታችን እየጠለቀ ይመጣል። እንደ አባት ከሚወደንና ዳሩ ግን ዘላለማዊ ከሆነ አምላክ ጋር ግንኙነት ማድረጉ ምንኛ ታላቅ ዕድል ነው። ሐ) በሕይወታችን ውስጥ ባለ ኃጢአት ላይ ድልን እንቀዳጃለን። ዮሐንስ ሙሉ በሙሉ ከኃጢአት ነፃ ልንሆን እንደማንችል ይናገረናል። ይህ ማለት ግን በቅድስና ልናድግ፥ ኃጢአትን ልናሸንፍና ለእግዚአብሔር ክብር ልንኖር አንችልም ማለት አይደለም። ነገር ግን ዮሐንስ የሚናገረው በሕይወታችን ውስጥ ስላለ ኃጢአት ብቻ ሳይሆን ከክፉ ስለሚመጣው የፈተና ምንጭ ጭምር ነው። (በግሪክ ቋንቋ፥ ትኩረት የተሰጠው ኃጢአትን በማሸነፍ ላይ ሳይሆን፥ «ክፉ» የተባለውን ሰይጣንን በማሸነፍ ላይ ነው፥ የሚፈትነን እርሱ ነውና።) ዮሐንስ የሚናገረው ሰይጣን መቼ በኃጢአት እንደሚፈትነን ነው? በብስለት እያደግን ስንሄድ በመንፈሳዊ ጥንካሬም እናድጋለን። በመንፈሳዊ ብስለት ማደግ ከሚያስገኛቸው ውጤቶች አንዱ ሰይጣን እንዳያሸንፈንና ወደ ኃጢአት እንዳይመራን መከላከል መቻል ነው። እግዚአብሔር በእምነታችን ጠንካሮች እንድንሆን ለማገዝ የሰጠን ዋናው መሣሪያ ምንድን ነው? ይህ በውስጣችን ሊኖር የሚገባው የእግዚአብሔር ቃል ነው። የውይይት ጥያቄ፡– ሀ) እነዚህ ሦስት እውነቶች ከእግዚአብሔር ጋር ያለንን ግንኙነት የሚያሳይ ጠቃሚ አመልካቾች የሚሆኑት ለምንድን ነው? ለ) መዝ 119፡9 አንብብ። ይህ ምንባብ ሰይጣንንና ኃጢአትን ስለምናሸንፍበት መንገድ ምን ይላል? ይህ ሰይጣንን ከሕይወታችን ለማራቅ መጸለይና መገሠጽ ብቻ በቂ እንዳልሆነ የሚያሳየን እንዴት ነው? ፪. ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት ማድረግ ማለት የዓለምን የአኗኗር ዘይቤ አለመውደድ ነው (1ኛ ዮሐ 2፡15-17) አንድን ሰው ስትወድ ሰውየው የሚወደውን እንጂ የሚጠላውን አታደርግም። እንወደዋለን የምንለው ሰው የማይፈልገውን ነገር የምናደርግ ከሆነ፥ ይህ ግንኙነታችንን፥ ከማደፍረሱም በላይ ለግለሰቡ ፍቅር እንደሌለን ያሳያል። እግዚአብሔርን ከወደድን እንዲሁም ከእርሱ ጋር ኅብረት ካለን፥ እርሱ የሚወደውን ልንወድና ደስ የማያሰኘውን ከማድረግ ልንቆጠብ ይገባል። ዮሐንስ እግዚአብሔር ከማይወዳቸው ነገሮች አንዱን ይጠቅሳል። ዓለምን ወይም በዓለም ያሉትን አትውደዱ ሲል ይመክረናል። ይህ ምን ማለት እንደሆነ መረዳቱ ጠቃሚ ነው። ዮሐንስ የሚናገረው ስለተፈጠረው ዓለም አይደለም። ምክንያቱም እግዚአብሔር ዓለምን ከመፍጠሩም በላይ መልካም መሆኑን ተናግሯልና (ዘፍጥ. 1፡31)። ዮሐንስ ሰዎችን ማለቱም አይደለም፥ ምክንያቱም እግዚአብሔር ሰዎችን ከመውደዱ የተነሣ ልጁ እንዲሞትላቸው ልኮታልና (ዮሐ 3፡16)። ዮሐንስ «ዓለም» ሲል ከእግዚአብሔር ፈቃድ ውጭ የሆነ ፍልስፍና ወይም ትምህርት ማለቱ ነው። ይህ የዓለም ዘይቤ በኩራትና በራስ ወዳድነት የተሞላ ነው። እነዚህ ባሕርያት በዐመፅ ወደ ተሞሉ ተግባራትና የግንኙነቶች መፈራረስ ይመራሉ። የገንዘብ፥ የሥልጣን፥ በወሲባዊ ግንኙነቶች ሌሎችን የማሸነፍና ለተሳሳቱ ዓላማዎች የመማር ፍቅር የሚመጣው የማያምኑ ሰዎች ከሚያስተምሩት የአኗኗር ዘይቤ ነው። እግዚአብሔር ልጆቹ እነዚህን ነገሮች ባለመውደድ ለእርሱ ያላቸውን ፍቅር እንዲገልጹለት ይፈልጋል። የውይይት ጥያቄ፡– ከዓለም ዘይቤ ክርስቲያኖች እንዳንድ ጊዜ የሚወዷቸውንና በሕይወታቸው ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ የሚያሳድሩትን ነገሮች ዘርዝር። (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)
ይህ ቀጣይነት ያለው ወረርሽኝ ከኮቪድ-19 ጋር በተያያዙ ምክንያቶች ደንበኞቻችን ተመላሽ ገንዘብ ማግኘት ይችሉ እንደሆነ ብዙ ጥያቄዎች እንዲያነሱ ምክንያት ሆኗል። ከኮቪድ-19 ጋር በተገናኘ ለተለያዩ ምክንያቶች ገንዘብ ተመላሽ እናደርጋለን፣ ስለዚህ እዚህ ላይ መክፈል ስለምንችላቸው ተመላሽ ገንዘቦች ላይ የተወሰነ ማብራሪያ ለመስጠት ሞክረናል። ኢንፌክሽን… ቦታ አስይዘው ከመገኘትዎ በፊት ባሉት 7 ቀናት ውስጥ በኮቪድ-19 ከተያዙ፣ ይህ ማለት ራስዎን ማግለል ወይም መከልከል ከኖረቦት፤ አወንታዊ PCR የፈተና ውጤት እና/ወይም ከመንግስትዎ ራስዎን ማግለልዎን በሚያረጋግጥ ማስረጃ የተደገፈ ከሆነ። የ PCR ምርመራ ውጤት ከተጠቀሙ በተፈቀደ ላብራቶሪ ውስጥ መካሄዱ እና የተረጋገጠ የQR ወይም የባር ኮድ መያዝ አለበት። ራስን ማግለል… በእርስዎ የቅርብ ቤተሰብ ውስጥ የሆነ ሰው በኮቪድ-19 ከተያዘ፣ ይህ ማለት እርስዎ አግባብ ባለው የብሄራዊ መንግስት ህግ መሰረት ራስዎን ማግለል ወይም መከላከያ ማድረግ ካለቦት፣ በአዎንታዊ(ፖዘቲቭ) PCR ምርመራ ወይም በመንግስት ራስን የማግለል ግንኙነት እና የአድራሻ ማረጋገጫ የተደገፈ ከሆነ። ቀደም ሲል የነበረ የጤና ሁኔታ… ቦታ ካስይዙ በሁላ ባሉት 7 ቀናት ውስጥ ቀደም ሲል በነበረው የጤና ሁኔታዎ ላይ ከፍተኛ ለውጥ ካጋጠመዎት እና ዶክተርዎ ለኮቪድ-19 ተጋላጭ እንዳይሆኑ በመስጋት ምክንያት እንዳይገኙ ከመከሮት፣ ገንዘቡን ልንመልስልዎ እንችላለን። ሆስፒታል መተኛት ወይም ሞት… የቅርብ ቤተሰብ የሆነ ሰው በኮቪድ-19 ምክንያት ሆስፒታል ከገባ ወይም ከሞተ፣ ቦታ ያስያዙበት ጉዳይ ከመጀመሩ በፊት ባሉት 30 ቀናት ውስጥ ከሆነ እና ማስረጃ ካሎት፣ ገንዘቡን ልንመልስልዎ እንችላለን። መክፈል የማንችለው… በኮቪድ-19 መያዝ በመስጋት ወይም በሚኖሩበት ቤት ወይም ቤተሰብዎ ጋር ያለ አወንታዊ (ፖዘቲቭ) የኮቪድ-19 ምርመራ እራስዎን እያገለሉ ከሆነ ገንዘቡን ተመላስ ማረግ/መክፈል አንችልም። የኮቪድ-19 ስርጭትን ለመቆጣጠር በሚወሰዱ እርምጃዎች ምክንያት ለተከሰቱት የጉዞ ገደቦች/ክልከላዎች ገንዘብ ተመላሽ ማድረግ/መክፈል አንችልም። ተመላሽ ምናረገው ገንዘብ ሁል ጊዜ ሙሉ በሙሉ በውላችን (እዚህ ሊነበብ ይችላል) መሰረት ታሳቢ ተደርጎ ነው፣ ተገቢ ማስረጃዎችን ሙሉ በሙሉ ምክንያታዊ በሆነ መልኩ እንዲቀርቡ እንፈልጋለን፣ እና ምንም አይነት ገንዘብ ተመላሽ የማድረግ ዋስትና አንሰጥም።
ተወልዶ ያደገው እዚሁ አዲስ አበባ የካ ሚካኤል አካባቢ ነው፡፡ በሰው ልጅ አቅም ሊታለፍ ቀርቶ ሊታሰብ የሚከብድ ብዙ መከራዎችን በትግል አሸንፏል፡፡ ምግብ ሳይበላ ለቀናት ውሎ አድሯል፣ ጎኑን ማሳረፊያ መኝታ አጥቶ ብዙ ተንከራትቷል፤ ልብስና ጫማ ለእሱ ቅንጦት ነበሩ፡፡ ከጉልበት ሰራተኛነት እስከ ሰው ቤት ሰራተኛነት ያልሰራው ሥራ የለም። በስደት ጀርመን ገብቶ ብዙ ውጣ ውረዶችን አሳልፏል፡፡ በአጠቃላይ ከህይወት ጋር ግብግብ ገጥሞ ነው የኖረው ግን የቱንም ያህል መከራና ፈተና አልበገረውም። ከልጅነት እስከ ዕውቀት የተጋፈጠውን መከራና ፈተና ለስኬት ያበቃውን ምስጢር የሚያስቃኝ “ስደተኛው ሼፍ” የተሰኘ መፅሐፍም ለንባብ አብቅቷል። ሼፍ አንተነህ ድፋባቸው፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ ከሼፍ አንተነህ ጋር ቀጣዩን አስደማሚ ቃለ ምልልስ አድርጋለች፡፡ እነሆ፡- • “እኔ ያጣሁት የሚበላና የሚለበስ ብቻ ሳይሆን ፍቅርም ነው” • መከራውንና ውጣ ውረዱን ያለፍኩበት መሳሪያ ትዕግስት ነው • አሁን ብቸገር የማላውቀው ዓለም ውስጥ አይደለም የምገባው ከጀርመን ወደ ሀገር ቤት፣ከአገር ቤት ወደ ጀርመን መለስ ቀለስ እያልክ ነው፡፡ ለስራ ነው ለእረፍት? ለሁለቱም ማለት ይቻላል፡፡ አንዳንዴ አገሬ ላይ ለመስራት የምፈልጋቸውን ስራዎች ለማጥናትም እግረ መንገዴንም ለማረፍ ነው ወጣ ገባ የምለው፡፡ ከልጅነትህ ጀምሮ በርካታ ተስፋ አስቆራጭ የሆኑና የሚያልፉ የማይመስሉ ፈተናዎችን ተጋፍጠሀል፡፡ በዚህ ሁሉ መከራ ውስጥ ተስፋ እንዳትቆርጥ ያገዘህ ምንድን ነው? እውነት ለመናገር እኔ ያሳለፍኩት ችግር ሲወራና ሲፃፍ ቀላል ይመስላል እንጂ ስኖረው በእጅጉ ከባድና አሰቃቂ ነበር። እንዳልሽው የሚያልፉ የማይመስሉ መከራዎች ነበሩ፡፡ ነገር ግን ያንን ጨለማ ያሸነፍኩበት ምክንያት እግዚአብሔር ያንን የሚሸከም ትከሻና የምታገስበት ፀጋ ሰጥቶኝ ነው ብዬ አምናለሁ። ችግሮቹም ያለፉት በእግዚአብሔር ነው፡፡ ያ ሁሉ እንዲያልፍ፣ የኔ ሕይወት ሰው እንዲያስተምር ያደረገውም ለበጎ ነው፡፡ ባያልፍ ኖሮ ዛሬ አያስተምርም ነበር፡፡ ስለዚህ ፀጋም አለ፡፡ በሌላ በኩል እኔ ሁሌ የማየው ነገን ነበር፡፡ ግልምጫውም፣ ንቀቱም፣ ረሀቡም፣ እርዛቱም ሆነ ሌሎች ችግሮች በህይወቴ ሲያልፉ ጥለውት የሚያልፉት ነገር አለ፡፡ አንዳንዱን ጠባሳ ጥሎ ሲያልፍ፣ አንዳንዱ ጠባሳ ሳይጥል እንዲሁ ተጋግጬ የማልፍበት ሁኔታ ነበር፡፡ ዋናው መከራውን ያለፍኩበት መሳሪያ ትዕግስት ነው፡፡ በጣም እታገስ ነበር፡፡ ስመታ እንዳልተመታ፣ ስናቅ እንዳልተናቅሁ እየቆጠርኩና ነገሮችን ለመርሳት እየሞከርኩ ነው ያሳለፍኩት፡፡ ለምሳሌ አንድ ሰው የምጠጣው ውሃ ውስጥ መርዝ ሲጨምር ባየው ምንም እንዳልተፈጠረ አድርጌ የመርሳትና ወደፊት የመቀጠል አቅም ነበረኝ፡፡ እንዲህ አይነት ትዕግስት ነው ያንን ሁሉ ችግር እንዳልፍ ያደረገኝ፡፡ ከልጅነትህ ጀምሮ ምግብም፣ልብስም የቤተሰብ ፍቅርም ሳታገኝ ተጎድተህ ነው ያደግኸው፡፡ አሁን ከዚያ ፍፁም ተቃራኒ በሆነ የህይወት መስመር ውስጥ ነው የምትገኘው፡፡ ለአንተ ማጣትና ማግኘት እንዴት ይገለፃል? እንግዲህ ማግኘትና ማጣት በዓለም ላይ ያሉ ነገሮች ናቸው፡፡ በነዚህ ሁለት ተቃራኒ መስመሮች ሰዎች ያልፋሉ፡፡ ነገር ግን አጥቶ ከማግኘት፣ አግኝቶ ማጣትን ለማንም አያድርስ ነው የምለው፡፡ አጥቶ ማግኘት ግን ጥሩ ነው፤ እርካታን ደስታን ይሰጣል፡፡ ያረጋጋልም፡፡ እኔ አሁን ላይ የተረጋጋ ህይወት ነው ያለኝ፡፡ ችግርን በደንብ ስለማውቀው አልፈራውም። ችግርን ከሀ እስከ ፐ ስለማውቀው አሁን ብቸገር፣ የማላውቀው ዓለም ውስጥ አይደለም የምገባው፡፡ አሁን አይ በለውና የሆነ ችግር ውስጥ ብገባ፣ እንደገና እንደምነሳ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ስለዚህ ማጣት አያስፈራኝም፤ አያስደነግጠኝምም፡፡ አሁን ላይ ስለማልፈራው እሱም ቶሎ ቶሎ አያገኘኝም፡፡ ይሄ ማለት አይቸግረኝም ማለት ሳይሆን የድሮውን ያህል አይደቁሰኝም፡፡ አይርበኝም፤ የምለብሰው አላጣም፤ ጫማም አልቸገርም፡፡ ያኔ የሚቀመስ ዳቦ እንኳን ይታጣል፡፡ ሌላው ቀርቶ ውሃ ተጠምቼ ወዲያው ውሃ የሚያጠጣኝ ላላገኝ እችል ነበር፤ ያ ሁሉ ታልፏል፡፡ አሁን እነዚያ ነገሮች ስጋት አይሆኑብኝም፡፡ አንዳንዴ እኮ አንድ ቤተሰብ በጣም ችግረኛ ቢሆንም፣ የእናት አባት ፍቅር አግኝተው ተደጋግፈው ይኖራሉ፡፡ እኔ ያጣሁት የሚበላና የሚለበስ ብቻ ሳይሆን የቤተሰብ ፍቅርም ነበር፡፡ እኔ መወደድ መዳሰስ፣መታቀፍ በአጠቃላይ ለሰው ልጅ ከምግብ በላይ አስፈላጊ የሆኑት ነገሮችን ነው የተነፈግሁት፡፡ እናትህ ከቤት ከማባረር ጀምሮ ብዙ ነገር እንዳደረጉህ ፅፈሀል። በተለይ አንድ ጊዜ የወንድምህ ቤተሰቦች ቤት ሰርግ ተደግሶ፣ ሁለታችሁም ሰርግ ቤት ከሄዳችሁ በኋላ በር ላይ እናትህና ወንድምህ ጥለውህ ገብተው፣ ከጎዳና ልጆች ጋር ተቀላቅለህ ምግብ የበላህበት አጋጣሚን አስታውሰሃል። እስካሁን እናትህን ተቀይመሃቸዋል ማለት ነው? እናቴ ለኔ በጣም ታሳዝነኛለች፤ ምክንያቱም የራሷ ተፅዕኖ አለባት፡፡ ያንን ያደረገችበት ምክንያት ክፉ ስለሆነች አልነበረም፤ እሷን የገጠሟት ሰዎች ህይወቷ በምሬት እንዲሞላ ያደረጉ ስለነበሩ ነው። በልጅነቷ ብዙ ወንዶች አግብታለች፤ በጣም ቆንጆ፣ አስተዋይ ብትማር ትልቅ ቦታ ልትደርስ የምትችል ሴት ነበረች። ጥሩ ወንዶች ስላልገጠሟት የተማረረ ህይወት ነው ያሳለፈችው። የዛ የተማረረ ህይወት ውጤት ነኝ እኔ፡፡ ስለዚህ እናቴ በህይወቷ ስትማረር፣ እኔን በመሳደብ በመርገምና በመደብደብ ነበር ምሬቷን የምታንፀባርቀው፡፡ ለምሳሌ የእኔ አባት ጥሏት ነው የሄደው፡፡ ያንን ንዴት በኔ ላይ ነው የምትወጣው፡፡ ምንም ባደርግላት፣ ምንም ብሰራላት አትደሰትም። እንደውም አንዳንዴ “አንተ የዛ አረመኔ ልጅ!” ትለኝ ነበር፡፡ ስለዚህ እንደዛ ያደረጋት በህይወቷ የገጠሟት ሰዎች እንጂ እናቴ በተፈጥሮዋ ክፉ ሆና አይደለም፡፡ የሰርግ ቤቱ ጉዳይ እንዳልሽው ለምን ከአዕምሮዬ አልጠፋም እንዳለኝ አላውቅም፡፡ በህይወቴ ከተከፋሁባቸውና ካዘንኩባቸው ቀናት አንዱ ነው፡፡ እየተማርክ የቀን ስራ ትሰራ ነበር፡፡ በሀያት የመኖሪያ ቤቶች ግንባታ፣ የጉልበት ሥራ እየሰራህ ፈጣሪ እንጀራ እንዲያበላህ ስለጸለይክበት ቀን እስቲ ንገረኝ...? በህይወቴ ከማስታውሳቸውና ከህሊናዬ ከማይጠፉ ነገሮች አንዱ ነው - ያ ቀን። በህይወቴ መንፈሳዊ ህይወትና እምነት የያዝኩባት ቀን ሆና ተመዝግባለች። ያኔ እድሜዬም መንፈሳዊ ህይወቴም ያልጠነከረበት ወቅት ነበር። ረሃብ ውስጥ ነበርኩ። ላለፉት ሁለትና ሶስት ቀናት ምግብ አልበላሁም። ነገር ግን ከባድ ስራ ይጠብቀኛል። ብረት ነው የምሸከመው። የዛን ቀን ከሰዓት ብረት አወርድ ነበር። እናም በጣም እርቦኝ እንዳነበብሽው፣ ኪሴ ውስጥ 35 ሳንቲም ብቻ ነው የነበረችኝ። ያን ጊዜ ከሀያት መገናኛ የአውቶብስ መሳፈሪያ 25 ሳንቲም ነበር፡፡ እናም ለዛ ብዬ ነው ሳንቲሟን ያስቀመጥኳት። አርማታ ስሸከም ውዬ ምግብ ሳልበላ በእግሬ ከሀያት መገናኛ መምጣት አልችልም። ረሃቡ የአንድ ቀን ቢሆን ጥሩ ነበር። ግን አይደለም፡፡ በእግር ለመሄድ ዕድል የሚሰጥ አቅም አልነበረኝም። በዛ በምሳ ሰዓት ሁሉም የቋጠረውን ምሳ ዕቃ እየፈታ ለመብላት ይተራመሳል። ያኔ በሀያት የሚሰራው ወደ 10 ሺህ ገደማ የሚሆን ሰው ነው። እኔ ምንም የለኝም። ስለዚህ 35 ሳንቲሟን አውጥቼ ከገበሬዎች ላይ ቆሎ ገዝቼ እየቆረጠምኩ “አምላኬ እባክህ እንጀራ አብላኝ” ብዬ ጸለይኩኝ። ቆሎውን እየበላሁ በዚያ ቅጽበት አንድ የማላውቀው ሰው ከኋላዬ መጥቶ “ሰላም ነህ” አለኝ። ሰውየው ምንድን ነው? ማለቴ አሰሪ ነው ወይስ? ኧረ አሰሪ አይደለም። ሽርጥ የለበሰ እንደኔው በቀን 6 ብር እየተከፈለው የሚሰራ የቀን ሰራተኛ ነው። እኔም የ6 ብር ደሞዝተኛ ነኝ በቀን። ያኔ በቀን 6 ብር ነው የሚከፈለው - ሰራተኛ ቀይ ወጥ በ3 ብር መብላት አይችልም። ያኔ ቀይ ወጥ 3 ብር ነበር። ከዚያስ ምን አለህ? ይህ ሰው “ምሳ እንብላ” አለኝ፡፡ “አይ እኔ ልበላ ነው፤ አመሰግናለሁ” አልኩት። እኔ ልበላ ነው ያልኩት፣ ያንን በኪሴ የያዝኩትን ከገበሬዎች የገዛሁትን ቆሎ ነው፡፡ “ኧረ ግዴለም ና እንብላ” ብሎ ይዞኝ ሄደ። ቆርቆሮ ቤቶች ውስጥ ካቦዎች አሰሪዎችና ከ10 ብር በላይ ደሞዝ ያላቸው የሚበሉበት ነው። እኛ ሳጠራ ቤቶች ውስጥ ነበር የምንበላው - ቂጣ በሚጥሚጣና ሽልጦ። እኔ ያኔ ያጣሁት ቂጣና ሽልጦ ነበር። ይህ ሰው ይዞኝ ሄደና ገባን። “አንድ ቀይ ወጥ” ብሎ አዘዘ። እኔ ለሁለት ልንበላ ነበር የመሰለኝ። ለኔ አዘዘና እሱ ወደ ጓዳ ገብቶ ከጓደኞቹ ጋ ማውራት ጀመረ። ለኔ ቀይ ወጥ መሃሉ ላይ ቅልጥም ያለው መጣልኝ፡፡ “ምሳው ቀርቧል ና እንብላ” አልኩት። “ኧረ ፍሬንድ ላንቺ ነው ያዘዝኩት፤ እኔ ምሳ እቃ ይዤ መጥቼ ነበር በልቻለሁ” አለኝና እንድበላ ገፋፋኝ። በጣም ገረመኝ። እንጀራ ከበላሁ በጣም ቆይቼ ነበር፤ በተለይ ስጋማ ካየሁትም በጣም ቆይቷል። ያንን ምሳ እየበላሁ እንባ ተናነቀኝ። በዚያች አጭር ጊዜ ፈጣሪዬ ፀሎቴን ሰምቶ የማላውቀውን ሰው ልኮ እንደዛ እንጀራ እንድበላ አደረገኝ። ያውም በቀይ ወጥ፣ ያውም ቅልጥም ያለው እንጀራ በዚያ ምድረበዳ አበላኝ፡፡ በእግዚአብሔር ላይ ያለኝ እምነት ከዚያን ጊዜ ጀምሮ መጠንከር ጀመረ። “ሁሌ አምንሃለሁ” ብዬ ወደ ሰማይ አንጋጥጬ እግዚአብሔርን አመሰገንኩኝ። በሳምንቱ እዛው ግቢ ብሎኬት ፋብሪካ ውስጥ 1 ብር ደሞዝ ጭማሪ ተደርጎ በሰባት ብር ተቀጠርኩ። ምግብም እንደሌላው በዱቤ መብላት ጀመርኩኝ። የምግብ ችግሬ እዛው እየተቀረፈ ፀሎቴም እየሰራ መጣ። አንዴ በሌሊት ከቤትህ ወጥተህ በጅብ ልትበላ ነበር ግን ለምንድን ነው በሌሊት የወጣኸው? የማልረሳቸው አስጨናቂ ጊዜያት በአንባቢ አዕምሮ ውስጥ እንደሚቀር አንቺ ማሳያ ነሽ። የእግዚአብሔርን ተዓምር ካየሁበት ዕለት አንዱ ይሄ ቀን ነው። ሜክሲኮ አካባቢ ኬክ ቤት ረዳትነት በስንት ፍለጋ ተገኝቶልኝ መስራት ጀምሬ ነበር። ሳንቲም ያለኝ ጊዜ 11 ሰዓት እነቃና በትራንስፖርት እሄዳለሁ። በዚያን ቀን ግን ሳንቲም ስላልነበረኝና በእገሬ ስለምሄድ ተኝቼ እንዳይረፍድብኝ ስነቃ ስተኛ ቆይቼ የሆነ ሰዓት ላይ ብንን ስል የረፈደብኝ መስሎኝ ነው ውጥት ብዬ መሄድ የጀመርኩት። እኔ 20 ጉዳይ ለ11 መስሎኝ፣ 20 ጉዳይ ለ10 ነው የወጣሁት፡፡ አስቢው…. ዘጠኝ ሰዓት ከምናምን ማለት ነው። እርግጥ ስወጣ ጨለማው ከብዶኛል። ያልለመድኩት አይነት ድቅድቅ ጨለማ ነው። ትንሽ እንደሄድኩ የየካ ጫካ ያስፈራል፤ ብዙ የጅብ ድምጽ ይሰማኛል። ሲጮሁ ራቅ ብሎ ያው የሰፈራችን ኳስ ሜዳ አካባቢ ሆነው ነበር የመሰለኝ። ነገር ግን ጉዞዬን ስቀጥል፣ በኔና በጅቦቹ መሃል ከ15 -20 ሜትር በሚሆን ርቀት ላይ አየኋቸው መሃላቸው ገባሁ። ወደ ኋላ ብመለስ ከተከተሉኝ ማምለጫ የለኝም። ያለኝ አማራጭ መቆም ብቻ ነበር። ብዙ ናቸው፤ አይናቸው ያበራል። አንዱ ግን እየቀረበኝ መጣ፤ ሊተናኮለኝ እንደሆነ ገባኝ፤ ድንጋይ ለማንሳት መሬቱ አይታየኝም። ግን ዝም ብዬ ጎንበስ ብዬ ድንጋይ እንደ ማንሳት ስል ሽሽት ይላል። ከዛ ደሞ ይቀርበኛል። በቃ ጭንቅ ውስጥ ገባሁ። በቃ ተበላሁ ብዬ ተስፋ ቆርጬ ነበር። “ፈጣሪዬ አውጣኝ፤ ተዓምር ስራ” ብዬ ጸለይኩኝ። እንደምንም መሬት ዳስሼ ሁለት ድንጋይ አነሳሁ። በዚያ ድንጋይ ሆዱን መታሁትና ጮኸ። በአንዱ ድንጋይ የአንድ ቤት ቆርቆሮ አጥር በሃይል ስመታ ሁሉም ገለል አሉልኝና በዚያች ቅጽበት አንድ መንገደኛ አግኝቼ ወደ ዋናው አስፓልት ወጣሁ። ያንን ጊዜ ባልተመቻቸ ሁኔታም ውስጥ ቢሆን እንድኖር አንድ ተጨማሪ እድል እንደተሰጠኝ ነው ያሰብኩትና እግዚአብሔርን ያመሰገንኩት። በእኛ አገር ባህልም እንበለው ስነ-ልቦና፣ ወግም እንበለው ልማድ… ወንደ ልጅ የፈለገ ቢቸገር በቤት ሰራተኝነት አይቀጠርም፡፡ አንተ ያን አድርገኸዋል… በዚያ ሰዓት ባህል ወግ…. የሚሉትን ነገር ማሰብ ለእኔ ቅንጦት ነበር። እኔ የማስበው ከሌብነት ውጪ ማንኛውንም ስራ ሰርቼ ራሴን ለማሸነፍ ነው። በወቅቱ መማር እፈልጋለሁ። መቀየር እፈልጋለሁ። ስለዚህ ስራ ሳልንቅ መስራትና መለወጥ ነበረብኝ። የቤት ሰራተኝነት አይደለም ምንም ቢሆን ለመስራት ቆርጫለሁ። ለምን? መማር አለብኝ፡፡ ለምን? በበቂ ሁኔታ መናቅን፣ መገፋትን፣ መራብን፣ ብቸኝነትን አይቻለሁ። ከዚህ ሁሉ ለመውጣት መማር መቀየር አለብኝ። በእርግጥ የቀጠሩኝ ባልና ሚስቶች የማላውቃቸው ሰዎች አይደሉም፡፡ መርዳትና ማስተማር ይችሉ ነበር፤ ግን ያንን አላደረጉም። በፊት በመንፈሳዊ ህይወት አብረን እናገለግል የነበርን ሰዎች ነን። ነገር ግን እግዚአብሔር በዚያ እንዳልፍ ፈልጎም እንደሆነ አላውቅም። ያ ሆነ። ሰውየው ከውጪ መጥቶ አገኘኝ፤ ሚስቱ የውጪ ዜጋ ናት። “አንተነህ በጣም ጎበዝ! እየተማርክ እንደሆነ ሰማሁ በርታ”! አለኝ። “አዎ እየተማርኩም እየሰራሁም ነበረ፤ ግን ት/ቤቱ 40 ብር ክፍያ ጨምሮብን ያንን መክፈል የሚያስችል ደሞዝ ስላልሆነ ያንን ስራ አቁሜ ሌላ እየፈለግሁ ነው” አልኩት። “አይ ችግር የለም፤ የቤት ሰራተኝነት ስሜት ካልተሰማህ ለምን አትሰራም” አለኝ። እኔ ደሞ በፊት የምናገለግልበት የውጪ ድርጅት ውስጥ በተላላኪነትም ቢሆን እንደሚያስቀጥረኝ ጠብቄ ነበር። ሲኤምሲ አፓርትመንቶች ውስጥ ቀጠረኝና ሄድኩኝ፡፡ ፡፡አሜሪካዊቷ ሚስቱም በፊት በጣም የምታውቀኝ የምንከባበር ነበርን። አሁን እንደማያውቁኝ ሆኑ። እሺ ብዬ ገባሁ፤ ሚስቱ ኪችን ውስጥ ብዙ የሚታጠብ እቃ ነበር፤ አሳየችኝ። ቤት እንዴት እንደሚጸዳ፣ ምግብ እንዴት እንደሚሰራ ሱቅ እቃ መገዛዛት፣ ሽንት ቤትና የሚታጠብበትን ኬሚካል ሁሉ አሳየችኝ። የህጻናት ልብስ አስተጣጠብና ሌላ ሌላውንም አሳየችኝ ብቻ ሁሉንም ስራ ብዬ ተቀበልኩኝ። ማንኛዋም የቤት ሰራተኛ የምትሰራውን ሁሉ እሰራለሁ። ብዙ እንግዳ ይበዛል፤ ምግብ ቶሎ ቶሎ እሰራለሁ። ብቻ ምን አለፋሽ… ስራዬ ብዬ ስለያዝኩት ምንም አልመሰለኝም። ስንት ብር ነበር ደሞዝህ? ምን ያህል ጊዜስ ሰራህ? ትምህርቴን ለመጨረስ የቀረኝ አራት ወራት ብቻ ነበር። እነሱ የሚኖሩት ሲኤምሲ ነው፤ እኔ የምማረው ፒያሳ ኤልኤም ኢንተርናሽናል የሆቴልና ቱሪዝም ኮሌጅ ነው። 260 ብር ይከፍሉኛል፤ 220 ብር ለት/ቤት እከፍላለሁ፤ አርባ ብር ትተርፈኛለች። ያቺ አርባ ብር አትበቃኝም። አንድ ሰው ዝም ብሎ በየወሩ 50 ብር ስለሚረዳኝ እያብቃቃሁ ነው የምኖረው…ለትራንስፖርትም ለምንም። አየሽ እነዚህ ሰዎች ቤት በተመላላሽነት ነበር የምሰራው፤፡ አንተ ምግብ እየራበህና እየናፈቀህ ነው ያደግኸው፡፡ ግን ደግሞ የምግብ ዝግጅት ሙያ ሰልጥነህ ሼፍ ሆነሀል… እንዴት ፍላጎቱ አደረብህ? እውነት ነው፤ ብዙ ሰው ወደ ምግብ ባለሙያነት የሚገባው ከቅንጦት ሊሆን ይችላል። የኔ እንደዛ አይደለም። የማትሪክ ውጤት ስላልመጣልኝ ከአንድ ጓደኛዬ ጋር ዶሮ ለማርባት ሞክረን ነበር። ከጫካ እንጨት ቆርጠን ዶሮ ቤት ሰራን፤ ዶሮዎች ገዝተን ስራ ጀመርን። 30 ዶሮዎች ነበሩ፤ አነር በላብን፤ ከአነር የተረፉትንም በሽታ ገብቶ ጨረሳቸው። በዚህ ስራ ብዙ ተስፋ ነበረን። ይሄ ተስፋ በዚህ ተሟጠጠ። እኔ ከዛ በፊት የቀን ስራ ነው ሰርቼ የማውቀው፤ ትምህርቴን ለመማርም ወተት ተሸክሜ እያመላለስኩ በወር 20 ብር ይከፈለኝ ነበር። 16 ብር ለ8ኛ ክፍል የግል ት/ቤት እከፍል ነበር። ብቻ ስራ ስፈልግ የማውቃቸው መንፈሳዊ ሰዎች ፈልገው፣ እዛ ሌሊት ወጥቼ ስሄድ ጅብ ልበላበት የነበረው ኬክ ቤት አስገቡኝ፤ ረዳት ኬክ ጋጋሪ ሆንኩኝ። በወር 130 ብር ደሞዝ። ከሰኞ እስከ ሰኞ እሰራለሁ። ጠዋት ገብቼ ቀን 10 ሰዓት እወጣ ነበር። ለኔ ዳቦ ማግኘት ቀላል አልነበረም። እየሰራሁ ሙያ ለመልመድ ስጣጣር ዋና ኬክ ጋጋሪው ፈቃደኛ አልነበረም። ይከለክለኝ ነበር፡፡ ሙያውን እንድለምድ አልፈለገም እኔም ለምን ተምሬ ሙያተኛ አልሆንም ብዬ ነው ኤልኤም ኢንተርናሽናል የገባሁት። በኋላ የቀለም ትምህርቱ አልቆ ወደ ተግባር ስንገባ የግብአት መግዣ ስለሚያስፈልግ 40 ብር ጭማሪ ተደርጎ፣ 130 ብሩ ስላልበቃኝ ትቼ ስራ ስፈልግ ነው እነዛ ባልና ሚስቶች በ260 ብር የቀጠሩኝ፤ የቤት ሰራተኛ የሆንኩት፡፡ በዚህ ምክንያት ነው፤ የተማርኩትም ሼፍም የሆንኩትም። መከራና ፈተናው አውሮፓም ሄደህ አልቀረልህም በሼፍነት ስትሰራ የምታውቀው ሰው ስፔን ለእረፍት ጋብዞህ የሄድክበትና ወደ ጀርመን የተሰደድክበት ሂደት እጅግ ከማይረሱ አሳዛኝ ታሪኮችህ ተጠቃሽ ነው። አሁን ላይ ስታስበው ምን ይሰማሃል? አሁን ላይ ሳስበው ያን ሁሉ እንዴት አድርጌ፣ በምን አቅሜ ቻልኩት እላለሁ። በጀርመን ከአንዱ ስደተኛ ካምፕ ወደ ሌላው የተንገላታሁበት፣ የእናቴን ሞት በፌስቡክ የሰማሁበት፣ በዛን ጊዜ አንድ ስደተኛ ጥገኝነት መጠየቅ የሚችለው ከአገሩ ወጥቶ መጀመሪያ እግሩ የረገጠበት ስለሆነ ወደ ስፔይን ይመለስ ስባል በጣም ብዙ መከራ ተደራርቦብኛል፡፡ እዚህ አገር ቤትም´ኮ በተለይ ሼፍ ሆኜ ለመስራት ስገባ ያጋጠመኝ ዋና ሼፍ ንቀቱ፣ በአባቴ ስም በብሔሬ ያላግጥ የነበረበት ሁኔታ… አንዱን ምግብ ጥሩ አድርጌ ስሰራ ወደ እቃ አጣቢነት፣ ከዚያ ወደ ኬክ፣ ከዚያ ወደ አንዱ እያንከለከለ ያደረሰብኝ በደል በእጅጉ አይረሳኝም። አፍሪካ ህብረት ለትልልቅ ዴሊጌቶች ዲፕሎማቶች ዋና ሼፍ ሆኜ ስሰራ “ረዳት ይመጣልሃል፣ ስራ በዝቷል” ተብሎ ተብሎ ማን ቢመጣ ጥሩ ነው ያ ያንገላታኝ የነበረ ሼፍ፡፡ ከእርሱ ጋር ነው የምትሰራው ተባልኩ ግን እሱም ዳግመኛ ወደ አፍሪካ ህብረት ድርስ አላለም። በዚህ መልኩ እጅግ ብዙ አሰቃቂ ነገሮችን አልፌ አሁን እዚህ ደርሼያለሁ። ተይው የአውሮፓውን እዚህ አገር ቤትም ነው የምልሽ። በእርግጥ በአሁኑ ሰዓት ጀርመን ኑረንበርግ ውስጥ እጅግ ቅንጡ በሆነና በባለ 5 ኮከብ “ዓለም አቀፍ ሆቴል” ውስጥ ነው የምትሰራው? አዎ እዛ ነው የምሰራው። አንዳንድ ሰው በእንደዚህ አይነት መከራ አልፎ ጥሩ ደረጃ ላይ ሲደርስ ያለፈ ታሪኩን ለማውራት ያፍራል፡፡ አንተ ሌላው ከኔ ይማር ብለህ ታሪክህን በግልጽ በመጽሐፍ ለአንባቢ አቅርበሃል፡፡ እንዴት ደፈርክ? ሁሌም ራስን ሆኖ…. ማንነትን ተቀብሎ በመኖር መርህ አምናለሁ። እኔ ያለፈውም አሁን ያለሁበትም ህይወቴ የኔ ታሪክ ነው። በስርቆትና በወንጀል አልተሳተፍኩም፡፡ እንደዚያ እየራበኝ ስርቆት አስቤ አላውቅም፤ ግን ዝቅ ብዬ ሰርቻለሁ። ብዙ ሰው ከእኔ እንዲማር ነው የጻፍኩት ፤ደግሞ ያስተምራል ብዬ አምናለሁ። መጽሐፉ ሲታተም ገንዘብ ለማግኘት አይደለም። አሁን ወደ ጀርመንኛ እየተተረጎመ ነው። እናም ራሴን ሆኜ መኖሬ ነው የሚስደስተኝ። ስለዚህ በህይወቴ የማፍርበት የምሸማቀቅበት ነገር የለም። በመጨረሻ የምትለው አለ? በዛ በችግሬ ወቅት ከጎኔ የቆሙ በርካቶች ናቸው። በጀርመንም ብዙ ያገዙኝ ጀርመናዊያን አሉ፣ አገር ቤትም እንደዛው ስም ባልጠቅስም ለሁሉም ምስጋናዬ ይድረሳቸው፡፡ ሁሉንም አመሰግናለሁ። መፅሐፉን ቅርጽ በማስያዝ በኩል ደራሲ ኃይለመለኮት መዋዕልና ጋዜጠኛ ብርሃኑ ሰሙን አመሰግናለሁ። በርካቶች የማመሰግናቸው ሰዎች አሉ። በመጨረሻም “ስደተኛው ሼፍ” የተሰኘው መፅሐፌ ሃቀኛ ያልተበረዘ፣ የውሸት ታሪክ የሌለበት፣ እውነተኛ ፅናትና የትግል ማሳያና ማሸነፊያ መንገድ ስለሆነ፣ ሰዎች አንብበው እንዲማሩበት እጋብዛለሁ።
በቁጥር አንጣላም። መቶ ….. ሶስት መቶ …. አራት መቶ …. ሰባት መቶ …. እስካሁን ያለው ሲደመር ቤት ትክክለኛውን ቁጥር ይቁጠረውና ንጹሃን የአማራ ተወላጆች አልቀዋል። እልቂታቸው ዘግናኝ ነው። አማራ ያልሞተው ዓይነት ሞት የለም። ላለፉት ሰላሳ ዓመታት አማራ በተጠና ፍረጃ ” ነፍጠኛ” ተብሎ ተዘርዝሮ የማያውቅ በደል ደርሶበታል። የህዝቡ ቁጥር ሳይቀር በፖሊሲ ደረጃ እንዲወርድ ተደርጓል። እንዳይወልድ ሆኗል። ይህ ሁሉ መከራ ለአማራ ህዝብ ለምን? ኦሮሞ በቋንቋው የመስራትና የመማር፣ ብሎም የመዳኘት፣ ራስን በራስ የማስተዳደር፣ በፌደራል ደረጃ አብዛኛ ቁጥር ስላለው ተመጣጣኝ ስልታን ሲጠይቅ ነበር። ይህን ጥያቄውን ማንሳቱ ሃጢአት ሆኖ መከራ ሲበላ፣ ሲታሰር፣ ሲገደለና “ጠባብ” ተብሎ ተፈርጆ ሲነገላታ ነበር። ዛሬ ያ ታሪክ የለም። በዚህም መነሻ በኦሮሞ ሕዝብ ስም ጠብመንጃ ይዞ ሰላማዊ ዜጎችን በጅምላ ለመጨፍጨፍ አንዳችም ምድራዊ ምክንያት የውም። የስልጣን ጥያቄ እንዳለ ይታወቃል። የስልጣን ጥያቄን ለማሳካት ግን በኦሮሞ ሰላማዊ ህዝብ ስም ሌሎችን በዘራቸው መርጦ ማረድ ፍጹም አውሬነት ነው። ለስልጣንም አያበቃም። ነገ ሌላ ዋጋ ያስከፍላል። ወደማይቆመው ደም መቃባት ያሸጋግርና ሌሎች ምስኪኖች እንዲያልቁ ምክንያት ይሆናል። ይህን አያምጣው!! በኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ወለጋ ሰኔ 1/2014 ዓ.ም ጊምቢ ወረዳ ባሉ ቀበሌዎች የኦነግ ሸኔ ሃይሎች የጅምላ ጭፍጨፋ ማካሄዳቸውን የተረፉ ምስክሮች ተናግረዋል። ከጭፍጨፋው ከተረፉት በላይ ምስክር የለምና ማንም ምንም ቢል ማመን ቀርቶ ለአፍታም ጆሮ የሚያውስ አካል የለም። ይህ አሳዛኝ፣ መኖርን የሚፈታተን ዜና ከተሰማ ጀምሮ ተቆርቋሪዎች ነን ፣ ልዩ አሳቢ ነን የምትሉ፣ ሰው የሆናችሁ መላው ኢትዮጵያዊያን … የደም ፖለቲካ ከሚቆምሩ ለምድ ለባሾች በስተቀር ሃዘን ላይ ነን። ከሃዘኑ በሁዋላ ምን ይሁን? ከ450 ያላነሱ የአኝዋክ ወገኖቻችን በአንድ ቀን መታረዳቸውን አንርሳ። በበደኖ ኡንቁፍቱ ገደል የሰው ልጆች ከነነብሳቸው መገደላቸውን አንርሳ፤ በደደር ሰዎች መታረዳቸውን አንዘንጋ። ሌሎች አካባቢዎችም በተመሳሳይ የሰው ልጆች ተሰይፈዋል። ይህ ሁሉ የሆነው ደግሞ ዘርን መሰረት በማድረግ ነበር። ዛሬም ያው ድራማ እንደቀጠለ ነው። ኢትዮጵያ ከዚህ አዙሪት እንዴት ትውጣ? ምን ቢደረግ ይሻላል? አማራው እስከመቼ እየታረደ ይቀጥላል? የፖለቲከኞች የደም ቁማርና የንጹሃንን ነብስ ለመብላት የሚማማሉት እስከ መቼ ነው? ህዝብስ ስለም “በስሜ አትግደሉ፣ ለልጅ ልጆቼ ቂምና ጥቁር ጠባሳ አታስቀምጡ” ሲል አይሟገትም። ሆ ብሎ አይነሳም? ከተራ መንተክተክ፣ ከማይረባ የፖለቲካ ንግድና ዝናና ሽቀላ ይልቅ ረጋ ብሎ ከላይ የተነሱትን ጉዳዮች ማሰቡ የውቅቱ ብልሃት ይመስለናል። ሁሉም አልቃሽ ከሆነ የመፍትሄ ድምጾች ይዋጣሉ። ለቅሶን በማቆም ይህን መረን የለቀቀ ወንጀል እንዴት ማስቆም እንደሚገባ ህግን ጠብቆ መንደፍ ግድ ይላል። የኦሮሚያ ክልል መንግስት የተለያዩ ሃላፊዎች እንደ መንግስት ሃላፊነታቸው ዛሬ ለደረሰው ግፍ በጥፋታቸው ልክ ተጠያቂ ሊሆኑ ይገባል። ከመንግስት አልፎ ዞን፣ ከዞን አልፎ ወረዳ፣ ከወረዳ ዝቅ ሲል ቀበሌዎቹ በተዋረድ በህግ ወረንጦ መዳነት አለባቸው። ይህ ውሎ ሳያድር ለህዝብ በግልጽ ሊነገር ይገባል። ከዚህ ጎን ለጎን በአካባቢው በቋሚነት የአገር መከላከያ ሃይላችን ሊሰፍርና እንደለመደው ክንዱን በክፉዋች ላይ እያነሳ ዜጎችን ከተመሳሳይ ጥቃት ሊጠብቅ፣ ከዛው ጎን ለጎን ህዝቡ ራሱን አደራጅቶና ታጥቆ በራሱ አደረጃጀት ማናቸውንም በትር እንዲመከት ሊደረግ ይገባል። የእሳካሁን ይበቃል። ከዚህ በላይ ህዝብ መታገስ በቃ ሊል ይችላልና!! እናንት በጋምቤላና በወለጋ የተጨፍቸፋችሁ ምስኪን ዜጎች አምላክ ምህረቱን ያብዛላችሁ። ለስልጣንና ስልጣን ይዞ ለመዝረፍ በንጹሃን ደም አመጽ ለማቀጣጠል የምትተጉ የደም ነጋዴዎች በይትኛውም መመዘኛ ሃጢያታችሁን ማቅለል እንደማትችሉ ተረዱ። ዛሬ በኦሮሞ ስም ንጹሃንን ለመቸፍጨፍ የሚያበቃ አንዳችም ምድራዊ ምክንያት የለምና አቁሙ!! ነብስ ይማር
የኮሮና ቫይረስ በአቬሽን ኢንዱስትሪ ላይ ከፍተኛ ኪሳራ እያደረሰ እንደሚገኝ የሚታወቅ ሲሆን ከወረርሽኙ ማግስት የሉፍታንዛ አየር መንገድ አንድ መቶ አውሮኘላኖችን ሊያጣ እንደሚችል ዘገባው አስታውቋል፡፡ ግማሽ የሚሆነው የሠራተኞች ቅነሳ በጀርመን እንደሇነ የገለፀው አየር መንገዱ ለዚህም ከአጋር ድርጅቶች እና ህብረት ሥራ ማህበራት ጋር ስምምነት ላይ ደርሻለሁ ብሏል፡፡ የሉፍታንዛ አየር መንገድ 135 ሺህ ሠራተኞች ያሉት ሲሆን ግማሽ የሚሆኑት ደግሞ በጀርመን የሚገኙ ናቸው፡፡ የአየር መንገዱ የሠራተኞች ዳይሬክተር ሚሼል ኒግማን የአብዛኞቹን ሠራተኞች የሥራ ቅጥር ሳናቋርጥ ሥራውን ለማስቀጠል እንሠራለን ማለታቸውን ብሉምበርግ ዘግቧል፡፡ ውድ አድማጮቻችን እና ተከታዮቻችን የኢትዮ ኤፍ ኤም ስርጭቶችን፣ዜናዎችን እና ሌሎች ዝግጅቶችን ለመከታተል የቴሌግራም ቻናላችንን ይቀላቀሉ። https://t.me/ethiofm107dot8
Albanian / Amharic / Arabic / Bengali / Bosnian / Chinese / Dutch / English / Finnish / French / German / Hindi / Indonesian / Malay / Persian / Oromo / Russian / Swedish / Somali / Tamil / Telugu / Thai / Turkish / Urdu እስልምና በኢትዮጵያ ታሪክ ክፍል አንድ [ክፍል ሁለት] [ክፍል ሦስት] ቅንብር በአዘጋጁ በወቅቱ ያለው የሙስሊሞች የተቃውሞ ሰልፎች ቅንብር እና ይህንን አስመልከቶ የገዢው ፓርቲ ወስዶ የነበረው አሁንም እየወሰደ ያለው እርምጃ ብዙዎችን እያነጋገረ ነው፡፡ ለዚህ የሙስሊሞች ተከታታይ የተቃውሞ ሰልፎችና ስር የሰደዱ የተለያዩ ድርጊቶች ምክንያቱና የትኩረት አቅጣጫው ምንድነው? ለአገሪቱና በአገሪቱ ላይ እንዲኖር ለምንፈልገው አብሮ ማደግ፣ ሰላም፣ የሰብዓዊ መብት መጠበቅና የእምነት ነፃነት ይጠቅማልን? ወ.ዘ.ተ የሚሉ ጥያቄዎችን ማንሳትና መወያየት ለመፍትሄም መዘጋጀት አስፈላጊ ናቸው፡፡ ማንኛውም የኢትዮጵያ ዜጋ በሚከተለው ሃይማኖት፣ የፖለቲካ አመለካከት፣ ዘርና ፆታ ተፅዕኖ ሳይደረግበት የሚኖርባት ኢትዮጵያን ማየት ሁሉም ሰው መውደድና መፈለግ ለዚህም የተቻለውን ጥረት ማድረግ ይኖርበታል፡፡ “እስልምና በኢትዮጵያ ታሪክ” በሚለው አምድ ስር በታሪክ ተመራማሪዎች የቀረቡ ታሪካዊ እውነቶችን በተከታታይ እናቀርባለን፡፡ ይሁን እንጂ ይህ የአሁኑ ጽሑፍ የሚዳስሰው ሁለቱ ዋና ዋና የሙስሊም የአመለካከት ትግሎች ወይንም “ሙስሊማዊ ርዕዮተ ዓለሞች”፤ ከየት መነጩ ወዴት ተሰማሩ አሁን በዓለማችን ላይ ምን ተፅዕኖ አላቸው፣ በተለይም የኢትዮጵያን የወደፊት እጣ እንዴት ሊቀርፁ ወይንም ቀለል ባለ ቋንቋ ሊነኩ ይችላሉ የሚለውን ለማሳየት እንደ መጀመሪያ ታሪካዊ መነሻ የቀረበ ነው፡፡ እንዲህ ያለውን ጽሑፍ በአንድ ክፍል ማቅረብ ከባድ ስለሚሆን አንባቢዎችንም እንዳያሰለች በሦስት ክፍሎች ለማቅረብ ተገደናል፡፡ የዚህ ገፅ አዘጋጆች ፖለቲከኞች ወይንም የአንድ የፖለቲካ ቡድን ደጋፊዎች አይደለንም፣ እኛ ተራ ኢትዮጵያውያን ነን፡፡ እንደማንኛውም ኢትዮጵያዊ የአገሪቱ ወቅታዊና የወደፊት ጉዳይ ያሳስበናል፡፡ የኛ ድረ ገፅ ስያሜው “ለእስልምና መልስ” የሚልና ትኩረቱም መንፈሳዊ በሆኑ ጉዳዮች ላይ ያነጣጠረ ነው፡፡ በአገሪቱ ውስጥ አሁን ባለው የእስልምና እምነት እንቅስቃሴ አማካኝነት እየቀረቡ ያሉትን ወቅታዊ ጽሑፎች፤ ታሪካዊ መረጃዎችን መከታተል እና ለነዚህም መልስ መስጠት አስፈላጊ ሆኖ አግኝተነዋል፡፡ በመሆኑም “የእስልምና ታሪክ በኢትዮጵያ” አምድ ስር እኛ ያገኘናቸውን ግንዛቤዎች ለአንባቢዎች ለማስተላለፍ እንሞክራለን፡፡ አዲስ የኢትዮጵያ ታሪክ፡ የአሁኗ ኢትዮጵያ የ18ኛው መቶ ዘመን መጨረሻ ላይ በፖርቹጋሎች እርዳታ ተመሰረተች የሚሉ ጽሑፎች በተለያዩ የሙስሊም ጸሐፊዎች በተለያዩ ቦታዎች እንዲሁም ቋንቋዎች እየተሰራጩ ነው፡፡ እነዚህ ታሪኮች እውነት ናቸውን፣ ለመሆኑ ዓላማቸው ምንድነው? ኢትዮጵያውያንን ይጠቅማሉ ወይንስ ይጎዳሉ? በኢትዮጵያ አየር መንገድ የሚታተመው “የሰላምታ መጽሔት” ሐሙስ ነሐሴ 3 2004 በድረ ገፅ ላይ ባቀረበው አምድ ላይ ጽሑፍ ያበረከተው Najib Mohammed የሚባል ሰው ነው፡፡ እርሱም ጽሑፉን ሊያጠቃልል ሲል በአስራ አራተኛው ክፍለ ዘመን ኢትዮጵያ የሰባት እስላማዊ ሱልጣኔቶች አገር እንደነበረች ጠቅሶ አሁን የምናያት ኢትዮጵያ በ18ኛው መቶ ክፍለ ዘመን መጨረሻ ላይ በፖርቱጋሎች እርዳታ እንደተመሰረተች አቅርቦልና፡፡ ናጂብ ይህንን አዲስ ታሪክ ያስቀመጠው ማስረጃዎችን በመጥቀስ ታሪክ በማገናዘብ አይደለም፤ የጻፈውን እውነታ እንድናገናዝብም የሰጠው ምንም ማስረጃ የለም፡፡ የዚህ ጽሑፍ አዘጋጅ ፀደይ በምትባል ጸሐፊ የተቀናበረ ሌላ ‘A leap of Faith’ tseday.wordpress.com/tag/harar/ የሚልና ጥሩ ጥናታዊ ታሪካዊ ጽሑፍን አንብቧል፡፡ ይህ የፀደይ ታሪካዊ ጽሑፍ እስልምና በኢትዮጵያ ላይ በግራኝ መሐመድ በኩል ያደረሰውን ጥፋት አሳይቷል፡፡ ፖርቹጋሎች የኢትዮጵያን መንግስት ከእስልምና ውድመትና እስላማዊ አገር ከመሆን እንዳዳኗት ያሳያል፡፡ በእርግጠኝነት ታሪክ የመሰከረው ኢትዮጵያ ለእስልምና በዓለም ላይ መኖር ከየትኛውም የዓለም ክፍል በበለጠ መልኩ ትልቅ አስተዋፅዖ እንዳደረገች ነው፡፡ አዲሱ የኢትዮጵያ ታሪክ እየተውጠነጠነ ያለው የሙስሊም የመጀመሪያ ስደትንና ከዚያ በመያያዝ ወደ እስልምና ተለውጧል የመጀመሪያ የእስላም ንጉስ ሆኗል፡፡ ስለሆነም ኢትዮጵያ የመጀመሪያዋ የእስላም አገር ናት የሚለው ታሪክ ነው፡፡ ፀደይ ባቀረበችው ጽሑፍ ላይ ይህ በዚያን ዘመን ተለወጠ ተብሎ የሚጠራው ንጉስ ንጉስ “አሻማ” ወይንም “ነጃሺ” በኢትዮጵያ ታሪክም ሆነ በኢትዮጵያ ቤተክርስትያን ታሪክ ውስጥ እንደማይታወቅ ነው፡፡ ይሁን እንጂ በዶ/ር መስከረም መላኩ በተሰራ የምርምር ጽሑፍ ‘Comparative Religion’ submitted to Spiritual institute of New York፤ 2009 Addis Ababa Ethiopia ጽሑፍ፣ ጽሑፉን ከሚቀጥለው ድረገፅ ላይ አግኝቶ ማንበብ ይቻላል፡፡ dcbun.tripod.com/id18.html የሰፈረው አስገራሚ አዲስ ታሪክ ነው፡፡ ያ ንጉስ እስልምናን ከተቀበለ በኋላ መሐመድ ስሙን አህመድ አል-ነጃሺ ብሎ እንደቀየረው፣ ቤተሰቦቹ እስልምናን እንደተቀበሉ፡፡ ከዚያም ቀጥሎ መንግስቱን ከአክሱም ወደ ውቅሮ ከቀየረ 15 ዓመታት በኋላ እንደሞተ ይናገራል፡፡ የዶ/ር መስከረም ጽሑፍ ለዚህ ታሪክ እውነተኛነት የመሐመድ 43ኛ ቀጥታ ዘር የሆነውንና የውቅሮውን መስጊድ የጎበኘውን ዶ/ር ኤም ኤን አለምን ጠቅሶ፣ በነጃሺ አዲስ እራዕይ መሰረት ንጉሱ እስልምናነ በኢትዮጵያ ውስጥ ሁሉ እንዳስፋፋ የዚያም ውጤት እስልምና እስከ አልጀሪያ ሞሮኮ ድረስ ክፍት በርን እንዳገኘ ያስረዳል፡፡ ይህ ጽሑፍ እንዳለ በሌላ ዶ/ር ሰላሃዲን እሸቱ በተባለ ሰው ደግሞ በሌላ መልኩ “Authentic History of King Negash of Abyssinia (Currently Ethiopia)” በሚል ርዕስ ቀርቧል፡፡ እንዲህ ዓይነት ጽሑፎች ሲዘጋጁ የበለጠ እውነት እንዲመስሉ ልዩ ልዩ ማስረጃ ሰጪ የሆኑ ቅንብሮች ማያያዝ የተለመደ ሆኗል፡፡ በፀደይ ጽሑፍ ስር ተያይዞ የቀረበውን ጥናታዊ ፍልም እንደምሳሌ ለመጥቀስ እወዳለሁ፡፡ ጥናታዊው ፊልሙ የተቀናበረው Dr. Abdullah Hakim በተባለ አሜሪካዊ ዜጋ ሲሆን ርዕሱ ‘Untold Ethiopia an Islamic Journey’ የሚል ነው፡፡ የጥናታዊ ፊልሙ ዓላማ ኢትዮጵያ ድብቅ የሆነ እስላማዊ ታሪክ እንዳላት ከሐረር ጀምሮ አክሱም ድረስ የዘለቀ እና የነጃሺንም ተረቶች ሁሉ ያያዘ ነው፡፡ የመናገር፣ የመጻፍና ፊልም የመስራትን መብትን ተጠቅሞ ማንም ሰው የፈለገውን ለማቅረብ መብቱ ሊጠበቅለት እንደሚገባ እኛ እናምናለን፣ አንባቢዎች ግን የቀረቡላቸውን ጽሑፎችም ይሁን የፊልም ቅንብሮች ከታሪክና ከእውነት ጋር የማገናዘብ ግዴታና በእውነት ላይ መቆም ስህተትንም ባገኙት አጋጣሚ መግለጥ ይኖርባቸዋል፡፡ እንደዚህ ዓይነት እንቅስቃሴዎች በረቀቀና ብዙዎች ባልነቁበት መንገድ የኢትዮጵያ ታሪክ በአዲስ መልኩ እየተጻፈና እየተቀናበረ መሆኑን ይጠቁማሉ፡፡ እንቅስቃሴው ስር የሰደደ ታሪካዊና ጥልቅ እንዲሁም በሚገባ በዕቅድ ተይዞ የሚመራ ውጤቱም ለአገሪቱ አስፈሪ ነው ብሎ መናገር ስህተት አይመስለንም፡፡ የዛሬው ጽሑፍ መሠረት፡ ይህ ጽሑፍ ሙሉ ለሙሉ የተመሰረተው የታሪክ ተመራማሪውና እጅግ ብዙ አስደናቂ ኢትዮጵያዊ ታሪኮችን በመፈልፈል ኢትዮጵያና እስላማዊ እንቅስቃሴ ላይ የምርምር ስራ በሰራው በፕሮሴፈር ኤርሊች ስራ ላይ ነው፡፡ በተለይም ፕሮፌሰር ኤርሊች ከሌላ ዕውቅ የታሪክ ፕሮፌሰር ከሙሰጠፋ ካብሃ ጋር ባዘጋጁትና በካብሪጅ ዩኒቨርሲቲ በታተመው የጆርናል ጽሑፋቸው Mustafa Kabha and Haggai Erlich, "The Ahbash and the Wahhabiyya -- Interpretations of Islam", International Journal of Middle East Studies, 2006, pp. 519 - 538. ላይ የተመሰረተ ነው፡፡ ፕሮፌሰር አርሊች “የክርስትያን ኢትዮጵያ ዓይናችን እያየ አዲስ ትርጉም ልትይዝ ምንም አልቀራትም” በማለት ስጋቱን ከአቅጣጫ ጠቋሚ እውነቶች ጋር ‘Saudi Arabia & Ethiopia’ በተባለው መጽሐፍ ውስጥ አቅርቧል፡፡ “ኢትዮጵያ አዲስ ትርጉም ልትይዝ ነው” የሚለውም እስላማዊ አገር እንድትሆን ከፍተኛና ስር የሰደደ ታሪካዊ እንቅስቃሴ መኖሩን በመጠቆም ነው፡፡ በእርግጥ አስገራሚና አስደንጋጭ ትዝብት ነው፡፡ እርሱ በታሪክ ጥናት ላይ ተመስርቶ እንደተናገረው ሊሆን ይችላል ወይንስ አይችልም የሚለው ከዚህ ጸሐፊ ችሎታና ግምት በላይ በመሆኑ ጊዜ የሚነግረን ነገር ነው በማለት ብቻ ያልፈዋል፡፡ ከስድስት ወራት በላይ ያስቆጠረው የሙስሊሞች የተቃውሞ እንቅስቃሴ ቀላል አይደለም፡፡ ብዙ ዋጋም እያስከፈለ ነው፡፡ ከበስተኋላ ሆኖ የሚመራው አካል እና ርዕዮተ ዓለም ይኖራልን? ለዚህ ጥያቄ አጭሩ መልስ ምንም ጥርጥር የለውም ነው፡፡ የሙስሊሞቹ የተቃውሞ ሰልፍ በተለያዩ የፖለቲካ፣ የሃይማኖት ተቋማትና ጋዜጠኞች ከፍተኛ የድጋፍ ሽፋን ተሰጥቶታል፣ መግለጫዎችም ማሳሰቢያዎችም ቀርበዋል፡፡ የተሰጡትን የተለያዩ ድጋፎች፤ ከኢአግ ጀምሮ የወጡትን መግለጫዎች፤ ሁሉንም ለማለት ባይቻልም አብዛኛዎቹን ጸሐፊው በቅርቡ ለመከታተል ሙከራ አድርጓል፡፡ ስለዚህም የኢትዮጵያ ሕዝብ ታሪካዊ እውነታዎችን ከምርምር ማህደራት መመልከት አለበት በማለት ያምናል፣ ይህም መጪዎቹን ጊዜዎች ለመተለምና መጪውን ትውልድ ለመመስረትና ለመቅረፅ የሚቻለውን እንዲያደርግ ይረዳዋልና፡፡ የታሪክ ተመራማሪዎቹ አመለካከት፡ ሁለቱ የታሪክ ተመራማሪዎች እንደሚሉት ከሆነ እስልምና ከፍተኛ የሆነ ዓለም አቀፋዊ ተፅዕኖ ቢኖረውም አገራዊና ማህበረሰባዊው ተፅዕኖም እንዲሁ ከፍተኛ እንደሆነ ነው፡፡ በጆርናላቸው ላይ እንዳሰፈሩትና እውነትም እንዳስተዋሉት ሁሉ እስልምና ሌላውን ማህበረሰብ መቅረፅ ብቻ ሳይሆን እንዳለበት አገርና ማህበረሰብም እራሱ የሚቀረፅ እንደሆነና ይህንንም በዘመናት እንዳሳየው ይገልፃሉ፡፡ ይህንን እውነት ለማሳየት እንደዋነኛ የሰርቶ ማሳያ ቦታ የሚጠቀሙበት የኢትዮጵያን ጉዳይ ነው፡፡ በመሆኑም የእስልምና አገር አቀፍም ሆነ ዓለም አቀፍ ቅርፁ ከኢትዮጵያ ጋር የተቆራኘ ነው ይላሉ፡፡ እኛ ሁላችንም እንለው የነበረውን “ኢትዮጵያ የክርስትያን ደሴት” የሚለውን አባባል ጥንታዊነት የታሪክ ሊቃውንቱ በጆርናላቸው ላይ ጠቀስ አድርገውታል፡፡ ይህም አገሪቱ በእስላም አገሮች የተከበበችና በዋና ዋናዎቹ እስላም አገሮች አፍንጫ ስር በመሆኗም የማያቋርጥ ትኩረት እንደተደረገባት ጠቁመዋል፡፡ ይህ የእነርሱ ታሪካዊ የምርምር ግንዛቤ በምዕራቡ ዓለም ላሉ የታሪክ ተመራማሪዎችና በብዙ ኢትጵያውያኖች፤ ማለትም ከላይ እንደጠቀስኩት በፖለቲከኞችና በአንዳንድ የሃይማኖት ቡድኖች ዘንድ በጭራሽ የታየ አይመስልም፡፡ በአገር አቀፍና በዓለም አቀፍ ሙስሊሞች ዘንድ ስለ ኢትዮጵያ ያለውን አመለካከት ስረ መሰረት በእርግጥ ብዙዎች አላጤኑትም፡፡ እንደ እውነቱ ግን የኢትዮጵያ ጉዳይ የኣለም አቀፍ ሙስሊሞች ጉዳይ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ጉዳይ ለሙስሊሞች ትርጉም ያለውና በጣም የሚያስቡበት ጉዳይ ነው፡፡ ሁለቱ የታሪክ ፕሮፌሰሮች የሚሉት “የኢትዮጵያ ጉዳይ በአሁኑ ጊዜ ላለው ዓለም አቀፍ እስልምና እጅግ በጣም ከፍተኛ አጀንዳ እንደሆነ ነው፡፡” ለዚህም ነው ከላይ የጠቀስኳቸው ዓይነቶች እጅግ ብዙ ታሪክ መሳይ ጽሑፎችና ጥናታዊ ፊልሞች መቀናበርና መሰራጨት ያለባቸው፡፡ ሁለቱ እስላማዊ አመለካከቶች ኢትዮጵያ የሁለት ዓይነት አለም አቀፍ የእስልምና ርዕዮተ ዓለም የትግል መድረክ ናት የሚሉት የታሪክ ተመራማሪዎች ሁለቱ ቡድኖች የሚከተሉት መሆናቸውን ያስረዳሉ፡ አንደኛው፡ “አል-አህባሽ” የሚባለውና ዋና መስሪያ ቤቱ ሊባኖስ የሆነው ዓለም አቀፍ እስላማዊ ድርጅት ሲሆን በብዙዎች ዘንድ የሚታወቀው “ኢትዮጵያውያኖቹ” በሚባለውም ስያሜ ጭምር ነው፡፡ ሁለተኛው፡ “ዋሃቢያ” የሚባለው አለም አቀፋዊ እስላማዊ ድርጅት ሲሆን በሳውዲ አረቢያ መንግስት የሚደገፍና አሁን ኢትዮጵያ ውስጥ ያለውን ተቃውሞ እንቅስቃሴ የሚመራው ነው፡፡ ምሁራኖቹ ታሪክን ቆፍረውና አጥንተው የሚነግሩን እነዚህ ሁለቱም ድርጅቶች በቀጥታ ከኢትዮጵያ ጋር ግንኙነት እንዳላቸው ነው፡፡ ሁለቱ ድርጅቶች ከኢትዮጵያ ጋር ያላቸውን ግንኙነትና በውስጣቸው ያለውን ቅራኔና ጥላቻ መረዳት ለኢትዮጵያውያኖች ሁሉ ወሳኝ ነገር ነው፡፡ ምክንያቱም በአሁኑና በመጪው ጊዜ አገሪቱ ምን ዓይነት ሁኔታ ፊት ለፊቷ እንደተጋረጠና እንዴትስ ከዚያ አዘቅት ልትወጣ ትችላለች የሚለውን በትክክል ለመረዳት ያስችላል፡፡ በፕሮፌሰሮቹ ጥልቅ ጥናት መሰረትና አሁን በአገሪቱ እየተካሄደ ያለው ትግል የአጠቃላይ የዓለም አቀፉ ሁለት እስላማዊ ርዕዮተ ዓለም ትግል ነፀብራቅ ነው፡፡ ማለትም ኢትዮጵያ ለሁለት እስላማዊ ትግሎች የጦርነት ሜዳ ስትሆን፣ ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ደግሞ የዚያ ጦርነት ተፋላሚ መጠቀሚያዎች ናቸው፡፡ የሁለቱንም እስላማዊ ርዕዮተ ዓለም በዝርዝር የምንመለከት ቢሆንም ፍንጭ ለመስጠት ያህል አንባቢው የሚከተሉትን እንደ አሲድ የመለያ ምልክት ሊወስዳቸው ይችላል፡፡ የአል-አሕባሽን ርዕዮተ ዓለም የሚከተሉት ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ካሉ፣ በየትኛውም አገር ካለ የገዢ መደብ ጋር በኢትዮጵያም ጭምር እስልምና በሰላም መኖር ይችላል የሚል አመለካከት ያለው ነው፡፡ የዋሃቢዝምን አመለካከት የሚደግፉት ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች እስልምና ባለበት አገር ሁሉ የበላይነትን መያዝ አለበት የሚሉት ናቸው፡፡ ለእነዚህ መለያቸው ”ነጃሺ”ን በተመለከተ ከተፈጠረው ተረት (ይህ ጸሐፊ የነጃሺን ታሪካዊ እውነታ በቅርቡ ያቀርባል) ጋር ያላቸው ቀረቤታ ነው፡፡ በነጃሺ ድረ ገፅ ላይ የተጻፉትን ወቅታዊ አንቀፆች ስታነቡ የኢትዮጵያ ሙስሊሞች በተለይም የዋሃቢዝምን የሚደግፉት እንቅስቃሴያቸው “የጊዜ ፈንጂ” ሆኖ ለመፈንዳት ጊዜ የሚጠብቅ እንደሆነ ኢትዮጵያዊ የሆነና ይችን አገር እወዳለሁ የሚል ሁሉ መረዳት ያስፈልገዋል፡፡ blog.ethiopianmuslims.net የአል-አሕበሽ ወይንም “ኢትዮጵያዊያኖቹ” ስያሜ ታሪካዊ ግንዛቤ፡- “ኢትዮጵያዊያኖቹ” እነማናቸው፣ የሚወክሉትስ ምን ዓይነት የእስልምና ርዕዮተ ዓለምን ነው? የእነርሱ ስም የሚወክለውስ መልእክት ምንድነው? የሚሉትን ጥያቄዎች የታሪክ ተመራማሪዎቹ የመለሱት እንደሚከተለው ነው፡፡ “አል-ሐበሻ” ወይንም “አል-አህባሽ” (እንዲሁም ደግሞ አል-ሁባሻን፣ አል-ሁቡሽ) የሚለው ስያሜ ኢትዮጵያውያን በጥንታዊ አረቦች የሚታወቁበት ስምና ከቀይ ባህር ማዶ ያሉ የአረቦች ጎረቤቶች አፍሪካውያን መጠሪያ ነው፡፡ ይሁን እንጂ በእስላማዊው ዓለም ፅንሰ ሐሳብ ውስጥ አል-ሐባሻ የሚለው መጠሪያ በጣም ጠቃሚ የሆነ ሌላም ትርጉም እንዳለው የታሪክ ሊቃውንቱ አሳይተዋል፡፡ እንደሚታወቀው ሁሉ የኢትዮጵያ መንግስት በአብዛኛው በክርስትያኖች የተያዘ ቢሆንም በጣም ብዙ ሙስሊሞች ስለሚኖሩበት ሙስሊሞችም የሚኖሩበት አገር ነው፡፡ “ሐበሻ” የሚለውም የአረብኛ ቃል በአፍሪካ ቀንድ ላይ ላሉት ክርስትያኖች ብቻ የተሰጠ ሳይሆን ለአጠቃላይ ሕዝቡ ነውና ሙስሊሞችንም ይጨምራል፡፡ በነ ፕሮፌሰር ኤርሊች ጥናታዊ ጽሑፍም መሰረት “ሐበሻ” የሚለው ቃል በሃይማኖት ላይ ያተኮረ ሳይሆን በቆዳ ቀለም ላይ ነው፡፡ በአረቦችና በእስልምና ዓይን አል-ሃባሻ ከጥቁር አፍሪካውያን ማለትም “ዙኑጅ” ይሏቸው ከነበሩት ከሱዳኖች የተለዩ ነበሩ ይሉናል፡፡ የታሪክ ተመራማሪዎቹ እንደሚሉት “ሓባሺ ሙስሊሞችን በተመለከተ ሁለት የፅንሰ ሐሳብ ክፍፍል ነበረ”፡፡ ሐበሾች ይወሰዱ የነበረው ከሌላ የአፍሪካ ባሪያዎች በጣም ጥሩዎቹ ተደርገው ነበር፣ እስከ አንደኛው የዓለም ጦርነት ድረስ በአሪቢያ ውስጥ በቆየው የባሪያ ንግድ ከኢትዮጵያ ይጋዙ ከነበሩት ሐበሻዎች ውስጥ ብዙዎቹ አኒሚስቶች (ተፈጥሮ አምላኪዎች) የነበሩ ሲሆን ጥቂቶቹ ግን ክርስትያኖች ነበሩ፡፡ ስለዚህም ፕሮፌሰሮቹ የሚሉት “ሐበሻ” የሚለው ቃል በእርግጥ ሃይማኖታዊ ያልነበረ፣ ነገር ግን መጠነኛ የሆነ የዘር ዝቅተኝነትን የሚያንፀባርቅ መጠሪያ እንደነበር ነው፡፡ ከዚህም ቀጥሎ ተመራማሪዎቹ የሚከተለውን ነገር በምርምራቸው ላይ አስፍረዋል ይህም፡ “የሰው ዘር ሁሉ እስልምናን” ለሚያራምዱት ማለትም ዘረኛ ያልሆኑት ዘመናዊና ዓለም አቀፋዊ ሙስሊሞች ዘንድ የክርስትያን ኢትዮጵያ ተቀባይነት ይያያዝ የነበረው የሐባሺ ሙስሊሞችን አሁንም ከማመስገንና ከማድነቅ ጋር ነው፡፡ ስለዚህም ብዙ ጠቆር ያሉና ድብልቅ ሙስሊሞች በቅፅል ስም የሚጠሩት “አል-ሐበሺ” ተብለው ነው፡፡ እንደተመራማሪዎቹ ጽሑፍ በታሪክ በተለያየ መደብ ላይ የነበሩ ብዙ ታዋቂ ሰዎች ላይ በዚህ ስም ተጠርተውበታል፡፡ እጅግ በጣም ብዙ ትውፊቶችም ለአሁኑ ጊዜ ሙስሊሞች ጥሪ የሚያቀርቡት ሙስሊሞች ሁሉ ኢትዮጵያውያንን እንዲያከብሯቸውና እንዲያውም እነርሱን እንደመሪዎች ጭምር እንዲቀበሏቸው ነው፡፡ በዘመናትም ባሉ እጅግ በጣም ብዙ ጽሑፎች ውስጥ ሙስሊም-ኢትዮጵያውያንን የሚያነሱና የሚያወድሱ ጽሑፎች እንዳሉ የታሪክ ሊቃውንቱ አሳይተዋል፡፡ እነዚህም ሁሉ ጽሑፎች ለሙስሊሞች ሁሉ ጥሪ የሚያደርጉት መቻቻልን እንዲያሳዩና በተለይም ከኢትዮጵያ ጋር ያላቸውን ግንኙነት በመቻቻል እንዲይዙት ነው፡፡ ይህንን በተመለከተ እነ ፕሮፌሰር ኤርሊች በምርምር ጽሑፋቸው ውስጥ ከዚህ በታች ያሉትንና ከብዙ ጥቂት ያሏቸውን የመቻቻል ምሳሌዎች ጠቅሰዋል፡ ጃላል አል-ዲን አል-ሱዩት በ15ኛው ክፍለ ዘመን “የኢትዮጵያውያንን ደረጃ ከፍ አድርጎታል”፤ እንዲሁም አህድ አል-ሂፍኒ አል-ኪናይ አል-አዛህሪ “በኢትዮጵያውያን ታሪክ ውስጥ ውቦቹ አልማዞች” በ20ኛው መቶ ክፍለ ዘመን፡፡ ከታወቁት (እውቅና ከላቸው) የኢትዮጵያ ሙስሊሞች እንደ ቢላል ቢን ራባህ (ቢላል አል-ሃባሺ) የመጀመሪያው ሙአዲዲን እንዲሁም እራሱ ናጃሺ እጅግ በጣም እስላማዊና ታሪካዊ ሰዎች እንዲሁም ቅዱሳን ሁሉ ተብለው ተቆጥረው ነበር፡፡ በ16ኛ መቶ ዘመን በመዲና የተጻፈ ሌላ ጽሑፍ ደግሞ (በ1583-4) የሚከተለውንና አረቢያኖች ስለባርነትና ስለሐበሻ ያላቸውን አመለካከት ይዟል፡ ‘ለአላህ ምስጋና ይሁን ሰውን ከአፈር ጭቃ የፈጠረውና አንዳንዶቹን ከሌሎቹ የመረጠው፡፡ በእነርሱ መካከል ያለው ልዩነት ሰማይ ከምድር እንደሚርቀው ነበር፡፡ ይሁን እንጂ እያንዳንዱ ቡድን አላህን ያመሰግናል ያስደስታልም፡፡ እርሱም ጌታዎችና ባሪያዎች ገዢዎችና ተገዢዎች አድርጓቸዋል፡፡ አላህ የኖህን አንዳንድ ዘሮችን ለይቶ በነቢይነትና በባለስልጣንነት፣ ለአንዳንዶቹ ደግሞ አገልጋይነትንና ባርነትን እስከ ትንሳኤ ቀን ድረስ መድቦላቸዋል፡፡ ... እርሱም የኢትዮጵያውያንን ቡድኖች ... እንደ ቢላል እንደ አል-ናጃሺ እንዲሁም ሌሎቹንም በእርሱ ያመኑትንና እስልምናን የያዙትን በፀጋና በመሪነት ለይቷቸዋል፡፡ ብዙዎቹም የነቢዩ ተከታዮች ፣ እንዲሁም ቅዱሳን የሆኑ ፃድቃን፣ በጣም ታዋቂ ሰዎች ሆነዋል በምድርም በገነትም እንዲሁም የሃይማኖት መሪዎችና ጊዜያዌ መሪዎች ሆነዋል፡፡” ይላል፡፡ ይሁን እንጂ የኢትዮጵያ ሙስሊሞችን በሁለት ዓይነት ክፍል ከፍሎ መመልከት ግልፅ እንደሆነ ምሁራኑ ያስቀምጡና ለዚህ ጥሩ ማስረጃው በሱኒ ባህል ውስጥ ያለውንና፡ “በእናንተ ላይ ማንም በስልጣን ላይ ይሁን ታዘዙ፣ ምንም እንኳን እርሱ አፍንጫው ደፋጣ ኢትዮጵያዊ ባሪያም ቢሆን” የሚለውን አባባል ይጠቅሳሉ፡፡ ስለዚህም ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች በአረቦች ዘንድ የሚታዩት በአንድ በኩል ምንም ባሪያዎች ቢሆኑ በእስልምና ውስጥ ብቃት ያላቸው መሪዎች ሊሆኑ እንደሚችሉ ሲሆን፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ኢትዮጵያውያንን በማህበረሰቡ ውስጥ በዝቅተኛው ደረጃ ላይ ያስቀምጣቸዋል ይላሉ፡፡ ለዚህ ሁለት ከፍል ላለው የአመለካከት ውዝግብ ግልፅ የሆነውና በሕይይት ያለው ማስረጃ ሼክ አብደላ አል ሃባሺ አል ሃራሪ የአሁኑ የአል-አህባሽ ዓለም አቀፍ እስላማዊ ማህበር መሪና በሊባኖስ የሚኖረው እስላማዊ ሊቅ ነው ይላሉ፡፡ ኢትዮጵያ የእስልምና ጠላት፡ የኢትዮጵያ ታሪክ በሰላምታ መጽሔት በናጂብ መሐመድ እንዲሁም በፀደይ በዌብ ሳይት እንደቀረቡት የ18ኛው መቶ ዘመን ታሪክ ሳይሆን በመሐመድም ዘመን የታወቀ ነበር፡፡ የሐበሾቹ ሐገር ኢትዮጵያ ክርስትናን እንደ ሃይማኖቷ አድርጋ የተቀበለችው የእስልምናው መስራች መሐመድ ከመነሳቱ ከሶስት መቶ ዓመታት በፊት እንደነበር በታሪክ የታወቀ ነው፡፡ ከላይ የጠቀስኩት የፀደይ ጽሑፍና የእነ ፕሮፌሰር ኤርሊቺም ጥናት የሚያሳየው አብርሃ የተባለው ክርስትያን የኢትዮጵያ ንጉስ በ570 ዓ.ም በየመን ይገዛ እንደነበር እንዲያውም በመካ ያለውን የከዓባ ጣዖት ለማፍረስ በዝሆኔዎቹ ዓመት ተብሎ በሚታወቀው ዓመት ዘምቶ እንደነበረ ግን እንዳልተሳካለት ነው፡፡ በቁርአን ምዕራፍ 105 የተጻፈው የዝሆኖቹ ጦርነት አፈታሪክ ከዚህ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ አገሪቱ በአረብ ባህረ ሰላጤ ጉዳዮች ላይ ለዘመናት ትካፈል ስለነበር እንደ ክርስትያን አንድ አማላክ አምላኪ “ሌላ” አገር ተብላ በመሐመድና በእርሱ ዘመን በነበሩት ሁሉ ዘንድ የታወቀች ነበረች፡፡ በእርግጥም ኢትዮጵያ በእስልምና እምነት እንቅስቃሴ የውጭ ግንኙነት የመጀመሪያዋ አገር ናት፡፡ ስለዚህም በ615-616ዓ.ም ለተደረገው ሂጂራ ኢትዮጵያ የመጀመሪያዋ አገር ነበረች፡፡ ሙስሊሞች ነጃሺ በማለት የሚጠሩት ክርስትያኑ የኢትዮጵያ ንጉስ በዚያን ጊዜ ለነበሩት አጠቃላይ እስላማዊ ማህበረ ሰብ ለማለት ይቻላል የፖለቲካ ጥገኝነትን ሰጥቶ ነበር፡፡ በሙስሊሞች ሁሉ ዘንድ ፃድቁ ተብሎ አሁንም የሚጠራው የክርስትያን ኢትዮጵያ ንጉስ ሙስሊሞችን ያዳነውና ዘለቄታዊ የቸርነት መልእክትን ለሙስሊሞች ዓለም ሁሉ የሰጠው አገሪቱ የክርስትያን አገር ስለነበረች እንደነበር ግልፅ ነው፡፡ ከዚህም ባሻገር ከላይ እንደጠቀስኩት ኢትዮጵያ የራሷ ሕጋዊ አስተዳደርና የአገር ክልል የነበራት አገርም ነበረች፡፡ ይህም ለማንም ግልፅ የሆነ እውነታ ነበር ነቢዩ የሚከተለውን አባባል ተናግሯል ተብሎ እንዲነገርለት ያደረገው “ኢትዮጵያውያንን ተዋቸው እናንተን እስካልነኳችሁ ድረስ” (utruku al-Habasha ma tarakukum)፡፡ ስለዚህም አሁን የምናያት ኢትዮጵያ በፖርቱጋሎች እርዳታ የተገኘች ናት የሚለው አዲስ ታሪክ የሺዎች ዓመታትን ታሪክ የሚያዛባና መሰረተ ቢስ ነው፡፡ ይሁን እንጂ የታሪክ ተመራማሪዎቹ እንደሚሉት በሌላ ጎኑ ደግሞ በ615-616 ከሆነውና ከታወቀው የክርስትያን ኢትዮጵያ ደግነት ታሪክ የተለየ እንዲሁም በጣም አከራካሪ የሆነ ትውፊት ቆየት ብሎ መጥቷል፡፡ እርሱም በ628 ማለትም ኢትዮጵያ ስደተኞቹን ካስተናገደች ከአስራ ሁለት ዓመት በኋላ የኢትዮጵያው ንጉስ ነጃሺ እራሱ እስልምናን እንደተቀበለ፤ በዙሪያው የነበሩት የኦርቶዶክስ ካህናትና የራሱ ሕዝብ ግን እንዳልተቀበሉት የሚነገረው አፈታሪክ ነው፡፡ እንደ ምሁራቹ ጥናታዊ ዘገባ ይህ አፈታሪክ መሰረታዊ የሆነ ታሪካዊ የእውነትነት ድጋፍ የለውም አወዛጋቢም ነው፡፡ ይሁን እንጂ ብዙ የፈጠራ ጽሑፎችና ፊልሞች ተቀናብረውለታል፡፡ በጥልቅና በጥንቃቄም የሚመራው “ክርስትያን ኢትዮጵያ “”ሌላ”” ናት”፣ ወይንም “ክርስትያን ኢትዮጵያን አትንኳት” የሚለውን አባባል ወደ ጎን ተጥሎ “ክርስትያን ኢትዮጵያ ጠላት ናት” ደግሞም “ክርስትያን ኢትዮጵያ የመጀመሪያው እስላም ንጉስ የተገደለባት” ማለትም በመጀመሪያ ትርጉም ወደ ተቃራኒና ሕጋዊ አገር አለመሆኗን ወደሚያሳይ ጥላቻ፤› ነው፡፡ በክርስትያን ኢትዮጵያ ላይ ከፍተኛ ጥላቻ እንዲመጣ ያደረገው የፈጠራ ታሪክ “ኢትዮጵያን ሕገ ወጥ” ለማድረግ የተጠናከረው ከእስልምና አስቀድሞ በ570 ዓም ከሆነው ክስተት ጋር ተያይዞ እንደሆነ የታሪክ ተመራማሪዎቹ በጆርናላቸው ላይ ጠቁመዋል፡፡ በዚያን ጊዜ ኢትዮጵያውያኑ የመንን ቅኚ ግዛት አድርገው ይዘው በነበሩበት ሰዓት “በዝሆን ዓመት ውስጥ” በመካ ከተማ ያለውን ጣዖት ካዓባን ለማጥፋት ያልተሳካ ሙከራን አድረገው ነበር፡፡ ከዚህም የተነሳ በኣረብ አገሮች በተለይም በሳውዲ አረቢያ እስካሁን ድረስ የሚፈራው ትንቢት ማለትም (እነዚያ ቀጫጭን እግር ያላቸው ኢትዮጰያውያን በስተመጨረሻው ካኣባን ያጠፋሉ) የሚለው እንደተነገረ ተመራማሪዎቹ ያሳያሉ፡፡ ይህ እንዲህ ከሆነ ለእስልምናው ዓለም ከኢትዮጵያ የበለጠ ጠላት ሊኖር አይችልም፡፡ ስለዚህም በታሪኩ ምርምር መሰረት ኢትዮጵያን በተመለከተ ያሉት ሁለቱ ዓለም አቀፍ እስላማዊ ትግሎች ሁሉ የሚሽከረከሩት በእነዚህ ሁለት ፈርጅ ባላቸው አመለካከቶች ላይ መሆኑን ነው ፕሮፌሰሮቹ የሚያስረዱት፡፡ እነዚህ ሁለት አመለካከቶች “ኢትዮጵያን አትንኳት” እና “ኢትዮጵያ ጠላት ናት” የሚሉት ናቸው፡፡ እንግዲህ አገራችን ኢትዮጵያ ከአረብ አገሮችና ለመካከለኛው ምስራቅም ጎረቤት ከመሆኗ የተነሳ እነዚህ ሁለት ነገሮች የኢትዮጵያን ጉዳይ የዓለም አቀፍ እስላሞች ሁሉ ዋና ጉዳይ አድርገው ያቀረቡታል፡፡ አል-አህባሽና የዋሃቢያ ጠላትነት መሰረት፡ በአሁኑ ጊዜ ያለው የተቃውሞ ሰልፍ መሰረታዊ የሆነ ጥንታዊ ታሪካዊነት አለው፡፡ የታሪኩ ተመራማሪ ፕሮፌሰር ኤልሪች ያቀረበው የሁለቱ ቡድኖች የጠላትነት ታሪክ መሠረቱ በኢትዮጵያ ከተማ በሐረር ውስጥ ነው፡፡ ሐረር በአፍሪካ ቀንድ የእስላም ዋና ከተማና የሙስሊም ሊቃውንት መኖሪያ ነበረች፡፡ የሐረር የረጅም ዘመን ታሪክ እራሱ በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉት ሙስሊሞችን አጣብቂኝ ሁለት ምርጫ መኖርን ያንፀባርቃል፡፡ በአንድ መንገድ በግንብ የተከበበችው ከተማ ከ10ኛው ክፍለ ዘመን እስከ 19ኛው ድረስ ግልፅ ካልሆነ ጅማሬ ተነስታ እራሷን የቻለች የእስልምና ግዛት ሆና የራሷ ፖለቲካዊ አመራርን ይዛ ነበረች፡፡ በእነዚያ ዘመናት ውስጥ ሐረር በብዙ መንገድ ከአረቢያ ጋር ግንኙነት የነበራትና የእስላማዊ ጂሃድ ማዕከል ነበረች ይህም በክርስትያን የኢትዮጵያ መንግስት ላይ የተነጣጠረ ነበር፡፡ በሌላ ጎኑ ደግሞ በ1887 በኢትዮጵያ ከተወረረች በኋላ ሐረር ያደገችው በኢትዮጵያ ባህል፣ ማህበረ ሰብ እንዲሁም በክርስትያን ባመዘነው የፖለቲካዊ ስርዓት ሁሉ ውስጥ በመዋሃድ እንደ እስላማዊ የመዋሃድ ሞዴልነት ነበር፡፡ ከፋሽስት ጣሊያን የአጭር ጊዜ ወረራ (1936-1941) ትርምስ በኋላ ግን የሐረር ማህበረሰብ እንደገና ወደ እነዚህ ተቃራኒ ታሪካዊ ሁኔታዎች አማካኝነት ተከፋፈለ፡፡ ወደ መካ ሐጂ እንዲያደርጉ በጣሊያኖች ወደ አረቢያ የተላኩት የመሪ ቡድኖች በዋሃቢ ተፅዕኖ በጣም ተነሳስተው ስለነበር ከ1941-1948 ድረስ ከኢትዮጵያ የመገንጠልን የእስላማዊ ነፃነትን እንቅስቃሴ ሙከራ አድርገው እንደነበር ሊቃውንቱ ያስረዳሉ፡፡ ከዚያም ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ከተደረገ የረጅም ጊዜ ትግል በኋላ ቡድኑ ተሸንፎ እንደተበታተነ፡፡ በመካና በመዲና በ1928-1938 የተማረው የእንቅስቃሴውም መሪ ሼክ ዩሱፍ አብደ አል-ራህማን አል-ሃራሪ ወደ ሳውዲ አረቢያ መዲና ተመለሰ፡፡ የሼክ ዩሱፍን ታሪክ በተለያየ መንገድ የሚቀርብ ቢሆንም እርሱ በአሁኑ ጊዜ ዋሃቢ በስተጀርባ ካሉት መሪዎች አንዱ ሲሆን ከአል-አህባሽ ጋር የቃላት ጦርነት ከሚያደርጉት በስተጀርባ ነው፡፡ የአል-አህባሽ መሪ፣ ሼክ አብዳላ ኢብን ሙሐመድ ኢብን ዩሱፍ አል-ሃራሪ በ1941-1948 በሐረር እና በኢትዮጵያ በነበሩት ጊዜያት የእርሱ ማለትም የዋሃቢ መሪው ዋና ተቃዋሚ ነበር፡፡ እርሱም የተወለደው በ1901 ሲሆን እስላማዊ ትምህርቱን ደግሞ ያገኘው በኢትዮጵያ ውስጥ እና ያደገው በኢትዮጵያ ክርስትያን - እስላም አብሮ መኖር ጥልቅ እምነት ውስጥ ነበር፡፡ ስለዚህም በሐረር ላይ ተደርጎ በነበረው ትግል ላይ በእነዚያ ዓመታት ውስጥ እርሱ ተሳትፎ ነበር፡፡ ትግሉም ያጠንጥን የነበረው በሁለት ጉዳዮች ላይ ነበር እዚህም ላይ የምንጠቀሰው በጣም በመጠኑ ብቻ ነው፡፡ አንደኛውም በሐረር ውስጥ የሚሰጠው የእስላማዊ ትምህርት ባህርይ ላይ ነበር፡፡ በ1941 የሐረሪ እስላማዊ አገር ብሄርተኞች ትምህርት ቤቱን እንደገና ያቋቋሙት በዘመናዊ ትምህርት ቤትነት በዋሃቢ አክራሪነት መሰረት በሚያምን ቡድን ፍላጎት ላይ እንደነበር እነዚህ የታሪክ ምሁራን ያስረዳሉ፡፡ ከጥቂት ወራት በኋላ ችግሩን በሚገባ ያጤነው የኢትዮጵያ መንግስት ትምህርት ቤቱን ዘጋው ከዚያም በዚህ ላይ የተሳተፉትን ግለሰቦች ወደ እስር ቤት ወይንም ወደ ስደት ላካቸው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ በ1946-1948 ድርስ የተሞከረው ጥረት ነበር ይህም ከክርስትያን ኢትዮጵያ ተገንጥሎ የመውጣት ሙከራ እንደነበር ሊቃውንቱ ያስቀምጣሉ፡፡ ይህንንም ያደራጁት እነዚያም እስላማዊ የሐረሪ ዜግነት አለን የሚሉት ነበሩ በዚህም ጥረታቸው በዚያን ጊዜ ከነበረው የሶማሊያ ብሄራዊ እንቅስቃሴ ጋር በማበር ሐረርን ከክርስትያን ኢትዮጵያ ገንጥሎ ከእስላማዊ ሶማሊያ ጋር ማዋሃድ ሙከራ አድርገዋል፡፡ እነርሱም እንደገና በኢትዮጵያ መንግስት ባለስልጣናት ተጋለጡና ተቀጡ፡፡ የታሪክ ተመራማሪዎቹ እነ ፕሮፌሰር ኤርሊች እንዳጠኑት በሁለቱም ሁኔታ ላይ የተሸነፉት ቡድኖች የአል-አህባሹን መሪ ሼክ አብደላን ወንጅለውት ነበር፡፡ የከሰሱትም ለኢትዮጵያ መንግስት መሳሪያ ሆነሃል በማለት ነበር፡፡ ሼክ አብደላ እና ተከታዮቹ ግን ፀረ እስላማዊ ዘመቻ ላይ ትብብር እንዳላደረጉ ሲናገሩ ቆይተዋል፤ ለዚህም ማስረጃቸው ሼክ አብደላ በ1948 በኢትዮጵያ ንጉሳዊ መንግስት ተጠርጥሮ ለተወሰነ ጊዜ መታሰሩንም እንዲሁም አገሩን ለቆ እንዲወጣ መገደዱንም ይጠቁማሉ፡፡ እንዲያውም እርሱና የእርሱ ተከታዮች የዋሃቢው መሪ የሆነውን ሼክ ዩሱፍ አብድ አል-ራህማናን ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ይተባበራል በማለት ይከሳሉ፡፡ (የዋሃቢው መሪ ሼክ ዩሱፍ ቆይቶ ቁርአንን ወደ አማርኛ እንዲተረጎም የበላይ ጠባቂ እንዲሆን በንጉሱ መንግስት ተሾሟል)፡፡ ለአንባቢዎች ግልፅ መሆን ካለበት ነገር ውስጥ እነዚህ ሁለት ከሐረር የተነሱትና የሁለት እስላማዊ ርዕዮተ ዓለም አለም አቀፍ መሪዎች አሁንም በሕይወት እንዳሉ ነው፡፡ የአል-አህባሹ በሊባኖስ ቤይሩት ሲሆን የዋሃቢው ደግሞ በሳውዲ መዲና ይገኛሉ፡፡ በሁለቱ መካከል ያሉት ቅራኔዎችና መካሰሶች ቀጥለዋል፤ በእነርሱ መካከል ያለው መራራ ጠላትነት በዛሬይቱ ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉትን ሙስሊሞች ለሀሉት ከፍሏቸዋል፡፡ የታሪክ ተመራማሪዎቹ በጆርናላቸው ላይ እንደምሳሌ ያቀረቡት በ1995 ዓም. ሼክ አብደላ በኢትዮጵያ ውስጥ የሚከተለውን ጽሐፉ የያዘ በራሪ ወረቀት አሰራጭቶ እንደነበር ነው፡- “ይህንን (የዋሃቢውን መሪ) ሼክ ዩሱፍ አብ አል-ራህማ የተባለውን ሰው ተጠንቀቁት፣ ከብዙ ጊዜ በፊት ኢትዮጵያን ጥሎ ወደ መዲና ሄዶ የነበረውን ሰው በዚያን ጊዜም እርሱ የዋሃቢያን መርሆዎች ከአጎቱ በዋሃቢዎች መካከል ተምሮ ነበር፡፡ እነርሱም ገንዘብ ሰጡትና የእነርሱን ቃል ለማስፋፋት ወደ ሐረር ተመለሰ፡፡ ከዚያም በኋላ የኃይለስላሴ የቅርብ ሰው ሆነና ቁርአንን ወደ አማርኛ ለመተርጎም ረዳው፡፡ ንጉሱም ለዚህ ስራው ሽልማት እንዲሆነው መሬትን ሰጡት፡፡ መንግስቱ ኃይለማርያም በኢትዮጵያ ውስጥ ኮሙኒዝምን ሲያስፋፋ ደግሞ (1974-1991) ወደ ዋሃቢዎች ተመልሶ ፈረጠጠ፡፡ እነርሱም ገንዘብ ሰጡትና የእነርሱን የሐሰት ትምህርት ለማስፋፋት እንደገና ወደ ኢትዮጵያ ተመለሰ፡፡ ይህንን ሰው ተጠንቀቁት ማንኘውንም ነገሩን ጭምር፣ የሐረርን ሕዝብ ሁሉ አስጠንቅቁ እንዲሁም መላውን የኢትዮጵያን ሕዝብ ሁሉ”፡፡ ይህንን ዓይነቱ “የአሕባሽ-ዋሃቢያ” ክርክርና እሰጥ አገባ በስፋት በሁሉም እስልምናዊ ጠቀሜታዎች ላይ የሚታይ ነው፡፡ የታሪክ ፕሮፌሰሮቹ የሚሉት ዋናው ጠቃሚ መታወቅ ያለበት ነገር ይህ “የአል-አህባሽ” ትምህርት ያደገው (የወጣው) ከዚህ ከኢትዮጵያ ታሪክ ጫፍ ላይ መሆኑን ነው፡፡ ሼክ አብደላ በ1948 ኢትዮጵያን ከለቀቀ በኋላ በኢየሩሳሌም የተወሰነ ጊዜን አሳልፏል ከዚያም ወደ ደማስቆ ገብቷል፡፡ ሼኩ ወደ ቤይሩት ሊባኖስ በ1950 ገብቶ እስካሁን ድረስ እዚያው ነው የሚኖረው፡፡ እነ ፕሮፌሰር ኤርሊች እንደሚሉት ሼኩ በሊባኖስ ከተማ እስከ 1983 ድረስ ለሕዝብ ታይቶ አያውቅም ነበር፡፡ በመጀመሪያዎቹ ዓመታት ውስጥ የአካባቢያዊ የእስልምና በጎ አድራጊ ድርጅት መሪዎች ከሆኑ የእስልምና ሊቃውንት ጋር አብሮ ቆይቷል፡፡ እርሱንም የሚያራምደውን ርዕዮተ ዓለም ሼክ ሙክታር አል-አላሊ በእርሱ ዳር አል-ፋትዋ ማህበር ውስጥ ድጋፍ አድርጎለታል፡፡ እንዲሁም ሼክ ሙሂይ አል-ዲን አል-አጁዝ ደግሞ በተመሳሳይ መንገድ በእርሱ “የእስላማዊ በጎ አድራጎት ድርጅት ፕሮጀክት ውስጥ ድጋፍን አድርጎለታል፡፡” ሼክ አጁዝ ሲሞት በ1983 ሼክ አብደላ የማህበሩ መሪ ተብሎ ተዋወቀ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ድርጅቱ በጣም የሚታወቀው “አሕበሽ” ተብሎ ነው፡፡ የአል-አሕበሽ እስላማዊ ርዕዮተ ዓለም ከዋሃቢያ እስላማዊ ርዕዮ ዓለም በጣም የተለየ ነው፡፡ የአል-አሕበሽ ርዕዮተ ዓለም ካለው መንግስት ጋር በሰላም መኖር እንደሆነ የሚያራምዱትን ትምህርት በምናነሳበት ጊዜ እንመጣበታለን፡፡ ይሁን እንጂ በኢትዮጵያ ውስጥ ተከታዮች የሉትም፣ ምክንያቱም ብዙዎቹ የኢትዮጵያ ሙስሊሞች የሚከተሉትና ለማራመድም የሚፈልጉት የዋሃቢያውን አመለካከት ነውና፡፡ ያለፉትን ወራቶች ተቃውሞዎችና የተሰጧቸውን ድጋፎች ሁሉ ልንገመግም የምንችለው ከእነዚህ ታሪካዊ እውነታዎች በመነሳት መሆን ይኖርበታል፡፡ አንድ አገር ውስጥ ያለውንና የማንወደውን አገዛዝ የሚቃወም ሁሉ ወደጃችን ነው ለማለትና ለመደገፍ ግን ጊዜው ገና ነው፡፡ የጠላቴ ጠላት ወዳጄ ነው የሚለውን የድሮውን አባባል ከመቀበላችን በፊት እንደገና፣ እንደገና ልንጨምቅ ይገባናል፡፡ የዚህ ድረ-ገፅና ጽሑፍ አዘጋጆች ፖለቲከኞች አይደለንም ነገር ግን ለታሪካዊ እውነታዎች የምናውቀውን የማስቀመጥና መልስ የሚሆኑ ነገሮችን ለወገኖቻችን ማሳየት ጠቃሚ ነው ብለን እናምናለን፡፡ በነፕሮፌሰር ኤርሊች ጆርናል ላይ የተመሰረተው የዚህ ጽሑፍ ክፍል ሁለትና ሦስት በተከታታይ ከቀረቡ በኋላ ሌሎች አስደናቂ ታሪካዊ እውነቶችን ልናቀርብላችሁ እንሞክራለን፡፡
ሚኒስትሪ ጥዕና ማላዊ ኣብ ቀረባ ኣብ ኣፍሪቃ ፈላማይ ዝኾነን ንትሕቲ ሓሙሽተ ዓመት ዝዕድሚኦም ህፃናት ዘገልግልን ክታበት ሕማም ዓሶ ከቅርብ ምዃኑ ኣፍሊጡ። እዚ RTS ብዝብል ዝፍለጥ ካብ ዝመሃዝ 30 ዓመታት ዘቑጸረ ኽታበት ኣብ ጋና፣ ኬንያን ማላዊን ተፈቲኑ ብተዛማዲ ትሑት ውፅኢት ከምዘለዎ ዝተረጋገፀ እኳ እንተኾነ ኣብ ነፍሲ ወከፍ ዓመት ጣንጡ ብእተስዕቦ ሕማም ዓሶ ንሞት ንዝሳጥሑ መብዛሕትኦም ህፃናት ዝርከብዎም ልዕሊ 400,000 ህይወት ኣፍሪካውቃን ግን ከትርፍ እዩ ተባሂሉ ትፅቢት ተገይሩሉ ይርከብ። እቲ ኽታበት ኣብ ዝቅፅል ወርሒ ዝዛዘም ናይ ፈተነ መደብ ስዒቡ ክዝርጋሕ እዩ ትልሚ ተታሒዙሉ ዝርከብ። ውድብ ጥዕና ዓለም ካብ 2019 ጀሚሩ ኣብ ዓመት ን360,000 ሕፃናት ማላዊ፣ ጋናን ኬንያን ክኸትብ ከሎ ካብዚኦም እቶም ሓደ ሲሶ አብ ማላዊ ዝርከቡ እዮም። ነዚ ኣመሊኪተን ሚንስተር ጥዕና ማላዊ ክሁምቢዝ ካንዶዶ ቺፖንዳ ከምዚ ይብላ። “ብፍላይ ኣብ ህፃናት ኢና ጠመተ ንገብር ምኽንያቱ ኣብ ወርሓት ክረምቲ፣ ከምኡ እውን ሕዳርን ታሕሳስን ብዙሓት ህፃናት ብሕማም ዓሶ ክሳቀዩ ንዕዘብ ኢና።” ቺፖንዳ ወሲኸን እዚ ውሳነ ነቲ ኣብ ኒውዮርክ ዝተሳለጠ ሓፈሻዊ ጉባኤ ሕቡራት ሃገራት ፕረዚደንት ማላዊ ላዛሩስ ቻክዌራ ምስ ወኪል PATH ዝተባህለ ንትርፊ ዘይሰርሕ ትካል ተራኺቦም ድሕሪ ምዝርራቦም እዩ ኢለን። ውዱብ ጥዕና ዓለም ነቲ ክታበት ቅድሚ ዓመታት አፍልጦ ዝሃቦ ኮይኑ ኣንፃር ሕማም ዓሶ ኣብ ዝግበር ቃልሲ ዓብዪ ግደ ከምዝህልዎ ገሊፁ እዩ። እዚ ግላክሶ ስሚዝ ክላይን ዝተባህለ ትካል ከም ክታበት ዓሶ ሞስኲሪክስ ገይሩ ዝሸጦ ዘሎ ክታበት 30% ውፅኢታዊ ዝኾነ ኮይኑ ኣርባዕተ ዓቀን እቲ ክታበት ምውሳድ የድሊ። ይኹን እምበር እዚ ብፋውንዴሽን ቢልን ሜሊንዳ ጌትስን ዝድገፍ ክታበት ዋግኡ ምስቲ ትሕዝትኡ ንምምጥጣኑ ስግኣት ኣልዒሉ ይርከብ። ኣብ ወርሒ ሓምለ ኣሶሼትድ ፕረስ ንዳይሬክተር ፕሮግራም ዓሶ ፋውንዴሽን ጌትስ ዝኾነ ፊሊፕ ዌልክሆፍ ጠቂሱ ከምዝበሎ እቲ ፋውንዴሽን ነቲ ክታበት ዝድግፉ ማሕበራት ዝሕግዝ ኮይኑ ብቀጥታ ነቲ ክታበት ዝገብሮ ገንዘባዊ ሓገዝ ግን ከምዘይህሉ ምግላፆም ይጠቅስ። ንሶም ከምዝበሎ እቲ ክታበት ብተዛማዲ ዝተሓተ ዓቅሚ ከምዘለዎን ከምኡ'ውን ክባርን ሎጂስታካዊ ንምብፃሑ ፈታኒ ን ምዃኑ እዩ። ማዚኮ ማተምባ ኣብ ማላዊ ኣምባሳደር ጥዕና ኣብ ምንቓሕ ሕብረተሰብ ዝነጥፍን እዩ። ንምጅማር እቲ ክታበት ኣመልኪቱ ድማ ከምዚ ይብል። “ኣብ መወዳእታ እቲ ክታበት ዓሶ ኣብ ማላዊ ክዋሃብ ክጅምር ምዃኑ ዘሐጉስ ዜና እዩ። ኣሃዛዊ ፀብፃብ ከምዝሕብርዎ ሕማም ዓሶ ኣብ ትሕቲ ሓሙሽተ ዓመት ዝዕድሚኦም ህፃናት ቀልጢፉ ዝዝርጋሕ ዘሎ ሕማም እዩ፤ ብምዃኑ ንንመኸላከሊ ዘገልግሎም ተወሳኺ ሓደ እታወት ንውስኽ ብምህላውና እዞም ትሕቲ ሓሙሽተ ዓመት ህፃናትና መከላኸሊ ክረኽቡ እዮም ዝብል ተስፋ ኣለና” ማተምባ ወሲኹ ብዛዕባ እቲ 30% እዩ ናይ ምክላኻል ዓቅሙ ዝብል ብዙሕ ዘጭንቅ ዘይሙዃኑን ኩሎም ክታበታት 100% ውፅኢታውያን ኣይኮኑን ይብል። ፀብፃባት ከምዝሕብርዎ ሕማም ዓሶ ኣብ ማላዊ ቀንዲ ቀታላይ ሕማም ክከውን ከሎ ካብ ተመላለስቲ ሕሙማን ሆስፒታላት እቶም 36% ብዓሶ ዝተተሓዙ ክኾኑ ከለዉ 15% ድማ ዓራት ሒዞም ዝሕከሙ ምዃኖም የርኢ። ገለ ገለ ተመራመርቲ ድማ ዋላ'ዃ ብተዛማዲ ዝተሓተ መጠን ውፅኢታውነት እንተሃለዎ ምስቲ ኣብ ኣፍሪቃ ዓመታዊ ዝረአ 200 ሚልየን ብሕማም ዓሶ ዝተሓዙን ካብዚኦም 400,000 ድማ ዝሞቱሉ ኩነታት ኣንፃር ዓብዪ ተጽዕኖ ክህልዎ ምኳኑ ይገልፁ።
ታሊባን በአሜሪካ እጅ የነበረውን የጦር አዛዥ ለማስፈታት ከሁለት አመት በላይ ታስሮ የነበረውን አሜሪካዊ የባህር ኃይል አርበኛ ለዋሽንግተን አሳልፎ መስጠቱን አስታወቀ፡፡ የአፍጋኒስታን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አሚር ካን ሙታቂ በካቡል ለጋዜጠኞች እንደተናገሩት "ዛሬ ማርክ ፍሬሪችስ ለአሜሪካ ተላልፎ ተሰጥቷል ፤ እኛም የጦር መሪው ሃጂ ባሻር ኑርዛይ በካቡል አየር ማረፊያ ተሰጥቶናል" ብለዋል። ልውውጡ የተከናወነው “ከረጅም ድርድር በኋላ” መሆኑን የገለጹት ሚኒስትሩ፤ በካቡል ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ አንድ የሀገራችን ልጅ ወደ ሀገሩ ሲመለስ የነበረውን አስደናቂ ስነ ስርዓት በማየታችን ደስተኛ ነን ሲሉ ተናግረዋል፡፡ ኑርዛይ በአውሮፕላን ማረፊያው ሲደርስ በአዲሱ የአፍጋኒስታን እስላማዊ ኢሚሬትስ (አይኢኤኤ) መንግስት የጀግና አቀባበል እንደተደረገለትም ኤኤፍፒ ዘግቧል፡፡ በማህበራዊ የትስስር ገጾች በመዘዋወር ላይ ያሉ ፎቶዎች የሚያሳትም፤ኑርዛይን የአበባ ጉንጉን በያዙና ጭንብል በለበሱ የታሊባን ባለስልጣናት አቀባበል ሲደረግለት ነው፡፡ ለበርካታ አመታት በአሜሪካ እጅ የቆየው የጦር አዛዡ ባሻር ኑርዛይ ወደ ሀገሩ ከተመለሰ በኋላ በሰጠው መግለጫ የታሊባን አመራሮች እሱን ለመስፈታት የተጓዙት የድርድር ርቀት አድንቋል፡፡ “ታሊባን ጠንካራ ቁርጠኝነቱን ባያሳይ ኖሮ ዛሬ እዚህ ባልነበርኩ ነበር” ብሏል ኑርዛይ። ባሻር ኑርዛይ - ከሄሮይን ኮንትሮባንድ ጋር በተያያዘ ለ17 ዓመታት በአሜሪካ ታስሮ የቆየ የጦር አዛዥ ሲሆን ማርክ ፍሬሪችስ ደግሞ እንደፈረንጆቹ በ2020 ታፍኖ ተወስዶ በታሊባን ቁጥጥር ስር የቆየ የአሜሪካ የባህር ኃይል አርበኛ ነው፡፡ የአሜሪካ የባህር ኃይል አርበኛው ማርክ ፍሬሪችስ በአፍጋኒስታን ውስጥ በግንባታ ፕሮጀክቶች ላይ በሲቪል መሃንዲስነት ሲሰራ የነበረ እንደሆነም ነው የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የገለጸው፡፡ ኑርዛይ በታሊባን ውስጥ ምንም አይነት ኦፊሴላዊ ቦታ አልነበረውም ነገር ግን በ 1990 ዎቹ ውስጥ ጠንካራው እንቅስቃሴ ብቅ ባለበት ወቅት “ጦር መሳሪያዎችን ጨምሮ ለታሊባን ጠንካራ ድጋፍ ያደረግ ነበር” ያሉት ደግሞ የአፍጋኒስታን መንግስት ቃል አቀባይ ዛቢሁላህ ሙጃሂድ ናቸው፡፡ ከአንድ አመት በፊት የአሜሪካና አጋሮቿ ጦር ከ20 ዓመታት ወታደራዊ ጣልቃ ገብነት በኋላ አፍጋኒስታንን ለቀው መውጣታቸውን ተከትሎ፤ ታሊባን አፍጋኒስታንን እያስተዳደረ እንደሚገኝ የሚታወቅ ነው፡፡
ባለፈው አመት የተከሰተው የታይፉን አውሎ ንፋስ ከፍተኛ ጎርፍ በማስከተሉ አገሪቱ በግብርናው ዘርፍ በቂ የእህል ምርት ማምረት አለመቻሉን ተከትሎ ሀገሪቱ የምግብ እጥረት እንደገጠማት አስታውቃለች፡፡ የሰሜን ኮሪያው መሪ ኪም ጆንግ-ኡን ከሀገሪቱ ከፍተኛ አመራሮች ጋር በነበራቸው ስብሰባ ላይ እንደተናገሩት “የህዝቡ የምግብ ሁኔታ አሁን እየተወሳሰበ ነው” ፣ ሀገሪቱ የምግብ እጥረት ገጥሟታል ብለዋል፡፡ ይህንን ተከትሎ አንድ ኪሎ ሙዝ 45 ዶላር እየተሸጠ እንደሚገኝ ኤንኬ ኒውስ ዘግቧል፡፡ ሰሜን ኮሪያ በኑክሌር መርሃግብሯ ምክንያት ከተጣለባት ዓለም አቀፍ ማዕቀቦች ጋር እየታገለች ቢሆንም ብሔራዊ የኢንዱስትሪ ምርት ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር ከ 25 በመቶ አድጓል ብለዋል ፡፡ በሚያዝያ ወር ላይ ኪም አገራቸው አርዱስ ማርች ተብሎ እንደሚጠራው ረሃብ እንዳያጋጥማት እና ህዝባችንን ልንረዳ ይገባል ብለው ነበር። አርዱስ ማርች ተብሎ የሚታወቀው በሰሜን ኮሪያ ክፉ የረሃብ ዘመን ሲሆን ይህም በአውሮፓውያኑ 1990 ወቅት ነው። በወቅቱ በረሃብ የሞቱ ሰሜን ኮሪያውያን ቁጥር በትክክል ባይታወቅም እስከ 3 ሚሊዮን ይገመታል። ውድ አድማጮቻችን እና ተከታዮቻችን የኢትዮ ኤፍ ኤም ስርጭቶችንቻናላችንን እና ሌሎች ዝግጅቶችን ለመከታተል የቴሌግራም ቻናላችንን https://t.me/ethiofm107dot8 ይቀላቀሉ።
ኣብ ተዋሰንቲ ዞባታት ሰሜን ሸዋ ወረዳ ኤፍራታ ግድምን ምምሕዳር ብሄረሰብ ኦሮሞ ወረዳ ጅሌ ጥሙጋን ብቕድሚ ትማሊ ሶኑይ ብዝተላዕለ ግጭት ኣባላት ፍሉይ ፖሊስ ሓዊሱ ብዓሰርተታት ዝግመቱ ሰባት ምሟቶምን ምቑሳሎምን ምንጭታት ድምፂ ኣሜሪካ ገሊፆም። ትኽክለኛ ቁጽሪ ዝሞቱ ሰባት ግን ኣይተፈልጠን። መንበሪ ኣባይቲ ከምዝተቓፀሉ እውን ሽሞም ክግለፅሎም ዘይደለዩ ነበርቲ ገሊፆም። ካብ መንግስቲ ሓበሬታ ንምርካብ ዝተገብረ ተደጋጋሚ ፃዕሪ ኣይትዓወት: እንተኾነ መበገሲ እቲ ግጭት ዝምልከት ካብ ዞባ ሰሜን ሸዋ ይኹን ካብ ምምሕዳር ብሄረሰብ ኦሮሞ ዝፍኖ ክልተ ዓይነት ሓበሬታ እዩ። በቲ ሓደ ወገን ሸኔ ኢሎም ዝፅውዕዎ ሰራዊት ነፃነት ኦሮሞ እዩ ኣበጊስዎ ዝብል ክኸውን ከሎ በቲ ካልእ ወገን ድማ ፈፀምቱ ዕጡቓት መንግስቲ እዮም ክብሉ ይካሰሱ ።
ለእርስዎ ማጨጃ የሚሆን ትክክለኛውን መተኪያ ምላጭ እንደላክን ለማረጋገጥ፣ እባክዎን የኦሪጂናል ዕቃ አምራች # ወይም የቢላዎን መለኪያ (ከላይ ከግራ ወደ ታች በስተቀኝ Blade ወይም ከላይ ከቀኝ ወደ ግራ በስተግራ ርዝመት ይለኩ)። በባለቤትዎ መመሪያ ወይም ክፍሎች ዝርዝር ውስጥ የአምራችዎን ክፍል ቁጥር ያረጋግጡ።የተዘረዘረው OEM # ከዚህ ቁጥር ጋር መመሳሰል አለበት።የአምራችህ ክፍል ቁጥር ካልተዘረዘረ በነፃ ስልክ ቁጥር 800-345-0169 ይደውሉልን እና ሙሉ የቢላ ማከማቻችንን እንፈትሻለን፣ እና/ወይም ለእርስዎ እንደምናገኝ እናያለን! ቢላዎችን በሚጭኑበት ጊዜ እባክዎ የማጨጃ አምራቹን የመጫኛ መመሪያዎችን ይከተሉ።እነዚህን መመሪያዎች አለመከተል በንብረት ላይ ጉዳት፣ በግል ጉዳት ወይም ሞት ሊያስከትል ይችላል። ለቻይና ፕሮፌሽናል ቻይና ከፍተኛ ጥራት ያለው Husqvarna Lawn እሴት የተጨመረበት ዲዛይን፣ አለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ የማምረቻ እና የአገልግሎት አቅሞችን በማቅረብ የኛ ተልእኮ የከፍተኛ የቴክኖሎጂ ዲጂታል እና የመገናኛ መሳሪያዎች ፈጠራ አቅራቢ መሆን ነው።Mower Blade መተካት/Zcd-Hsqv-M031፣ በሁሉም ቦታ ሸማቾችን ለረጅም ጊዜ ለሚሰሩ አነስተኛ የንግድ ማኅበራት እንዲደውሉልን በቃሉ ውስጥ እንቀበላለን።የእኛ መፍትሄዎች ዋናዎቹ ናቸው.አንዴ ከተመረጠ ፣ ለዘላለም በጣም ጥሩ! የቻይና ፕሮፌሽናል ቻይናየሣር ማጨጃ Bladeእና Mower Blade ዋጋ፣ ጥራት ያላቸውን እቃዎች ብቻ እናቀርባለን እና ንግድን ለማስቀጠል ብቸኛው መንገድ ይህ እንደሆነ እናምናለን።እንደ ሎጎ፣ ብጁ መጠን፣ ወይም ብጁ ምርቶች እና መፍትሄዎች ወዘተ በደንበኛው ፍላጎት መሰረት ብጁ አገልግሎት መስጠት እንችላለን።
የትህነግ ክንፍ የሆነውንና በውጭ አገር የሚንቀሳቀሰው ሃይል ከመንግስት ጋር ለመደራደርና በዋቅሻ ውስጥ ያሉትን አመራሮች ለማስለቀቅ በሚቀርባቸው ዲፕሎማቶችና ተከፋይ ወስዋሾች እንቅስቃሴ መጀመሩን በዘገብንበት ወቅት በቅርቡ መንግስት የዘመቻውን ሁለተኛ ክፍል ኦፕሬሽን እንደሚጀምር በማርች ስምንት መረጃ አብረን መጠቆማችን ይታወሳል። የዚሁ አካል ስለመሆኑ በውል ያልተነገረለት ጥቃት በደቡብ ትግራይ በደቡባዊ ትግራይ ኦፍላ ወረዳ አውሸራ በተባል ስፍራ ከ80 በላይ የሚሆኑ የሕወሓት ታጣቂዎች መደምሰሳቸው ተሰምቷል። የአካባቢው ነዋሪዎችም አረጋግጠዋል። ከዚሁ ጋር ተያይዞ በአንድ ቀን ልዩነት ” ማዕከላዊ እዝ” በሚል የሚጠራው የትህነግ ሰራዊት መመታቱ ተገልጿል። በተደጋጋሚ ወታደራዊ መረጃዎችን በመጠቆም የሚታወቀው አርአያ ተስፋማሪያም የመረጃ ምንጮቹን ጠቅሶ ” በማይጨው ቦራ በተባለ ቦታ የመከላከያ ሰራዊት በወሰደው የማጥቃት ዘመቻ ‘ማዕከላዊ እዝ’ ተብሎ የተሰየመውን የጁንታው ሀይል ሙሉ በሙሉ መደምሰሱን ከመከላከያ ከፍተኛ የጦር አዛዦች የተገኘው መረጃ አረጋግጧል ” ሲል አስታውቋል።” ከተከዜ ሸሽቶ ወደ ተጠቀሰው ቦራ ተራራ የመጣው ይህ የጁንታ ሀይል ደብረፂዬን እና የቀድሞ ኢታማዦር ሹም ጄ/ል ፃድቃን ይመሩት እንደነበረ የጠቆሙት ምንጮቹ አያይዘውም ‘ማዕከላዊ እዝ’ ብለው የሰየሙት ሀይል ሙሉ በሙሉ ከተደመሰሰ በኃላ በዛሬው እለት ደብረፂዬን፣ ፃድቃንና ሌሎች የጁንታው መሪዎች የመሸጉበት ቦታ ደርሶ የመከላከያ ሰራዊታችን እንደከበባቸው አስታውቀዋል። በዚህ ኦፕሬሽን የተከበቡት ጄኔራሎችና ሌሎች መሪዎች እጣ ፈንታ ብዙ ጊዜ ሳይወስድ እንደሚታወቅ ከፍተኛ የጦር አዛዦች ገልፀውልኛል” ሲልም ጨምሮ አስታውቋል።ይህ መረጃ በመንግስት አካላት በይፋ ባይገለጽም ኢትዮ12 ኦፕሬሽኑ እንደሚጀመር መረጃ ነበራት። በዚሁ መነሻ የቀደመውን መረጃ የሰጡንን ወገኖች ጠይቀን ” ዘመቻው የሚጠበቅ ነው። የተለሳለሰ አቋም የነበራቸውን ለመያዝና የሚከፈለውን ዋጋ ለመቀነስ ሲባል፤ እንዲሁም የተበተነው ሃይል እንደ ቡጉንጀ አንድ ላይ ተሰባስቦ ለከበባ እንዲመች ሲሰራ ነበር” ሲሉ ዝርዝር መረጃ ለጊዜው እንዳልደረሳቸው ተናግረዋል።ከትናንት ጀምሮ በትህነግ ሰራዊት ላይ ደረሰ ስለተባለው ጥቃት ከትህነግ የውጭ ክንፍም ሆነ አልፎ አልፎ ” ከበረሃ” ነው የሚባለው አካል እስካሁን ማስተባበያ አልሰጠም። ይልቁኑም የተባበሩት መንግስታት ትግራይ በቅርቡ እንደሚገባና ትግራይ ራስዋን እንድታስተዳድር ድጋፍ እንደሚሰጣቸው ደጋፊዎች አዲስ አበባ ሆነው በማህበራዊ ገጻቸው እያስታወቁ ነው።
የብሪታንያ ንግስት ኤልሳቤጥ ሁለተኛ ህልፈትን ተከትሎ የአለም መሪዎች ሀዘናቸውን እየገለፁ መሆኑ ተነግሯል።የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን፣ የፈረንሳዩ መሪ ኢማኑኤል ማክሮን ፣ የቻይናው ፕሬዚዳንት ሺ ጂ ፒንግን ጨምሮ በርካታ የአለም መሪዎች ትናንት በ96 አመታቸው ላረፉት ንግስት ኤልሳቤጥ ሁለተኛ የተሰማቸውን ጥልቅ ሀዘን አስተላልፈዋል።የንግስት ኤልሳቤጥ ሁለተኛ እረፍት ከተሰማበት ሰአት አንስቶ እንግሊዛውያን ብርቱ ሀዘናቸውን በመግለፅ ላይ መሆናቸውን ቢቢሲ ዘግቧል። #ብሪታንያ የብሪታንያው ልኡል ቻርለስ የአገሪቱ አዲሱ ንጉስ ሆነው ተሾመዋል።ንግስት ኤልሳቤጥ ሁለተኛ ማረፋቸውን ተከትሎ ነው ልኡሉ ቻርለስ 3ኛ ተብለው በይፋ የብሪታንያ ንጉስ ሆነው የተሾሙት ።አዲሱ የብሪታንያ ንጉስ ቻርለስ 3ኛ የጋራ የብልፅግና አገራት መሪ ብሎም የ 15 አገራት ንጉስ ሆነው እንደሚያገለግሉ ቢቢሲ ዘግቧል። #ሩሲያ ቱርክ የሩሲያ የእህል ምርትን ለአፍሪካ አገራት ለመላክ ፈቃደኛ መሆኗን አስታውቃለች።የቱርኩ ፕሬዚዳንት ታይፕ ኤርደዋን የዩክሬን እህል ለአውሮፓ መሄዱ ትክክል አለመሆኑን ገልጸው ቱርክ የሩሲያን እህል ለአፍሪካ ለመላክ ዝግጁ ነች ብለዋል።የመንግስታቱ ድርጅት ፣ ቱርክ ፣ ሩሲያ እና ዩክሬን ከዩክሬን እህል ወደ አፍሪካ እንዲላኩ ከ 3 ወራት በፊት ስምምነት መድረሳቸውን አስታውሶ አናዶሉ ዘግቧል። #ቱርክ ቱርክ የአሸባሪውን የአይ ኤስ ኤስ ከፍተኛ መሪ በቁጥጥር ስር ማዋሏን ይፋ አደረገች ።የቱርክ ፕሬዚዳንት ታይፕ ኤርዶዋን የአገሪቱ የፀጥታ ሃይሎች ባካሄዱት ዘመቻ የአሸባሪው የአይ ኤስ ኤስ አመራር የሆነውን አቡ ዘይድን በቁጥጥር ስር አውለናል ብለዋል ::የአይ ኤስ ኤስ አመራሩ አቡ ዘይድ በህገ ወጥ መንገድ ወደ ቱርክ ገብቶ ሲንቀሳቀስ የደህንነት ሃይሎች ተከታትለው በቁጥጥር ስር አውለውታልም ሲሉ ኤርዶዋን መናገራቸውን አልጀዚራ ዘግቧል።
የህወሃት ቡድን በልዩ ሃይሉ አማካኝነት በአገር መከላከያ ሰራዊት ሰሜን ዕዝ ላይ ጥቃት መሰንዘሩን ተከትሎ በሰሜን ኢትዮጵያ የህግ ማስከበር ዘመቻ ከተጀመረ 18ኛ ቀኑ ላይ ደርሷል። የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን በማይካድራ የተፈጸመውን አሰቃቂ ግድያ ቦታው ላይ በነበረው የመንግስት አስተዳድር ወይም በትግራይ የጸጥታ ሃይል አጋዥነት እና ሳምሪ በተሰኘ የወጣቶች ቡድን መፈጸሙንም በያዝነው ሳምንት ማሳወቁ አይዘነጋም። ኮሚሽኑ በዚህ አሰቃቂ እና ማንነትን መሰረት ባደረገ የግድያ ወንጀል በማይካድራ 600 ንጹሀን ዜጎች መገደላቸውን ገልጿል። የሟቾች ቁጥር ከዚህም በላይ ሊሆን እንደሚችል የገለጸው ኮሚሽኑ ክስተቱ የጦር ወንጀል የመሆን እድሉ የሰፋ ሊሆን እንደሚችልም በቅድመ ምርመራ ሪፖርቱ ጠቁሟል። ይሁንና በቦታው ያሉ የህክምና ባለሙያዎች በኮሚሽኑ የተጠቀሰው ቁጥር ስህተት አለበት ሲሉ የህክምና ባለሙያውን ቡድን የመሩት ዶክተር ስምኦን ደሳለኝ ለኢትዮ ኤፍ ኤም ተናግረዋል። እንደ ዶክተር ስምዖን አስተያየት ከሆነ በአካባቢው በተፈጠረው ጦርነት የተጎዱ ሰዎችን ለማከም ወደ አካባቢው ማምራታቸውን ተናግረው በማይካድራ ሆን ተብሎ ግድያ የተፈጸመባቸው ሰዎች ከ750 በላይ እንደሆነ በአይናቸው ማየታቸውን እና ይሄንን አሃዝም የሰብአዊ መበት ኮሚሽን ላሰማራቸው መርማሪዎች መናገራቸውን ነግረውናል። የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን ኮሚሽነር ዶክተር ዳንኤል በቀለ በበኩላቸው ጉዳዩን ለመመርመር ወደ ሰፍራው ያቀናው የምርመራ ቡድን መረጃዎችን ሐኪሞችን ጨምሮ በአካባቢው ካሉ የተለያዩ አካላትን ጠይቀው መመለሳቸውን ተናግረዋል። በምርመራው የተገኘውን መረጃ ከተለያዩ ቦታዎች ስለምንቀበል በራሳችን መመዘኛ አጣርተን ነው ይፋ የምናደርገው ሆኖም ግን በዚህ አሰቃቂ ግድያ ህይወታቸው ያለፉ ዜጎች ቁጥር 600 ብቻ ነው ብለን አልገለጽንም በቀጣት ተጨማሪ እናዋናው ሪፖርት ሲሰራ ትክክለኛው የሟቾች ቁጥር ይታወቃል ሲሉም ዶክተር ዳንኤል ምላሽ ሰጥተውናል።
በኮንሶ ዞን እና በአሊ ልዩ ወረዳ እንዲሁም በደራሼ ልዩ ወረዳ እና በኮንሶ የተከሰተው ግጭት ሙሉ ለሙሉ መብረዱን የደቡብ ክልል የሰላምና ጸጥታ ቢሮ አስታወቀ፡፡ – Ethio FM 107.8 Skip to content በኮንሶ ዞን እና በአሊ ልዩ ወረዳ እንዲሁም በደራሼ ልዩ ወረዳ እና በኮንሶ የተከሰተው ግጭት ሙሉ ለሙሉ መብረዱን የደቡብ ክልል የሰላምና ጸጥታ ቢሮ አስታወቀ፡፡ By Ethio Admin November 24, 2020 November 24, 2020 የሀገር ውስጥ ዜና የደቡብ ክልል የሰላምና ጸጥታ ቢሮ ኃላፊ አቶ አለማየሁ ባውዲ ለኤትዮ ኤፍ ኤም እንዳስታወቁት በእነዚህ አከባቢዎች የተከሰተውን ግጭት ብሔረሰብ ተኩር ለማስመሰል የተደረገውን ጥረት ከሽፏል፡፡ በትግራይ ክልል እየተካሄደ ያለውን ህግ የማስከበር ስራ ለማጠናከር በአከባቢው ላይ የነበረው የመከላከያ ሰራዊት መልቀቁን ተከትሉ አጋጣሚውን ለመጠቀም ከህውሀት እንዲሁም ከኦነግ ሸኔ ጋር ሲል ያላቸው እና ለዘመናት ሲጠነስሱት የነበረው ሴራ ያላቸው ግለሰቡች አላማቸውን ለማሳካት ግጭቱን እንደቀሰቀሱት ይናገራሉ አቶ አለማየሁ፡፡ በደራሼ ልዩ ወረዳ እና በኮንሶ መካከል ግጭቱ የብሔረሰብ ለማስመሰል ኮታ ገጠም የሆኑ አርሶ አደሮች እርስ በእርስ እንዲጋጩ ተደርጓል ነው ያሉት፡፡ በተመሳሳይ በኮንሶ እና በጉርጂ-አማሮ አማካኝ አከባቢ የልዩ ወረዳ ጥያቄን እናስመልስላችኋለን በሚል በከፍተኛ ሁኔታ እንቅስቃሴ ሲደረግ እንደነበር ደርስንበታል ብለውናል፡፡ በዚህ ሰበብም ህይወት ጠፍቷል፤በርካታ ቤቶች ተቃጥለዋል፤ንብረት ወድሟል፤በርካቱችም ቀያቸውን ጥለው ተሰደዋል፡፡ በአጠቃላይ የደረሰውን ጉዳት እና በዚህ ውስጥ ግንባር ቀደም ተሳታፊ የሆኑትን ሰዎች ፖሊስ በቅርቡ ምርመራውን እንዳጠናቀቀ ይፋ እንደርጋለን አሁን ግን መናገር አልችልም ብለውናል፡፡
ኒውዮርክ ኣብ ዝርከብ ቤተ-ክርስትያን መጥምቃውያን ኣቢስንያ ዝተዳለወ ስነ-ስርዓት፣መራሒ ኢትዮዽያ ዝነበሩ ኣቶ መለስ ዜናዊ ዝተፈላለየ ትርጉም ከምዝነበሮ ዝሓበረ’ዩ።ብደረጃ ኣፍሪቃን ኢትዮዽያን፣ ድኽነት ንምውጋድ ዝገበርዎ ፃዕሪን ብቅዓት ኣመራርሖምን፣ኣብ ኢትዮዽያ ዘመዝገብዎ ቁጠባዊ ዕብየትን ገዲፎምዎ ዝሓለፉ ሰናይ ግብሪታትን ተጠቂሶም‘ዮም። ብካልእ ወገን፣ኣቶ መለስ ንኢትዮዽያ ኣብ ዝመርሑለን ፳፩ ዓመታት፣ መስርሕ ዴሞክራሲ‘ታ ሃገር ምጉታቱ፣ኩነታት ሰብኣዊ መሰላት ከምዝሓመቀን ናፅነት ትካላት ዘይምህላውን ዝጥቀሱ ኣሉታዊ ነጥብታት ኮይኖም‘ለው። ኣብ ቤተ-ክርስትያን መጥምቃውያን ኣቢስንያ ፃውዒት ተገይሩሎም ዝተረኸቡ ላዕለዎት ሰበ-ስልጣን፣ንዋና ፀሓፊ ሕ/ሃ ኮፊ ኣናን፣ኣብ ቤት ምኽሪ ፀጥታ ሕ/ሃ ኣምባሳደር ኣሜሪካ ሱዘን ራይስ፣ፍሉጣት ምጣንያዊ ኪኢላታትን ኣምባሳደር ኢትዮዽያ ኣብ ኒውዮርክን ገሊኦም‘ዮም። ኣምባሳደር ዴቪድ ሽን፣መንግስቶም ኣብ መትከላት ዴሞክራስን ነፃነትን ናብ ዋጋ ዕዳጋ ኣይኣቱን ይብሉ።ተቃወምቲ ኢትዮዽያ፣መንግስቲ ኣሜሪካ ስለ ረብሕኡ ኢሉ፣ነቶም መትከላት ይሸራርፎም‘ሎ ኢሎም ንዘቅርብዎ ቅሬታ እውን ሪኢቶኦም ሂቦም‘ለው። ምንስቴር ወፃኢ ኣሜሪካ ዓመታዊ ሪፖርት ሰብኣዊ መሰላት ኢትዮዽያ ምርኣይ ይካኣል‘ኮ‘ዩ።እዞም ዝዝረበሎም ዘሎ ብንፁር ሰፊሮም‘ለው።ላዕለዎት ሰበ-ስልጣን ኣሜሪካ ክዛረቡ ከለው፣ኣብ ኣደባባይ እንተኾይኑ ልስሉስ ቋንቋ እዮም ዝጥቀሙ።ምስ መራሕቲ ኣብ ዕፁው ኮይኖም ግና፣ብርቱዓት ቃላት እዮም ዝጥቀሙ።ስለዚ መብዛሕትና ነቲ ኣብ ኣደባባይ ዝቃላሕ ኢና ንሰምዕ ኢሎም ኣምባሳደር ዴቪድ ሽን።
በሙያዋ ምክንያት የተለያዩ ሀገራትን ተዘዋውሮ ለማየት ዕድል ላገኘችው ህይወት ዮሃንስ ለጥቁር እና ጠይም ቆዳ የሚሆኑ ጤናማ የውበት መጠበቂያ ምርቶችን ማግኘት ፈተና ሆኖባት ቆይቷል። የኃላ ኃላ የተመረቀችበትን የመድሃኒት ቅመማ ዘርፍ ከትውልድ ሀገሯ ኢትዮጵያ ሀገራዊ አሻራዎች ጋር አስተባብራ በዐይነቱ ለየት ያለ የውበት መጠበቂያ አምራች ድርጅት መስራች ሆናለች። ህይወት የመሰረተችው ድርጅት አስካላይት ፎርሚዩላ ይባላል። ከአሜሪካ ድምጽ ጋር በነበራት ቆይታ እንዳስረዳችው የዛሬ አራት ዓመት ገደማ የተቋቋመው ድርጅት ተፈጥሯዊ የሆኑ የውበት መጠበቂያ ምርቶችን እያቀረበ ይገኛል። በቅርቡ ደግሞ በዘርፉ የመጀመሪያ ነው የተባለለትን ከጤፍ የሚገኙ ንጥረነገሮችን በግብዓትነት የሚጠቀም የቆዳ ውበት መጠበቂያ እንዳመረተም ታክላለች። አስካላይት ፎርሚዩላ ከምርቶቹ መጠሪያ ጀምሮ ሳይቀር የኢትዮጵያ ብሎም የአፍሪካን አሻራ ላለመልቀቅ የሚጥር ዓይነት ነው። የአስራ ሶስት ወር ጸጋ፣ አዲስ ፣ፓን አፍሪካ ፣ጣና እና ጣእቱ የሚባሉ ምርቶችን ለአብነት መጥቀስ ይቻላል። ሁሉም ተገቢውን የምርት ጥራት እና ቁጥጥር ሂደት አልፈው ለገበያ መሰራጨታቸውን ህይወት ትናገራለች። ለመሆኑ ኢትዮጵያዊያን ለዘመናት የተጠቀሙበት ጤፍ በምን ሁኔታ ለውበት መጠበቂያነት ዋለ?ሀብታሙ ስዩም ይሄንና ሌሎች ተያያዥ ጥያቄዎችን ለህይወት ዮሃንስ አቅርቧል። ሙሉ መሰናዶውን ያዳምጡ።
ብሰንኪ ፋሽስታውያንን መሻርክቶምን ዘራያት ኣተኣኻኪቦም ኣብ ልዕሊ ህዝቢ #ትግራይ ዘካየድዎ ቅሉዕ ወራር ፣ ብርክት ዝበለ ማሕበረሰብ ንስነ-ልቦናዊ ፣ ማሕበራውን ኢኮኖምያውን ማህሰይቲ ተቓሊዑ እዩ። ማሕበረሰብ ኣጋጢምዎ ካብ ዘሎ ማህሰይቲ ንምቅላል ኣተሓሳስባ ደቂ ሰባት ንምዕባይ ዝሰርሕ ትካል ኣሊፍ ሸዋል ብምኽንያት በዓል ዒድ ምርኢት ኪነ ጥበብ ኣሳሊጡ። ኣባላትን ኣመራርሓን ትካል ኣሊፍ ፋሽስታውያን ሓይልታት ዘራያቶም ኣተኣካኺቦም ኣብ ልዕሊ ህዝቢ ትግራይ ብዝወልዕዎ ቅሉዕ ኲናት ስነ-ልቦና ወገናቶም ንምሕዋይን ዝተፀገሙ ወገናት ንምሕጋዝን ይሰርሑ ከም ዘለዉ ተዛሪቦም። ተሳተፍቲ ወገናት ብግደኦም ትካል ኣሊፍ ይገብሮ ዘሎ ኣብ ምሕዋይ ስነ ልቦና ኮነ ማሕበራውን ኢኮኖሚያውን ዓርሰ ምትሕግጋዛት ኣጠናኺሩ ክቕፅለሉ ተላብዮም። ህዝቢ ትግራይ ኣጋጢምዎ ዘሎ ዓፀባ ንምምካት ድማ ሃይማኖት ከይፈለየ ነንባዕሉ ክተሓጋገዝ ይግባእ ኢሎም። ፀሓፊ ሓፈሻዊ ቤት ምኽሪ ጉዳያት እስልምና ትግራይ ሓጂ መሓመድ ካሕሳይ ብወገኖም ትካል ኣሊፍ ኣተሓሳስባ ደቂ ሰባት ንምዕባይን ንዝተፀገሙ ወገናት ንምሕጋዝ ዝገብሮ ዘሎ ምንቕስቃስ ዝነኣድ እዩ ተጠናኺሩ ክቕፅል ድማ ፀዊዖም።
መንግስቲ ኢትዮዽያ ኣብ ዝተፈላለያ ከተማታት ኣሜሪካን ካናዳን ንዜጋታቱን ኢትዮዽያ ዝመቦቅሎምን ሰባት ብዛዕባ ትልሚ ምዕባለን ትራንስፎርሜሽንን ንምዝርራብ ዝወጠኖ ኣኼባ ቀዳምን ሰንበትን ተካይዱ። ናይ ዋሽንግተን ዲሲ ኣኼባ ግና ቀዳም ተቋሪፁ ትማሊ ሰንበት ኣብ ውሽጢ ኤምባሲ ኢትዮዽያ ተዛዚሙ‘ሎ።እቲ ኤምባሲ ግና ኩሎም ኣኼባታት ኣሜሪካን ካናዳን ብዓወት ተዛዚሞም ይብል። ዕላማ እቲ ኣኼባ ”ብዛዕባ ውጥን ምዕባለን ትራንስፎርሜሽንን ምስ ኢትዮዽያውያንን ኢትዮዽያ ዝመቦቆሎምን”ይብል ኣብ ውሽጢ‘ቲ ኣዳራሽ ዝተሰቅለ ፅሑፍ።እንተኾነ ቀዳም ምይይጥ ኣይተገብረን። ምንስቲር ትምህርቲ ኢትዮዽያ ኣቶ ደመቀ መኮንን መብርሂ ምሃብ ምስ ጀመሩ፣ሓደ ተሳታፊ ንዝተቀትሉ ኢትዮዽያውያን ናይ ሕልና ፀሎት ይቅደም“ ዝብል ድምፂ ኣስምዐ።ናይ ድጋፍ ድምፂ‘ውን ተቃለሐ።ፖሊስ ዩኒቨርስቲ ሃወርድ ክንዲ ዝኻኣለ ደፊኡን ጎቲቱን ኣውፅኦም።ኣምባሳደር ግርማ ተጎቲትኩም ካብ ትወፁ፣ኮፍ ኢልኩም ኣዳምፁ እንተበሉ ሰማዒ ኣይተረኽበን። ስሞም ክገልፁ ዘይመረፁ ተኣካባይ ኣብ ሪኢቶኦም "መዓስ ኢኹም ካብ ስልጣን ትወርዱ? ዕስራ ዓመት ኣይኣኽለኩምን ድዩ? ኣምባሳደር ብርሃነ ”ባድመ ናይ ኢትዮዽያ ድያ ናይ ኤርትራ? ንኣምባሳደር ግርማ ”ኣብ‘ዚ እዋን ብዙሓት ኦሮሞቶት ኣብ ኢትዮዽያ ኣብ ማእሰርቲ እናተሳቀዩ ንሶም እንታይ ይገብሩ‘ለው?" ዝብል ሕቶ ኣቅረቡ። ኣቶ ወንድኣየሁ ካሳ ዝተባሃሉ ካልእ ተሳታፊ ንመንግስታዊ ውጥንን ንቅንዕና እቶም ኣጋይሽን ክገልፁ ከለው "ኣብ‘ዚ እዋን‘ዚ ኣብ ሃገርና ብዛዕባ ዝሳለጥ ዘሎ ተበግሶ ለውጢ ክትገልፁልና ከለኹም፣ ብዘይመጠን ተሓጒስና።ሃገርና ኢትዮዽያ ብጥምየትን ደርቂን ትጥቀስ፣ህዝባ መቀለዲ ኮይኑ መስሐቂ ኮይኑ ዝፀንሐ ምኻኑ ንፈልጥ ኢና።ህዝቢ ኢትዮዽያ ካብ ጥምየት ተናጊፉ ኣይኮነን ዝባሃል ዘሎ።ገና ብዙሕ ጉዕዞ ይተርፈና‘ሎ።ይኹን‘ምበር እቲ ኣንፈት ኣብ ቅኑዕ መስመር‘ዩ ዘሎ" ኢሎም። እዚ ከምዚ‘ሉ ከሎ፣ኣብ ፊት ንፊት ዩኒቨርስቲ ሃዋርድ መአከቢ ኣዳራሽ ክራምፕተን ተኣኪቦም ዝነበሩ ብኣማኢት ዝቁፀሩ ተቃወምቲ፣ቀዳም ድሕሪ ምሳሕ ድምፆም የቃልሑ ነይሮም።ኣብ ኢትዮዽያ ህንፀት ህንፀት ዴሞክራሲን ምሩፅ ምሕደራን ኣብ ምስፋን ኢህወደግ ኣሉታዊ ተራ ኣለዎ፣ብራሃፅና ዘጥረናዮ ገንዘብ ንባንኪ ስዊስ ኣይነርክብን ዝብሉ ጭርሖታት ኣቃሊሖም።ኣብ ምርጫ 97ን ብድሕሪኡን ብኢህወዴግ ተቀቲሎም ናይ ዝበልዎም ሰባት ስእሊ‘ውን ሒዞም ነይሮም። ብዛዕባ‘ቲ ኣኼባታት ኤምባሲ ኢትዮዽያ ኣብ ዋሽንግተን ዲሲ እንታይ ይብል? ሓላፊ ርክብ ህዝቢ ኣቶ ወሃደ በላይ ኩሎም ኣኼባታት ዩ-ስን ካናዳን ብዓወት ተዛዚሞም ይብሉ።ንሶም ወሲኾም ዝተወሰኑ ኣኽረርቲ ሰባት ነቲ ኣኼባ ንምዝራግ ፈቲኖም ከምዝፈሸሎም'ውን ገሊፆም። ዕለታዊ ፈነወ ድምጺ ኣመሪካ 04/12/2022 ፈነወ ትግርኛ ሰንበት ድምጺ ኣሜሪካ ፈነወ ቛንቛ ትግርኛ ካብ ሶኑይ ክሳብ ሰንበት ይፍነው። ፈነወ ቛንቛ ትግርኛ ካብ ሶኑይ ክሳብ ዓርቢ ብዕለታዊ ዜና ይጅምር፥ እዋናዊ ጉዳያትን ሰሙናዊ መደባት'ውን የጠቓልል ።ቀዳምን ሰንበትን ኣብቲ ሰሙን ዝተፈነው መደባት ብምድጋም ፈነወ ቛንቛ ትግርኛ ይኻየድ።
1. የአመጋገብ አካላት ምንጭ እና የተመጣጠነ ንጥረ ነገር ፍጹም ይዘት የምግብ መፍጫውን መወሰን ላይ ተጽእኖ ይኖረዋል.ከዚህ በተጨማሪ የአመጋገብ ሂደት በምግብ መፍጨት ላይ የሚያስከትለውን ውጤት ችላ ሊባል አይችልም. 2. የምግብ ጥሬ ዕቃዎችን ቅንጣት መቀነስ የምግብ መፈጨትን ያሻሽላል፣ በዚህም የምግብ አጠቃቀምን ያሻሽላል፣ ነገር ግን በምግብ አሰራር ወቅት ምርታማነትን ይቀንሳል፣ የምግብ ወጪን ይጨምራል እና የመንቀሳቀስ ችሎታን ይቀንሳል። 3. የ pretreatment ክፍል ሂደት ሁኔታዎች, ቅንጣት በማድቀቅ, extrusion የእንፋሎት granulation ሂደት ወይም ማድረቂያ ሁሉ መኖ ያለውን የአመጋገብ ዋጋ እና በዚህም መፈጨትን ላይ ተጽዕኖ ይችላሉ. 4. የቤት እንስሳትን መመገብ እና ማስተዳደር እንደ ቀድሞ የተመገቡትን ምግቦች አይነት እና መጠንን የመሳሰሉ የምግብ መፈጨትን ሊጎዳ ይችላል። Ⅱ. የቤት እንስሳው ራሱ ምክንያቶች የምግብ መፈጨትን በሚወስኑበት ጊዜ ዝርያን፣ ዕድሜን፣ ጾታን፣ የእንቅስቃሴ ደረጃን እና የፊዚዮሎጂ ሁኔታን ጨምሮ የእንስሳት ምክንያቶች ግምት ውስጥ መግባት አለባቸው። 1. የልዩነት ተጽእኖ 1) የተለያዩ ዝርያዎችን ተፅእኖ ለማጥናት, Meyer et al.(1999) 4.252.5 ኪ.ግ (በዘር ከ4 እስከ 9 ውሾች) በሚመዝኑ 10 የተለያዩ የውሻ ዝርያዎች የምግብ መፈጨት ሙከራ አድርጓል።ከነሱ መካከል የሙከራ ውሾች የታሸጉ ወይም የደረቁ የንግድ አመጋገቦች በደረቁ የ 13g / (kg BW·d) የሚወስዱ ሲሆን የአየርላንድ ቮልፍሆውንድ ደግሞ በ 10 ግራም / ዲ.(ኪግ BW·d)በጣም ከባድ የሆኑ ዝርያዎች በሰገራ ውስጥ ብዙ ውሃ ነበራቸው, የሰገራ ጥራት ዝቅተኛ እና ብዙ ጊዜ ሰገራ ይንቀሳቀሳሉ.በሙከራው ውስጥ፣ ትልቁ የአይሪሽ ዎልፍሀውንድ ሰገራ፣ ከላብራዶር ሰርስሮ አውጪው ያነሰ ውሃ ይዟል፣ ይህም ግምት ውስጥ የሚገባው ክብደት ብቻ እንዳልሆነ ይጠቁማል።በዝርያዎች መካከል ግልጽ የሆነ የምግብ መፈጨት ልዩነት ትንሽ ነበር.ጄምስ እና ማኬይ (1950) እና Kendall et al.(1983) መካከለኛ መጠን ያላቸው ውሾች (ሳሉኪስ, የጀርመን እረኞች እና ባሴት ሃውንድ) እና ትናንሽ ውሾች (ዳችሹንድ እና ቢግልስ) ተመሳሳይ የምግብ መፈጨት ችግር ነበራቸው, እና በሁለቱም ሙከራዎች ውስጥ, በሙከራ ዝርያዎች መካከል ያለው የሰውነት ክብደት በጣም ቅርብ ከመሆኑ የተነሳ ልዩነቱ በምግብ መፍጨት ውስጥ ትንሽ ነበሩ.ይህ ነጥብ ከኪርክዉድ (1985) እና ከሜየር እና ሌሎች ከክብደት መጨመር ጋር አንጻራዊ የሆድ ክብደት መቀነስ መደበኛነት ጠቃሚ ነጥብ ሆነ።(1993)የትናንሽ ውሾች ባዶ አንጀት ክብደት ከ6% እስከ 7% የሰውነት ክብደት ሲይዝ የትላልቅ ውሾች ደግሞ ከ3% እስከ 4% ይወርዳሉ። 2) ዌበር እና ሌሎች.(2003) የእድሜ እና የሰውነት መጠን በውጫዊ ምግቦች መፈጨት ላይ ያለውን ተጽእኖ አጥንቷል.ምንም እንኳን እነዚህ ትላልቅ ውሾች የሰገራ ውጤታቸው ዝቅተኛ እና ከፍ ያለ የእርጥበት መጠን ቢኖራቸውም በሁሉም የዕድሜ ክልል ውስጥ ባሉ በትልልቅ ውሾች ውስጥ የተመጣጠነ ምግብ መፈጨት በጣም ከፍተኛ ነበር። 2. የዕድሜ ተጽእኖ 1) በ Weber et al.(2003) ከላይ፣ በሙከራው ውስጥ ጥቅም ላይ በሚውሉት አራት የውሻ ዝርያዎች ውስጥ የማክሮ ኤለመንቶች መፈጨት (1-60 ሳምንታት) በከፍተኛ ሁኔታ ጨምሯል። 2) ጋሻ (1993) በፈረንሣይ ብሪታኒ ቡችላዎች ላይ የተደረገ ጥናት እንደሚያሳየው ደረቅ ቁስ ፣ፕሮቲን እና ጉልበት በ11 ሳምንት ውሾች ውስጥ የመፍጨት አቅም ከ2-4 አመት ከሆናቸው ውሾች 1 ፣ 5 እና 3 በመቶ ዝቅ ያለ ነው። .ነገር ግን በ6 ወር እና 2 አመት ውሾች መካከል ምንም ልዩነት አልተገኘም።ስለ ቡችላዎች የመፈጨት ችግር የቀነሰው በአመጋገብ ፍጆታ ብቻ (በአንፃራዊ የሰውነት ክብደት ወይም የአንጀት ርዝማኔ) ወይም በዚህ የእድሜ ክልል ውስጥ ያለው የምግብ መፈጨት ቅልጥፍናን በመቀነሱ እንደሆነ ግልጽ አይደለም። 3) ቡፊንግተን እና ሌሎች.(1989) ከ 2 እስከ 17 ዓመት ዕድሜ ያላቸውን የቢግል ውሻዎች መፈጨትን አነጻጽሮታል።ውጤቶቹ እንደሚያሳዩት, ከ 10 ዓመት እድሜ በፊት, የምግብ መፍጨት መቀነስ አልተገኘም.በ 15-17 አመት እድሜ ውስጥ, የምግብ መፍጫውን ትንሽ መቀነስ ብቻ ታይቷል. 3. የስርዓተ-ፆታ ተጽእኖ ሥርዓተ-ፆታ በምግብ መፍጨት ላይ ስላለው ተጽእኖ በአንጻራዊነት ጥቂት ጥናቶች አሉ.በውሻ እና በድመት ውስጥ ያሉ ወንዶች ከሴቶች የበለጠ የምግብ አወሳሰድ እና የመውጣት መጠን ከሴቶች ይልቅ የምግብ መፈጨት አቅማቸው ዝቅተኛ ሲሆን በድመቶች ውስጥ ያለው የፆታ ልዩነት ከውሾች የበለጠ ነው ። III.የአካባቢ ሁኔታዎች የመኖሪያ ቤት ሁኔታዎች እና የአካባቢ ሁኔታዎች በምግብ መፍጨት ላይ ተጽእኖ ያሳድራሉ, ነገር ግን በሜታቦሊክ ኬኮች ወይም በሞባይል ኬነሎች ውስጥ የተቀመጡ ውሾች ጥናቶች የመኖሪያ ቤት ሁኔታ ምንም ይሁን ምን ተመሳሳይ የምግብ መፈጨትን ያሳያሉ. ውጤታማ የአካባቢ ሁኔታዎች, የአየር ሙቀት, እርጥበት, የአየር ፍጥነት, የወለል ንጣፎች, የግድግዳዎች እና ጣሪያዎች መከላከያ እና የሙቀት ማስተካከያ እና የእነሱ መስተጋብር ሁሉም በንጥረ-ምግብ መፈጨት ላይ ተጽእኖ ያሳድራሉ.የሙቀት መጠን በሁለት መንገድ የሰውነት ሙቀትን ወይም ፍፁም የምግብ ቅበላን ለመጠበቅ በማካካሻ ሜታቦሊዝም ይሠራል።ሌሎች የአካባቢ ሁኔታዎች፣ ለምሳሌ በአስተዳዳሪዎች እና በእንስሳት መፈተሽ እና በፎቶፔሪዮድ መካከል ያለው ግንኙነት በንጥረ-ምግብ መፈጨት ላይ ተጽእኖ ሊያሳድር ይችላል፣ ነገር ግን እነዚህ ተፅዕኖዎች ለመለካት አስቸጋሪ ናቸው።
አለም አቀፍ የኢትዮጵያ ሴቶች ድርጅት ሰሞኑን ድምጻዊ ሀጫሉ ሁንዴሳ ግድያን አስከትሎ በአገራችን ኢትዮጵያ በተከሰተው አሳዛኝና አሰቃቂ ድርጊት ውድ ህይወታቸውን ላጡት በግፍ ስልተገደሉትና ስለተጨፈጨፉት ኢትዮጵያውያን ወገኖችች በሞላ የተሰማንን ጥልቅ ሀዘን እንገልጻለን፤ ድርጊቱንም አጥብቀን እናወግዛለን፣ ወንጀሎኞች ለፍርድ እንዲቀርቡ እንጠይቃለን፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ ጸርና ጠንቅ የሆነውን የወያኔን የጎሳ ክልል ስርአት ለማስወገድ የተደረገው የለውጥ ትግል ተጠልፎና ተቀልብሶ፣ አንዱን ጸረ ኢትዮጵያ የጎሳ መንግስት (የወያኔ/ኢህደግ)በሌላ የጎሳ መንግስት (ኦነግ/ብልጽገና) በመተካት ህዝብን ለእልቂት የሚዳርገን አጥፊ ነባራዊ እውነታ ላይ እንድንገኝ ሆነናል፡፡ በአሁኑ ጊዜ በተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍለ ከተማዎች፣ በአዲስ አበባ፣ በሀረር፣ በሻሸመኔ፣ በድሬዳዋ፣ በአርሲ ነገሌ በዝዋይ በባሌ ወዘተ፤ በማንነታቸው ምክንያት ብቻ እየተለዩ በተለይ በአማራው ህዝብ ላይ ካለፈው በቀጠለ ትኩረት እንዲሁም ሌሎች ኦሮሞ ባልሆኑ ማህበረሰቦች ላይ በታጠቁ የኦሮሞ ጽንፈኛ ሀይሎች የዘር ማጥፍትና ማጥራት ወንጀል ተካሂዶል አሁንም እንደ ቀጠለ ነው፡፡ በአንድ አገር ውስጥ በሚፈጠር ጦርነት ሆነ በግጭት ወቅት የመከራና የችግሩ ገፈት ቀማሽ ተጠቂዎች በአብዘሀኛው ሴቶችና ልጆች ናቸው፡፡ ዛሪም እጅግ በርካታ ኢትዮጵያውያን ሴቶች በገዛ አገራቸው ተሰደዋል፣ ተፈናቅለዋል፣ በአሰቃቂ ሁኔታ ተግድለዋል። ነፈሰ ጡሮችና ህጻናት ቤታቸው በላያቸው ላይ ፈርሶና ተቃጥሎ መንገድ ላይ ወድቀዋል፤ በርካታ ሴቶች ተደፍረዋል፣ ጭካኔ ለተሞላበ ኢሰባአዊ ጥቃት ተዳርገዋል። አማራ በመሆናቸው ብቻ በደንቢ ደሎ፣ ወለጋ ከፈለ ሀገር በኦሮሞ ታጣቂ ወንበዴዎች ለብዙ ወራት የታገቱት ወጣት ሴቶችን ለማስፍታት የአብይ አህመድ አስተዳደር ጉልበት የለውም ወይም ጆሮ ዳባ በማለት በተዘዋዋሪ ያስጠቃል። ለሚፈልገውና በሚፈልግበት ጊዜ ግን ወንጀለኞችን ያዝኩ ይላል፣ የታገቱት ወጣት ሴቶች የት እንዳሉ ማወቅም ሆነ ወንጀለኞችን መያዝ ግን ተሰኖታል። ወንጀለኞች እንድ ልብ ህዝብን ሲገድሉ፣ ስያሸብሩና ሲዘርፉ አይቶ እንዳላየ የሚያልፈው የአብይ አህመድ አስተዳደር፣ እውነትኛ የህዝብ ወገን የሆኑትን አገር ወዳድ የፖሊቲካ መሪዎችና ታጋዮችን፣ ያለምንም ወንጀል በጅምላ ማሰርና ማንገላታት ላይ ግን በሰፊው በብርቱ ተሰማርቶል። ስለዚህም የአለም አቀፍ የኢትዮጵያ ሴቶች ድርጅት ስለ ኢትዮጵያውን ወገኖቻችን በአጠቃላይ፣ በተለይ አማራ በመሆናችው ስለ ታገቱት ሴቶችን ልጆቻችን ዝም አንልም እንላለን፡፡ በማህበረሰብ መቃወስ፣ በህዝብ መፈናቀል፣ ሞትና ትርምስ ለፖለቲካ ትርፍ የሚጠቀሙ መንግስትም ሆነ መንግስታዊ ያልሆኑ የፖለቲካ ሃይሎች በስውርም በግልጽም የጥፋት ተባብሪ ስለሆኑ ለሚደርሰውም ጉዳት ተጠያቂ ያደርጋቸዋል፣ ከህዝብ እልቂትና ስቃይ በተጨማሪ የኢትዮጵያ አገራዊ ሉኦላዊነትና አንድነትን የሚያሰጋ አደጋ ሊከሰት የሚያስችል አጋጣሚን ይፈጥራልና፡፡ የአብይ አህመድ መንግስት ይህን ውስብስብ ችግር ለመፍታትም ሆነ የዜጎችን ደህንነት፣ የአገርን ሰላም ለማስጠበቅ አሁን በያዘው መንገድ አለመቻሉን ሆነ አለመፈለጉን፣ (ከከንቱ ወዳሴና ሃሳዊ ጮሌነት ባሻገር) በተድጋጋሚ ላልፉት ሁለት አመታት አሳይቶል፡፡ ይህን አለመገንዘብና ተገቢውን አለማድረግ በተለይ ለአገርና ወገን የሚያስቡ ምሁራን፣ የሰብዊ መብት ተቆርቆሪዎችና የፖለቲካ ደርጀቶች፣ በአሁኑ ወቅት በእውነት ጎን ባለመቆማቸው በህዝብ ላይ ለሚደርሰው በደልና ሞት ታሪክ ወደፊት ተጠያቂ ያደርጋቸዋል። ጽንፋዊ ልዩነትንና ጥላቻን ባነገቡ የኦሮሞ የጎሳ ሃይሎች ሰላማዊ ህዝብ ለጥቃት ሲዳረግ መንግስት ነኝ የሚል ሃይል በሰበብ ባስባቡ ማስጠቃት እንጂ አስፈላጊውን ጥበቃ ስለማያደርግ በተደጋጋሚ እንደታየው፤የኢትዮጵያ ህዝብ ባጠቃላይ፣ የአማራ ህዝብ በተለይ ለዘመናት ባካበትው የአብሮነት ጥበብ በመጠቀም የራሱን ደህንነት የመጠበቅና ኢትዮጵያን በትንንሽ የጎሳ አገሮች ለመበታተን፣ እንዲሁም ህዘቦንም በቁጥር እንዲቀነስ ለሚፈልጉ ሀይሎች ሰለባ ላለመሆን አስፈላጊውን ማድረግ ታሪካዊ ኢትዮጵያዊና ሰብአዊ ሃላፊነት አለብን። ስለዚህም የአለም አቀፍ የኢትዮጵያ ሴቶች ድርጅት ህዝባችንን ከበለጠ እልቂትና የእርስ በርስ ግጭት ለማዳን በጊዜ አሰፈላጊውን ትብብር ሁሉ እንዳረግ ዘንድ ወገናዊ ጥሪ ለአገር ወዳድ ኢትዮጵያዊ ሁሉ እናቃርባለን። ዛሪ ህዝብን ለዚህ ሰቆቃ የዳረገው ዋናው የችግሩ መንሳኤ የወያኔ/ኦነግ/ኢህድግ/ብልጽገና ድርጅቶች የታነጹበትና የሚመሩበት ጸረ ኢትዮጵያ ህገ መንግስትና ፖሊሲ ነው፡፡ ስለዚህም ለዘለቄታው ይህን የጎሳ ክልል ስርአትና ህገ መንግስትን ኢትዮጵያዊነትን መሰረት ባደረገ ህገ መንግስት በመተካት ህዝብን በአንድነት፣ በእኩልነት በፍትህ የሚያስተዳድር መንግስት መመስረት አገርንና ህዝብን ከጥፋት ያድናል፣ ይህ ላጭር ጊዜ ሆነ ለረጅም ጊዜ መፍትሄ ይሆናል። ይህ እስኪሆን ግን የጎሳ መለያ ሰባዊነትን ሰለሚያጠፋና ጭካኔን ስለሚያጠናክር የጎሳ መታወቂያን ማስወገድ ወሳኝ ቁልፍ ተግባራዊ ትግል ነው ብለን እናማናለን፤ ከጎሳዊ ወደ አገራዊና ህዝባዊ መንግስት መሸጋገር ፖለቲካዊ ትክክልኝነት ብቻ ሳይሆን በጎሳ ማንነት ምክንያት ሚከሰትውን ጥፋትና እልቂት ማስወገድና መከላከል ስለሚይስችል ይህን አማራጭ ተግባራዊ ለማድረግ በአጽኖት እንዲታሰብበት ለሚመልከታቸው ሁሉ ጥሪ እናደርጋለን። ለብዙ ወራት የአማራ ወጣት ተማሪዎች ልጆቻችን በኦሮሞ አካባቢ በታጠቁ ዘረኛ ሀይሎች መታፈናቸው ያስቆጣን መሆኑን እያሳወቅን በአስቸኮይ እንዲለቀቁ አጥብቀን እንጠይቃለን። ሰለልጆቻችን ደህንነት አጥጋቢ ምላሽ እስኪገኝ በአብይ መንግስትና በተባብሪውች ላይ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊና ዲፕሎማሳዊ ማእቀብ እንዲደርግ በድጋሚ የትብብር ጥሪ እናቀርባለን። ለሚደረሰው የአእምሮና የአካል ጉዳት፣ጥፋትና ቀውስ መንግስትም ሆነ ሌሎች ወንጅለኞችን ተጣያቂ እናደርጋለን። ህዝቡን፣ ማሳደድ፣ ማዋከብ፣ ማሰር እንዲቆምና በግፍ የታፈኑና በጅምላ የታሰሩት ንፁሀን ዜጎች፣ የተቃዋሚ ድርጅት መሪዎችና አባላት፣ እነ ወ/ሮ አስቴር ስዩም፣ አቶ እስክንድር ነጋ፣ አቶ ስንታየሁ ቸኮል፣ ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት፣ አቶ ልደቱ አያሌውና ሌሎች በርካት በብዙ ሺ የሚቆጠሩ የአዲስ አበባ ኖዋሪዎችን ባስቸኮይ እንዲፈቱ እንጠይቃለን፡፡ በአንጻሩ በሰላምዊ ህዝብ ላይ በደል ያሚያደርሱትን ወንጀለኞች፣ ኢትዮጵያዊ ቅርሶችን በማውደምና በጭፍጨፋ ተግባር በቀጥታ ሆነ በተዘዋሪ የታሳተፉትን የመከላከያና የልዩ ሃይልን፣ እንዲሁም ሌሎች የታጠቁ ጸረ ህዝብ ሃይሎችን በህግ እንዲጠየቁ እናሳስባለን። ጥያቄዎቻችን በአግባቡና በአስቸኳይ እስኪመለሱ ማንኛውንም የሰላማዊ ትግል በመጠቀም በመንግስትና በሚመለከታቸው ተባብሪውች፣ የፖለቲካና የንግድ ተቆማት ላይ የማህበራዊ፣ ኢኮኖሚና፤ ዲፕሎማሳዊ ማቀብና ዓድማ እንዲደረግ ከወዲሁ የትብብር ጥሪያችንነ ለኢትዮጵያውያን በሙሉ እናስተላለፋለን። በአጠቃላይ በኢትዮጵያውያን ሴቶች ላይ የሚደርሰውን የፖለቲካና የኢኮኖሚ እንዲሁም የጾታ ጭቆናንና ጥቃትን አጥብቀን እናወግዛለን፤ በተለይም በአማራ ሴቶች ላይ በየጊዜው ከሚደርሰው ግፍና መከራ ተጨማሪ ለልዩ የዘር ማጥፋት ጥቃት ሰለባ ሆነዋል፣ እንዳይወልዱ የማምከን ወንጀል ተካሂዶባቸዋል። የኢትዮጵያ እናቶች መከርና ለቅሶ ይቁም እያለን በሴትነታቸው ምክንያት የሚደርሰባቸውን ጉዳት ለማስወገድ፣ መብታቸውን ለማስጠበቅ ማደራጀትና ማጠናከር አለም አቀፍ የኢትዮጵያ ሴቶች ድርጅት ወቅቱ የሚጠይቀው አስፈላጊ የጋራ ተግባር ነው እንላለን።
የአረብ ሊግ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ትላንት ካይሮ ላይ ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን በተመለከተ ግብጽን በመደገፍ ያወጣውን የውሳኔ ሃሳብ ሙሉ ለሙሉ እንደማይቀበለው የኢትዮጵያ መንግሥት አስታወቀ። የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በጉዳዩ ላይ ባወጣው መግለጫ እንዳለው ሊጉ በግድቡ ዙሪያ እየተደረገ ያለውን ድርድር ቁልፍ እውነታዎችን ሳያገናዝብ በውሳኔ ሃሳቡ የሰጠው ጭፍን ድጋፍ እንዳሳዘነው አመልክቷል። የህዳሴ ግድብ ድርድሮች ላይ አቅጣጫ ለማስቀመጥ ውይይት ተካሄደ ኢትዮጵያ፤ የአሜሪካንን መግለጫ ተከትሎ ብሔራዊ ጥቅሜን አሳልፌ አልሰጥም አለች መግለጫው በተጨማሪም የውሳኔ ሃሳቡን እንደማትቀበል አሳውቃለች የተባለችውን የሱዳንን አቋም ያደነቀ ሲሆን፤ ከግድቡ አንጻር በተቀነባበረው የአረብ ሊግ አቋም ላይ "ሱዳን በድጋሚ ለምክንያታዊነትና ለፍትህ ያላትን አቋም አሳይታለች" ሲል አወድሷታል። የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤቱ እንዳለው ኢትዮጵያ ለረጅም ጊዜ ይዛው የቆየችውን "የአሁኑንና የመጪውን ትውልድ ፍላጎት ለማሟላት የአባይ ውሃ ሃብቷን የመጠቀም መብቷን" ታስከብራለች። አባይ ድንበር ተሻጋሪ ወንዝ እንደመሆኑ ውሃውን ከሚጋሩ አገራት ጋር በመተባበር መርህ ጉልህ የሆነ ጉዳት በማያደርስ ሁኔታ ፍትሃዊና ተቀባይነት ባለው መንገድ መጠቀምን ትደግፋለች። በተጨማሪም በግልጽ በሚደረግ ውይይት ሁሉንም የሚጠቅም ስምምነት ላይ መድረስ እንደሚቻል ኢትዮጵያ እንደምታምን መግለጫው አመልክቷል። የበላይነት ለመያዝ የሚደረግ ጥረት ውጤት የማያመጣ ከመሆኑ በተጨማሪ አሁን ባለው አገራት እርስ በርስ ተሳስረው በሚኖሩበት ዘመን ቦታ የለውም ሲል የጋራ ተጠቃሚነትን አስፈላጊነት ጠቅሷል። ግድቡን በውሃ ለመሙላትና የውሃ አለቃቀቅን በተመለከተ መሰረት ለሆነውና ቀደም ሲል ለተደረሰው የመርህ ድንጋጌ ስምምነት ኢትዮጵያ ተገዢ መሆኗን እንደምታረጋግጥና በዚህ ስምምነትም የመጀመሪያ ደረጃ የግድቡ የውሃ ሙሌት ከግድቡ የግንባታ ሂደት ጋር ጎን ለጎን ይካሄዳል እንደሚልም መግለጫው አመልክቷል። የህዳሴው ግድብ ድርድር ትኩረቱን ስቶ የውሃ ድርሻ ክፍፍል ላይ ሆኗል ተባለ በህዳሴ ግድብ ላይ የአሜሪካ እና የዓለም ባንክ ሚና እልባት ሊያገኝ እንደሚገባ መንግሥት አስታወቀ በመጨረሻም መግለጫው የአረብ ሊግ ከኢትዮጵያ ጋር ለረጅም ዘመናት በነበረው ግንኙነትና የጋራ ዕሴቶች አንጻር ከእውነት ጋር እንደሚቆም እምነት እንዳለው ጠቅሶ ወደፊትም ለጋራ ግብ በቅርበት ለመስራት እንደሚፈልግ ገልጿል። በተያያዘ ዜና ከታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ አንጻር አገራዊ ክብርን አሳልፎ የሚስጥ ስምምነት ውስጥ መንግሥታቸው እንደማይገባ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ ትናንት መናገራቸው ተዘግቦ ነበር። የብልፅግና ፓርቲ የአመራሮች ሥልጠና ማጠቃለያ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባስተላለፉት መልዕክት "ከውጭ ለምናገኘው ሀብት ብለን አገራዊ ክብራችንን አሳልፈን አንሰጥም" ብለዋል። ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይም በመልዕክታቸው ግድቡ የሌሎችንም ሀገራት ጥቅምን በማይጋፋ መልኩ አጠናቀን ጥቅም ላይ እናውለዋልን ሲሉም አምልክተዋል። ጨምረውም "ምንም እንኳ ቀደም ብለን ማጠናቀቅ ቢኖርብንም፤ በባለፈው ሳንቆጭ የያዝነውን ሳንለቅ ግድቡን አጠናቀን የህዝባችንን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ መስራት ያስፈልጋል" ብለዋል። የአሜሪካ የገንዘብ ሚኒስትር ባለፈው ቅዳሜ ያወጡት መግለጫ ከኢትዮጵያ ባለስልጣናትና ከህዝቡ ጠንካራ ተቃውሞ የገጠመው ሲሆን በሂደቱ የአሜሪካ ገለልተኝነት ላይ ከተለያዩ ወገኖች ጥያቄን አስነስቷ። የአሜሪካ መግለጫ የድርድር ሰነዱ ሳይፈረም በዚህ ዓመት መገባደጃ ላይ ይጀመራል ይተባለው የውሃ ሙሌት ሥራ መካሄድ እንደሌለበት በአጽንኦት ቢያስቀምጥም ኢትዮጵያ በዚህ እንደማትስማማ አሳውቃለች።
FILE - Displaced Tigrayan women, one wearing an Ethiopian Orthodox Christian cross, sit in a metal shack to eat food donated by local residents at a reception center for the internally displaced in Mekele, in the Tigray region of northern Ethiopia, on May አጋሩ በትግራይ ለህጻናትና ሴቶች የሚታለደው የእህል ክምችት በቀጣይ ሳምንት እንደሚያልቅ የዓለም ምግብ ድርጅት አስታወቀ share Print በሰሜን ኢትዮጵያ በግጭቱ መባባስ የዓለም ምግብ ድርጅት ተሽከርካሪዎች ካለፈው ታህሳስ ወር አጋማሽ ጀምሮ መቀሌ መድረስ ያልቻሉ መሆኑን ድርጅቱ በመግለጫ አመልክቷል፡፡ የኢትዮጵያ የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ትላንት ባወጣው መግለጫ የኢትዮጵያ መንግሥት ለትግራይ ክልል ህዝብ የዕለት ደራሽ እርዳታ ያለ ምንም መስተጓጎል እንዲቀርብ ለማስቻል በየጊዜው ከአጋር አካላት ጋር ምክክር በማድረግ እየሠራ ይገኛል ብሏል፡፡ የምግብ ድርጅቱ በትግራይ 2.1 ሚሊዮን በአማራ 650ሺ እንዲሁም በአፋር 534ሺ ሰዎች ዘንድ የምግብ እርዳታ ለማድረስ ያቀደ መሆኑን አስታውቋል፡፡ ይሁን እንጂ ከሚቀጥለው ወር ጀምሮ በገንዘብ እጥረት ሳቢያ በሚቀጥለው ወር በሁሉም የሰሜን ኢትዮጵያ አካባቢዎች የምግብና እርዳታ ሊኖረው እንደማይችል አስታውቋል፡፡ በመሆኑም የ337 ሚሊዮን ዶላር የገንዘብ እርዳታ የጠየቀ ሲሆን በሶማሊያ ድርቅ ለተጎዱ 170 ሚሊዮን ጠይቋል፡፡
አሜሪካ የባድመ ጉዳይ ሁለቱ አገሮች ቀደም ሲል በ2008 የድንበር ኮሚሽኑ ውሳኔ በደረሱበት ስምምነት መሰረት ተግባራዊ እንዲሆን ስታሳስብ መቆየቷንና ሁለቱ አገሮች ይህንኑ ተግባራዊ እንዲያደርጉ ጥሪ ማሰማቷን አስታወቀች። “ባለፉት ጥቂት ሳምንታት አብዛኞቻችሁ ባድሜን አመልክቶ አሜሪካ (ያላት ወይም የያዘችው አቋም ለማለት ነው) ፖሊሲ ምን እንደሆነ ስትጠይቁን ነበር” ይላል የአሜሪካ መንግስት አስመራ በሚገኘው ኤምባሲው ኢፊሳል የማህበራዊ ገጽ ላይ ያሰፈረው ጽሁፍ። ከግራ ይመልከቱ። በአጭር መልዕክት በግልጽ የተቀመጠው ጽሁፍ አስከትሎ “በ2002 የኤርትራና ኢትዮጵያ የድንበር ኮሚሽን ባድሜና ተጓዳኝ አወዛጋቢ አካባቢዎችን ለኤርትራ ሰጠ” ሲል የቀደመውን ውሳኔ ያስታወሳል። ይህ ውሳኔ ሲወሰን ነብሳቸውን ይማረውና የወቅቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የነበሩት አቶ ስዩም መስፍን ነብሳቸውን ይማረውና ጥቁር ክራባት አስረው ” ባድመ ለኢትዮጵያ ተወሰነች” የሚል ዲስኩር በአገሪቱ ብሄራዊ ቴሌቪዥን አሰምተው ነበር። በቀጣይም ድፍን የአዲስ አበባ ነዋሪ መስቀል አደባባይ በመውጣት በደስታ እንዲጨፍር ተደርጎ ነበር። ሁኔታው ያስገረማቸው ሃሰት እንደሆነ ውሳኔውን አያይዘው ሲገልጹና የትህነግን ቅሌት ሲያጋልጡ ” ጸረ …” ተብለውም ነበር። ተቀማጭነቱ አመራ የሆነው የአሜሪካ ኤምባሲ “… በ2018 የሰላም ስምምነት የኤርትራና ኢትዮጵያ የድንበር ኮሚሽን ውሳኔን ተግባራዊ ለማድረግ ቁርጠኛ ናቸው” ብሏል። አያይዞም ” ዩናይትድ ስቴትስ ሁለቱ ሀገራት ይህን ለማድረግ ሁሉንም አስፈላጊ ቀሪ እርምጃዎች እንዲወስዱ አሳስባለች” ሲል በርካቶች ላቀረቡት ጥያቄ የአሜሪካንን አቋም ይፋ አድርጓል። ፕሬዚዳንት ኢሳያስን አስወግዶ የኤርትራን ደጋማ ስፍራ በመጠቅለል አሰብን የመውረስ፣ ምጽዋን የመጋራት ዓላማ ይዞ እንደሚንቀሳቀስ በተደጋጋሚ ሲያስታውቅ የነበረው ትህነግ ለዚህ የአሜሪካ ምላሽ ይህ እስከተጻፈ ድረስ የሰጠው ምላሽ የለም። ለውጡ ይፋ ከመሆኑንና የትግራይ ነጻ አውጪ ግንባር ወደ ትግራይ ጠቅልሎ ከመግባቱ በፊት በኢህአዴግ ደረጃ የአልጀርሱን ውሳኔ በመቀበል ሰላም እንዲሰፍን መወሰኑ ይታወሳል። ይህም ውሳኔ በራሱ በኢህሃዴግ አማካይነት ለህዝብ ከለውጡ በፊት ተገልጾም ነበር። ለውጡ የወለደው አዲሱ አመራር ወደ ሃላፊነት እንደመጣ ይህንኑ ውሳኔ ተከትሎ ትህነግ የተሳሳተ መረጃ ማሰራጨቱን በመጥቀስ በተወካዮች ምክር ቤት በይፋ ውሳኔው ቀድሞ የተወሰነ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማስረጃ አቅርበው፣ውሳኔው ሲወሰን የነበሩ መስክረው ጉዳይ መታለፉም ይታወሳል። በባድመ ጦርነት ከሰባ ሺህ እስከ ዘጠና ሺህ ህይወት የገበረው የትህነግ አስተዳደር ፣ አዋቂዎች ለክርከር ይዞ የቀረበው ሰነድ እንደማይጠቅመው እየተነገረው አልጀርስ ሄዶ ያልተወሰነልትን ” ተውሰነልኝ” በማለት ማታለሉ “የመንግስትነት ክብርን የማይመጥን፣ የዱርዬ ስብሰብ፣ የአንድን አገር ብሄራዊ መገናኛዎች የውሸት መፈልፈያ ያደረገ፣ ትውልዱን ቅጥፈት ያስተማረ … ” በሚል በተከታታይ በውጭ የሚኖሩና አገር ቤት ሆነው የደፈሩ ሞግተውታል። የትግራይን ሕዝብ ከጎረቤቶቹ ጋር በሰላም ተፋቅሮ እንደቀድሞ እንዳይኖር፣ ራሱ ሕዝቡም ጠላት እንደከበበው እንዲያስብ በማድረግ የገፋበት ትህነግ፣ በመቶ ሺህ ሰዎችን ያስፈጀበት ጦርነት ብቻ ሳይሆን፣ ይህንኑ ጦርነት በድል የቋጩትን፣ ድንበር ላይ ሆነው ለሃያ ሁለት ዓመታት ሲጠብቁ የነበሩትን የአገር መከላከያ ሰራዊት አባላት ጾታና እድሜ ሳይመርጥ በክህደት ያጠቃበት መሆኑ በታሪክ ከባድመ ጋር የሚመዘገብ ሆኗል።
ተመስገን የአንድ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን መጋቢ ነው። አንድ ቀን አንዲት የኳየር ዘማሪ የሆነች ወጣት ወደ እርሱ መጥታ ማርገዟን ገለጸችለት። ተመስገን በነገሩ በጣም ተናደደ። «የቤተ ክርስቲያናችንን ስም ያጠፋሽ ኃጢአተኛ ሴት ነሽ። እኛ እንዳንቺ ዓይነቷን ሴት አንፈልግም» አላት። ልጅትዋ በኃፍረት ተሸማቅቃ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ወጥታ ሄደች። ክርስቲያን የነበሩት ወላጆቿም በእርግዝናዋ ስላፈሩ ከቤታቸው ለቅቃ እንድትሄድ አስገደዷት። መሄጃ ስፍራ ስላጣች በጎዳና ላይ ትንከራተት ጀመር። ከዚያም ለራሷና ለልጇ የመተዳደሪያ ገንዘብ ለማግኘት ስትል እምነቷን ትታ ወደ ሴተኛ አዳሪነት ገባች። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ዮሐ 8፡1-11 አንብብ። ኢየሱስ ለሴቲቱ ያደረገውን፥ ተመስገን ለኳየር ዘማሪዋ ካደረገው ጋር አነጻጽር። የሰዎቹ ተግባር የሚለያዩት ወይም የሚመሳሰሉት እንዴት ነው? ለ) ለኳየር ዘማሪዋ ክርስቶስ ምን ዓይነት ምላሽ የሚሰጣት ይመስልሃል? ሐ) እንደ ተመስገን ዓይነት መጋቢዎች እንደዚህ ዓይነት ሁኔታ ሊገጥማቸው ምን እንዲያደርጉ ትመክራቸዋለህ? በኃጢአት ላይ ያለህን ጥብቅ አቋም ሳትለውጥ፥ ምሕረትን፥ ይቅርታንና ፍቅርን የምታሳየው እንዴት ነው? ብዙ ምሑራን ዮሐንስ 7፡53-8፡11 ያለው ክፍል የዮሐንስ ወንጌል የመጀመሪያ ቅጅ አካል ነው ብለው አያምኑም። በርካታ የዮሐንስ ወንጌል የጥንት ቅጆች ይህን ክፍል አይጨምሩም። ይህን ክፍል ብንዘለው ታሪኩ ከ7፡52 ወደ 8፡12 ምንም ሳይደናቀፍ ይቀጥላል። ይህም በመገናኛው ድንኳን በዓል ጊዜ የተነገረ አሳብ ነው። ይህ የአመንዝራይቱ ሴት ታሪክ ለምን በዚህ ስፍራ እንደገባ ባናውቅም፥ ፈሪሳውያን ክርስቶስን ለማጥመድ በሚፈልጉበት ጊዜ የተከሰተ እውነተኛ ታሪክ ሳይሆን አይቀርም። አንድ ቀን ክርስቶስ በቤተ መቅደስ እያስተማረ ሳለ፥ የሃይማኖት መሪዎች በምንዝር የተያዘች ሴት አስከትለው ደረሱ። ይህንንም ያደረጉት ክርስቶስን ለማጥመድ አስበው ነበር። በሴቲቱ ላይ ባይፈርድ፥ በዝሙት የተያዙ ሰዎች ተወግረው መሞት እንዳለባቸው የሚያዘውን የብሉይ ኪዳን ሕግ በመተላለፉ (ዘዳግ 22፡22-24፤ ዘሌዋ 20፡10) ሊከሱት ሆነ። ባንጻሩ በሴቲቱ ላይ በመፍረድ እንድትወገር ቢያደርግ፥ የብዙ ሰዎችን ወዳጅነት ያጣ ነበር። በተለይም ይከተሉት የነበሩትን «የኃጢአተኞችና የቀራጮችን» ወዳጅነት ያጣ ነበር። ሮማውያን፥ አይሁዶች የሞት ቅጣት እንዲበይኑ አይፈቅዱላቸውም፡፡ ስለሆነም፥ ሴቲቱ ተወግራ እንድትሞት ቢያደርግ ኖሮ የሮም መንግሥት ይቀጣው ነበር፡፡ እነዚህ ፈሪሳውያን የእግዚአብሔር ሕዝብ ጻድቃን ሆነው እንዲኖሩ ከልባቸው የማይፈልጉ መሆናቸው ግልጽ ነው። የሙሴ ሕግ የተሰጠው ግን ሕዝቡ በጽድቅ እንዲኖር ለመርዳት ነበር። አለዚያ ከሴቲቱ ጋር ዝሙት የፈጸመውንም ሰውዩ በያዙት ነበር። በእግዚአብሔር ፊት፣ ዝሙትን መፈጸም ለወንድም ሆነ ለሴት ኃጢአት ነው። ወንዱ ሰውዬ የት ነበር? አንዳንዶች ወንዱ ሰውዩ ከፈሪሳውያን አንዱና ክርስቶስን ለማጥመድ ሲል ሴቲቱን የተጠቀመ ነው ይላሉ። የሚወገሩት ዝሙት ሲፈጽሙ የተገኙት ብቻ በመሆናቸው፥ ቢያንስ ፈሪሳውያን ሰውየውን ያውቁት ነበር። መሪዎቹ ምንም ዓይነት ርኅራኄ አልነበራቸውም። አለዚያ ክርስቶስን ሰው ወደሌለበት ስፍራ ወስደው ስለ ሴቲቱ ጉዳይ ሊያማክሩት ይችሉ ነበር። ሴቲቱ በትዕቢተኛ ሃይማኖተኞች መካከል የተገኘች መሣሪያ ነበረች። በመጀመሪያ ክርስቶስ ምንም አልተናገረም። ነገር ግን በመሬት ላይ አንድ ነገር ይጽፍ ጀመር። ምን ይሆን የጻፈው? ከሴቲቱ ጋር ዝሙት የፈጸመውን ሰውዩ ስም ይሆን የጻፈው? ሴቲቱን ለመውገር የቆሙትን ፈሪሳውያን ኃጢአት ይሆን የዘረዘረው? ምንም የምናውቀው ነገር የለም። ከዚያም ኃጢአት ሠርቶ የማያውቅ ሰው፥ በሴቲቱ ላይ የመጀመሪያውን ድንጋይ እንዲወረውር ጠየቃቸው። ይህን በማለቱ ክርስቶስ የብሉይ ኪዳንን ሕግ እየደገፈ ነበር። ነገር ቀን ኃጢአት ሠርቶ የማያውቅ ሰው እንዲወግራት በመጠየቁ ማንም ሰው እንዳይወግራት እየተከላከለላት ነበር። ከዚህም በተጨማሪ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ዘንድ ትልቅ ስፍራ ያለው ምሕረትና ይቅርታ እንጂ፥ በትምክህት የተሞላ ፍርድ እንዳልሆነ እያስተማራቸው ነበር። ከዚያም ኢየሱስ መሬት ላይ ተመልሶ ይጽፍ ጀመር። የጻፈው ነገር መሪዎቹን ስላሳፈራቸው አካባቢውን ጥለው ሄዱ። ሴቲቱ ብቻ በክርስቶስ አጠገብ እንደ ቆመች ቀረች። ክርስቶስ የፍቅር አምላክ እንደ መሆኑ፥ ለዚህች ኃፍረት ላሸማቀቃት ሴትት የፍቅር እጁን ዘረጋላት። በተጨማሪም፥ እግዚአብሔር ኃጢአትን ዝም ብሎ የማያልፍ ቅዱስ አምላክ ነው። ይህች ሴት አጥፍታለች። ምን ይባላት? በመጀመሪያ፥ ክርስቶስ ሊፈርድባት አልፈለገም። ሁለተኛ፥ በኃጢአት እንድትቀጥልም አልፈለገም። ስለሆነም፥ ሕይወቷን እንድትለውጥ ነገራት። እንደ ክርስቶስ እኛም ኃጢአተኞችን መውደድና መቀበል አለብን። ይህ ማለት ግን ከኃጢአት ሕይወታቸው ጋር እንስማማለን ማለት አይደለም። በሕይወታቸውና በእምነታቸው እግዚአብሔርን ያከብሩ ዘንድ የንጽሕናን ሕይወት እንዲኖሩ መርዳት አለብን። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ትልቅ ኃጢአት ፈጽመዋል በሚባሉ ሰዎች ላይ ክርስቲያኖች የሚናገሩት የትምክህት ቃል ምንድን ነው? ለ) አንዳንድ ጊዜ ሰዎች የኃጢአት ልምምዳቸውን እንዲተዉ ሳንወቅሳቸው፥ በደፈናው የምናልፋቸው አንዳንድ መንገዶች ምንድን ናቸው? ሐ) ክርስቶስ በምድር ላይ ቢሆን ኖሮ ከነዚህ ሰዎች ጋር ምን ዓይነት ግንኙነት የሚያደርግ ይመስልሃል? (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)
ከ25 ዓመታት በፊት አንድ የኮሌጅ ዲፕሎማ የነበረው አስተማሪ ሲቀጠር የመነሻ ደመወዙ 347 ብር ነበር። ይህን ገቢ በወቅቱ ከነበረው የዶላር ምንዛሬ አንጻር ስናየው 173.5 ዶላር ይመዝን ነበር። ይህ አስተማሪ ገና ሲቀጠር የቀን ገቢው 5.8 ዶላር ነበር ማለት ነው። ከፍ ያለ ነበር። ከ25 አመት “እድገት” በሁዋላ በህወሃት ኢህዓዴግ ዘመን አንድ የኮሌጅ አስተማሪ ዲፕሎማውን ይዞ ሲቀጠር 1663 ብር ቢከፈለው አሁን ባለው ምንዛሬ ሲታይ 77.3 ዶላር ያገኛል። ይህ ማለት የቀን ገቢው በዶላር 2.57 ሳንቲም ነው ማለት ነው። ይህ ማለት የደርግ ጊዜው አስተማሪ ደመወዝ ከህወሃት ኢህዓዴግ ጊዜ አስተማሪው ደመወዝ ከሁለት እጥፍ በላይ ይበልጣል ማለት ነው። በዓለም አቀፍ ደረጃ የድህነት ወለል የሚባለው ሁለት ዶላር አካባቢ ሲሆን ይህ በህወሃት ኢሃዴግ ዘመን የኮሌጅ ዲፕሎማ የያዘው አስተማሪ በዚያው በድህነት ወለል አካባቢ ነው ማለት ነው። ነገር ግን በደርጉ ጊዜ ከሃያ ዓምስት ዓመት በፊት የነበረው ዲፕሎማ አስተማሪ በቀን የሚያገኘው ገቢ ወደ 6 ዶላር የሚጠጋ ሲሆን እጅግ በተሻለ ህይወት ውስጥ የነበረ በዓለም አቀፍ የገቢ መለኪያም የተሻለ ገቢ የነበረው ነበረ። በአሁኑ ሰዓት አንድ የሁለተኛ ደረጃ አስተማሪ ሲቀጠር 2197 ብር የሚያገኝ ሲሆን ይህ ማለት 102 ዶላር ማለት ነው። ይህ መምህር በቀን 3.40 ሳንቲም የሚያገኝ ሲሆን በደርግ ጊዜ ዲፕሎማው ወደ 6 ዶላር የሚጠጋ በቀን ያገኝ ስለነበር በደርጉ ጊዜ የነበረ ያ ጀማሪ የዲፕሎማ መምህር የዛሬውን የዲግሪውን መምህር ክፍያ በጅጉ ይበልጠዋል። በዚህ ቀላል መንገድም ሆነ በፈለገው የኢኮኖሚክ ሞዴል ብናሰላው በህወሃት ኢህአዴግ ጊዜ ያለው ሲቪል ሰራተኛ ገቢ ከደርጉ ጊዜ መምህር በጅጉ ወርዶ እናያለን። በደርግ ጊዜ አንድ የሁለተኛ ደረጃ አስተማሪ ሲቀጠር የቀን ገቢው ወደ ዘጠኝ ዶላር የሚጠጋ ሲሆን በአሁኑ ጊዜ የሚቀጠረው መምህር 3.40 ሳንቲም ብቻ በመሆኑ ልዮነቱን ማየት ይቻላል። የነዚህን የሁለት ዘመናት መምህራን ለማወዳደር አንዱ ሌላው ነገር ደግሞ የግሽበትን (inflation) ጉዳይ አንስተን ነው። በደርግ ጊዜ ያ 347 ብር ያገኝ የነበረ መምህር አንድ ዳቦ በአስር ሳንቲም ይገዛ ነበር፣ አንድ እንቁላል በአስር ሳንቲም ይገዛ ነበር። አሁን 1663 ብር የሚያገኘው ደግሞ አንድ ዳቦ በአማካይ አንድ ብር ከሃምሳ ሳንቲም ቢገዛ አንድ እንቁላል ሶስት ብር ይገዛል። በሃያ አምስት ዓመታት እንቁላል የ3000% ጭማሪ ሲያሳይ ዳቦ በ1500% ጨምሯል። የመምህሩ ገቢ ደግሞ የዋጋውን ግሽበት የሚፎካከር ሆኖ አያድግም። ደመወዝ ደግሞ አራት መቶ ፐርሰንት ገደማ ብቻ ነው ያደገው። ለናሙና በጠቀስናቸው እንቁላልና ዳቦ የዋጋ ጭማሪ ጋር የደመወዙ ጭማሪ ሲወዳደር ከፍተኛ ክፍተት (gap) የሚያሳይ ሲሆን ይህ ክፍተት ነው የመምህሩን ትዳር የማሸነፍ አቅም መድከም የሚያሳየው። ዳቦና ደመወዝ ሲወዳደሩ ዳቦ በአንድ ሺህ ፐርሰንት ቀድሟል። እንቁላልና ደመወዝ ሲወዳደሩ እንቁላል ከሁለት ሺህ አምስት መቶ ፐርሰንት በላይ ቀድሞ ሄዷል። እናም የዛሬው መምህር ቁርሱን እንቁላል በዳቦ ለመብላት ይሄን ያህል ደክሟል ማለት ሲሆን በአንጻሩ የደርጉ ጊዜ መምህር በየቀኑ ያለ አሳብ መመገብ ይችላል። የደርጉ ጊዜ መምህራን በተለይ በገጠሩ አካባቢ ህብረተሰቡ ቤት ይሰጣቸው ስለነበር የቤት ኪራይ አያስቡም። ከተማም ቢሆን የቤት ኪራይ ኑሯቸውን የሚፈታተን ባለመሆኑ ከቁም ነገር አይቆጥሩትም ነበር። የህወሃት ኢሃዴግ ጊዜ አስተማሪ በተለይ በከተሞች አካባቢ የሚኖረው ኑሮ ምን ያህል እንደሚከብደው መገመት አያዳግትም። በደርጉ ጊዜ የነበሩ መምህራን ደመወዛቸው ከኑሮው ጋር ከዓለም አቀፍ የድህነት ወለል አንጻር ከፍ ያሉ ስለነበሩ ለቤተሰብ አምሳም፣ መቶም ብር ከዚያም በላይ ተቆራጭ አድርገው ይጦሩ ነበር። የህወሃት ኢሃዴግ ጊዜ አስተማሪ ለቤተሰቡ ተቆራጭ አድርጎ መርዳቱ ቀርቶ እሱ ራሱን ችሎ መኖር ከብዶት ይታያል። አሁን የመምህሩን ኑሮ ከደርግና ከአሁኑ ጋር እያወዳደርኩ የምገልጸው ለናሙና እንጂ አጠቃላይ የሲቪል ሰራተኛው ኑሮ በዚህ ችግር የሚገለጽ ነው። የኢትዮጵያ ሲቪል ሰራተኛ ባለፉት ሃያ አምስት አመታት በዚህ መንግስት በጣም የተጎዳና ሲታለል የኖረ ነው። ያሳዝናል። ኑሮ እንዲህ ቁልቁል ሲሆን ገቢ እንዲህ ቁልቁል ሲሆን … እውነተኛ ፓርላማ ቢኖር ይህ ጉዳይ ከባድ አገራዊ ጉዳይ ሆኖ ክርክር ሊደረግበት መፍትሄ ሊሰጠው ይገባ ነበር። እዚህ ጋር አንድ የሚነሳ ነገር ይኖራል። የመምህሩ ደመወዝ ከደርግ ጊዜው ጋር ሲነጻጸር በአሃዝ ጨምሯል። ነገር ግን በዶላር ሲሰላ ደግሞ እየቀነሰ መጥቷል፣ ከግሽበቱ ጋር ሲሰላ ደግሞ ከዛሬ ሃያ አምስት አመት ከነበረው ጋር ሲታይ አስደንጋጭ ለውጥ አለ ይህ እንዴት ሊሆን ቻለ? ልንል እንችላለን። በመጀመሪያ ደረጀ የኢትዮጵያ መንግስት ደመወዝ የሚጨምርበትን ስልት ማወቅ አለብን። የኢትዮጵያ መንግስት ደመወዝ የሚጨምረው አገሪቱ ስላደገች አይደለም። ጭማሪው ሃገሪቱ የተሻለ አምርታ ያ ምርት ወደታች መንቆርቆር ስለጀመረ አይደለም። ጭማሪው የምርት (GDP) መጨመር ያመጣው ሳይሆን መንግስት የሆነ ዘመን ላይ የህዝቡን የተቃውሞ ስሜት ያይና ይህንን ተቃውሞ የሚያበርድበትን መንገድ ያስባል። እናም ለደመወዝ ጭማሪው ሲል ብቻ ገንዘብ በገፍ ያትማል። በመሰረቱ የአንድ ሃገር የገንዘብ ህትመት መጠን የሚወሰነው በሃገሪቱ አጠቃላይ ምርት (GDP) መጠን ነው። ገንዝብ ማለትም የአንድን ሃገር ጠቅላላ ምርት ወይም GDPን የምናካፍልበት መሳሪያ ነው እንጂ በራሱ ወረቀት ነው። መንግስት ለዚህ ብዙ ግድ የለውም። ታዲያ መንግስት ገንዘብ በገፍ ያትምና ለጊዜው ለሰራተኛው ከፍ ያለ ቁጥር በማሳየት የሲቪሉን ሰራተኛ አፍ ለመያዝ ይሞክራል። ነገር ግን የቁጥሩ ጭማሪ እድገትና ብዙ ምርት ገፍቶት የመጣ ባለመሆኑ መንግስት ደመወዝ በጨመረ በማግስቱ ሁሉ ነገር ይጨምራል። ኑሮ ውድነቱ ሰማይ ይደርሳል። ለምን ይሄ ሆነ ስንል ከፍ ሲል እንዳልነው ጭማሪው በህትመት ላይ ያተኮረ እንጂ የሃገር እድገት ውጤት ባለመሆኑ ነው። የተመረተው ምርት በሃገሪቱ ከታተመው ገንዘብ ጋር ስለማይመጣጠን ብሮች ይጋሽባሉ። ዋጋ ያጣሉ ማለት ነው። ስለዚህ የኢትዮጵያ የሲቪል ሰራተኛውን ደመወዝ ጉዳይ ስናይ የሰራተኛው ሪል ገቢ አየቀነሰ ይሄዳል እንጂ እየጨመረ አይሄድም። የጨመረው ከላይ የምናየው ቁጥሩ ሲሆን ከግሽበት አንጻር ሲሰላ ግን ከደርጉ ጊዜ መምህር የአሁኑ መምህር ገቢ በጣም ቀንሷል። እንዲህ እየሆነ ነው ላለፉት ሃያ አምስት አመታት የኖረው። ህወሃት ኢሃዴግ ስልጣን ከያዘ ወዲህ ደመወዝ ይጨመራል ነገር ግን ደመወዝ በተጨመረ ቁጥር የሰራተኛው ኑሮም ከአምናው ዘንድሮ እያቃተው የመጣበት ምስጢር መንግስት ቁጥር እያሳየ አንደኛ ገቢው በዶላር ሲሰላ እየወረደ ይሄዳል ሁለተኛውና ዋናው ጉዳይ ደግሞ ጭማሪው እድገት የገፋው ባለመሆኑ ከግሽበቱ ጋር ተፎካክሮ ሊቆም አልቻለም። አንዱ የምርት ውጤት ከህዝብ ብዛት ጋር ሳይጣጣም ቀርቶ የመጣው ችግር ሲሆን ሌላው ችግር ደግሞ ያለችውን ሃብት ወደ አንድ አቅጣጫ የማዛወር ስራ እየተሰራ ስለሆነ ነው። መንግስት ያለችውን ምርት ፍትሃዊ በሆነ መንገድ ሊያከፋፍል ቢችል አገሪቱ ይህን ያህል የሚያመረቃ እድገት ስላላሳየች አጥጋቢ ደመወዝ ባይገኝም ከደርግ ጊዜ ግን ሊቀንስ አይገባውም ነበር። ኢትዮጵያ በእርዳታ መቀበል ከሰሃራ በታች ካሉ አገራት ቀዳሚ ናት። በአሁኑ ሰዓትም የመንግስትን ባጀት ከ 50-60% የሚደርሰውን የሚሸፍነው ከተባበረችው አሜሪካ፣ ከአወሮፓ ህብረትና ከሌሎች ለጋሾች በሚገኝ ርዳታ ነው። ኢትዮጵያ በዓጼ ምኒሊክ ዘመን ራሷን የቻለች አገር የነበረች ሲሆን በአጼ ሃይለስላሴ ዘመንም የተሻለች የተከበረች አገር ነበረች። በደርግ ጊዜ በእርዳታ ላይ መደገፋችን ከፍ ብሎ የታየበት ዘመን ሲሆን ከእርዳታ የሚገኘው የመንግስት ባጀት ሽፋን ግን ዝቅተኛ ነበር። ደርግ በህይወት ዘመኑ ያገኘውን ርዳታ የአሁኑ መንግስት በአንድ አመት ጊዜ አግኝቶታል። በዚህ መንግስት ግን ከፍ ሲል እንደገለጽነው ከግማሽ አካላችን በላይ በርዳታ ላይ የተደገፍን ሲሆን ይህ ርዳታ ቢያቆም የሃገሪቱ መንግስት ሊፈታ ይችላል። ወደ ስራተኛው ደመወዝ እንመለስና ያለችውን ሃብትና እርዳታ በተገቢው መንገድ ስለማንካፈል ከደርጉ ጊዜ ሰራተኞች ኑሮ ያሁኑ ከእጥፍ በላይ ወድቋል:: ለዚህም ሌላው ምክንያት ደግሞ ለሰራተኛው የተወሰነ ቁጥር እያሳዩ በዘዴ የሃብት ዘረፋ እየተደረገ ስለሆነ ነው። ሲቪል ሰራተኛው በየዓመቱ እየደከመ የሚሄድበት ምስጢርም ከሰራተኛው ጉልበት ላይ እየቀነሱ የነ ኤፈርትን ሃብት እያደለቡ ስለሆነ ነው። ሲስተማቲክ የሃብት ዝውውር ይባላል ይህ አይነቱ ዘዴ። የህወሃት ካምፓኒዎች በጣም እያደጉ ሃብት እየጨመሩ ሲሄዱ ሰራተኛው ትንሽ የቁጥር ጨዋታ እያየ ነገር ግን ከአምናው ዘንድሮ ትዳር የማሸነፍ አቅሙ እየወረደ ያለው በዘዴ የጉልበት ዋጋ ዝውውር እየተደረገ ስለሆነ ነውና ሲቪል ሰራተኛው ለመብቱ ሊታገል ይገባዋል። ዋናው ነገር መንግስት አስር ጊዜ በኢኮኖሚ አደግን እያለ የሚለው ነግረን ነገር ተጽእኖው በሲቪሉ ሰራተኛ ላይ አይታይም። አይታይም ብቻ ሳይሆን ሰራተኛው በዘዴ እየተዘረፈ ድህነት እየጨመረ ነው የመጣው።ይሁን እንጂ የኢትዮጵያን የኢኮኖሚ እድገት ጉዳይ በተመለከተ በሌላው ዓለም ባልተለመደ ሁኔታ በሁለት ጎራዎች ከፍተኛ ክርክር ይታያል። ክርክሩ ኢትዮጵያ በያዘችው የእድገት አቅጣጫ ሳይንስ ላይ ሳይሆን እድገት በኢትዮጵያ አለ የለም በሚል ነው። ለዚህ ነው በሌላው ዓለም የተለመደ ክርክር አይደለም የሚያስብለን። መንግስትና ደጋፊዎቹ ሽንጣቸውን ገትረው ባለፉት ሃያ አመታት በተለይም ባለፉት አስር አመትታ ከፍተኛ እድገት አሳይተናል፣ እድገቱ ደግሞ በፍጥነቱ ከዓለም ከፍተኛ ደረጃ ይዟል፣ ከአፍሪካ አንደኛ ነን እነ ጋና፣ ሞሪሺየስ፣ አንጎላ ሁሉ እኛ ያሳየነውን ፈጣን እድገት አላሳዩም የሚል ነው። በጥንድ ቁጥር ነው ያደግነው የሚል ነው። ይህን የሚቃወመው ሰፋ ያለው ማህበረሰብ ደግሞ አንዳንዴ ያፌዝበታል አንዳንዱ ደግሞ ከመንግስት ሰዎች ጋር ሸንጡን ገትሮ ይከራከራል። ክርክሩን አስደማሚ የሚያደርገው በራሱ እድገት አለ የለም የሚለው ነገር መከራከሪያ መሆኑ ነው። ልክ እድገት የማይጨበጥ የማይዳሰስ ይመስል ክርክሩ መነሳቱ አስደማሚ ነው። በሌላ በኩል ደግሞ ትንሽ ምክንያታዊ መሆን የፈለጉ ወገኖች እድገትና ልማት የሚሉትን ጽንሰ ሃሳቦች ይከፋፍሉናል በኢትዮጵያ ውስጥ እድገት አለ ነገር ግን ልማት የለም የሚል ነው። የኢኮኖሚ ባለሙያዎች እድገት የሚለውን አሳብ የሚገልጹት ጠበብ አድርገው ነው። እድገት ማለት የGDP ጭመራ ማለት ነው በአጭሩ። በየዓመቱ GDP ከጨመረ የኢኮኖሚ እድገት ታየ ለማለት ያስችላቸዋል። በሌላ በኩል ደግሞ የኢኮኖሚ ልማት ሲሉ በአብዛኛው ተቀባይነት ያለው አሳብ ልማት ማለት ልክ እንደ ኢኮኖሚ እድገት በቀላሉ የሚለካም አይደለም። ሰፋ ያለ ጽንሰ ሃሳብ ሲሆን ዋናው ጉዳይ ግን ያ አለ የተባለው የኢኮኖሚ እድገት ያመጣቸውን ተጽእኖዎች የሚመለከት ነው። ተጽእኖው ከሚገለጽባቸውን ጉልህ ጉዳዮች ደግሞ በአብዛኛው HDI (Human Development IndeX) በመባል የሚታወቀውን መለኪያ ያካትታል። ይህ ማለት በአንድ ፖለቲካ ጠገግ ውስጥ ያሉ ዜጎች በሶስት ዋና ዋና አቅጣጫ (Dimension) ለውጥ ሲያሳዩ ማለት ነው። እነዚህ ጉዳዮች አንደኛ ረጅም እድሜ (long and healthy life) ሁለተኛ የእውቀት የትምህርት ልማት ሶስተኛ የኑሮ ደረጃ (A decent standard of living ) ናቸው። የኢኮኖሚ እድገት ሲባል እንግዲህ የሃገሪቱ እድገት በነዚህ አቅጣጫዎች የዜጎችን ህይወት ሲቀይር ነው ማለት ነው። ዞሮ ዞሮ የኢኮኖሚ እድገት ወይም የ GDP ጭምራ አላማ በዚህ ዓለም ላይ ለሰው ልጆች እድገትን ለማምጣት በመሆኑ ብዙ ጊዜ ስለ ሃገር እድገት ሲነሳ የ GDP ጭመራው ብቻ ሳይሆን HDI መሻሻልን ይመለከታል። የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድግጅቶችና አብዛኛው ድሃ የሚባለው ህዝብ ብዙ ጊዜ እድገትን ከHDI ጋር እንዲያያዝለት ይፈልጋል። ስለሆነም በአንድ አገር ውስጥ አንድ መንግስት የኢኮኖሚ እድገት ማምጣቱን እንደ ድል አድርጎ ቢጨፍር አብዛኛውን ህዝብ አያስደምመውም። አብዛኛው ህዝብ የሚደሰተው ያ እድገት በHDI ላይ ተጽእኖው ሲያርፍ ነው። ወደ ኢትዮጵያ ወቅታዊ ጉዳይ እንመለስና መንግስት ከፍተኛ እድገት አስመዝግቢያለሁ ይላል። ነገር ግን ከፍ ሲል እንዳየነው እድገቱ በሲቪል ሰራተኛው ላይ አይታይም። ሰራተኛው ባለበት እንኳን ሳይቆም ከግሽበቱ አንጻር ገቢው ከደርግ ጊዜው መምህር በጣም ቀንሷል:: ይሁን እንጂ መንግስት አድጊያለሁ ይላል። እድገት ብቻ ሳይሆን ልማትም ታይቷል፣ የገበሬው ህይወት ተቀይሯል፣ የሰራተኛው ህይወት ተቀይሯል፣ የማህበራዊ አገልግሎት ተሻሽሏል ባይ ነው። ይሁን እንጂ አንዳንድ መንግስትን ከፍጹም ተጠያቂነት በተወሰነ ደረጃ ሊያተርፉት የሚሹ አካላት እድገት አለ ነገር ግን ልማታዊ ያልሆነ እድገት ነው ያለው ይላሉ። ይሁን እንጂ አብዛኛው ህዝብ ይህ ክርክር አንጀቱ ጠብ አይልም። ዋናው ጉዳይም ይሄ አይደለም። ይልቅ ፍትሃዊው ጥያቄ መንግስት እድገት አለ ከአፍሪካም ከዓለምም አንደኛ ወጥተናል ካለ እሺ በጣም ጎበዝ ደስ ይለናል በል እንግዲህ ያንን እድገት በገበታችን በገቢያችን ላይ አሳየን፣ በማህበራዊ ተቋምት አቅርቦት ስፋት አሳየን የሚለው ጥያቄ ሚዛን ይደፋል። በመጀመሪያ ግን አንድ የኢኮኖሚ ባለሙያ እንዳሉት መንግስት እድገት አለ ሲል እድገቱ ከየት እንደመጣ ይጠየቃል። ከመንግስት አካላት ውስጥ የሚሰሙ ካሉ ይመልከቱት:: መንግስት የሚለው ለዚህ እድገት ግዙፉን ድርሻ የተሸከመው ግብርናው ነው። ግብርና መር ፖሊሲ እንዳለው የሚናገረው መንግስት ግብርናችን አገራችንን በጥንድ ቁጥር አሻግሯል የሚል ነው። እዚህ ላይ ታዲያ አጥብቆ ጠያቂዎች ጠይቀውታል። ለመሆኑ ግብርናው ሃገሪቱን ለአስር አመት ዝንፍ ሳይል እንዲህ ለማሳደግ የሚችለው እንዴት ነው? ቢያንስ በግብርናው መሪነት ከፍተኛ ለውጥን ለማሳየት የሚከተሉት ጉዳዮች መገምገም አለባቸው። አንደኛው ገበሬው ዘምኗል ማለት ነው። የጎልማሶች ትምህርት ተሻሽሎ ገበሬው ቴክኖሎጂዎችን የመቀበል አቅሙ ዳብራል ማለት ነው። ከትምህርት የተነሳ ኢኖቬቲቭ ሆኗል ማለት ነው። ሁለተኛ ብዙ ያልታረሱ ለም መሬቶች ታርሰዋል ማለት ነው። ምርት ይጨምር ዘንድ አንዱ ነገር ገበሬው እርሻውን ማስፋት ችሏል ማለት ነው።የመስኖ ልማት ተስፋፍቷል ማለት ነው። ሶስተኛ የአፈርና ውሃ ጥበቃ ስራው ተሻሽሎ የመሬቱ ለምነት ጨምሯል ማለት ነው አራተኛ ከፍተኛ የሆነ የእርሻ ግብዓት፣ እንደ ዩሪያ፣ ዳፕ፣ ምርጥ ዘር፣ ፔስት ሳይድ፣ የምርት መሳሪያዎችን ተጠቅሟል ማለት ነው። አምስተኛ የግብርና ምርት ውጤት ኤክስፖርት በጣም አድጓል ማለት ነው። እነዚህን ነጥቦች ስንገመግም በርግጥ ግብርናው ይህን ጥንድ ቁጥር እድገት አምጥቷል ወይ የሚለውን መላምት እውነትነት ያረጋግጥልናል። በአጭሩ ለማየት ያህል የጎልማሶች ትምህርትን በተመለከተ በደርጉ ጊዜ ተጀምሮ የነበረው የመሰረተ ትምህርት ፕሮግራም በዚህ መንግስት በመደምሰሱ ማንበብና መጻፍ የጀመሩ ጎልማሶች 60% ደርሶ የነበረው በአሁኑ ጊዜ መጻፍና ማንበብ ጀምረው የነበሩ ሁሉ ወደ መሃይምነት ተመልሰው ወደ 37.5% ዝቅ ብሏል። ይሄ በዓለም አልታየም:: በዚህ በኩል መንግስት ገበሬውን አክስሮታል እንጂ አላተረፈም ስለዚህ ዘመናዊ ትምህርት በዚህ እድገት ውስጥ ሚናው አይታይም። በርግጥ የልማት ሰራተኞችና የግብርና ባለሙያዎች ገበሬውን በሙያ ለማገዝ ይጥራሉ ይሁን እንጂ ባለመማሩ ቴክኖሎጂን በቀላሉ በመቀበሉ ላይና በፈጠራ አቅሙ ላይ ጉልህ ሚና ይጫወት የነበረው ትምህርት አላደገምና በዚህ በኩል ለዚህ እድገት ትምህርት አስተዋጾው የለም ማለት ነው። ሁለተኛው ጉዳይ ደግሞ ምርት ሊያድግ የሚችለው በርግጥ የገበሬው ይዞታ ተስፋፍቶ ያልታረሱ መሬቶች ታርሰው ከሆነ ነው። የሃገሪቱን ዋና ዋና ምርት በተመለከተ ከ90% በላይ የሚሆነውን ምርት የሚያመርተው ገበሬ በአማካይ አንድ ሄክታር መሬት የሚያርሰው ገበሬ ነው። ታዲያ እጅግ ብዙውን የሚያመርተው ያ አንድ ሄክታር የሚያርሰው ገበሬ ከሆነና ይህ ገበሬ ደግሞ መሬት መሸጥም ሆነ መግዛት ስለማይችል መሬቱ አይሰፋም አይጠብምና እንዴት ሆኖ ነው ምርት በከፍተኛ ሁኔታ የሚጨምረው። በርግጥ በቆላው አካባቢ ሰፋፊ ለም መሬቶች ታርሰዋል። ነገር ግን ከባለፈው አስር ዓመት ጊዜ ጀምሮ እጅግ ለም የሆኑ መሬቶችን መንግስት ለመሬት ነጣቂዎች በመስጠቱ እነዚህ መሬቶች ታረሱ ማለት የሃገሪቱን ምርት ሊያሳድጉ ነው ማለት አይቻልም። ስለሆነም ያን ያህል ከባድ ለውጥ ለማምጣት የሚያስችል እርሻ በአነስተኛ ያዡ ገበሬ ዘንድ ስላልሰፋ ያን ያህል ምርት ተመረተ ለማለት አይቻልም። በግብርና ኤክስፖርቶቻችን ዘንድ ብዙ የምንደገፍ ሲሆን ቡና፣ የቅባት እህሎች፣ አትክልትና ፍራፍሬ፣ የእንስሳት ውጤቶች ተደማምረው ወደ ሶስት ቢሊዮን ዶላር ነው የምናገኘው። የሚያሳዝነው መንግስት ራሱ ወደብ አልባ ያደረጋት ኢትዮጵያ ይህቺን ለፍታ ጥራ የላከቻትን የግብርና ምርት ገቢ መልሳ ለወደብ ትከፍላለች። እዚያው ወደብ ላይ የውጭ ንግዳችን ይቀራል። ጂቡቲ ከፍተኛውን ድርሻ ስትይዝ፣ ሱዳን፣ ሶማሌላንድና ኬንያም ትንሽ ትንሽ ይካፈሉናል። ገማቾች እንደሚሉት ለጂቡቲ ብቻ ወደ ሁለት ቢሊዮን ዶላር ለወደብ እንከፍላለን። ይህ ደግሞ በልማት ላይ ከባድ ተጽእኖ አለው። የማዳበሪያና የእርሻ ግብዓቶችን ጉዳይ ስናይ ደግሞ ፍላጎቱ የጨመረ ቢሆንም ያን ያህል ከባድ ለውጥን ሊያመጣ የሚችል እድገት እንዳላሳየ ባለሙያዎች ይገልጻሉ። በሌላ በኩል በየዓመቱ ሁለት ቢሊዮን ሜትሪክቶን ለም አፈር እየታጠበ የሚሄድባት አገር በመሆኗ እርሻው የሃገሪቱን ኢኮኖሚ ለመለወጥ ጉልበት ያንሰዋል:: ሃገሪቱ የመስኖ ልማትን ችላ ያለች በመሆኗ ዝናብ ላይ ብቻ ጥገኛ በሆነ ግብርና ይሄን ያህል እድገት ማምጣት አይቻልም። አስር በመቶ የሚሆነውን እንኳን በመስኖ ማልማት ያልቻለ መንግስት ግብርናው አደገ ማለት ተቀባይነት የለውም። ኢትዮጵያ ከብዙ ሃገራት የተሻለ የዝናብ መጠን በዓመት በዓማካይ ብታገኝም ስርጭቱ ችግር ስላለበት ማለትም አንዳንዴ በሃይል ይወርድና መሬቱን ይሸረሸራል፣ አንዳንዴ በቂ ዝናብ አይዘንብምና የግድ በከርሰ ምድርና በመስኖ ካልተደገፈ ግብርናው የሃገሪቱን ኢኮኖሚ ማሳደግ ቀርቶ ጎታች ነው የሚሆነው። የእስንሳት ሃብታችንን ስናይ ምንም እንኳን በቁጥር ከአፍሪካ አንደኛ ብንሆንም ነገር ግን የተሻሻለ መኖ ባለመኖሩና ርባታው ባለማደጉ በግብርናው ላይ ይሄ ነው የሚባል ጉልህ ተጽእኖ አያመጣም። በአጠቃላይ የግብርናውን ጓዳ ጎድጓዳ ስናይ ይሄን ያህል አመርቂ የሆነ ውጤት ከግብርናው ሊገኝ የሚያስችል ሁኔታ የለም። ከፍ ሲል እንዳልነው ዘጠና ዘባት በመቶ የሆነውን ሰብል የሚያመርተው ገበሬ መሬቱ አይሰፋም አይጠብም። አይሸጥም አይገዛምና ይህ በሆነበት አገር ምርት የሚፈለገውን ያህል ሊጨምር አይችልም። መንግስት ኢንዱስትሪው ነው ይህን ለውጥ ያመጣው ብሎ ስላልተከራከረ ብዙ ማለት አያስፈልግም። ኢንዱስትሪውና ማንፋክቸሪንጉ ያለው አስተዋጾ ገና ስላላደገ አምስት በመቶ የሚሆን አስተዋጾ እንኳን ስለሌለው ይህ ጥንድ ቁጥር እድገት ከዚያ አካባቢም እንዳልመጣ ይታወቃል። ሰርቪስ ሴክተሩ ከግብርናው ቀጥሎ የሃገሪቱን ኢኮኖሚ የተሸከመ ቢሆንም ይህም በሃጋሪቱ ውስጥ አሁን የሚነገረውን ጥንድ ቁጥር ያለው እድገት ለማምጣት አይችልም። በመሆኑም ይህ እድገት ከየት መጣ? ተብሎ መንግስት ቢጠየቅ ምላሽ አይኖረውም። በጣም ሲበሳጭ እድገት ማሳያ ብሎ የሚገልጸው አንዱ የመንገዶች ስራና ከተሞች አካባቢ ያሉ የኢንፍራስትራክቸር ለውጦችን ነው። በርግጥ የሚታዩ እነዚህ መንገዶችና ህንጻዎች ከዚህ ከጥንድ ቁጥሩ ጋር በተያያዘ የመጡ እድገቶች አይደሉም። ይህ የሚታየው መንገድ ስራ በአብዛኛው በእርዳታና በብድር የሚሰራ ነው። አንጻራዊ በሆነ መንገድ የማህበራዊ ተቋማት ግንባታዎች ቢታዩም በአብዛኛው ከብድርና እርዳታ ጋር የተገናኙ ናቸው እንጂ የእድገቱ ውጤቶች አይደሉም። ገና ኢትዮጵያ የዛሬ ሰላሳ አርባ አመት የምትከፍለው የብድር እዳ ነው። መቼም ስለ እድገት ስናወራ ስለ ኢኮኖሚ ልማት ማንሳት የግድ ነውና መንግስት በኢኮኖሚ ልማት በኩልም ተሳክቶልኛል ይበል እንጂ ከእድገቱ ባለ ድርሻ ሊሆን የሚገባው ሰፊ የሆነው ገበሬ ይህ የጥንድ ቁጥር እድገት አርሶታል ወይ? ካልን ችግሩ ደግሞ በገበሬው ይብሳል። ከፍ ሲል እንዳልኩት ገበሬው የመሬት ባለቤት ባለመሆኑ ከይዞታው አይፈናፈንም። ይዞታው አይጨምርም። የገጠመው ችግር ምንድን ነው? ልጆች ይወልድና ሲደርሱ ይሻሙታል። ያቺኑ መሬት ስድስት ቤተሰብ ይዞ ይኖራል። ኑሮው ከእጅ ወደ አፍ ብቻ ይሆንበታል። አንዳንዴም ከዚያች ቁራጭ መሬት ላይ የሚያገኘው እህል አመቱን ሙሉ ስለማይመግበው እርዳታን ጠባቂ ይሆናል። ከሁለት እስከ አራት ወር በዓመት ርዳታን ይፈልጋል። በመሆኑም የገበሬው ኑሩ ዛሬ ከመቼውም የበለጠ ከፍቷል። እንደ ድሮው ልጁን ትምህርት ቤት ልኮ ልጁ ኮሌጅ በጥሶ ደመወዝ ቆርጦ ይጦረኛል የሚል ተስፋ የለውም። አስተማሪው ልጁ እንኳን አባትና እናቱን ሊረዳ ራሱንም ትዳር ያንገዳግደው ይዟል። አብዛኛው ገበሬ በተለይ በደጋ ያለው ኑሮው ከድጡ ወደ ማጡ ሆኗል።አንዱ ለዚህ ችግር የዳረገን ነገር በርግጥ የህዝብ ብዛትም ነው። መንግስት በቤተሰብ እቅድ ረገድ የሰራው ስራ የለም። ይህ መንግስት ስልጣን ከያዘ ወዲህ ባለፉት ሃያ አምስት አመታት ብቻ የኢትዮጵያ ህዝብ በሃምሳ አምስት ሚሊዮን ጨምሯል። የሚገርመው ነገር በዚህ ሃያ አምስት አመት የመጨመረው ህዝብ ብዛት የአፍሪካን የአስራ አምስት አገራትን ህዝብ ተደምሮ ያክላል። እነዚህ አሃገራት ሴራሊዩን፣ ሊቢያ፣ ማእከላዊ የአፍሪካ ሪፐብሊክ፣ የኮንጎ ሪፐብሊክ፣ ሞሪታኒያ፣ ናሚቢያ፣ ቦትስዋና፣ ጋምቢያ፣ ኢኳቶሪያል ጊኒ፣ ሌሴቶ፣ ጋቦን፣ ጊኒ ቢሻው፣ ሞሪሺየስ፣ ስዋዚላንድ ናቸው። የነዚህ ሃገራት ህዝብ በሙሉ ተደምሮ ወያኔ ከመጣ የጨመረውን የህዝብ ብዛት ያክላል። የነዚህ አገሮች የቆዳ ስፋት ተደምሮ የኢትዮጵያን አምስት ጊዜ ያክላል። የሰው መብዛት በአንድ በኩል ሃይል ቢሆንም ነገር ግን በዚህ የመሬት ፖሊሲ በታሰረች አገርና በብሄር ፌደራሊዝም በተኮለኮለች አገር እንዲሁም ኢኮኖሚው ከህዝብ ብዛቱ ጋር አብሮ በማያድግበት አገር ህዝቡን ለድሃነት የሚያጋልጥ ነገር ነው። በአጠቃላይ የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ እድገት ስናይ መንግስት በጥንድ ቁጥር እያደግን ነው ቢልም ይህ እድገት ግን በዘዴ ሲቪሉን ሰራተኛ ደሙን እየመጠጠ ያለ ነው። ሰፊውን ገበሬ ደሙን እየመጠጠ ያለ ነው። አነስተኛ የሆኑ ነጋዴዎች ከህወሃት የንግድ ድርጅቶች ጋር መወዳደር ስለማይችሉ የነሱንም ደም የመጠጠ ነው። መንግስት ይህንን ያፈጠጠ እውነት ምንም ሊያደርገው አይችልም። እጅግ ብዙ ድሃዎችን እያፈሩ፣ የሲቪል ሰራተኛውን ጉልበት እየሰረቁና ሃብት በዘዴ እያዛወሩ አንድ የጠገበ ሃብታም ማፍራት እድገት አይደለም። ስለሆነም አሁን ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው የኢኮኖሚ ሁኔታ የሚታዩ ግንባታዎች ከሙስና የተራረፉ የብድርና የእርዳታ ውጤቶች ሲሆኑ ሌላው የሃገሪቱ ሃብት ግን እንደነ ኤፈርት አይነቶቹ የህወሃት ድርጅቶች ሰብስበውት ይታያል። በዚህ መሃል በጣም የተጎዳው ሲቪል ሰራተኛውና ገበሬው እንዲሁም ድሃው ነጋዴ ነውና ይህ የህብረተሰብ ክፍል ለለውጥ መነሳት ይኖርበታል። “ጎልጉል፡ የድረገጽ ጋዜጣ የሕዝብ” እንደመሆኑ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ ሥር የድርጅቶችና የማንኛውም ግለሰብ ነጻ ሃሳብ የሚስተናገድ ሲሆን ከአንባቢያን የሚላኩልን ጽሁፎች በጋዜጣው የአርትዖት (ኤዲቶሪያል) መመሪያ መሠረት ያለ መድልዖ በዚህ ዓምድ ሥር ይታተማሉ፡፡ ይህ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ በ“የኔ ሃሳብ (Opinion)” ዓምድ የታተመ ጽሁፍ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® አቋም ሳይሆን የጸሃፊው ነው፡፡
“የመድሀኒትና የጤና ጥበቃ ምርቶች ተቆጣጣሪ አገልግሎት፣ የኮቪድ-19 ክትባት ሙከራችን ላይ የሚያደርገውን ግምገማ ማፋጠን መጀመሩን እናረጋግጣለን ሲል፣ የአስታራዘኒካ ቃል አቀባይ ተናግሯል። የግምገማው ሂደት ሲፋጠን፣ ተቆጣጣሪዎቹ የክትባት መድሃኒቱን የማጽደቅ ሂድትን ለማፋጠን ሲሉ፣ ክትባቱ በተግባር ላይ ሲውል የመመልከትና ስለ ክትባቱ የአመራረት ሂደት የመመልከትና ከአምራቾቹ ጋር የመነጋገር ተግባር ያካሄዳሉ። አስቸኳይ የጤና ሁኔታ ሲኖር፣ የመድሃኒትነትና የክትባትነት ተስፋ ያለው ሁኔታ ሲፈጠር፣ ሂደቱ ከተለመደው በላይ እንዲፋጠን የሚጠቀሙበት ዘዴ መሆኑ ታውቋል። አስትራዘኒካና ፕፊዘር የኮሮናቫይረስ የክትባት መድሃኒት ለማግኘት በሚደረገው መረባረብ፣ የቅድሚያ ቦታ ከያዙት መካከል መሆናቸው ተገልጿል። ጆንሰን ኤንድ ጆንሰንና ሞደርና ኩባንያዎችም፣ የክትባት መድሃኒቱን ለመስራት እየተጣደፉ ከሚገኙት፣ የመድሃኒት ኩባንያዎች መካከል ናቸው። የብሪታንያው የመድሃኒት ኩባንያ፣ ዛሬ በተናገረው መሰርት፣ የኮቪድ-19ኙ የሙከራ ክትባት፣ በዕድሜ በገፉትና በወጣቶች ላይ የመከላከል ብቃት አሳይቷል። እስካሁን ባለው ጊዜ፣ በዓለም ደረጃ 1.19 ሚልዮን የሚሆኑ ሰዎች፣ በቫይረሱ ተይዘው ለሞት ተዳርገዋል። የሀገራትን ኢኮኖሚ አዳሽቋል። በቢልዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች የኑሮ ሁኔታን አተራምሷል።
ፅባሕ ቀዳም 24 ጥቅምቲ ዓለምለኸ መዓልቲ ፖሊዮ እዩ።ዋላ'ኳ ዕንቅፋትን ለበዳ ቫይረስኮሮናን እንተጋጠመ'ውን ዓለም ነዚ ኣብ ክልተ ሃገራት ጥራሕ ዝርከብ ዘልምስ ሕማም ንምጥፋእ ጉዕዝኡ ቀፂሉ ይርከብ። ኣብ ሓደ እዋን ፖሊዮ \ሕማም ኣልምሲ\ ኣብ ዓመት ንኣማኢት ኣሽሓት ህፃናት የልምስ ነይሩ። ኣብ ኣፍሪካ ጥራሕ ኣብ ነፍሲ ወከፍ 75,000 ቆልዑ የጥቅዕ ነይሩ። ሎሚ እቲ ጉዳይ ከምኡ ኣይኮነን። ካሮል ፓንዳክ ምስ ናይ ሮታሪ ኢንተርናሽናል ፖሊዮ ፕላስ ዝተባህለ ፕሮግራም ፖሊዮ ንምጥፋእ ንልዕሊ ዕስራዓመታት ዝሰርሓ እየን። "ፖሊዮ ካብ ዓለም ንምጥፋእ ብዘመዝገብናዮ ቀንዲ ዓወት ኣፍሪቃ ካብዚ ቫይረስ ፖሊዮ ነፃ ኮይና።" ዝማዕበላ ሃገራት ብክታበት ካብ ፖሊዮ ነፃ ዝወፃሉ ልዕሊ ሓምሳ ዓመት ኮይኑዎ ኣሎ።ኣብ 1988 ዓለምለኸ ተበግሶ ምጥፋእ ፖሊዮ ኣብ ምምዕባል ኣብ ዝርከባ ሃገራት ተመሳሳሊ ስራሕ ንምስራሕ ወሲኑ። ማእለያ ዘይብሉ ወለንተኛነት፣ብሓገዝ ብዙሓት ትካላት ረድኤት ዓለምለኸ መሪሕነት፣ከባቢያዊ መሪሕነት ብዙሕ ስራሕ ወሲዱ። ቫይረስ ፖሊዮ ሎሚ ኣብ ኣፍጋኒስታንን ፓኪስታንን ጥራሕ ይርከብ። ኣብቶም ዝሓለፉ ክልተ ዓመታት ብሰንኪ ህውከትን ግጭትን ሰባት ብምምዝባሎም ዝተመዛበሉ ሰባት ኣብ ዘዕቖብሉ ከባቢ ድማ ትሑት ኣገልግሎት ጥዕናን ጽሬትን ስለዘሎ ኣብ ክልቲአን ሃገራት እቲ ቫይረስ ዳግም ተላዒሉ። ኣብ ውድብ ጥዕና ዓለም ዞባ ምብራቓዊ ሜድትራኒያን ዳይረክተር ምጥፋእ ፖሊዮ ዝኾኑ ዶክተር ሓሚድ ሰይድ ጃፋሪ ብዙሓት ሰባት ኣብ ሓደ ከባቢ ተፃቢቦም ኣብዝነብርሉ እሞ ድማ እኹል ኣገልግሎት ጥዕናን ጽሬትን ኣብዘይብሉ ቫይረስ ፖሊዮ ክባዛሕ ጥጡሕ ባይታ ዝፈጥር እዩ ይብሉ። ኣብ ኣፍጋኒስታን ታሊባን ገዛ ንገዛ እናዘርካ ዝካየድ ናይ ክታበት ወፍሪ ኣይፈቅድን።እዚ ነቲ ስራሕ ከቢድ ከምዝገብሮ ካሮል ፓንዳክ ይገልፃ። ፖሊዮ ካብ ዓለም ንምጥፋእ ዝካየድ ወፍሪ ንምዕዋት ይቀራረብ ኣሎ።ዛጊት ዓብይ ስራሕ ተሰሪሑእቲ ሕማም ካብ ኣፈጋኒስታንን ፓኪስታንን እንተድኣ ተፀሪጉ ዘይጠፊኡ ብደረጃ ዓለም ዳግም ክባዛሕ እዩ።ቫይረስ ከመይ ክባዛሕ ከምዝኽእል ድማ ኮቪድ-19 ኣብነት እዩ። ዕለታዊ ፈነወ ድምጺ ኣመሪካ 26/11/2022 ፈነወ ትግርኛ ቀዳም ድምጺ ኣሜሪካ ፈነወ ቛንቛ ትግርኛ ካብ ሶኑይ ክሳብ ሰንበት ይፍነው። ፈነወ ቛንቛ ትግርኛ ካብ ሶኑይ ክሳብ ዓርቢ ብዕለታዊ ዜና ይጅምር፥ እዋናዊ ጉዳያትን ሰሙናዊ መደባት'ውን የጠቓልል ።ቀዳምን ሰንበትን ኣብቲ ሰሙን ዝተፈነው መደባት ብምድጋም ፈነወ ቛንቛ ትግርኛ ይኻየድ።
ከሳምንት በፊት የተጀመረው 33ኛው የአፍሪካ ዋንጫ በሁለተኛ ዙር የምድብ ጨዋታዎች ቀጥሏል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድንም ምድቡን የመጀመሪያ ጨዋታ ያደረገው በመክፈቻው ወቅት ሲሆን በኬፕቨርዴ 1ለ0 የተሸነፈበት ነው። በዚህ ጨዋታ ዋልያዎቹ ተከላካዩ ያሬድ ባየህ በቀይ ካርድ ከሜዳ ከተሰናበተ በኋላ ከ70 ደቂቃዎች በላይ በ10 ተጨዋቾች ኬፕቨርዴን በኳስ ቁጥጥር የተወሰነ ብልጫ የነበረው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የረባ ሙከራ ባለማድረጉ አስፈላጊውን ነጥብ ይዞ መጨረስ አልቻለም። ከጨዋታው በኋላ ዋና አሰልጣኝ ውበቱ አባተ “የገጠምነው በአንጋፋ ተጨዋቾች ጥሩ ስብስብ ከነበረው የኬፕቨርዴ ቡድን ጋር ነው። የልምድ ማነስ ለሽንፈት ዳርጓል።” በማለት ለካፍ ኦንላይን አስተያየት ሰጥተዋል። ከጋዜጠኞች ጋር ባደረጉት ውይይት ደግሞ የአፍሪካ ዋንጫን መሳተፋችን ብቻ በቂ ነው ብለው የተናገሩ ሲሆን ከተጣለባቸው ሃላፊነት አንጻር መሳተፉ ብቻ እንደሚያረካ ቡድኑ ግን በሚያሳየው ብቃት ምርጥ 3ኛ ሆኖ የሚያልፍበት ዕድል መኖሩንም ጠቁመዋል። ከዚሁ ምድብ በመክፈቻው ጨዋታው ካሜሮን 2 ለ1 ቡርኪናፋሶን አሸንፋለች። በምድቡ ሁለተኛ ጨዋታ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ከአዘጋጇ ካሜሮን ጋር ተገናኝቶ 4 ለ1 ተሸንፏል። በዚሁ ጨዋታ ላይ በ4ኛው ደቂቃ ላይ ዳዋ ሁጤሳ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የመሪነት ጎሉን አስቆጥሮ ነበር። የካሜሮን ብሔራዊ ቡድን አጥቂው ካርል ቶኮምቢ እና አምበሉ ቪንሰንት አቡበከር እያንዳንዳቸው ሁለት ጎሎችን አስቆጥረው 4ለ1 አሸንፏል። በምድቡ ሁለተኛ ዙር ጨዋታ ደግሞ ቡርኪናፋሶ ኬፕቨርዴን 1ለ0 አሸንፋለች። ካሜሮን በ6 ነጥብና በ4 የግብ ክፍያ ወደ ጥሎ ማለፍ መሸጋገሯን ስታረጋግጥ ቡርኪናፋሶ እና ኬፕቨርዴ በእኩል 3 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዘዋል። የኢትዮጵያ ቡድን ያለምንም ነጥብ በ4 የግብ ዕዳ መጨረሻ ላይ ነው። ዋልያዎቹ በካሜሮን ከተሸነፉ በኋላ ዋና አሰልጣኝ ውበቱ አባተ ለካፍ ኦንላይን በሰጡት አስተያየት “ከካሜሮን ጋር ባደረግነው ጨዋታ በጥሩ ብቃት የምንችለውን ሁሉ አድርገናል። የመሪነቱን ግብ በጨዋታው መጀመሪያ ላይ ብናስቆጥርም ውጤቱን አስጠብቀን ለመቆየት አልቻልንም። በትልቅ ውድድሮች ላይ ትምህርት እየወሰድን ነው። በእኛና በካሜሮን መካከል በልምድ ደረጃ ሰፊ ልዩነት አለ። እያንዳንዱ ጨዋታ ደግሞ የየራሱ ባህርያት አሉት። ግጥሚያዎች የተለያዩ ቢሆኑም ያሉንን ችሎታዎች በማሳየት ጥሩ ኳስ ተጫውተናል” ብለዋል። በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝነት ከ473 ቀናት በላይ ያስቆጠሩት ውበቱ አባተ በ4 የወዳጅነት ጨዋታዎች፣ 4 የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ጨዋታዎች፣ 4 የዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ጨዋታዎችና 2 የአፍሪካ ዋናጫ ማጣሪያ ጨዋታዎችን አድርገዋል። በእነዚህ ውድድሮች 13 ብሄራዊ ቡድኖች ጋር ተገናኝተው በ6ቱ ሲያሸንፉ፤ በ3 አቻ ተለያይተው 7ጨዋታዎችን ተሸንፈዋል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የምድቡን የመጨረሻ ጨዋታ ሰኞ ከቡርኪናፋሶ ጋር ያደርጋል። ሁለቱ ቡድኖች በአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ጨዋታ ሲገናኙ ከ8 ዓመታት በኋላ ለ2ኛ ጊዜ በእግር ኳስ ታሪካቸው ደግሞ 4ኛ ጨዋታቸው ነው። በ2013 እ.ኤ.አ ላይ ደቡብ አፍሪካ ባስተናገደችው 29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ በተገናኙበት ወቅት ቡርኪናፋሶ 4ለ0 ማሸነፏ ይታወሳል። በሌላ በኩልሁለቱ ቡድኖች በ2000 እ.ኤ.አ ላይ በዓለም ዋንጫ ማጣሪያ በደርሶ መልስ ተገናኝተው ነበር። በመጀመሪያ ጨዋታ ኢትዮጵያ 2 ለ 1 ስትረታ በመልሱ ደግሞ ቡርኪናፋሶ 3 ለ 1 አሸንፋለች። በ2013 ደቡብ አፍሪካ ባስተናገደችው 29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ከ31 ዓመት በኋላ በአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎው ከምድ ማለፍ አልቻለም ነበር። በወቅቱ ዋልያዎቹ በመክፈቻው ጨዋታ ከዛምቢያ ጋር 1ለ1 አቻ ከተለያዩ በኋላ በቡርኪናፋሶ 4ለ0 እንዲሁም በናይጀሪያ 2ለ0 ተሸንፈው ከውድድሩ ውጭ በመሆን 14ኛ ደረጃ በመያዝ የአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፏቸወን አጠናቅቀዋል። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በ33ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎው በሁለቱ የምድብ ጨዋታዎች ኳስን ተቆጣጥሮ ለመጫወት ችሏል። ከኬፕቨርዴ ጋር 44% እንዲሁም ከካሜሮን ጋር 50% የኳስ ቁጥጥር ነበራቸው። ይሁንና በሁለቱም ጨዋታዎች ላይ በቡድኑ ላይ የተስተዋለው ትኩረት ማጣት፣ የመከላከል ችግርና የልምድ ማነስ ከተፎካካሪነት አውጥቶታል። ከኬፕቨርዴ ጋር በተደረገው ጨዋታ የቡድኑ አጨዋወት ቅጥ የሌለውና ወደ ግብ መድረስን ያላሰበ ነበር። ዋልያዎቹ የሚይዟቸውን ኳሶች ወደ ተቃራኒን ግብ ክልል ይዞ ከመግባት ወይም ወደ ግብ ከመሞከር ይልቅ በቅብብሎሽ ጊዜያቸውን ሲያባክኑ ነበር። በርካታ አጋጣሚዎች ላይም ኳሶቹን ያለአግባብ በመጠለዝም አበላሽተዋል። በምድቡ ሁለተኛ ጨዋታ ደግሞ ዋልያዎቹ በማራኪ ኳስ አጨዋወት በ4ኛው ደቂቃ ላይ ግብ ማስቆጠራቸው የሚያስደንቅ ቢሆንም በቀጣይ ውጤታቸውን ለማስጠበቅ እንደ ቡድን የፈጸሙት ተግባር የሚያረካ አልነበረም። ከአዘጋጇ የካሜሮን ቡድን ጋር 1ለ1 አቻ ሆነው ለእረፍት ወደ መልበሻ ክፍል ገብተዋል። ለ2ኛው ግማሽ ወደ ሜዳ ከተመለሱ በኋላ ግን የሚጠበቀውን መስዋእትነት ሊከፍሉ አልቻሉም። በጨዋታው ላይ በተጋጣሚያቸው እንቅስቃሴ ላይ ትኩረት አድርገው ባለመከላከላቸው ዋጋ አስከፍሏቸዋል። የማይበገሩት አንበሶች የኢትዮጵያን የተከላካይ መስመር ድክመት ባገናዘበ መልክ ጎሎችን አከታትለው በማስቆጠር ድል አድርገዋል። በ33ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ የኢትዮጵያ ቡድን ባደረጋቸው ሁለቱም የምድብ ጨዋታዎች ምርጥ ብቃቱን ያሳየው የግብ ጠባቂው ተክለማርያም ሻንቆ ነው። ከኬፕቨርዲ ጋር በተደረገው ጨዋታ ከ3 በላይ ግብ የሚሆኑ ኳሶችን ያዳነው ተክለማርያም፣ ከካሜሮን ጋር በተደረገው ጨዋታውም በተመሳሳይ ማራኪ ትኩረትን በማሳየት ዋልያዎቹን ከከባድ ሽንፈት ታድጓቸዋል። የካፍ ድረገጽ ባወጣው አሃዛዊ መረጃ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በአዘጋጅነት ከተሳተፈባቸው የአፍሪካ ዋንጫዎች ውጭ በሌሎች አገራት በተካሄዱ የአፍሪካ ዋንጫዎች ላይ በመሳተፍ ካደረጋቸው 18 ጨዋታዎች በ15 ጨዋታዎቹ ተሸንፎ በሁለቱ ጨዋታዎች አቻ ተለያይቷል። ከሜዳው ውጭ በአፍሪካ ዋንጫ በመሳተፍ ያሸነፈው ብቸኛ ግጥሚያ በ1963 እ.ኤ.አ ላይ ቱኒዚያን 4 ለ 2 የረታበት ነው። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የውጤት ታሪክን 11VS11 የተባለ ድረገጽ እንደተነተነው ከ1943 እ.ኤ.አ ወዲህ በአህጉራዊና በዓለም አቀፍ ውድድሮች ከ411 በላይ ጨዋታዎችን አድርጓል። 146 ጨዋታዎችን ሲያሸንፍ፣ በ84 አቻ ተለያይቶ በ171 ጨዋታዎች ተሸንፏል። የአፍሪካ ዋንጫው ሲጀመር ከ130 ሚሊዮን በላይ ኢትዮጵያውያን ትኩረታቸውን ወደ ብሄራዊ ቡድኑ ማድጋቸው ይታወቃል። ብዙዎቹ ደጋፊዎች ዋልያዎቹ ከምድባቸው ጥሩ ተፎካካሪ ሆነው በመገኘት ወደ ጥሎ ማለፍ ምዕራፍ መሸጋገራቸውን ጠብቀዋል። በብሔራዊ ቡድኑ የአፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎ የሚመዘገብ ውጤት የአገሪቱን አንድነት ያጠናክራል በሚልም ተስፋ ያደረጉ ጥቂት አልነበሩም። የዋልያዎቹ ስብስብ ከመላው አገሪቱ በተሰበሰቡ ተጨዋቾች እንደተገነባ ይታወቃል። ዋና አሰልጣኝ ውበቱ አባተ ለዶቼቬሌ በሰጠው ልዩ ቃለ ምልልስ በጉዳዩ ላይ ሲናገር “አንዳንዶች የፖለቲካ ችግሮችን ከቡድኑ ጋር ለማያያዝ ቢሞክሩም፤ እኛ ግን እንደዚያ አናስብም። ጥንካሬ ይሰማናል፤ ሁላችንም ኢትዮጵያውያን ነን። እዚህ የተገኘነው ኢትዮጵያን ለመወከል ነው” ብሏል። “አብረን ስንሆን ሁሉም በጋራ ይዘምራሉ። ተጨዋቾቹ በጋራ መዘመራቸው የኢትዮጵያን አንድነት ይወክላል” በማለትም ተጨማሪ አስተያየታቸውን ዋና አሰልጣኝ ውበቱ አባተ የገለጹ ሲሆን “አሁን በውድድር ላይ እንገኛለን። በብዙ ውጣውረዶች ውስጥ አልፈን ነው እዚህ የደረስነው። በአፍሪካ ዋንጫው ላይ መሳተፋችን በራሱ ትልቅ ድል ነው። በውድድሩ ላይ በመገኘታችን የኢትዮጵያን ገጽታ ለመገንባት ያስችለናል” በማለት ለጀመርመኑ የዜና አገልግሎት ዶቼቬሌ ተናግሯል። የቀድሞውን የብሔራዊ ቡድን አሰልጣኝና በአሁኑ ወቅት በእግር ኳስ ፌዴሬሽኑ ስራ አስፈጻሚ የሆኑት ኢንስትራክተር ሰውነት ቢሻውን በተመሳሳይ አጀንዳ ላይ ለዶቼቬሌ አስተያየት ሰጥተዋል። “ተጨዋቾች ኢትዮጵያን ሲወክሉ፣ ብሔራቸው ምንም አስፈላጊነት የለውም። ተጨዋቾች ለብሔርተኝነት ፍላጎት የላቸውም። ሁሌም ንግግራቸው ስለአንድነትና ቡድናቸውን የተሻለ ደረጃ ስለማድረስ ነው” በማለት።
ውድ የመቅረዝ ወዳጆች! እንዴት ዋላችኁ? እንዴት አረፈዳችኁ? እንኳን ለጾመ ነቢያት በሰላምና በጤና አደረሳችኁ፡፡ ዛሬም አባታችን ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እጅግ ጣፋጭ የኾነ ስብከቱን ቀጥሏል፡፡ የዛሬውን ስብከት የተረጐምንላችኁ የኦሪት ዘፍጥረትን እየተረጐመ ባስተማረው የአራተኛው ቀን ስብከቱ ነው፡፡ ምእመናኑ ወደ ጉባኤው መምጣታቸውን ቀጥለዋል፡፡ በየቀኑ ያስቀድሳሉ፤ በየቀኑ ይቈርባሉ፡፡ ቅዳሴውን ካስቀደሱና ከቅዱስ ቁርባኑ ከተሳተፉ በኋላም ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በሚያስተምራቸው ትምህርት ነፍሳቸውን መግበው ይሔዳሉ፡፡ ይኽን በየቀኑ እያየ አባታችን ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በጣም ይደሰታል፡፡ የምእመናኑ ትጋት እያየ ርሱም ማስተማሩን ቀጥሏል፡፡ በተለይ በሦስተኛው ቀን ዶፍ ዝናብ እየዘነበባቸው እንኳን ምእመናኑ አለመበተናቸውን አይቶ ቅዱሱን እጅግ በጣም አስደስቶታል፡፡ በመኾኑም በዛሬው ስብከቱ ይኽን የምእመናኑን ትጋት አይቶ ያስተማረው ትምህርት ነው፡፡ ምንም እንኳን ከዛሬ 1600 ዓመታት የተሰበከ ስብከት ቢኾንም ዛሬም አዲስ ነው፤ አይጠገብም፤ ነፍስን ይመልሳል፡፡ እስኪ እኔ ነገር ከማስረዝምባችኁ ከራሱ ከሊቁ አብረን እንማር፡፡ የነቢያትን፣ የሐዋርያትን፣ የሊቃውንትን ጉባኤ የባረከ አምላክ የእኛንም ይባርክልን፡፡ በያለንበት ኾነንም ቃሉን እንድንማር ልቡናችንን ይክፈትልን፡፡ አሜን!!! እጅግ የምወዳችኁ የእግዚአብሔር ቤተ ሰቦች! በታላቅ ትጋትና ጉጉት ኾናችኁ በየቀኑ ወደ ቤተ ክርስቲያን መምጣታችኁ እያየኹ ነፍሴ ደስ ተሰኘች፤ ዕለት ዕለትም አምላኬን ስለ እናንተ አመሰግነዋለኹ፡፡ ረሃብ የጤነኝነት ስሜት ነው፤ ቃለ እግዚአብሔርን ለመማር መጓጓትም በመንፈሳዊ ሕይወት ጤነኛ መኾናችንን የሚያመለክት ነው፡፡ ክብር ምስጋና ለስም አጠራሩ ይኹንና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተራራው ስብከቱ፡- “ጽድቅን የሚራቡና የሚጠሙ ብፁዓን ናቸው፤ ይጠግባሉና” /ማቴ.5፡6/ ያለውም ይኽን የሚያስረዳ ነው፡፡ እንዴት አድርጌ እንደማመሰግናችኁ አላውቅም፡፡ ምክንያቱም ጽድቅን ከመራባችኁና ከመጠማታችኁ የተነሣ ብፁዓን ኾናችኁ ሳለ አኹንም ይኽን ማድረጋችኁን አላቆማችኁምና፡፡ ልጆቼ! አባታችን እግዚአብሔር እንዴት እንደሚወደን እያያችኁ ነውን? ከእኛ የሚመጣ ትንሽ መነሣሣት ካለ እግዚአብሔር ከእኛ መነሣሣት በላይ በኾነ በረከት ነው የሚባርከን፡፡ እኛ ትንሽ ፈቃደኞች ስንኾን ርሱ ግን ከእኛ በላይ ብዙ ጸጋና በረከት ይሰጠናል፡፡ እኔም ይኽን እየተመለከትኩ እናንተን ለማስተማር እጓጓለኹ፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወታችን ለውጥ እንድናመጣ በጣም እጥራለኹ፡፡ ማስተማሬንም እቀጥላለኹ፡፡ እናንተ በመንፈሳዊ ሕይወታችኁ እንድትበረቱ ማንኛውንም ዓይነት መሥዋዕት እከፍላለኹ፡፡ ምክንያቱም እዚኽ ብቻ እንድታቆሙ አልፈልግምና፡፡ ከዚኽም በበለጠ ወደ መንፈሳዊ ከፍታ እንድትወጡ እፈልጋለኹ፡፡ ከዚኽ በበለጠ በምትውሉበት የሥራ ቦታ፣ በምትውሉበት የትምህርት ቦታ አስተማሪዎች እንድትኾኑ እፈልጋለኹ፡፡ ቆማችኁ በማስተማር ሳይኾን መልካም ሥራችኁን አይተው ብዙዎች እንዲማሩ እፈልጋለኹና ትጋቴን ከወትሮው ይልቅ እጨምራለኹ፡፡ ድካሜ በከንቱ እንዳልቀረ እያየኹ ነውና ከዚኽ የበለጠ ማስተማር እንዳለብኝ ይሰማኛል፡፡ ከምንም በላይ ደስ ያለኝ ደግሞ የዘራነውን ዘር ቀን በቀን እየጐመራ ነው እየሔደ ያለው፡፡ በወንጌል ላይ እንደተጠቀሰው ዓይነት እንቅፋት አላጋጠመንም፡፡ እንደምታስታውሱት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዘሩ ምሳሌ ባስተማረው ትምህርት ከተዘራው ዘር አንድ አራተኛው ብቻ ጥሩ ፍሬ ሲያፈራ ሦስት አራተኛው ግን እንደተጠበቀው አልኾነም፡፡ በመንገድ ዳር ላይ የወደቀው ዘር ወፎች መጥተው በልተዉታል፡፡ ብዙ መሬት በሌለበት በጭንጫ ላይ የወደቀው ፀሐይ ሲወጣ ጠውልጎ ወዲያው ደርቋል፡፡ በእሾኽ መካከል የወደቀውም እሾኹ አንቆታል፡፡ በመልካም መሬት ላይ የወደቀው ግን መቶ፣ ስድሳ፣ ሠላሳ ፍሬ አፈራ /ማቴ.13፡3-8/፡፡ እኔም ትምህርቴ በመንገድ ዳር፣ ወይም በጭንጫ፣ ወይም በእሾኽ መካከል እንዳልወደቀ እየተመለከትኩ ነውና ትጋቴ እንዲጨምር አደረጋችኁኝ፡፡ መልካም እርሻ ኾናችኋልና በትጋት እንዳስተምራችኁ አድርጋችኁኛል፡፡ እጅግ የምወዳችኁ ልጆቼ! ይኽን ኹሉ የምላችኁ ግን በውዳሴ ከንቱ ላመሰግናችኁ ፈልጌ አይደለም፡፡ ይኽን ኹሉ እንድል ያደረገኝ አንድ ነገር ስለተመለከትኩኝ ነው፡፡ ትናንት በዘነበው ኃይለኛ ዝናብ እንኳን አልተበተናችኁም፡፡ ዝናቡ እየዘነበባችኁም ቢኾን ቃሉን ለመማር ቁጭ ብላችኁ ነበር፡፡ ይኽ ለእኔ ትልቅ መልእክት አለው፡፡ እግዚአብሔር በእኔ በባርያው አድሮ የሚያስተምረውን ትምህርት በሙሉ ልባችኁ ኾናችኁ እየተቀበላችኁ እንደኾነ አሳይቶኛል፡፡ እንድተጋ አድርጋችኁኛል የምለውም ስለዚኹ ነው፡፡ ቃለ እግዚአብሔርን በማስተዋል የሚያደምጥ ሰው ቃሉ ከልቡናው ትከሻ አይወርድም፡፡ ዘወትር ያስታውሰዋል፡፡ ደግሞም ፈቃደኛ ለኾነ ልብ ማስተማር እንዴት ደስ ይላል መሰላችኁ፡፡ መጽሐፍስ “ፈቃደኛ ለኾነ ልብ የሚያስተምር ሰው ብፁዕ ነው” ብሎ የለ /ሲራክ 25፡9/፡፡ ከጾም ውጤቶች አንዱ ይሔ ነው፡፡ ገና ይኽን ስንዠምር ጾም የነፍስ የሥጋ ቁስልን ትፈውሳለች ያልኳችኁ ይኸው ነበር፡፡ ወዮ! ገና ከአኹኑ ይኸን ያኽል ለውጥ ካየን፥ በሚቀጥሉት ቀናት ትምህርቱን የበለጠ ስንማርና የጾም ወራቱ ሲቀጥልማ እንዴት እንኾን ይኾን? ስለዚኽ የምወዳችኁ ልጆቼ! ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለ፡- “በፍርሐትና በመንቀጥቀጥ የራሳችኁን መዳን ፈጽሙ” ብዬ እለምናችኋለኹ /ፊልጵ.2፡12/፡፡ ጠላት ዲያብሎስን በምንም መልኩ ለስንፍና አንጋብዘው፡፡ ከዚኽ የበለጠ እንትጋ እንጂ ከእንግዲኽ ወዲኽ ወደኋላ መመለስ አያስፈልገንም፡፡ ዲያብሎስ አኹን ያፈራነውን ፍሬ እያየ መበሳጨቱ አይቀርም፡፡ ይኽን የያዝነውን ፍሬ ለማስጣልም እንደሚያገሣ አንበሳ ኾኖ በዙርያችን እንደሚዞር በፍጹም መርሳት የለብንም /1ኛ ጴጥ.5፡8/፡፡ ነገር ግን ጠንቃቃዎችና በእግዚአብሔር ቸርነት የምንደገፍ ከኾነ ዲያብሎስ ምንም ሊያደርገን አይችልም፡፡ ችግር የሚኾነው እኛው ወደኋላ ማየት ስንዠምር ነው፡፡ አያችኁ ልጆቼ! ለመንፈሳዊ ሕይወታችን ደንታ ቢስ ካልኾንን የምንለብሰው ጸጋ መንፈስ ቅዱስ እንዲኽ ብርቱ የኾነ የጦር ዕቃ ነው የሚያለብሰን፡፡ ስለዚኽ ኹለንተናችንን (ንግግራችንን፣ አለባበሳችንን፣ አሰማማችንን፣ ማንኛውንም አካሔዳችንን) በእግዚአብሔር ዕቃ ጦር ማለትም በእግዚአብሔር ቃል የምናለብሰው ከኾነ ዲያብሎስ የሚወረውረው ጦር እኛን ሊጐዳን አይችልም፡፡ እንደዉም ተመልሶ ርሱን ነው የሚጐዳው፡፡ እጅግ የምወዳችኁ ልጆቼ! ብቻ እኛ ፈቃደኞች እንኹን እንጂ፣ ብቻ እኛ በጾም በጸሎት ቃለ እግዚአብሔርንም በማድመጥ እንበርታ እንጂ የእግዚአብሔር ቸርነት እኛን ከብረት በላይ ጠንካራ ነው የሚያደርገን፡፡ አኹን ከእኛ መካከል አንድን ብረት በቦክስ ቢመታ ማን ነው የሚጐዳው? ብረቱ ወይስ እጃችን? ብረቱ ምንም አይኾንም፤ እጃችን ግን በእጅጉ ይጐዳል፡፡ የፈለገ ያኽል ጠንካሮች ብንኾንም ብረትን ማቁሰል አንችልም፡፡ ርሱ ነው የሚያቆስለን፡፡ በእግራችን ይኽን ብረት ብንመታው እኛው ደም በደም ኾነን እንቆስላለን እንጂ ብረቱ ምንም አይኾንም፡፡ ልክ እንደዚኹ እኛም በጾም፣ በጸሎት፣ በስግደት፣ ከቅዱስ ሥጋውና ከክቡር ደሙ በመቀበል፣ በመልካም ምግባር ኹለንተናችንን የምንከላከል ከኾነ፥ ዲያብሎስ እኛን ለመጉዳት የሚወረውረው ጦር መልሶ የሚጐዳው ራሱ ዲያብሎስን ነው፡፡ የእግዚአብሔር ቸርነት ከእኛ ጋር ስለሚኾን ጠላት እግዚአብሔርን አልፎ ሊያጠቃን አይችልም፡፡ ጸጋ መንፈስ ቅዱስ ከእኛ ጋር ስለሚኾን ዲያብሎስን ልምሾና ምንም ዓቅም የሌለው ነው የሚያደርገው፡፡ ስለዚኽ እጅግ የምወዳችኁ ልጆቼ! መንፈሳዊ ትጥቅን እንታጠቅ፡፡ ሳንታጠቅ ከጠላት ዲያብሎስ ጋር አንታገል፡፡ ትርፉ መቁሰል አልፎም መሞት ብቻ ነውና፡፡ ስለዚኽ መንፈሳዊውን ትጥቅ ለመታጠቅ የምናደርገው ትጋት ጨምረን እንቀጥልበት ብዬ እለምናችኋለኹ፡፡ የትም ብንሔድ ይኽን መንፈሳዊ ትጥቃችንን ትተን መሔድ የለብንም፡፡ ወደ ቤተ ክርስቲያን ብንመጣ፣ ወደ ሥራ ቦታ ብንሔድ፣ ወደ ትምህርት ቤት ብንሔድ፣ ወደ ቤታችን ብንሔድ፣ ብንነቃ፣ ብንተኛ ያለዚኽ ትጥቅ መንቀሳቀስ የለብንም፡፡ ትጥቃችንን ይዘን የትም ብንሔድ ጠላት ያጠቃናል ብለን አንሰጋም፡፡ ደግሞም ይኽን ተሸክሞ ለመዞር (ክላሽ፣ መትረየስ፣ ሽጉጥ እንሚባሉት) እንደ ምድራዊ ትጥቆች አይከብድ፡፡ እንደዉም የበለጠ ብሩሃን (ብርሃን የተሞላን) ያደርገናል፡፡ ይኽን ብርሃን እያየም ጠላት ዲያብሎስ ሊያጠቃን አይችልም፡፡ ከእኛ ጋር ያለውን ብርሃን ለማየት ዓይኑ አይችልምና፡፡ እንዲኽ ከኾነም ደጋግሜ እንደነገርኳችኁ በጾም የሚገኘውን የነፍስ የሥጋ ቁስላችንን እናክማለን፡፡ ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!! ላይ ኖቬምበር 24, 2014 ምንም አስተያየቶች የሉም: ይህን ኢሜል አድርግጦማር አድርግ!Twitter ላይ አጋራFacebook ላይ አጋራለPinterest አጋራ ጾም - ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው (ክፍል ሦስት) (መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ቅዳሜ ኅዳር 13 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!! ውድ የመቅረዝ ወዳጆች እንዴት ናችኁ? ዛሬም ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስብከቱን ቀጥሏል፡፡ ባለፈው ትምህርቱ ሊቁ ብዙ ነገር አስተምሮናል፡፡ በጾም ወደ እግዚአብሔር የበለጠ እንደምንቀርብ፣ ምሥጢራተ እግዚአብሔርን ለማወቅና ለመረዳት ልቡናችን ብሩህ እንደሚኾን፤ ከዚኽ በተጨማሪ በጾም አዳም ከመደበሉ በፊት በገነት የነበረውን ሕይወት እንደምንለማመደው አስተምሮናል፡፡ ምክንያቱም አዳም ከመበደሉ በፊት የእንስሳት ተዋጽኦዎችን አይበላም ነበር፤ ይኽን መብላት የዠመረው ከበደለ በኋላ ነው፡፡ ሥጋውን የሚያስወፍሩና ነገረ እግዚአብሔርን ከማሰብ የሚያርቁ ተግባራትን አይፈጽምም ነበር፡፡ እኛም በመጾማችን ሥጋችንን እየቀጣን ሳይኾን በገነት የነበረውን አዳምን መስለን የበለጠ ወደ እግዚአብሔር የምንቀርብበት መንፈሳዊ መንገድ እንደኾነ አስተምሮናል፡፡ ዛሬስ ምን ብሎ ነፍሳችንን ይመግባት ይኾን? የሊድያን ልቡና የከፈተ አምላክ የእኛንም ይክፈትልን አሜን!!! ዛሬ ብሩህ የኾነ ፊታችኁን እያየኹ እጅግ በጣም ደስ ብሎኛል፡፡ ደስታዬ ግን ልጆች ከወላጆቻቸው ጋር ሲጫወቱ እንደሚያመጡት ዓይነት ደስታ አይደለም፡፡ የእኔ ደስታ ከዚኽ የተለየ ነው፡፡ ምክንያቱም ቃለ እግዚአብሔር የተራበችውን ነፍሳችኁን ለመመገብ እንዴት ተጠራርታችኁ እንደመጣችኁ፣ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ሰው ከእግዚአብሔር አፍ በሚወጣ ቃል ኹሉ እንጂ በእንጀራ ብቻ አይኖርም” ብሎ የተናገረውን ቃሉን በተግባር ለመፈጸም /ማቴ.4፡4/ ይኽንን በዓል ለማክበርም እንዴት ጓጕታችኁ እንደመጣችኁ ዐይቼ ደስታዬ ልዩ ነው፡፡ ስለዚኽ ኑ እንደ ገበሬዎች እንኹን ብዬ እለምናችኋለኹ፡፡ ገበሬዎች እርሻቸው እንደለሰለሰ፣ ምንም ዓይነት አረምም እንደሌለ ሲያረጋግጡ እኽል ይዘሩበታል፡፡ እኛም ኑ እንደገበሬዎቹ እንኹን፡፡ በእግዚአብሔር ቸርነት የልቡናችን እርሻ ከለሰለሰ፣ በዚኹ በልቡናችን እርሻ የሚዘራውን ቃለ እግዚአብሔር የሚያንቁትን እንደነ ስልቹነትና ግዴለሽነት የመሰሉ አረሞች ከተነቀሉልን፣ ልቡናችን ሰማያዊ ምሥጢራትን ለመመርመር ብሩህ ከኾነልን፣ ከምድራዊ ነገር ይልቅ ሰማያዊ ነገርን ማስቀደም ከዠመርን ከዛሬ ዠምረን ጠለቅ ባለ መልኩ መማማር እንዠምራለን፡፡ ልቡናችን እንዲኽ በቃለ እግዚአብሔር ከለሰለሰ በኋላ ቃሉን የበለጠ ብንዘራበት ፍሬ ማፍራት የሚችል ይኾናልና፡፡ ጾሙም እየገባ ስለኾነ ስለ ምድራዊ መብልና መጠጥ ማሰብ ስለቀነስን ቃሉን ለማድመጥ ምቹ ነው፡፡ አብዝቶ የበላና የጠጣ ሰው ቃሉን ተማር ብንለው እንዴት ሊሰማን ይችላል? ስለበላው ምግብና ስለጠጣው መጠጥ የሚያስብና ሥጋው ወፍሮ የሚያስቸግረው ሰው እንባችን እንደ (አባይ) ወንዝ እየፈሰሰ ብንነግረውም ደንታ አይሰጠውም፡፡ ስለዚኽ አኹን ቃሉን ለመማር ምቹ ጊዜ ነው፡፡ በቤታችን ውስጥ አንድን ነገር ለቤተሰባችን ማሳመን የምንፈልግ ከኾነ ከቤት ሠራተኛዋ ዠምሮ ኹሉም ሰው ሰላማዊና ለማድመጥ ዝግጁ የኾነበትን ሰዓት መምረጥ አለብን፡፡ ጾም ደግሞ የነፍስ ዕረፍትን የምትሰጥ፣ ሽማግሌዎችን ደስ የምታሰኝ፣ ለወጣቶች ቀና መንገድን የምታስተምር፣ ሰውን ኹሉ ጠንቃቃና አርቆ አሳቢ የምታደርግ፣ በየትኛውም ዕድሜ የሚገኘውን ሰው የምታስጌጥ፣ ኹሉንንም እንደ ዕንቁ ፈርጥ የምታሳምር ናት፡፡ ስለዚኽ ከዛሬ ዠምሮ በከተማችን ምንም ዓይነት ሁካታ አይኑር፤ ዳንኬራ ቤቶች የሚሔድ አይገኝ፤ በመንፈሳዊ ሕይወቱ ቸልተኛ ሰው አይገኝ፤ እኅቶች አለባበሳቸውን ያስተካክሉ፡፡ ኹሉም ሰው ክርስቲያን ክርስቲያን ይሽተት፡፡ ከትናንትናው ጉባኤ በኋላ ዛሬ ላይ ሳያችኁ ይኽን እመለከታለኹ፡፡ በዚኽም ጾም ምን ያኽል ኃይል እንዳላት አስተዋልኩኝ፡፡ ጾም የሰዎችን አስተሳሰብ እንዴት እንደምትቀይር፣ የገዢዎች ብቻ ሳይኾን የተገዢዎችም፣ የአሠሪዎችም የሠራተኞችም፣ የወንዶችም የሴቶችም፣ የሀብታሙም የድኻውም፣ በአጠቃላይ የሰውን ልቡና እንዴት የማንጻት ኃይል እንዳላት ተገነዘብኩኝ፡፡ ገዢውም ተገዢውም ሲጾም ራሱን ዝቅ ማድረግ ይለማመዳል፡፡ ጾም ድኻውም ሀብታሙም እኩል የምታደርግ መሣሪያ ናት፡፡ በሚጾም ልቡና እኔ እበልጥ እኔ እበልጥ ምንም ዓይነት ቦታ የለውም፡፡ በዚኽ ጉባኤ ላይ የታደማችኁ እጅግ የምወዳችኁ ምእመናን ሆይ! ጾም ለየትኛውም ዓይነት መንፈሳዊና ሥጋዊ በሽታ እንዴት ዓይነት ፍቱን መድኃኒት እንደኾነ ተገነዘባችኁን? ይኽን ከእናንተ እየተመለከትኩ ትጋቴ ከትናንቱ ይልቅ ዛሬ እጅግ ጨመረ፤ በመኾኑም ልቤ እናንተን ለማስተማር ተነሣሣ፡፡ እግዚአብሔር በእኔ በባርያው አድሮ የሚዘራው ቃል በጭንጫ ላይ ሳይኾን በመልካም እርሻ እየበቀለ እንደኾነ ዐየኹ፡፡ በአጭር ጊዜም ፍሬውን ማየት ችያለኹ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ከዚኽ በኋላ እዚያ ለታደሙት ምእመናን በኦሪት ዘልደት (ዘፍጥረት) ምዕራፍ አንድ ቁጥር አንድ እስከ ኹለት ያለውን ኃይለ ቃል ነው የሚተረጕምላቸው፡፡ በነገራችን ላይ በጥንታዊቷ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት በዐቢይ ጾም በብዛት የሚተረጐመው መጽሐፍ ኦሪት ዘፍጥረት ነው፡፡ ከስሙ መረዳት እንደምንችለው መጽሐፉ ስለ ብዙ ልደታት የሚናገር ነው፡፡ የሰማይና የምድር ልደት፣ የሰው ልጅ ልደት፣ የሰንበት ልደት፣ የጋብቻ ልደት፣ የኃጢአት ልደት፣ የመሥዋዕት (የድኅነት) ልደት /3፡15/፣ የትንቢት ልደት /3፡15/፣ የሰው ሥልጣን ልደት /9፡1-6/፣ የሀገራት ልደት /11/፣ የእግዚአብሔር ሕዝቦች ልደት /12፡1-3/፡፡ በዚያን ጊዜ ወደ ክርስትና ይመጡ የነበሩት አዳዲስ አማንያንም በፋሲካ ነበር የሚጠመቁት፤ ማለትም ዳግም የሚወለዱት፡፡ ይኸውም ሐዋርያው ጳውሎስ ጥምቀት ማለት ከክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ የምንተባበርበት ዳግም አዲስ ልደትም የምናገኝበት እንደኾነ ያስተማረውን ትምህርት በተግባር ለመፈጸም ነው /ሮሜ.6፡4-6/፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅም የኦሪት ዘፍጥረትን በዚኽ ጊዜ የሚተረጕምላቸው ስለዚኹ ነው፡፡ በዚኽ ዕለት ካስተማረው ትምህርት የሚከተሉት ዋና ዋና ነጥቦች እናገኛለን፡- · እግዚአብሔር ከመዠመሪያ አንሥቶ ለሰው የተናገረው በሰውኛ ቋንቋ እንደኾነ፤ · ሰው ቢበድልም እንኳ ፍቅሩ አላስችል ብሎት ፍቅራችንን እናድሰው እያለ ከነ አዳም፣ ከነ ቃየን፣ ከነ ኖኅ፣ ከነ አብርሃም (በተለይ ከአብርሃም ጋር በቤቱ እንግዳ ኾኖ በመግባት) ዝቅ ብሎ እንደተጨዋወተ፤ · ከእስትንፋስ ይልቅ ለሰው ልጆች ቅርብ ኾኖ ሳለ ሰዎች አላስተውል ቢሉት የበለጠ እንዲያውቁት ፈልጐ በሙሴ በኩል ደብዳቤ እንደላከላቸው፤ · ሙሴም የተቀበለውን ደብዳቤ ለሕዝቡ በየጊዜው ያነብላቸው (ይነግራቸው) እንደነበረ፤ · ሙሴ የሰማይና የምድር ፈጣሪ እግዚአብሔር መኾኑን እንደነገራቸው፤ እኛም ይኽን አሜን ብለን ልንቀበል እንደሚገባን፤ · የእግዚአብሔር አሠራር ከሰው አሠራር ልዩ እንደኾነ፡፡ ለምሳሌ ሰው አንድን ቤት ሲሠራ ከመሠረት እንደሚዠምር ቀጥሎም ጣርያና ግድግዳ እንደሚሠራ፤ እግዚአብሔር ግን ከሰማይ ማለትም ከጣርያው ዠምሮ ቀጥሎም ምድርን ማለትም መሠረቱን እንደፈጠረ፤ · ሰው ከምድር አፈር ተፈጥሮ ሳለ አፈሩ እንዴት ብሎ ነርቭ፣ አጥንት፣ የደም ቧንቧ፣ ጡንቻ፣ ፀጉር፣ ምላስ፣ ሳንባ፣ ልብ እንደኾነ ስናስብ ልቡናችን ተደንቆ ተደንቆ ዝም ብለን እግዚአብሔርን ማድነቅ ብቻ ሊኾን እንደሚገባና ይኽን ላደረገ ጌታ ምስጋና ብቻ ማቅረብ እንደሚገባን፤ ይኽንና ይኽን የመሰለ ጣፋጭ ትምህርት ካስተማራቸው በኋላ ሊቁ የሚከተለውን ይነግራቸዋል፡- እጅግ የምወዳችኁና እዚኽ ጉባኤ ላይ የታደማችኁ ቃሉንም ያዳመጣችኁ ምእመናን ሆይ! አኹን ለጊዜው የትርጓሜው ትምህርታችን ገታ እናድርግና አንድ ነገር ታደርጉ ዘንድ እለምናችኋለኹ፡፡ ወደየቤታችን ስንሔድ ቃሉን ለመተግበር እንጣጣር፡፡ ቃሉን በልቡናችን ጽላት እንቅረጸውና ዘወትር እንደ እንጀራ እንመገበው፡፡ አባቶች ለቤተሰቦቻችኁ ዛሬ የተማርነውን ትምህርት ድገሙላቸው፡፡ እኛቶችም ይኽን ከባሎቻቸው ያድምጡ፡፡ ልጆች ከእናቶቻቸው ይኽን ያድምጡ፡፡ ልጆች ብቻ አይደለም፤ ከቤት ውስጥ ያሉት እንስሳትም ይኽን ያድምጡ፡፡ ይኽን ያደረግን እንደኾነ፣ በዚኽ ጉባኤ የተማርነውን ትምህርት ከቤታችን ሔደን በተግባር የምንኖረውና ቃሉን ደጋግመን የምንበላው ከኾነ ቤታችን ቤተ ክርስቲያን ትኾናለች፡፡ ዲያብሎስም ወደ ቤታችን መግባት አይቻለውም፡፡ የነፍሳችን ጠላት የኾነው ርኵስ መንፈስ ተኖ ይጠፋል፡፡ በርሱ ፈንታም ወደቤታችን መንፈስ ቅዱስ ሰተት ብሎ ይገባል፡፡ ሰላምና ፍቅር፣ አንድነትና መስማማት ወደ ቤታችን ከነጓዛቸው ሰተት ብለው ይገባሉ፡፡ ይኽን ያደረጋችኁ እንደኾነ እኛንም የበለጠ ታተጉናላችኁ፡፡ የቃሉን ምሥጢር የበለጠ እንድናስተምራችኁ ታበረቱናለችኁ፡፡ ገበሬ የዘራውን እኽል ፍሬ ሲያፈራለት አይቶ እጅግ ደስ እንደሚሰኝ ኹሉ እኛም ደስ እንሰኛለን፡፡ ተደጋግፈንም ክርስቲያን ክርስቲያን የምንሸት እንኾናለን፡፡ ስለዚኽ ደጋግሜ እንደነገርኳችኁ በመንፈሳዊ ሕይወታችን የትም ብንኾን ቸልተኞችና ደንታ ቢሶች ልንኾን አይገባንም፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ሲናገር እንዲኽ ይላል፡- “መልካሙን ሥራችኁን አይተው በሰማያት ያለውን አባታችኁን እንዲያከብሩ ብርሃናችኁ እንዲኹ በሰው ፊት ይብራ” /ማቴ.5፡16/፡፡ የተማርነውን ትምህርት በተግባር የምንፈጽም ከኾነ በዚኽ ጉባኤ የተማርነው ትምህርት ግቡን መትቷል ማለት ነው፤ ፍሬ አፍርተናል ማለት ነው፤ በእውነት ክርስቶስን መስለነዋል ማለት ነው፡፡ ዳግመኛም ቅዱስ ያዕቆብ እንደነገረን እምነት ያለ ሥራ የሞተ ነው፤ ሥራም ያለ እምነት እንደዚኹ የሞተ ነው /ያዕ.2፡26/፡፡ የፈለገ ያኽል በእምነታችን ምንም እንከን የሌለን ብንኾን፣ ነገር ግን በተግባራዊ ሕይወታችን ሰነፎችና በኀጢአት ሕይወት የምንኖር ከኾነ ስሕተት የሌለው እምነታችን ምንም አይጠቅመንም፡፡ ልክ እንደዚኹ እውነተኛ እምነት ውስጥ ሳንኖር የፈለገ ያኽል መከራ ብንቀበልም፣ የምድር መልአክ ብንመስልም አይጠቅመንም፡፡ ስለዚኽ በየጊዜው የምንማረው ትምህርት ጊዜአዊ ስሜታችንን የሚያረካ ሳይኾን ሕይወታችንን የሚቀይረው ሊኾን ይገባል፡፡ ጌታችን ሲናገር፡- “ይኽን ቃሌን ሰምቶ የሚያደርገው ኹሉ ቤቱን በዓለት ላይ የሠራ ልባም ሰውን ይመስላል” ብሏል /ማቴ.7፡24/፡፡ ይኽ ሰው ልባም የተባለው ቃሉን ስለሰማ ብቻ አይደለም፤ ቃሉን ሰምቶ እንደ ዓቅሙ ለመተግበር ስለሚጣጣር እንጂ፡፡ ቃሉን ሰምቶ ለጊዜው የሚደሰትና “አቤት የዛሬው ጉባኤ ሲያስደስት” ብሎ የማይተገብር ሰው ግን ሰነፍ ሰው ነው፡፡ ይኽ ሰነፍ ሰውም ቤቱን በአሸዋ እንደሠራ ሰው ነው፡፡ ቤቱን በአሸዋ የሠራ ሰው ነፋስ ወይም ጐርፍ ሲመጣ ይፈርሳል፡፡ ፈተና ባጋጠመው ሰዓት ዐለት በተባለው ክርስቶስ ስላልቆመ ይሸነፋል፡፡ ልባም ሰው ግን በእነዚኽ ፈተናዎች የበለጠ ይፈካል፡፡ ክርስቶስን እየመሰለ ይሔዳል፡፡ ልባሙ ሰው ፈተና ባጋጠመው መጠን ከክርስቶስ ጋር ስለሚኾን መልካም ሥራው የበለጠ እየታየ ይሔዳል፡፡ ሰነፍና ለመንፈሳዊ ሕይወቱ ደንታ የሌለው ክርስቲያን ግን የፈለገ ያኽል እዚኽ ጉባኤ መጥቶ ቁጭ ብሎ ቢማርም ፈተና ባጋጠመው ጊዜ በቀላሉ ይወድቃል፡፡ ፈተናው ከብዶት ሳይኾን እርሱ ሰነፍ ስለኾነ (ክርስቶስ አብሮት ስለሌለ)፡፡ ስለዚኽ የጦር ዕቃችንን እናንሣ፡፡ የአንድ ሳምንት ጿሚዎች ሳንኾን ዘወትር ብርቱዎች እንኹን፡፡ ይኽን ያደረግን እንደኾነ በፈተና እንጸናለን፡፡ ትዕግሥተኞች እንኾናለን፡፡ በመንግሥተ ሰማያት ከምናገኘው ደስታ ጋር ስናነጻጽረው የአኹኑ ሕይወታችን ፈተና ምንም እንዳልኾነ እናውቃለን፡፡ አኹን ትዕግሥተኞችና በፈተና የምንጸና ከኾነ 30፣ 60፣ 100 ያማረ ፍሬ ማፍራት እንችላለን፡፡ ቸርና ሰው ወዳጅ እግዚአብሔር በፈተና እንድንጸና ይርዳን፡፡ የይምሰል ሳይኾን የእውነትና እግዚአብሔር የሚወደው የጾም ወራት ያድርግልን፡፡ ዳግም በመጣ ጊዜ የሕይወት ቃል እንዲያሰማን ፈቃዱ ይኹን፡፡ ምስጋና፣ ክብር፣ አኰቴት ለአብ፣ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ዛሬም ዘወትርም እስከ ዘለዓለሙ ድረስ ይኹን፡፡ አሜን!!! ላይ ኖቬምበር 24, 2014 ምንም አስተያየቶች የሉም: ይህን ኢሜል አድርግጦማር አድርግ!Twitter ላይ አጋራFacebook ላይ አጋራለPinterest አጋራ ጾም - ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው (ክፍል ኹለት) (መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ሐሙስ ኅዳር 11 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!! ውድ የመቅረዝ አንባብያን፡፡ በትናንቱ ጕባኤ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ብዙ ነገር አሳስቦን ነበር፡፡ ጉባኤውን ለመታደም ወደ ቤተ ክርስቲያን ዓውደ ምሕረት ከመጣን አይቀር ከነበሽታችን ልንመለስ እንደማይገባ ይልቁንም መንፈሳዊ መድኃኒትን ውጠን ልንመለስ እንደሚገባን፣ የነፍስና የሥጋ መድኃኒት ከምትኾን ከጾም ጋር አብረው የማይሔዱ ነገሮች ምን ምን እንደኾኑ፣ ከእንግዲኽ ወዲኽ ቤተ ክርስቲያን ቀኖና አውጥታ ጾም ነው ስላለችን ብቻ ሳይኾን በዓላማ ልንጾም እንደሚገባና ሌላ ብዙ ነፍስን የሚያለመልሙ ትምህርቶችን አስተምሮን ነበር፡፡ ምንም እንኳን የዛሬው ትምህርት ለእኛ ኹለተኛ ጕባኤ ቢኾንም ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ግን ከትናንቱ ጋር በአንድ ቀን ጕባኤ ያስተማረው ነው፡፡ የመዠመሪያው ቀን ስብከቱም ዛሬ ላይ እንጨርሳለን፡፡ በነገራችን ላይ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ቁመቱ አጭር ስለነበረ ምእመናኑ ባዘጋጁለት መድረክ ላይ ወጥቶ ነበር የሚያስተምረው፡፡ ዛሬ በየዓውደ ምሕረቱ የምንመለከተው አትሮንስም ከዚያን ጊዜ ዠምሮ አገልገሎት ላይ የዋለ ነው፡፡ መልካም ጕባኤ እንዲኾንልን በመመኘት ፊታችንና መላ ሰውነታችንን ሦስት ጊዜ በማማተብ ትምህርቱን በትጋት ኾነን እንድንማር በድጋሜ ጋበዝናችኁ፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወት ቸልተኛ መኾንና ለራስ ሕይወት ግድ አለመስጠት የብዙ ኃጢአቶች ምክንያት እንዲኹም ነጸብራቅ ነው፡፡ ልክ እንደዚኹ ጾምም የብዙ በረከት ምክንያት እንዲኹም ነጸብራቅ ነው፡፡ እንደምታስታውሱት አዳም በገነት በነበረ ጊዜ ለመንፈሳዊ ሕይወቱ ቸልተኛና ግድ የሌለው እንዳይኾን ብሎ ልዑል እግዚአብሔር አንድ ትእዛዝ ሰጥቶት ነበር፡፡ እንዲኽ በማለት፡- “ከገነት ዛፍ ኹሉ ትብላለኅ፤ ነገር ግን መልካሙንና ክፉን ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ” /ዘፍ.2፡16-17/፡፡ እዚህ ጋር “ብላ፤ አትብላ” የሚለው የሚለው ትእዛዝ በምሳሌ ስለ ጾም ጥቅም የሚያስረዳ ነው፡፡ የሰው ልጅ ግን ይህቺን አንዲት ትእዛዝ ለመጠበቅ አልታዘዝ አለ፤ ትዕግሥት አጣ፤ ሞትንም በራሱ ላይ አመጣ፡፡ የሰው ልጆች ጠላትና ክፉ መንፈስ የኾነው ዲያብሎስም እንደምታስታውሱት አዳም በገነት የአታክልት ስፍራ ደስ ብሎት እንደ ሰማያውያን መላዕክት ኾኖ እየኖረ ስለነበረ ቀናበት፡፡ አምላክ ትኾናለህ ብሎም አታለለውና የነበረውን ቅድስና እንኳን አሳጣው፡፡ አያችኁ ልጆቼ! ያለንን ቅዱስ ነገር በአግባቡ ሳንይዝ ይልቁንም ሌላ ከዚኽ የበለጠ ነገር መመኘት መዘዙ ብዙ ነው፡፡ ጠቢቡ ሰው “በዲያብሎስ ቅንኣት ምክንያት ሞት ወደ ዓለም ገባ” ያለንም እኮ ስለዚኹ ምክንያት ነው /ጥበብ 2፡24/፡፡ እንግዲኽ ሞት ወደ ሰው ልጆች እንዴት በስንፍና እንደመጣ እያስተዋላችኁ ነው ልጆቼ? በኋላ ዘመን መጽሐፍ ቅዱስ ሲጻፍም በመንፈሳዊ ሕይወት መድከምን እንዴት እንደሚነቅፍ እንመልከት፡- “ሕዝቡም ሊበሉና ሊጠጡ ተቀመጡ፤ ሊዘፍኑም ተነሡ” /ዘጸ.32፡6/፤ “ወፈረ፤ ደነደነ፤ ሰባ፤ የፈጠረውንም እግዚአብሔርን ተወ፤ የመድኃኒቱንም አምላክ ናቀ” /ዘዳ.32፡15/፡፡ የሰዶም ኗሪዎችም የዲን እሳት ዘንቦባቸው የጠፉት ለመንፈሳዊ ሕይወታቸው እጅግ ቸልተኞች ስለነበሩና ለመብልና ለመጠጥ ሰፊ ቦታን ስለ ሰጡ ነው፡፡ ነቢዩ ሕዝቅኤል ስለዚኹ ጉዳይ ሲነግረን እንዲኽ ብሏል፡- “የሰዶም ኃጢአት ይኽ ነበረ፤ ትዕቢት እንጀራን መጥገብ መዝለልና ሥራ መፍታት” /ሕዝ.16፡49/፡፡ በአጭር አነጋገር አብዝቶ መብላትና መጠጣት፣ ጾምን ችላ ማለት የብዙ ኃጢአቶች ምክንያት ነው፡፡ እንግዲኽ ራስን አለመግዛት እንዴት አደገኛ እንደኾነ አያችኁ? አኹን ደግሞ ጾም እንዴት በረከትን እንደሚያመጣ እንመልከት፡፡ ሙሴ 40 ቀን ስለጾመ የእግዚአብሔር ሕግ የተጻፈበትን ጽላት ተቀበለ /ዘጸ.24፡18/፡፡ ከተራራው ሲወርድ ግን የሕዝቡን ኃጢአት ተመለከተና ኃጢአተኛ ሕዝብ የእግዚአብሔርን ሕግ መቀበል አይችልም ሲል ብስንት መለማመጥ የተቀበለውን ጽላት ወርውሮ ሰበረው፡፡ ይኽ ታላቅ ነቢይ በተሰበረው ፋንታ ሌላ ጽላት ለመቀበል 40 ቀናት ነው የጾመው /ዘጸ.34፡28/፡፡ ታላቁ ነቢይ ኤልያስም ልክ እንደ ሙሴ 40 ቀንና 40 ሌሊት ጾሟል፡፡ እንዲኽ በመጾሙም በእሳት ሠረገላ ተነጥቆ ወደ ሰማይ ተወሰደ፤ እስከ አኹን ድረስም አልሞተም፡፡ እጅግ አስደናቂ የኾነው ሰው ነቢዩ ዳንኤልም እጅግ ብዙ ቀናትን ይጾም ስለነበረ ተንኰለኞች ወደ አንበሳ ጕድጓድ እንኳን ቢጥሉት አንበሶች ሊበሉት አልቻሉም፡፡ አንበሶቹ ለነቢዩ ዳንኤል እንደ በጐች ነበሩ፡፡ አንበሶቹ በግ የኾኑት ግን ተፈጥሯቸው ተለውጦ በግ በመኾን ሳይኾን ዳንኤልን ሳይበሉት ከነተናጣቂ ተፈጥሯቸው ሳሉ ነው፡፡ የነነዌ ሰዎች የእግዚአብሔርን ቁጣ ያስቀሩት በመጾማቸው ነው፡፡ እንደዉም በነነዌ የጾሙት ሰዎች ብቻ አልነበሩም፤ እንስሳቱም ጭምር እንጂ፡፡ በዚኽም ምክንያት እግዚአብሔር ሊያደርገው ከተናገረው ክፉ ነገር ተጸጽቶ አላደረገውም /ዮናስ 3፡10/፡፡ ከብሉይና ከሐዲስ ኪዳን እንዲኽ በመጾማቸው የተጠቀሙ ብዙ ሰዎችን መጥቀስ እንችላለን፡፡ ነገር ግን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያደረገው ነገር ኹላችንንም የሚያስተምር ነውና እሱን ብንመለከት፡፡ ኹላችኁም እንደምታውቁት አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ 40 ቀንና 40 ሌሊት ጾሟል /ማቴ.4/፡፡ ሲጾምም ዲያብሎስን ድል አድርጎ አሳይቶናል፡፡ ጌታችን ይኽን ያደረገበት ምክንያት ዲያብሎስን ለማሸነፍ እኛም የጾምን ትጥቅ መታጠቅ እንዳለብን ሲያስተምረን ነው፡፡ እዚኽ ጋር ምናልባት ከእናንተ መካከል፡- “አባታችን! ቅድም እንደነገርከን እነ ሙሴ፣ እነ ኤልያስ 40 ቀንና 40 ሌሊት ጾመዋል፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ልክ እንደ ሙሴና እንደ ኤልያስ አንዲት ቀን እንኳን ሳይጨምር መጾሙ ለምንድነው?” ብሎ የሚጠይቅ ሊኖር ይችላል፡፡ ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይኽን ያደረገው ያለ ምክንያት አይደለም፡፡ ጌታችን እንዲኽ የጾመው እኛን በጣም ስለሚወደን ነው፡፡ ምክንያቱም ሲዠምርም የእኛን ሥጋ ሳይዋሐድ መምጣት ይችል ነበር፡፡ ነገር ግን በጣም ስለሚወደን ሥጋችንን ተዋሐደ፤ ከእኛ ከሰዎች ያልራቀ መኾኑን ሲያስረዳንም ጾመ፡፡ እንግዲኽ ከላይ ለማየት እንደቻልነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ሌሎችም ቅዱሳንም በመጾማቸው ምክንያት ዲያብሎስን አሸንፈውታል፡፡ በተለይ ቅዱሳኑ በመጾማቸው ምክንያት ለሥጋቸውም ለነፍሳቸውም ብዙ ጥቅምን አግኝተዉበታል፡፡ ስለዚኽ እጅግ የምወዳችኁ ልጆቼ! የጾም ጥቅም እንዴት ትልቅ እንደኾነ እየተማርንና እየተመለከትን ሳለ የጾም ወራት ሲቃረብ ደስ ብሎን ልንቀበለውና ንቁዎች ኾነን እጅግ ብዙ ጥቅምን ልናገኝበት ይገባናል ብዬ እማልዳችኋለኹ፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “የውጭው ሰውነታችን ቢጠፋ እንኳን የውስጡ ሰውነታችን ዕለት ዕለት ይታደሳል” ብሎ እንዳስተማረን /2ኛ ቆሮ.4፡16/ ጾም ሲገባ እጅግ ደስ ሊለን ይገባል፡፡ ከዚኽ የሐዋርያው ቃል እንደምንረዳው ጾም ማለት ነፍሳችን የበለጠ የምትወፍርበት መንገድ ነው ማለት ነው፡፡ እንጀራ ሥጋችን እንዲወፍር እንደሚያደርገው ኹሉ ጾም ደግሞ ነፍሳችን እንድትወፍር ያደርጋታል፡፡ ጾምን የምታዘወትር ነፍስ ከእግዚአብሔር ጋር ያላት ቀረቤታ እጅግ ስለሚጨምር ገና በዚኽ ምድር ሳለች ቅድስና በቅድስና እየጨመረች፣ ምሥጢራተ እግዚአብሔርን እያስተዋለች፣ የመንግሥተ ሰማያትን ጣዕም እየቀመሰች ትሔዳለች፡፡ እጅግ ብዙ ጭነትን የተሸከመች መርከብ ባሕሩንና ወጀቡን ማለፍ እንደሚያቅታት ኹሉ መብልና መጠጥ የሚያበዛ ሰውም የዚኽን ዓለም ወጀብ ማለፍ አይችልም፡፡ ቀለል ያለና ተመጣጣኝ የኾነ ጭነትን የያዘች መርከብ ግን ብዙ ችግር ሳይገጥማት የታሰበላት ቦታ በታሰበላት ጊዜ ትደርሳለች፡፡ መብልና መጠጥን ሳያበዛ ጾም የሚወድ ክርስቲያንም ንቃተ ኅሊናው ብሩህ ነው፡፡ በዚኽ ምድር በሚያጋጥሙት ችግሮችም በቀላሉ እጅ አይሰጥም፡፡ ዛሬ ላይ በዚኽ ምድር የሚያጋጥሙት ጊዜያዊ ችግሮች እንደ ጥላና ሕልም እንደሚያልፉ ይገነዘባል፡፡ እንዲኽ እንዳናስብና በዚኽ ምድር በሚያጋጥሙን ጥቃቅን ችግሮች እንድንጨናነቅ የሚያደርጉን በመንፈሳዊ ሕይወታችን እጅግ ቸልተኞች ስንኾን ነው፡፡ ምክንያቱም የዘወትር ሐሳባችን መብልና መጠጥ ላይ ከኾነ በመንፈሳዊ ሕይወታችን ደካሞች ነው የምንኾነው፡፡ ሥጋችን ይወፍራል፡፡ የማሰብና የማመዛዘን ዓቅማችን ይቀንሳል፡፡ ለነፍሳችን ምንም በማይጠቅም እንተ ፈንቶ ነገርም ተጠምደን እንውላለን፡፡ ስለዚኽ እጅግ የምወዳችኁ ምእመናን ሆይ! በጊዜያዊ ነገር ብቻ እየተጠመድን በመንፈሳዊ ሕይወታችን ቸልተኞች አንኹን ብዬ እለምናችኋለኹ፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወታችን ቸልተኞች ስንኾን የምንጐዳው በሚመጣው ዓለም ብቻ አይደለም፡፡ በዚኽ ምድር ሳለንም በመብልና በመጠጥ ብዛት ምክንያት የሚመጡ ብዙ በሽታዎች ተጠቂዎች ነው የምንኾነው፡፡ እኛ በሐዲስ ኪዳን ያለን ክርስቲያኖች ነን፡፡ በዚያ በጨለማው የብሉይ ኪዳን የነበሩ ሰዎች እንኳን በመንፈሳዊ ሕይወታቸው ቸልተኞች እንዳይኾኑ ይልቁንም ጾምን እንዲያዘወትሩ ይነገራቸው ነበርና እባካችኁ ቸልተኞች አንኹን ብዬ እለምናችኋለኹ፡፡ እስኪ አምላካችን እግዚአብሔር ምን እንደሚለን እናድምጥ፡- “ክፉውን ቀን ከእናንተ ለምታርቁ፣ የግፍንም ወንበር ለምታቀርቡ፣ ከዝሆን ጥርስ በተሠራ አልጋ ላይ ለምትተኙ፣ በምንጣፋችኁም ላይ ተደላድላችኁ ለምትቀመጡ፣ ከበጐችም መንጋ ጠቦትን ከጋጥም ውስጥ ጥጃን ለምትበሉ፣ በመሰንቆም ድምፅ ለምትንጫጩ፣ እንደ ዳዊትም የዜማን ዕቃ ለምታዘጋጁ፣ በፋጋ የወይን ጠጅ ለምትጠጡ፣ እጅግ ባማረ ሽቱም ለምትቀቡ፣ ስለዮሴፍ መከራ ግን ለማታዝኑ ለእናንተ ወዮላችኁ” /አሞጽ.6፡3-6/፡፡ ልጆቼ! እግዚአብሔር በነቢዩ አሞጽ አድሮ እስራኤላውያንን እንዴት አድርጐ እንደወቀሳቸው፣ መብልንና መጠጥን ሲያበዙ እንዴት አድርጐ እንደገሠፃቸው አያችኁን? እንደዉም በደንብ አስተውላችኁት ከኾነ አብዝተው መብላታቸውንና መጠጣታቸውን ብቻ አይደለም የወቀሳቸው፡፡ ጨምሮም እነዚኽ ሰዎች ከዚኽ በላይ ደስታ እንደሌላቸው፥ ደስታቸው ግን እንደ ጧት ጤዛ ብዙ እንደማይቆይ ነግሯቸዋል፡፡ አኹን በዚኽ ምድር ላይ የምንመለከታቸው ነገሮች ልክ እንደዚኽ የሚጠፉ ናቸው፡፡ ክብርም በሉት፣ ሥልጣንም በሉት፣ ሀብትና ንብረትም በሉት፣ የምናገኛቸው መልካም አጋጣሚዎችም በሉት፣ ኹሉም ጠፊዎች ናቸው፡፡ ከእነዚኽ አንዱ ስንኳ ዘለዓለማዊ የለም፡፡ ኹሉም እንደ ወራጅ ውኃ የሚያልፉ ናቸው፡፡ የሙጥኝ ብለን ልንይዛቸው ብንሞክር እንኳን ብዙ ልናቆያቸው አንችልም፡፡ የምንቀረው ባዶአችን ነው፡፡ መንፈሳዊ ነገሮቻችን ግን የእነዚኽ ተቃራኒ ናቸው፡፡ እንደ ጽኑ ዐለት አይንቀሳቀሱም፤ ትተዉን አይሔዱም፡፡ በጊዜ ብዛት አይበላሹም (Expire date የላቸውም)፡፡ እስኪ አኹን ልጠይቃችኁ ልጆቼ! የማይጠፋውን ሀብት በሚጠፋው ሀብት የምንቀይረው እንዴት ብንደነዝዝ ነው? ዘለዓለማዊውን ደስታችን በዘለዓለማዊ ለቅሶ፣ ዘለዓለማዊውን ሕይወት በጊዜያዊ ሕይወት፣ ዘለዓለማዊውን ሀብታችን በሚጠፋ ሀብት መቀየራችን ምን ዓይነት ስንፍና ቢይዘን ነው? ስለዚኽ በዚኽ ጕባኤ የታደማችኁ ኹላችኁም ምእመናን ሆይ! እለምናችኋለኹ፡፡ ለመንፈሳዊ ሕይወታችን ተገቢውን ትኵረት እንስጠው፡፡ ለምድራዊ ነገር ፈጣን ኾነን ሳለ ለመንፈሳዊ ሕይወታችን ሰነፎች አንኹን፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወታችን ጠንካሮች እንድንኾን የምታደርገንን ጾምንም እንውደዳት፡፡ ከርሷ ጋር ያሉት ሌሎች በጐ ምግባራትንም (ጸሎት፣ ስግደት፣ ምጽዋት፣ ወዘተ) እንውደዳቸው፡፡ ከዛሬ በኋላ አዲስ የአኗኗር ስልትን (Renewed Life style) እንዠምር፡፡ በየቀኑ መልካም ምግባራትን መሥራት የሚያስደስተን እንኹን፡፡ በዚኽ በምንቀበለው ጾም ብዙ መንፈሳዊ ተግባራትን እናድርግና ራሳችንን በሰማያዊ ክብር እናስጊጥ፡፡ እንዲኽ የምናደርግ ከኾነ ጾሙ ሲፈታ ወደ ቅዱስ ሥጋውና ወደ ክቡር ደሙ ሳናፍር መቅረብ ይቻለናል፡፡ በልቡናችን ውስጥ የነበረውን ቆሻሻ ኹሉ ስለምናስወግድ ንጹሓን ኾነን ከዚያ ሰማያዊ ማዕድ ተሳታፊዎች መኾን እንችላለን፡፡ ከዚያም በጐ ምግባራችን የማይጠፋና ኃይልን ስለሚያገኝ በመጨረሻው ቀን ኑ እናንተ የአባቴ ብሩካን የሚለውን የሕይወት ቃል መስማት እንችላለን፡፡ የእግዚአብሔር ጸጋ ስለማይለየን ሕይወታችን በጸሎትና በምልጃ የተሞላ ይኾናል፡፡ እግዚአብሔርን ደስ አሰኝተን መኖር ይቻለናል፡፡ ይኽን እንድናደርግ ሰውን በመውደዱ ሰው የኾነው ክርስቶስ ይርዳን፡፡ አሜን!!! ላይ ኖቬምበር 24, 2014 ምንም አስተያየቶች የሉም: ይህን ኢሜል አድርግጦማር አድርግ!Twitter ላይ አጋራFacebook ላይ አጋራለPinterest አጋራ ጾም - ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዳስተማረው (ክፍል አንድ) (መቅረዝ ዘተዋሕዶ፣ ረቡዕ ኅዳር 10 ቀን፣ 2007 ዓ.ም.)፡- በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!! ይኽን ጽሑፍ ወደ አማርኛ የመለስነው ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የኦሪት ዘልደትን መጽሐፍ ከተረጐመበት ከመዠመሪያው ድርሳኑ ላይ ነው፡፡ ስብከቱ ረዘም ስለሚልም አንዱን ድርሳን በክፍል በክፍል አድርገን አቅርበነዋል፡፡ ሊቁ ይኽን ስብከት የሰበከው ዐቢይ ጾም ሊገባ ጥቂት ቀናት ሲቀሩት እንደኾነ ከስብከቱ መረዳት እንችላለን፡፡ ምንም እንኳን ከፊታችን የምንቀበለው ጾም ጾመ ነቢያት ቢኾንም የጾም ዓላማው አንድ ነውና ለዚኽም ጊዜ ይስማማል በማለት አኹን ልናቀርበው ወደናል፡፡ በመኾኑም ልክ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በሚያስተምርበት ዓውደ ምሕረት እንዳለን ኾነን በማሰብ ፊታችንና መላ ሰውነታችንን በትእምርተ መስቀል ሦስት ጊዜ በማማተብ ቃሉን በትሕትና እንድንማር እንጋብዛችኋለን፡፡ መልካም ጉባኤ!!! ቤተ ክርስቲያን እንደዚኽ በልጆቿ ደምቃ ሳይ፥ እናንተም ጕባኤውን ለመታደም ደስ ብሏችኁ ስትመጡ ዐይታ ነፍሴ ሐሴት አደረገች፤ ደስም ተሰኘች፡፡ ጕባኤውን ለመታደም መጥታችኁ ፊታችኁ እንደምን በደስታ እንደተመላ ዐይቼ ጠቢቡ ሰው “ደስ ያለው ልብ ፊትን ያበራል” እንዳለው ልቤ በደስታ ፍንክንክ አለብኝ /ምሳ.15፡13/፡፡ ቀጣዩ ወራት የቁስለ ነፍሳችንን መድኃኒት የምናገኝበት ወርሓ ጾም ነውና ይኽን የምስራች እነግራችኍ ዘንድ ዛሬ ጧት ከወትሮው በተለየ ትጋት ነው የተነሣኹት፡፡ ደግ አባት ነውና ባለፉት ወራት የሠራነውን ኃጢአት ሥርየት እናገኝበት ዘንድ ሽቶ አምላካችን ፈውሰ ሥጋ ፈውሰ ነፍስ የሚኾን ቅዱስ ጾምን አዘጋጅቶልናል፡፡ ስለዚኽ ከእኛ መካከል አንድ ስንኳ ተስፋ የሚቈርጥ፣ በድብርትም የሚያዝ ከቶ አይገኝ፡፡ ይልቁንም ደስ የምንሰኝበትን፣ የሕመማችንን ፈውስ የምናገኝበትን መድኃኒት እረኛችን እግዚአብሔር አዘጋጅቶልናልና ወርሓ ጾም በመምጣቱ ደስ ልንሰኝ ይገባል፡፡ አሕዛብ ይኽን ወራት ደስ ተሰኝተን መቀበላችንን አይተው ይፈሩ፡፡ በእኛና በእነርሱ መካከል ሰፊ ልዩነት እንዳለ አይተውም ይማሩ፡፡ በዓላቶቻቸው በዘፈንና በስካር፣ ይኽም በመሰለ ሌላ ርኵስ ግብር የተሞሉ ናቸውና፡፡ ምእመናን ከዚኽ አሕዛባዊ ግብር ተለይተን በዓል ልናደርግ ይገባናል፡፡ በምግባር በትሩፋት ልናጌጥ ልናሸበርቅ ይገባናል፡፡ እውነተኛ ጾም ማለት ሰዎች የሚድኑበት፣ ሰላምና አንድነት የሚያገኙበት፣ ክፉ ግብርን ቈርጠው የሚጥሉበት፣ አርምሞን ገንዘብ የሚያደርጉበት፣ በመብልና በመጠጥ ከመንጋጋት የሚላቀቁበት ነው፡፡ በዚኽ በወርሓ ጾም ዕረፍተ ሥጋ ወነፍስ እንዲኹም አርምሞ፣ የነፍስ ወሥጋ ፍቅርና ደስታ፣ ራስን መግዛት፣ እንዲኹም ሌሎች እዚኽ መዘርዘር የማንችላቸው ብዙ የብዙ ብዙ ምግባር ትሩፋቶችን ገንዘብ የምናደርግበት ነው፡፡ እንኪያስ እጅግ የምወዳችኁ ምእመናን ሆይ! አንዳች የሚረባንን ነገር ይዘንም ወደ ቤታችን እንመለስ ዘንድ ቃላችንን በታላቅ ትጋትና ጉጉት ኾናችኁ ተቀበሉት ብዬ እማልዳችኋለኹ፡፡ ኹላችንም ወደዚኽ ጉባኤ የመጣነው ሌላ ነገር ሽተን አይደለምና፡፡ ወሬ ለማውራት፣ የተባለውን ነገር ምንም ሳንሰማ ለማጨብጨብ፣ ከዚያም ምንም የሚረባ ነገርን ሳንይዝ ወደ ቤታችን ለመመለስ ወደዚኽ ጉባኤ አልመጣንምና ቃላችንን በማስተዋል ትከታተሉት ዘንድ እማልዳችኋለኹ፡፡ እግዚአብሔር በእኔ በባርያው አድሮ ለነፍሳችን ድኅነት የሚጠቅም ነገር ይናገራል፡፡ ስለዚኽ እጅግ ብዙ የሚጠቅም ነገር ሰንቀን ወደ ቤታችን እንመለስ ዘንድ እማልዳችኋለኹ፡፡ ምክንያቱም ቤተ ክርስቲያን ማለት ሐኪም ቤት ናት፡፡ ወደርሷ የሚመጡትም ተገቢውን መድኃኒት አግኝተው መሔድ አለባቸው፡፡ ቃሉን ብቻ አድምጠን ነገር ግን በሕይወታችን አንዳች ተግባራዊ የኾነ ለውጥ ከሌለን ወደ ጉባኤ መምጣታችን፣ ቃለ እግዚአብሔር መማራችን አንዳች ረብሕ የለውም፡፡ ብጹዕ ሐዋርያ ጳውሎስ እንዲኽ እንዳለ፡- “በእግዚአብሔር ፊት ሕግን የሚያደርጉት ይጸድቃሉ እንጂ ሕግን የሚሰሙ ጻድቃን አይደሉምና” /ሮሜ.2፡13/፡፡ ክብር ምስጋና ለስም አጠራሩ ይኹንና አምላካችን ክርስቶስም፡- “በሰማያት ያለውን የአባቴን ፈቃድ የሚያደርግ እንጂ ጌታ ሆይ ጌታ ሆይ የሚለኝ ኹሉ መንግሥተ ሰማያት የሚገባ አይደለም” /ማቴ.7፡21/፡፡ ስለዚኽ እጅግ የምወዳችኁ ምእመናን ሆይ! ቃሉን በመስማታችን ብቻ አንዳች የምንጠቀመው ነገር ስለሌለ የሰማነውን የምናደርግ እንጂ የምንሰማ ብቻ አንኹን፡፡ እንዲኽ ከኾነም (ሰምተን የምንፈጽም ከኾነ) እምነታችን ሕይወት ያለው እምነት ይኾናል፡፡ ስለዚኽ እግዚአብሔር ስለ ጾም የሚያስተምረንን ትምህርት ለማዳመጥ እዝነ ልቡናችንን እንክፈት፡፡ ጾም ሙሽሪትን ትመስላለች፡፡ ሙሽሪትን በሠርግ አዳራሽ ኾነው የሚቀበሏት ሰዎች ቤቱን ያስጌጡታል፤ ይሸልሙታል፡፡ ወደ ሠርጉ አዳራሽ የሚገባውን ሰው የሠርግ ልብስ ለብሶ እንደኾነ፣ የቆሸሸ እንዳልኾነ አይተው ያስገቡታል፡፡ እኛም እንዲኽ ልንኾን ይገባናል ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡ ልቡናችንን በማንጻት፣ ልል ዘሊል ከመኾን በመራቅ፣ የክፋት እርሾን በማስወገድ፣ ከጾም ጋር አብረው የሚመጡትን የሚያጅቧትን መልካም ምግባራትንም ለመቀበል የልቡናችንን ውሳጤ በመክፈት የምግባር እናት፣ የማስተዋል እንዲኹሉም ለሌሎች ምግባራት ኹሉ ንግሥት የምትኾን ጾምን ልንቀበላት ይገባናል ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡ ይኽን ያደረግን እንደኾነ ታላቅ ሐሴት እናደርጋለን፤ ርሷም ቁስለ ነፍሳችንን ትፈውስልናለች፡፡ በሌላ አገላለጽ ብነግራችኁ ሐኪሞች በአንድ ታማሚ ሰውነት ውስጥ ያለውን ቆሻሻ፣ መርዘኛ ፈሳሽን ማስገድ ሲፈልጉ መዠመሪያ የሚያደርጉት ነገር ቢኖር ታማሚው ምግብ ከመውሰድ እንዲቈጠብ ነው፡፡ ታማሚው ለጊዜው ምግብን ከመብላት ካልተከለከለ ሓኪሞቹ የሚሰጡት መድኃኒት እንደተፈለገው ውጤት አይሰጥም፡፡ እኛም ቁስለ ነፍስ ቁስለ ሥጋ የምትፈውሰውን ጾም ስንቀበላት ከዚኽ በላይ ልንኾን ይገባናል ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡ ድኅነተ ሥጋ ድኅነተ ነፍስን የምንሻ ከኾነ ልቡናችንን ንጹሕና ንቁ በማድረግ ልንወስዳት ይገባናል፡፡ እንዲኽ ካልኾነ ግን ከጥቅሟ ይልቅ ጉዳቷ ያመዝናል፡፡ ዛሬ የምነግራችኁ ነገረ ለአንዳንዶቻችኁ እንዲኹ ተራ የልበ ወለድ ንግግር እንደሚኾንባችኁ አውቃለኹ፡፡ እኔ ግን በዓላማ (ድኅነተ ሥጋ ድኅነተ ነፍስን ለማግኘት) የምንጾም እንኹን እንጂ እንዲኹ የልማድ ባርያ አንኹን ብዬ እማልዳችኋለኹ፡፡ እስኪ ንገሩኝ! በየቀኑ ሆዳሞችና ሰካራሞች በመኾናችን የምናገኘው ጥቅም ምንድነው? አንዳች የምናገኘው ጥቅም የለም፡፡ ይልቁንም የከፋ ጉዳትን በራሳችን ላይ የምናመጣ ነን ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡ ከልክ በላይ ጠጥተን ስንሰክር የማስተዋል ልቡናችን ይጠፋል፤ የጾም ጥቅሟም አብሮ ይጠፋል፡፡ እስኪ ንገሩኝ! እስከ እኩለ ሌሊት ድረስ ብዙ መጠጥን ከሚጠጡ ሰዎች በላይ የሚያንገሸግሽ ምን አለ? ወይንን በመጠጣት በየመሸታ ቤቱ አድረው ፀሐይ ከምትወጣባቸው ሰዎች በላይ የሚያሳዝን ማን አለ? እነዚኽ በመጠጥ ብዛት የሚሰክሩ ሰዎች ከሚያገኙት ሰው ጋር ይጋጫሉ፤ ጠጪው ሰካራሙ ተብለው በማኅበረ ሰብኡ ይታወቃሉ፤ ቤታቸው የተናቀ ነው፤ የሚናገሩት ነገር ቁምነገር ስለሌለው ሕፃን ዐዋቂው ይሳለቅባቸዋል፡፡ ከዚኽም በላይ በጣም የሚያሳዝነው ነገር ደግሞ የእግዚአብሔር ቃል እንደሚል “ሰካሮች የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም” /1ኛ ቆሮ.6፡10/፡፡ ወዮ! … ወዮ! … ወዮ! … እንደ ጧት ጤዛ ለሚጠፋ ርካታ የዘለዓለምን መንግሥት ማጣት እንደምን ያለ ጉስቁልና ነው? እዚኽ ጉባኤ የተሰበሰብን ምእመናን በእንደዚኽ ዓይነት ስንፍና ከመያዝ እግዚአብሔር ይጠብቀን! እያንዳንዷን ቀን በትዕግሥትና ራስን በመግዛት ኾነን በዙርያችን ከሚያንዣብበው የዲያብሎስ ወጀብም ተጠብቀን ወደ ነፍሳችን ወደብ ይኸውም ወደ እውነተኛ ጾም ከርሷ የሚገኘውን ድኅነተ ሥጋ ድኅነተ ነፍስም እናገኝ ዘንድ እግዚአብሔር ይርዳን፡፡ ላይ ኖቬምበር 24, 2014 ምንም አስተያየቶች የሉም: ይህን ኢሜል አድርግጦማር አድርግ!Twitter ላይ አጋራFacebook ላይ አጋራለPinterest አጋራ በጣም አዲስ ልጥፎች በጣም የቆየ ልጥፍ መነሻ ደንበኛ ይሁኑ ለ፡ ልጥፎች (Atom) በአውሮጳ የካህናት አንድነት ማኅበር ሊቋቋም መሆኑ ታወቀ በ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከመላዋ አውሮጳ የተውጣጡ ካህናት፡” የ... በእንተ ሙኒክ ደብረ ብሥራት ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያንና ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ገብረ ሕይወት ፍስሐ [ጀርመን ] ምእመናን ከአንዱ ሀገር ወደ ሌላው ሀገር በተለያየ ምክንያት መሰደዳቸው አይቀሬ ነው:: ታዲያ ሲሰደዱ በሄዱበት ሀገር ሁሉ ቤተክርስቲያን ያስፈልጋቸዋል :: ምንም አያጠያይቅም የተመቻቹ ሁኔታዎችም አሉ... አስቸኩዋይ ጥሪ ለምእመናን በሙሉ የታላቁ የደብረ ሊባኖስ ገዳምን ለመርዳት ገዳሙ ጥሪ አስተላለፈ ገዳሙ በአሁን ሰዓት በመሬት መንሸራተት ምክንያት ከፍተኛ አደጋ እንደተጋረጠበት ተጠቅሶ ሰኔ 8 ቀን ከ7፡30 ጀምሮ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የስ... ጾመ ፍልሰታ የእመቤታችን ዕረፍት ጾመ ፍልሰታ የእመቤታችን ዕረፍት Written By Hulubante Abebe on Tuesday, August 5, 2014 | 1:02 PM መ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ ...
ደብዛዛ ጥቁር የእጅ መታጠቢያዎ አስገራሚ ይመስላል። ደብዛዛ ጥቁር ሲያጠናቅቅ ጭንቅላቱን ይለውጣል ፡፡ በተከታታይ ፍጹም ደብዛዛ ጥቁር ማጠናቀቅ ይቻላል። መልክን ሳይቀይር ደብዛዛ ጥቁር የእጅ መታጠቢያ ማጠናቀቅን በቀላሉ ለማፅዳትና ለመጠበቅ እንዲችሉ ያደርጉታል ፡፡ ሁሉም የ ‹Xinpaez› ንጣፍ ቀለም እንክብካቤ ምርቶች ያለ ሲሊኮን ፣ ሰም እና ሙሌት በልዩ ሁኔታ የተቀረጹ ናቸው ፣ ይህም ማለት አንፀባራቂ አይጨምሩም እና የደብዛዛውን ገጽታ አይረብሹም ማለት ነው ፡፡ ሰዎች ከማንፀባረቅ ይልቅ በቀላሉ የሚጣፍ ጭረት መናገሩ ይወዳሉ ፣ ግን ያ በትክክል ትክክል አይደለም! ባለቀለም ቀለም ጭረትን የሚያረጋግጥ አይደለም ፣ ግልጽ ነው ፣ ግን ቢያንስ ቢያንስ የሻወር ምልክቶች ላይ ችግሮች በጭራሽ አይኖርዎትም ፡፡ የጨረር-ቱኒል ቴክኖሎጂ ካልሲዎችዎን ሊተውልዎ የሚችል አስገራሚ የውሃ ግፊት ይሰጣል (ሻወር ውስጥ ቢለብሷቸው ብቻ) ፣ ግን ፍሰቱ ለስላሳ እና አስደሳች ነው! | 30% የውሃ ቆጣቢን በማግኘት በሚያስደንቅ ኃይል እና ፍሰት ፍጥነት በአጉሊ መነጽር የተደባለቀ አየር እና ውሃ ጠብታዎችን የሚያፈነጥቅ የጨረር ቀዳዳ ማይክሮ-ጀት ዥዋዥዌ የኃይል ዋሻዎች ይፈጥራሉ ፡፡ አብሮገነብ የውሃ ማጣሪያ ማድረስ የላቀ ባለብዙ-ደረጃ የውሃ ማጣሪያ ለጤናማ ፣ ወጣት ለሚመስሉ ቆዳ እና ፀጉር። የዲስክ ማጣሪያ ቆሻሻዎችን እና ቆሻሻዎችን በማገድ የሻወርን ውሃ ያጸዳል ፡፡ የእጅ ማጣሪያ ካርትሪጅ እርሳሶችን ፣ ክሎሪን ፣ ፀረ-ተባዮችን እና ከባድ ብረቶችን ለማስወገድ ፣ ዝገትን ፣ ኖራን እና ሽቶዎችን ለመከላከል ፣ ውሃ ለማለስለስ እና የ PH ሚዛኑን ለማሻሻል ኃይለኛ KDF ፣ ካልሲየም ሰልፌት እና ገባሪ ካርቦን ያጣምራል ፡፡
ቆልዑ ንጡፋት ምዃን ዝፈትዉ ኮይኖም ብዙሓት ጋንታታት ስፖርት ከኣ ብዙሕ ኣወንታዊ ንጥፈታት እዩ ዘለወን። ኣብ ከባቢኻ ዘለዋ ጋንታታት ስፖርት ኣየኖት ምዃነን ፈሊጥካ ተወከሰን መታን ውላድካ ክጽንበረን። ውላድካ ሓደ ዓይነት ስፖርት ምስ መረጸ ንውላድካ ኣመዝጊብካ ክፍሊት ኣባልነት ክትከፍል ኣለካ። ቆልዑ ኣብ ልምምድ ኣብ ሰዓቶም ክርከቡ ንኣሰልጣኒ፡ደቅ ጋንትኡ ኣገዳሲ እዩ፡ ከምኡውን ውላድካ ክዳሎ ቅሩብ ግዜ ይረክብ። ቆልዑ ኣብ ንኡስ ዕድሚኦም ኣብ ልምምድ ክሳተፉ ልሙድ ተርእዮ እዩ። ንክትሰምዕ ጠውቅ: ኣብ ጋንታ ስፖርት ብኸመይ ኢኻ ኣባል ትኸውን፧ ፋልማይ ትሳተፎ ልምምድ ዕድመኻ ብዘየገድስ ስፖርት ኣብ ዝኾነ ግዜ ክትጅምር ትኽእል ኢኻ፡ ሓሊፉካ እዩ ዝበሃሎ ኣይኮነን። ብዙሓት ቤት-ትምህርቲ ክጅምሩ ከሎዉ ደቅ ሽዱሽተ ዓመት ምስ ኮኑ እዮም ዝጅምሩ። ገሊኦም ዓይነታት ስፖርት ንካብኡ ዝንእሱ ቆልዑ ከማን ባይታ ኣጣጢሐን የጀምራ እየን። ቆልዑ ኣብ ከባቢኦም ኣብ ስፖርት ክነጥፉ ልሙድ ተርእዮ ኮይኑ ተደላዪ እዩ ድማ። መታን መገዲ ክሓጽረሎም፡ ከምኡውን እቶም ንጥፈታት መብዛሕትኡ ግዜ ምስ ደቅ ክላሶም ስለዘካይዱዎም። ነቶም ቆልዑ ምቾትን ውሕስነትን ክመስመዖም ምግባር እዩ እቲ ቀንዲ ዘገድስ። ገሊኦም ቆልዑ ዝተወሰነ ዓይነት ስፖርት ወይ ንጥፈት ከካይዱ ይደልዩ፡ ገሊኦም ቆልዑ ድማ ኣዕሩኽቶም ይገብሩዎ ብምህላዎም ዝተባብዑ ኣሎዉ። ሓንሳብ ሓንሳብ ወለዲ ውን ደቆም ስፖርት ክጅምሩ የተባብዑዎም እዮም። ቆልዑ ነንበይኖም ስለዝኾኑ ዝተፈላለዩ ዝንባለታት ስለዘለዎም ወለዲ ደቆም ክፈትውዎ ይኽእሉ እዮም ኢሎም ዝግምቱዎ ንክረኽኽቡሎም ክሕግዙዎም ይኽእሉ እዮም። ውላድካ ነቲ ንጥፈት ዝፈትዎ እንተኾይኑ ወይ እንተደኣ ፈትዩዎ ክቕጽሎን ንነዊሕ ግዜ ባህታ ክፈጥረሉ ዘሎ ተኽእሎ ይዛይድ እዩ። ንቤት-ትምህርቲ ውን ኣብቲ ትቕመጡሉ ቦታ እተን ዝቐረባ ጋንታታት ስፖርት ኣየኖት ምዃነን ምሕታት ይከኣል እዩ። ኩሉ ግዜ ክሕግዘካ ዝኽእል ሰብ ኣሎ። ንኣብነት ቋንቋ እንተደኣ በርቲዑካ ንመምህር ወይ ኣብ ኮሙነ ዘሎ ተወካሲ ኣካል ክትሓቶም ትኽእል ኢኻ፡ ንሶም ድማ ምናልባሽ ምስ ዝምልከቶ ኣካል ናይታ ጋንታ ስፖርት ከራኽቡኻ ይኽእሉ ይኾኑ። ኣብ ገሊኦም ኮሙነታት ድማ ኣብ ሽማግለ ስፖርት ዝሰርሑ ክሕግዙኻ ዝኽእሉ ሰራሕተኛታት ኣሎዉ። ምስ መራሒ ክለብ/ተወካሲ ኣካል ምስ ተራኸብካ ልምምዳት ኣበይን መዓስን ከምዝካየዱ፡ ከምኡ ውን እንታይ ዓይነት መሳርሒታት ከምዘድሊ ክትሓትት ኣገዳሲ እዩ። ኣብ ቀዳማይ ልምምድ ክትሳተፍ ከለኻ ቅኑዕ መሳርሒታት ዋላ እንተዘይሃለወካ ምንም ዝብል ኣይኮነን፡ ምኽንያቱ መጀመርታ ክትሳተፍ ከለኻ ምስኦም ምልላይ እዩ ዝለዓለ ኣገዳስነት ዘለዎ፡ ንዓኻን ንውላድካን። ገሊኦም ዓይነታት ስፖርት ውሕስነት ንምዕቃብ ገለ ተወሳኺ መሳርሒታት ይሓቱ እዮም። ዝኾነ ካልእ ሕቶ ምስ ዝህልወካ ምሕታት ከሰክፈካ የብሉን። ኣብ ልምምድ ኣብ ሰዓትካ ክትርከብ ኣገዳሲ እዩ፡እንተተኻኢሉ ከማን ልምምድ ቅድሚ ምጅማሩ ገለ ደቓይቅ ኣቐዲምካ ክትመጽእ እዩ ዝሓሸ። ሽዑ ምስ ኣሰልጣኒ ወይ ካልኦት ዓበይቲ ክትዘራረብ ግዜ ይህልወካ። ግዜ ምኽባር ክበሃል ከሎ ብእዋኑ ቅድሚ ልምምድ ምጅማሩ ክትርከብ ኣለካ ማለት እዩ። ከምኡ እንተደኣ ጌርካ ኣሰልጣኒ ስርሑ ተቃልለሉን ውላድካ ንኽዳሎ ቅሩብ ግዜ ይረክብን ማለት እዩ። ኣሰልጣኒ ኣብኡ እንተሃልዩ ንሱ ወይ ንሳ እዩ ልምምድ ክካየድ ከሎ ዝውስን፡ ንስኻ ከም ወላዲ ውላድካ እዚ ከኽብሮ ክትሕግዞ ኣገዳሲ እዩ።ምስ ኣሰልጣኒ ክትዛረብ እንተተደሊኻ ተዛረቦ ኢኻ፡ ግን ዘረባ ዓበይቲ ምስ ዓቢ ሰብ ክትዘራረበሉ ከምዘለካ ኣይትረስዕ ኢኻ። ኖርወየኛ ዘይትኽእል እንተኾንካ ንውላድካ ከም ኣተርጓሚ ኣይትጠቐመሉ፡ ኣብ ክንድኡ ቋንቋዊ ሓገዝ ክግበረልካ ዘሎ ዕድላት ኣጻሪ። መኪና ዘይብልካ እንተኾይንካ ውላድካ ካልኦት ናብ ልምምድ ክማልኡዎ ዝኽእሉ እንተኾይኖም ሕተት። ብዙሓት ብእግሮም ዝኸዱ፡ብሽግለታ ዝዝውሩ ወይ ኣውቶቡስ ዝወስዱ ኣሎዉ። እቶም ዝነኣሱ ቆልዑ ምስ ወለዶም ኣብ ልምምድ ክመጹ ልሙድ ተርእዮ እዩ። እንታይ እዩ ልሙድ ንምፍላጥ ንኣሰልጣኒ ምሕታት ወይ ምዝታይ ጠቓሚ ከይኮነ ኣይተርፍን እዩ፡ ማለት ካብ ስፖርት ናብ ስፖርት ክፈላለ ዝኽእል ኮይኑ ጎኒ ጎኑ ድማ እቶም ቆልዑ ነንበይኖም ብምዃኖም ዘድልዮም ደገፋት ክፈላለ ይኽእል እዩ፡ እዚ ንባዕሉ ንቡር እዩ። እቲ ቀንዲ ዘገድስ ውላድካ ውሕስነት ክስመዖን ክምችኦን እዩ። ውላድካ ኣብ ሓደ ዓይነት ስፖርት ክሳተፍ እየ ኢሉ ምስ ወሰነ ኣብቲ ጋንታ ስፖርት ከተመዝግቦ ኣለካ። ከም ኣባል ንኽትምዝገብ ወይ ውላድካ ንኸተመዝግቦ ስም፡ዕለተ-ልደት፡ጾታ፡ኣድራሻ ገዛ፡ ቁጽሪ ተለፎንን ኢመይልን ኣብ አለክትሮኒካዊ መዝገብ ኣባልነት ናይታ ጋንታ ስፖርት ከተእቱ ኣለካ። ብዙሓት ጋንታታት ስፖርት ‘’Min idrett’’ ዝበሃል ኣገልግሎት እየን ዝጥቀማ። ከም ተወሳኺ ክፍሊት ኣባልነት ክትከፍል ኣለካ፡ ከምኡውን ካብቲ ክፍሊትን ምዝገባን ዝተመዝገበሉ ዕለት ኣትሒዝካ ከም ኣባል ኢኻ ትቑጸር። ክፍሊት ኣባልነት ዓመታዊ እዩ ክኽፈል ዘለዎ። እታ ጋንታ ስፖርት ቅኑዕ ሓበሬታ ክወሃባ ኣገዳሲ እዩ መታን ሓበሬታ ክትለዋወጡ። እቶም ዝነኣሱ ቆልዑ ወለዶም እዮም ሓበሬታ ዝለዋወጡን ርክባት ዘካይዱን፡ ይኹን ደኣ እምበር እንዳዓበዩ ምስ መጹ ኣሰልጣኒ ምስቶም ስፖርተኛታት ብቐጥታ ሓበሬታ ክለዋወጥን ክራኸብን ይኽእል እዩ። ብዙሓት ጋንታታት ኣብ ፈይስቡክ፡ ስፖንድ ወይ ካልኦት ማሕበራዊ መራኸቢታት ኣገደስቲ መልእኽታት ዝህባሉ ናተን ጉጅለታት ኣለወን። ልምምዳት ምስራዝ፡ ልምምድ ዝካየደሉ ግዜ ምቕያር፡ መጸዋዕታ ኣኼባ ንወለዲ ወይ ወፈራ ክካየድ ከምዝኾነ ክኾኑ ይኽእሉ እዞም መልእኽትታት። ብዛዕባ እዚ ውላድካ ክምዝገብ ከሎ ነቲ ኣሰልጣኒ ክትሓቶ ትኽእል ኢኻ። ጽቡቕ ርክብ ክህሉ ንጋንታ ስፖርት፡ንዓኻ ከም ወላዲ ንውላድካን ብጣዕሚ ኣገዳሲ እዩ። ውላድካን ንስኻን ብዝተኻእለ መጠን ከምዝምቸኣኩም ምግባር እዩ እቲ ዕላማ፡ ነዚ ክውን ንምግባር ድማ ካብ ኩሎም ኢድ ዘለዎም ሰባት ጻዕሪ ይሓትት እዩ። ንምኽፋል ሓገዝ ዘድልየካ እንተኾይኑ ንቤት-ጽሕፈት ናቭ/ኮሙነ ወይ ኣገልግሎት ስደተኛታት ከተመልክት ትኽእል ኢኻ። ገሊአን ጋንታታት ስፖርት ድማ ሓገዛ ክወሃበካ ከተመልክተሉ ትኽእል ናተን ካዝና ስምረት/ሓድነት ኣለወን። ብዝተረፈ ተወሳኺ ሓበሬታ ንምርካብ ብዛዕባ ስፖርትን ቁጠባን ዘዳለናዮ ክፋል ስምዓዮ።
ቅድሚ ዓሰርተ ዓመታት ተመራመርቲ ስነ-ጥንቲ እስራኤል ኣብታ ትውልዲ ማርያም መግደላዊት ዝዀነት ከተማ ሚግዳል፡ ናይ ጥንቲ ምኵራብ (ቤት ጸሎት) ረኺቦም ነይሮም። ሕጂ ድማ ኣብ ካልእ ወገን እቲ ጽርግያ ካልእ ምኵራብ ምርካቦም ተፈሊጡ ኣሎ። እዞም ክልተ ኣብያተ-ጸሎት ኣብ እዋን የሱስ ክርስቶስ ዝነበረሉ ግዜ ዝተረኽቡ እንኮ ቅዱሳን ስፍራ ምዃኖም’ዩ። ተመራማሪት ስነ-ጥንቲ ዩኒቨርስቲ ሃይፋ ዝዀነት ዲና ኣይሻሎም ጎርኒ ብዛዕባ’ቲ ርኸበት ኣመልኪታ ከምዚ ትብል፤“ናብ ቀዳሞት ዓመታት ምውላድ ክርስቶስ ዝነበረ ኣከባቢ ኢና ዘሎና። እዚ ርኽበት’ዚ ንጹር ናይ ግዜ ሰሌዳ ዘቐምጥ’ዩ። ካብዚ ዝቕድም ጭብጢ ዛጊት ኣይጸንሓናን። ስለዚ ከኣ’ዩ እዚ ኵዕታ’ዚ ኣዝዩ ኣገዳሲ ዝኸውን፡”ኢላ። ኣብቲ እዋን፡ ኣብ የሩሳሌም ዝርከቡ ኣመንቲ ኣይሁድ ንጸሎትን መስዋእቲን ኣብ ቤት መቕደስ የካይዱሉ ኣብ ዝነበሩ እዋን፡ ኣብ ሚግዳል ግን ኣመንቲ ኣብቲ ሕጂ ተረኺቡ ዘሎ ምኵራብ (ቤት ጸሎት)ብምዃን መጽሓፍ ቅዱስ የንብቡ ምንባሮም እቶም ተመራመርቲ የመልክቱ። ርኽበት እዚ ሓድሽ ቤት ጸሎት ብዙሕ ሓበሬታ ከም ዘፈልፈለ ኣብቲ ኵዕታ ዝሳተፉ ዘለዉ ተመራመርቲ ይገልጹ። እቲ ንምርምር ዝኵዓት ዘሎ ኣብቲ ኣቐዲሙ “ማግዳላ” ተባሂሉ ዝጽዋዕ ዝነበረ ቦታ ኰይኒ፡ ሰፊሕ መሬት ዝሽፍን’ዩ። ኣብቲ ስራሕ ተዋፊሮም ዝርከቡ ካብ ምዕራብ ቓዛ ዝመጹ ፍሊስጤማውያን ኰይኖም፡ ናብቲ ቦታ ክኣትዉን ክወጹን ወረቐት ፍቓድ እናርኣዩ’ዮም ዝመላለሱ። ብመሰረት ሕጊ እስራኤል፡ ዝዀነ ህንጻዊ ስራሓት ቅድሚ ምጅማሩን ምጽዳቑን ብተመራመርቲ ስነ-ኵዕታ ዳህሳስ ክግበረሉ ኣለዎ። ብኸምኡ’ዮም ድማ ሓያሎ ኣዝዮም ኣገደስቲ ታሪኻውያን ቅርስታት ብኣጋጣሚ ዝርከቡ ዘለዉ። እቲ ተመዲቡ ዝነበረ ስራሓት ጽርግያ ክቋረጽ ድዩ ወይስ ኣንፈት ክቕይር ዛጊት ብመንግስቲ ዝተዋህበ መግለጺ የሎን።ተመራመርቲ ግን ኣገዳስነት እቲ ርኽበት ኣብ ግምት ብምእታው ነቲ ናይ ህንጻ መደብ ክስረዝ ተስፋ ገይሮም ኣለዉ። ዋላ’ኳ የሱስ ክርስቶስ ኣብቲ ቦታ ይምህር ከም ዝነበረ ብሰፊሑ ይጸሓፍ ደኣ’ምበር፡ ዛጊት ካብ ተረኺቡ ዘሎ ኵዕታ ግን ብቐጥታ ንስም ክርስቶስ ዝጠቅስ ምልክት ኣይረኸቡን። ካልኦት ተመራመርቲ መጽሓፍ ቅዱስ ድማ ማርያም መግደላዊት ኣብዛ ሕጂ ተረኺባ ዘላ ምኵራብበጺሓ ክትከውን ከም እትኽእል ይእምቱ።
“ሲጋራ ማጨስ በሰውነት ውስጥ ያሉትን ሁሉንም የሰውነት ክፍሎች የሚጎዳ ነው፤ በዚህም በየዓመቱም ከ1 ነጥብ 2 ሚሊዮን በላይ ሰዎች ህይወታቸው ያጣሉ”ም ነው ያሉት ዳይሬክተሯ። ከሲጋራ በስተቀር የትንባሆ ምርቶችን መጠቀም በአፍሪካ እየጨመረ እንደመጣም ማትሺዲሶ ሞኤቲ አስረድተዋል። ሞይቲ ትንባሆ ማጨስን ማቋረጥ ለካንሰር፣ ለልብ ህመም፣ ለደም መርጋት (ስትሮክ) እና ለሌሎች በሽታዎች የመጋለጥ እድልን ለመቀነስ የሚያስችል መንገድ ከመሆኑም በሻገር ዕድሜን ይጨምራል ብለዋል። ትንባሆ ማቆም ከባድ ቢሆንም ዛሬ ለመጀመር ጥሩ ቀን ነው የሚል ምክር በማከልም ጭምር። “የማይቻል ይመስላል ወይም ማጨስ ትልቅ ችግር የሌለው ይመስላል፤ ግን ዛሬ የምታደረጉት ነገር ለወደፊቱ የጤና ችግሮች እና የከፋ ሞት ሊያስከትል ይችላል”ም ነው ያሉት የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ዳይሬክተር ማትሺዲሶ ሞኤቲ። በአፍሪካ ካሉ አምስት ጎረምሳዎች አንዱ ትንባሆ ይጠቀማል ያሉት ዳይሬክተሯ “ይህ መለወጥ አለበት፤ ሲጋራ ማጨስን አቁሙና የመፍትሔው አካል ይሁኑ” ሲሉም ምክር ለግሰዋል።
በፌደራል መንግስትና በህውሓት ታጣቂ ሃይሎች መካከል በደቡብ አፍሪካ ፕሪቶሪያ፣ ለአንድ ሳምንት ሲካሄድ የቆየው የሰላም ንግግር በስምምነት ተቋጭቷል። ሁለቱ ወገኖች ተኩስ ማቆምንና ህውሓትን ትጥቅ ማስፈታትን ጨምሮ በ12 ነጥቦች ላይ ከስምምነት ደርሰዋል። ሁለቱ ወገኖች ከስምምነት ላይ የደረሱት ደም አፋሳሹ የሰሜኑ ጦርነት ከተጀመረ ድፍን ሁለት ዓመት ሊሞላው አንድ ቀን ብቻ ሲቀረው ነበር፤ባለፈው ረቡዕ ጥቅምት 23 ቀን 2015 ዓ.ም፡፡ ታጣቂው ቡድን ህወኃት በትግራይ በነበረው የሰሜን እዝ ላይ አሰቃቂ ግድያና ጥቃት በመፈጸም ነበር የጦርነቱን እሳት የጫረው፡፡ በጦርነቱ ብዙ እልቂት፣ውድመትና መፈናቀል ደርሷል፡፡ በኢትዮጵያ ዘላቂ ሰላምና መረጋጋትን ለመፍጠር ምቹ ሁኔታን ይፈጥራል የተባለውና በሁለቱ ወገኖች የተፈረመው ይኸው የሰላም ስምምነት፤አሥራ ሁለት ነጥቦችን የያዘ ሲሆን ኢትዮጵያን አሸናፊ በማድረግ የተቋጨ ነው ተብሏል፡፡ ጠ/ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ባለፈው ረቡዕ ምሽት በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ባጋሩት መግለጫ፤ የሰላም ስምምነቱ “ከአራት ዓመት ተኩል በፊት የተጀመረውን ለውጥ ወደፊት ለማራመድ አስተዋጽኦው ከፍተኛ ነው” ብለዋል። የሰላም ስምምነቱን ተግባራዊ ለማድረግና ለሰላም ቁርጠኛ መሆናቸውንም ጠ/ሚኒስትሩ ገልጸዋል፡፡ የኢትዮጵያ ወዳጆች በጦርነቱ የተጎዱ የሰሜን ኢትዮጵያ አካባቢዎችን መልሶ ለመገንባትና በአጠቃላይ ላለው ልማት ድጋፋቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉም ጠ/ሚኒስትሩ በመግለጫቸው ጠይቀዋል። የፖለቲካ ምሁሩ ዶ/ር አንተነህ ተስፋዬ በደቡብ አፍሪካ የተደረሰውን የሰላም ስምምነት አስመልክቶ በሰጡት አስተያየት፤ሁለቱ ወገኖች የደረሱበት የሰላም ስምምነት ሁለት ዓመታትን ያስቆጠረውን ደም አፋሳሽ ጦርነት ለማስቆም የሚያስችልና የትግራይን ህዝብ መሰረታዊ ችግር የሚፈታ እንደሆነ ቢታመንም፣ ለአገሪቱ ዘላቂ ሰላም በማስፈኑና በዜጎች መካከል የተፈጠረውን ቂምና ቁርሾ በማስቀረቱ ረገድ ብዙም ተስፋ የሚጣልበት አይደለም ይላሉ፡፡ እርቅ ዘላቂነት የሚኖረው በመንግስታት መካከል ብቻ ሲካሄድ እንዳልሆነ የሚገልጹት ምሁሩ፤ዜጎች በሚፈጠረው እርቅ ውስጥ ተሳታፊ ሊሆኑና በአግባቡ ይቅር ሊባባሉ ይገባል ብለዋል። በጦርነቱ ቀጥተኛ ተጎጂ የሆኑት የአማራና አፋር ክልል ህዝቦችን ያገለለና እነሱ እንዲመክሩበት ያልተደረገ እርቅ፣ ከቂም በቀልና ቁርሾ የፀዳ ሊሆን አይችልም ሲሉም ይሞግታሉ፡፡ የፌደራል መንግስት ከተለያዩ አገራትና ተቋማት የሚደርስበትን ጫናና እጅ ጥምዘዛ ተቋቁሞ ቡድኑን በትጥቅ ትግል ካሸነፈና ድል ማግኘቱን ካረጋገጠ በኋላ ከህወሓት ጋር ለድርድር መቀመጡ ለዲፕሎማሲያዊ አካሄዱ የሚያስቆጥርለት ነጥብ እንዳለ ባይካድም፣ ከዜጎቹ ጋር ስለሚኖረው ሁኔታ ሊያስብበትና የጦርነቱ ሰለባ የሆኑ ዜጎቹን የድርድሩ አካል ሊያደርግ ይገባል ብለዋል፤አሁንም መንግስት ከዜጎቹ ጋር በተለይም ከአማራና አፋር ክልል ህዝቦች ጋር ሊወያይና ሊመካከር እንደሚገባ በማሳሰብ፡፡ የወልቃይትና ራያ ጉዳይም በአገሪቱ ህግ መሰረት ይፈታል የሚለው ደግሞ ወደ ከፋ ችግር ሊያስገባ የሚችል በመሆኑ ከፍተኛ ትኩረት ሊደረግበት ይገባል ብለዋል፤የፖለቲካ ምሁሩ፡፡ የሰላም ስምምነቱ የወገን እልቂትን የሚያስቆም በመሆኑ የሚደገፍ ነው ያሉት የኦፌኮ ሊቀመንበሩ ፕሮፌሰር መረራ ጉዲና በበኩላቸው፤በአገሪቱ ያለው ቀውስ እንዲቆም ግን ሁሉን አቀፍ የሆነ የሰላም ስምምነት ማድረግ ያስፈልጋል ብለዋል። የፌደራል መንግስቱ ከሁሉም ኃይሎች ጋር ሁሉን አቀፍ የሰላም ስምምነት ካላደረገ ወዴት እንደምንሄድ መተንበዩ አስቸጋሪ ነው ያሉት ፕሮፌሰሩ፤ይህ በማይሆንበት ሁኔታ የተጠበቀው ሰላም ሊመጣ እንደማይችል ተናግረዋል። መንግሥትና ህወኃት የተስማሙባቸው ዋና ዋና ጉዳዮች፡- የኢትዮጵያን ሉአላዊነትና የግዛት አንድነት ማረጋገጥና የኢፌዲሪ ህገ-መንግስትን ማስከበር፤ ህወሓት ሙሉ በሙሉ ትጥቅ እንዲፈታ ስምምነት ላይ ተደርሷል። በዚህ መሰረትም ስምምነቱ ከተደረገበት ቀን ጀምሮ ባሉ 30 ቀናት ውስጥ ቡድኑ ሙሉ በሙሉ ትጥቅ እንዲፈታ የሚደረግ ሲሆን፤ ይህንን ውሳኔ ተግባራዊ ለማድረግም የሁለቱ ወገን ከፍተኛ ወታደራዊ አመራሮች አመቺ ቦታ መርጠው እንዲነጋገሩ ስምምነት ላይ ተደርሷል። ስምምነቱ በተፈረመ አምስት ቀናት ውስጥ የሁለቱ ወገን ወታደራዊ አመራሮች የትጥቅ ማስፈታት ሂደት የሚመራበትን ዝርዝር አፈጻጸም በጋራ በማውጣት ተግባራዊ ስራዎች መስራት ይጀምራሉ። የሁለቱ ወገን ከፍተኛ ወታደራዊ መኮንኖች በተገናኙ አስር ቀናት ውስጥ ህወሓት ያሉትን ሁሉንም የቡድንና ከባድ መሳሪያዎችን ለመከላከያ ሰራዊት ያስረክባል። ስምምነቱ በተፈረመ በ7 ቀናት ውስጥ የፌደራል መንግስት መቀሌን ተረክቦ በከተማው ውስጥ እና ዙሪያ ሁሉንም አይነት የጦር መሳሪያ ያስፈታል። በመሬት ላይ ያለውን የፀጥታ ሁኔታ ከግምት ውስጥ በማስገባት የሕወሓት ተዋጊዎችን ከሰራዊቱ እንዲወጡ ለማድረግና መልሶ ወደ ማህበረሰቡ ለመቀላቀል የሚያስችል ስራ ለመስራት ስምምነት ላይ ተደርሷል። የጥይት ድምጽ በዘላቂነት እንዳይሰማ እና ጦርነቱ እንዲያበቃ የሚያስችል ዘላቂ የግጭት ማስወገድና የተኩስ አቁም ስምምነት ላይ ተደርሷል። በትግራይ ክልል ህገ-መንግስታዊ ስርዓትን ወደነበረበት ለመመለስ የሽግግር እርምጃዎችን ተግባራዊ ለማድረግ ከስምምነት ተደርሷል። በአጭር ቀናት ውስጥ በትግራይ አሁን ያለው የህወሓት መዋቅር ፈርሶ የፌደራል መንግስት የሚመራው የጊዜያዊ አስተዳደር ይቋቋማል። በሚዋቀረው ጊዜያዊ አስተዳደር ውስጥም የትግራይን ህዝብ የሚወክል አካል ይሳተፋል፡፡ የሚመሰረተው ጊዜያዊ አስተዳደር በሁሉም የትግራይ አካባቢዎች የማህበራዊ አገልግሎቶች በፍጥነት እንዲጀመሩ ሁኔታዎችን ያመቻቻል። ተግባራዊነታቸውንም ያረጋግጣል። በሁለቱም ወገኖች በኩል የጥላቻ ፕሮፓጋንዳን ለማስቆም ስምምነት ላይ ተደርሷል። ህወሓት ያለ ፌደራል መንግስቱ እውቅና ከማንኛውም የውጪ አካል ጋር ግንኙነት ማድረግ ያቆማል። እንዲህ አይነት ተግባር የሚፈጽሙ ግለሰቦች ካሉ በሀገሪቱ ህግ መሰረት የሚጠየቁ ይሆናል። የፌደራል መንግስት ህወሓትን ከአሸባሪነት መዝገብ ለማስወጣት የሚያስችል ሁኔታዎችን እንዲያመቻች ስምምነት ላይ ተደርሷል። አጨቃጫቂዎቹ የወልቃይትና የራያ ጉዳዮችም በአገሪቱ ህግ መሰረት የሚዳኙ መሆኑም በስምምነቱ ላይ ተጠቅሷል። Read 11534 times Tweet Published in ዜና More in this category: « ዓለም የሰላም ስምምነቱን አወድሶታል ክቡር ዶ/ር አሊ ቢራ ከዚህ ዓለም በሞት ተለየ » back to top ላንተና ላንቺ ጎጆ…የካንሰር ሕሙማን ማረፊያ ጎጆ የካንሰር ህሙማን ማረፊያ በአዲስ አበባ ተክለሀይማኖት በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል አካባቢ ወደጎላ ሚካኤል በሚወስደው መንገድ ከተክለሀይማኖት ጤና ጣቢያ ውስጥ የራሱን ማረፊያ በማሰራት ስራ የጀመረ ነው፡፡ ጎጆ እንዲመሰረት ምክንያት ከሆኑት መካከል ህብረተሰብ “ናሽናል አቪዬሽን ኮሌጅ ተምሮ ችግር የሚያወራና የሚያቃስት ሰው አይገኝም” Written by ናፍቆት ዮሴፍ ህልምን እውን አድርጎ የማለፍን ያህል ስኬት የለም የዛሬው እንግዳችን በኢትዮጵያ አየር መንገድ ውስጥ አብራሪ ነበሩ-ፓይለት። በኬንያ፣ በታንዛንያና አውስትራልያ በዚሁ ሙያ ለረዥም ዓመታት አገልግለዋል። ባጠቃላይ በዚህ ሙያ ውስጥ ከሩብ ክፍለ ዘመን ርዕሰ አንቀፅ በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ ከዕለታት አንድ ቀን ሁለት እውቅ ሀብታም ገበሬዎች በአንድ መንደር ይኖራሉ። ሁለቱም ራሳቸው ላይ ምናምኒት ፀጉር አልነበራቸውም። በዚህም ምክንያት “ሁለቱ እንቁላሎች” የሚል ቅጽል ስም ተሰጥቷቸው ነበር። በጣም የሚዋደዱ ባልንጀሮች ናቸው። አንድ
Anthony Martial leaves Man Utd and joins Sevilla on loan. Juventus signed Vlahović and Zakaria. Vamos.bet is the biggest betting company in Ethiopia. Frank Lampard is the new Everton's coach. Senegal is the first AFCON 2021 finalist, will they face off Egypt or Cameroon? Habesha offers the best betting odds in Ethiopia. Aubameyang aims to revive his career in Barcelona. Luis Diáz joins Liverpool from FC Porto. Adama Traoré heads to Barcelona on loan transfer. Halllo welcome Football ያንግ ቦይስ እና ቀይ ሰይጣኖቹ በቲያትር ኦፍ ድሪምስ አቻ ወጥተዋል! by Bereket Aberra 9. 12. 2021 goal.com የግሪንዉድ ድንቅ ጎል በራይደር ግብ ተጣፍቶ በኦልድትራፎርድ ጨዋታው 1-1 ተጠናቋል። ማንቸስተር ዩናይትድ ወደ መጨረሻው 16 ሲያልፍ የስዊዘርላንዱ ቡድን ከአውሮፓ ውድድር ውጪ ሆኗል! ለሙከራ የገባው የማንቸስተር ዩናይትድ ቡድን ረቡዕ በኦልድትራፎርድ ባደረገው የመጨረሻ የዩኢኤፍኤ ቻምፒየንስ ሊግ ምድብ 6 ጨዋታ ከያንግ ቦይስ ጋር 1-1 በሆነ አቻ ውጤት ሲጠናቀቅ ምርጥ የማይባል ብቃት አሳይቷል። ዩናይትድ በምድቡ አንደኛ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ እርግጠኛ ሲሆን አዲሱ አሰልጣኝ ራልፍ ራንኒክ እሁድ እለት ካደረጉት የመጀመርያ ጨዋታ 11 ለውጦችን አድርጓል አንቶኒ ኢላንጋ እና አማድ ዲያሎ የዩሲኤል የመጀመሪያ ጨዋታቸውን አድርገዋል። የስዊዘርላንዱ ቡድን ቢያሸንፍ ከምድቡ ሶስተኛ ሆነው በማጠናቀቅ አውሮፓ ሊግን እንዲቀላቀል እድል ይሰጠው ነበር። ነገር ግን ዩናይትድ ነበር በተሻለ መልኩ ጨዋታውን የጀመረው እና በ9 ደቂቃ በማይታመን ሁኔታ ሜሰን ግሪንዉድ ሉክ ሾው ያሻማውን ኳስ በአክሮባት መትቶ መሪነቱን አግኝቷል። thefootyscores.com ሆኖም ዩናይትዶች መሪነታቸውን በእጥፍ የሚጨምሩባቸውን ኳሶች ሳይጠቀሙ ቀርተው በ42 ደቂቃ ፋቢያን ራይደር ዶኒ ቫን ደ ቢክ ለማቀበል የሞከረውን ኳስ በጥሩ ሁኔታ በማግኘት ግብ ጠባቂው ዲን ሄንደርሰን አሳልፎ አስቆጥሯል። የዴቪድ ዋግነር ያንግ ቦይስ ያስቆጠሩት ጎል በራስ መተማመናቸውን ያዳበረ ሲሆን ከጥቂት ሰከንዶች በኋላም ሊደግሙ ተቃርበው ነበር ፣ ዩናይትድ ጎል ከገባበት በኋላ ሪትሙን ማግኘት ተስኖት ነበር። rpp.pe እንግዶቹ ከእረፍት በኋላ አሸናፊውን ግብ የማግኘት እድል ያለው ቡድን መምሰላቸውን የቀጠሉ ሲሆን ኩዌንቲን ማሴራስ የተሻለ ማድረግ ሲገባው ወደ ውጪ መትቶ ሲወጣ ኢላንጋ ጥሩ ሙከራ በያንግ ቦይስ ግብ ጠባቂ ጊዩም ፋይቭሬ ተመልሶበታል። ራግኒክ በሁለተኛው አጋማሽ ለግብ ጠባቂው ቶም ሄተን እና አማካዮች ዚዳን ኢቅባል እና ቻርሊ ሳቬጅ የመጀመሪያ ጨዋታቸውን የማድረግ እድል ሰጥቷል። በዚህ ምድብ በአታላንታ እና ቪላሪያል መካከል ሊደረግ የነበረው ጨዋታ በከባድ በረዶ ምክንያት ለሌላ ጊዜ ተላልፏል። ሆኖም ያ ጨዋታ ዩናይትድ ወይም ያንግ ቦይስ በምድብ 6 ከሚጨርሱበት ቦታ ጋር ምንም ግንኙነት የለውም። Related Topicsamad dialloanthony elangaatalantaatalanta v villarealChampions Leaguecharlie savageDavid Wagnerdean hendersondonny van de beekEuropa Leaguefabian riederGuillaume FaivreLuke ShawManchester UnitedMason Greenwoodold traffordQuentin Maceirasralf rangnickTom HeatonucluelVillarealYoung Boyszidane iqbal
1. የቀለም ደረጃ መለኪያ ትክክለኛ መሳሪያ ነው, በመጓጓዣ, በአያያዝ, በማራገፍ, መጫኑ በጥንቃቄ መቀመጥ አለበት, አይመታም, ድብደባ, የኳርትዝ መስታወት ቱቦን ይከላከላል እና የቀለም ማጣሪያ ይሰበራል.ከመጫንዎ በፊት መመሪያዎቹን በጥንቃቄ ያንብቡ. 2. ከመጫኑ በፊት, የቀለም ማጣሪያው በጠንካራ የተፈጥሮ ብርሃን ምንጭ (በደቡብ ምስራቅ አቅጣጫ) እና የመመልከቻው አቀማመጥ ርካሽ እንደሆነ መታሰብ አለበት.የቀለም ማጣሪያው እና የመመልከቻ ቦታው አቅጣጫ ማስተካከል ካስፈለገ በሁለቱም ጫፎች ላይ ያለው ትልቅ ባለ ስድስት ጎን ነት ይለቀቅ እና ጥብቅ መሆን አለበት.የቀለም ደረጃ መለኪያው ከፋብሪካው ከመውጣቱ በፊት 1.5 እጥፍ የሥራ ጫና ሆኗል, ተጠቃሚው ያለፈቃድ የኳርትዝ ቱቦን መበታተን የለበትም, እና የኳርትዝ ቱቦው የቀለም ማጣሪያ አቀማመጥን በማስተካከል ላይ መበታተን የለበትም.በመጓጓዣ ንዝረት ምክንያት ተጠቃሚው የመሳሪያው ቅድመ ሁኔታ ከመጫኑ በፊት 1.5 እጥፍ የሥራ ግፊት ሃይድሮሊክ ሙከራ ሊሆን ይችላል. 3. የኳርትዝ መስታወት ቱቦ ደረጃ መለኪያ የላይኛው እና የታችኛው ክፍል (ክሮች) ከእቃው ጋር ከተገናኘ በኋላ በእቃው ውስጥ ያለው ፈሳሽ ከፍተኛ ሙቀት ከሆነ, የኳርትዝ ቱቦው ከመደበኛው ቀዶ ጥገና በፊት ለግማሽ ሰዓት ያህል በቅድሚያ እንዲሞቅ ማድረግ አለበት. የኳርትዝ ቱቦን ላለመበተን.ጥቅም ላይ በሚውልበት ጊዜ, በመጀመሪያ ቀስ በቀስ የላይኛውን እና የታችኛውን ቫልቮች ይክፈቱ, ስለዚህም ፈሳሹ የመስታወት ቱቦውን ግድግዳ ይቃኛል.በመያዣው ውስጥ ያለው ፈሳሽ ግፊቱን ለመጨመር ወደ ፈሳሽ ደረጃ መለኪያ ሲገባ, የቀለም ማሳያው ግልጽ ላይሆን ይችላል, ምክንያቱም በእቃው ውስጥ ያለው ፈሳሽ ንጹህ ስላልሆነ ወይም ግፊቱ ያልተረጋጋ, በጊዜያዊ ክስተት ምክንያት የሚፈጠረው ፈሳሽ መለዋወጥ, ለምሳሌ የተረጋጋ. የፈሳሹን ደረጃ በግልጽ ማሳየት ይችላል. 4. የፈሳሽ ደረጃ መለኪያው በተለመደው አሠራር ላይ በሚሆንበት ጊዜ የቫልቭ ግንድ ከብዙ 4 መዞሪያዎች (የብረት ኳስ የቫልቭ ግንድ የላይኛው ክፍል እንዳይነካ ለመከላከል) የብረት ኳስ አውቶማቲክ መታተምን ለማረጋገጥ. 5. የኳርትዝ መስታወት ቧንቧ ደረጃ መለኪያ በየጊዜው መታጠብ አለበት የኳርትዝ መስታወት ቧንቧ ማጽጃ ወኪል እና ክሮምሚክ አሲድ ማጠብ, ፍሳሽ.በቀይ እና አረንጓዴ ማሳያ ላይ ተጽዕኖ እንዳያሳድር የቀለም ማጣሪያ ሊወገድ እና ሊጸዳ ይችላል.
ኣብ ትግራይ ብፍላይ ኣብ ከባብታት ገጠር ክሳብ ሎሚ ኣዋልድ ትምሃሮ ምህሮ ሓዲገን ክምርዐዋ ዘገድድ ሕብረተሰባዊ ፀቕጢ ኣሎ። ነዚ ፀገም ሰጊረን ብትምህርተን ዝነፍዓ ደቀንስትዮ ድማ ብበዝሒ ይረኣያ ኣለዋ። ጓል 13 ዓመት ዮርዳኖስ ስብሃትን ጓል 15 ዓመት ልእልቲ ገብረመስቀልን ኣብ ምብራቕ ትግራይ ኣብ ጣብያ ፅገሬዳ ምሉእ ቀዳማይ ብርኪ ቤት ትምህርቲ ፅገሬዳ ትምሃሮ 8ይ ክፍሊ እየን። ኣብ ገዘአን ንወለደን ይሕግዛ፣ትምህርተን ብግቡእ የፅንዓን። ብፍላይ ልእልቲ ካብ ቀዳማይ ክፍሊ ኣትሒዛ ክሻብ 8ይ ክፍሊ ቀዳመይቲ ብምውፃእ ዝላዓለ ውፅኢት ተመዝግብ ኣላ። “ወለደይ ገና ተምሃሪት ራብዓይ ክፍሊ እናሃለኹ ዝተምሃሩ ኣበይ በፂሖም ኮይኖም ብምባል ከመርዕዉኒ ድልየት ከምዝነበሮም ተረዲአ፤ ኮይኑ ግና ብቑልዕነትካ ሓዳር ምግባር ዘለዎ ጣጣ ስለዘረዳእኹዎም ሓሳቦም ቀይሮም” ብምባል ዘጋጠማ ትነግር። ኣብቲ ከባቢ ብዙሓት ኣዋልድ ኣብ ዘይዕድሜአን ትምህርቲ ገዲፈን ክምርዐዋ ከምዝግበር ኣብ መወዳእትኡ ግና እተን ኣዋልድ ነቲ መርዓ ራሕሪሐነኦ ከምዝጠፍኣ ኣብ ዘላቶ ቁሸት ብዛዕባ ዘጓነፈ ክስተት ትገልፅ ልእልቲ። ተምሃሪት ዮርዳኖስ ብወገና ኣብቲ ቤት ትምህርቲ ምስ ዘለዉ መምሃራን ፅቡቕ ቅርበትን ምትሕግጋዝን ከምዘሎ ትገልፅ ኮይኑ ግና እቲ ቤት ትምህርቲ እኹል ወናብርን መፃሕፍትን ከምዘይብሉ ትዛረብ። ሎሚ እውን ብዙሓት ተምሃሮ ኣብ ባይታ ኮፍ ኢሎም ይማሃሩ ምህላዎም ትገልፅ ዮርዳኖስ። ፅገሬዳ ኣብ ወረዳ ክልተ ኣውላዕሎ ካብ ከተማ ውቕሮ ናብ ምብራቕ ሸነኽ 38 ኪሎ ሜትሮ ሪሒቕካ ትርከብ ገና ዘይዓበየት ጥንታዊት ሓውሲ ከተማ እያ። ዕለታዊ ፈነወ ድምጺ ኣመሪካ 04/12/2022 ፈነወ ትግርኛ ሰንበት ድምጺ ኣሜሪካ ፈነወ ቛንቛ ትግርኛ ካብ ሶኑይ ክሳብ ሰንበት ይፍነው። ፈነወ ቛንቛ ትግርኛ ካብ ሶኑይ ክሳብ ዓርቢ ብዕለታዊ ዜና ይጅምር፥ እዋናዊ ጉዳያትን ሰሙናዊ መደባት'ውን የጠቓልል ።ቀዳምን ሰንበትን ኣብቲ ሰሙን ዝተፈነው መደባት ብምድጋም ፈነወ ቛንቛ ትግርኛ ይኻየድ።
የዩናትድ ስቴትስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር፣ ማይክ ፓምፔዮ፣ በቅርቡ ወደ መከካለኛው ምስራቅ ባደረጉት ጉዞ፣ ሁለት አብይት ጭብጦች ተከስተዋል፡፡ የመጀመሪያው፣ አብዛኛው የመካለለኛው ምስራቅ አገሮች፣ ባህሬን፣ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶችና ሱዳን እንዳደረጉት ሁሉ፣ የአብርሃም ስምምነትን በመቀበል፣ ከእስራኤል ጋር ያላቸውን መልካም ግንኙነት እንደሚያሻሽሉ፣ እምነት ማሳደሩ አንደኛው ነበር፣ ይላል ርዕሰ አንቀጹ ሀታውን ሲጀምር፡፡ ሁለተኛው በጠበኛይቱ ኢራን የተደቀነውን አደጋ በመገንዘብ በኩል፣ አካባቢው አንድ አቋም ይዞ መገኘቱን ርእሰ አንቀጹ ያስረዳል፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ማይክ ፓምፔዮ፣ ከእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤጃሚን ኔታኒያሁ እና፣ ከባህሬን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር፣ አቡዱላጢፍ ቢን ራሺድ አል ዛያኒ ጋር፣ ከመገናኘታቸው በፊት “ ይህ ስምምነት በብዙ ምክንያቶች አሰፈላጊ ነው፣ እነዚህ ስምምነቶች ለመላው ዓለም፣ ለንግድ፣ ለኢኮኖሚና ለልማት በርካታ አስደናቂ እድሎችን ይከፍታሉ፡፡ ስምምነቶቹ እንደ ኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ያሉ፣ እኩይ ተዋንያን፣ በአካባቢው ያላቸውን ተጽእኖ ይቀንሳል፡፡ የኢራን መሪዎች፣ አቅጣጫቸውን የማይቀይሩም ከሆነ፣ የበለጠውን እየነጠላቸው ይሄዳል፣ ብለው መናገራቸውን፣ ርእሰ አንቀጹ ጽፏል፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚንስትሩ ፓምፔዮ፣ አቡዳቢ ውስጥ ከአል አረቢያ ቴሌቪዥን ጋር፣ ባደረጉት ቃለ መጠይቅ፣ “በአባቢው ያሉት ብዙዎቹ አገሮች፣ የአብርሃምን ስምምነት፣ በራሳቸው ጊዜ ወደፊት እንደሚቀበሉ ገልጸው፣ ይህን የሚያደርጉትም፣ ለአገራቸው ደህንነት እና ብልጽግናን ስለሚጨምር፣ እንዲሁም ደግሞ ይህን ትክክል የሆነ ነገር፣ ለህዝባቸው ማድረግ ስለሚኖርባቸው ነው” በማለት መናገራቸውን፣ ርእሰ አንቀጹ አትቷል፡፡ ፓምፔዮ፣ ቀደም ሲል፣በአካባቢው ሰላም ሊረጋገጥ የሚችለው፣ በፍልስጤምና እስራኤል መካከል ያለው ችግር፣ ሙሉ በሙሉ ሲፈታ ብቻ ነው ተብሎ ይታሰብ እንደነበር በመግልጽ “ይህ እምነት፣ ሁኔታዎችን ያላገነዘበ ስለነበር፣ መሰረታዊ ስህተት ነበር፡፡ አሁን ያለው እውነታ ግን፣ የባህረ ሰላጤዎቹ አገራትና እስራኤል፣ የጋራ ጠላታቸው፣ኢራን መሆንዋን መገንዘባቸው ነው” ብለው መናገራቸውን፣ ርእሰ አንቀጹ ገልጿል፡፡ የእስራኤልና የፍስልጤምን ግጭት መፍታት አስፈላጊነትን አበክረው የገለጹት ፓምፔዮ፣ በአካባቢው ሰላምን ለማምጣት ግን ፣ሁኔታውን እንደቅድመ ሁኔታ ይዘን፣ ለ40 ዓመታት መቆየት የለብንም ማለታቸውም፣ በርእሰ አንቀጹ፣ ተመልክቷል፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ፓምፔዮ፣ የአብርሃምን ስምምነት፣ “የመከከለኛው ምስራት የወደፊት እጣ ጠቋሚ ነው” ብለው የጠሩት መሆኑን ርዕሰ አንቀጹ ገልጾ፣ “ይህም የአሜሪካን ተሳትፎና አመራር ጠይቋል” ማለታቸውንም ጠቅሷል፡፡ በመጨረሻም፣ ማይክ ፓምፔዮ “ያንን ስናደርግ፣ አሜሪካ መካከለኛው ምስራቅን ጨምሮ፣ በመላው ዓለም፣ የመልካም ነገሮች አስፈጻሚ ኃይል ስትሆን፣ ሌሎችም አገሮች፣ ተገቢውን ምርጫ በማድረግ፣ ለብልጽናቸው ጭምር ሲሉ ከኛ ጋር አብረው መሰለፍና ከእስራኤልም ጋር መወዳጀት ይፈልጋሉ፡፡ ብለው መናገራቸውን በመግለጽ ርእሰ አንቀጹ ጹሁፉን ደምድሟል፡፡
ብዙ የፋሽን ባለሙያዎች ጭምብልን እንደ አዲስ የፋሽን እቃዎች ይቆጥሩታል, በስርዓተ-ጥለት የታተሙ, አርማ ለጥፍ, የአሮማቴራፒ ዘለበት እና ጭንብል ሰንሰለት በማንጠልጠል በተለያዩ ዲዛይኖች ከፍተኛ ጥረት አድርገዋል. በወረርሽኙ ምክንያት ሰዎች ከለበሱት የመጀመሪያዎቹ ጭምብሎች አብዛኛዎቹ ጠፍተዋል ምሳሌ ህይወት እየገፋ ሲሄድ, ወረርሽኞችን መከላከል ቀስ በቀስ ልማድ ሆኗል.ጭምብሎች ከዝቅተኛ-ድግግሞሽ የሕክምና አቅርቦቶች ወደ ዕለታዊ ፈጣን ተንቀሳቃሽ የፍጆታ ዕቃዎች በሕዝብ ግንዛቤ ተለውጠዋል። የአካባቢ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ መጽሄት ዘገባ እንደሚያመለክተው በአለም ላይ በየወሩ ጥቅም ላይ የሚውሉት እና የሚጣሉ ማስክዎች ቁጥር 129 ቢሊየን የሚጠጋ ሲሆን አብዛኞቹ ነጠላ መጠቀሚያዎች ናቸው። በሆስፒታል ውስጥ ያሉት የቆሻሻ ጭምብሎች ለህክምና ቆሻሻዎች ጥቅም ላይ ይውላሉ እና በከፍተኛ ሙቀት ውስጥ በባለሙያ የህክምና ቆሻሻ ኩባንያ ይቃጠላሉ;በነዋሪዎች አኗኗር የሚሰበሰቡ የቆሻሻ ጭምብሎች ለህክምና ቆሻሻዎች ጉዳት በሌለው የሕክምና ሂደት ውስጥ አልተካተቱም።ብዙውን ጊዜ የሚወድሙት በማቃጠል ወይም በቆሻሻ መጣያ ከቤት ውስጥ ቆሻሻ ጋር ነው። የፑሩ ኩባንያ የቆሻሻውን የፕላስቲክ ሪሳይክል ማሽን ይሠራል እና ዲዛይን ያደርጋል።ይህ ማሽን የፕላስቲክ ቆሻሻን በመቀነስ እና በውጤቱም የባህር ውስጥ የፕላስቲክ ፍርስራሾችን በመቀነስ ረገድ ከፍተኛ አስተዋጽዖ ያደርጋል።ሪሳይክል ሰሪዎችን ከምርት እና ፍጆታ ("አፕስትሬስትሪ" እየተባለ የሚጠራው) ደረጃ ወደ ሪሳይክል እና ቆሻሻ አያያዝ ("ታች ተፋሰስ" እየተባለ የሚጠራ) ደረጃ ሊረዳቸው ይችላል። የውሃ ፕላስቲክ ሪሳይክል ማሽን ለሪሳይክል ፒፒ ላልተሸመነ ዳይፐር ቀሪዎች ፣የመከላከያ አልባሳት እና የሚቀልጥ ሪሳይክል ጥራጥሬ በሰዓት ከ200-1200 ኪ. ፒፒ-ያልተሸመነ የጨርቅ ዳይፐር ቀሪዎች፣ መከላከያ ልብስ፣ ኮምፓክት፣ ፊልም ኤክስትራክተር፣ የሃይድሮሊክ ጣቢያ፣ የስክሪን መለወጫ ስርዓት፣ የፔሌትስቲንግ ሲስተም፣ የማድረቂያ ስርአት እና ሌሎች መሳሪያዎችን ጨምሮ።
ለዚህ ተከታታይ ጽሑፍ መነሻ የሆነን የተሻሻለው የውጭ ጉዳይ ፖሊሲና እሱን ተከትሎ እየታዩ ያሉ ለውጦችን ጨምሮ፤ የአካባቢው እንቅስቃሴዎች፣ ከኢትዮጵያ የውስጥ ጉዳዮች ጋር የሚገናኙ በመሆኑ ነው። በሥራ ላይ ያለው የውጭ ጉዳይ ፖሊሲያችንም ከቀይ ባህር ጂኦ-ፖለቲካ አኳያ የሚከተላቸው አቅጣጫዎች፣ ቀጣይ የኢትዮጵያ የዲፕሎማሲ ፖለቲካ ማጠንጠኛ መሆኑ አይቀሬ ይመስላል። በዚህ ተጠየቅ፣ ኢትዮጵያ የቀይ ባህር ተዋናይ ለመሆን በምታደርጋቸው እንቅስቃሴዎች ዙሪያ፣ አካባቢያዊና ዓለም ዐቀፋዊ ገች ሁኔታዎችንም ሆነ መውጫ ስትራቴጂዎችን በጨረፍታ ተመልክተን ርዕሰ- ጉዳያችንን እናሳርጋለን። የቀይ ባህር፣ ገች ሁኔታዎች፡– ኢትዮጵያ ወደ ቀይ ባሕር ስትመለስ የተዋናይነት መደላድሎቿ የጋራ ወደብ ልማት፣ የባሕር ኃይል እና የባሕር ላይ ደህንነት ጉዳዮች ቀዳሚዎቹ ናቸው። እነዚህን መደላድሎች ሊያደናቅፉ ከሚችሉ ጭብጦች ውስጥም፣ ከዐምዱ ውስንነት አኳያ አራት ነጥቦች ላይ ብቻ እናተኩራለን። ፩ የገልፍ መንግሥታት ወደቦችን በሙሉ የመቆጣጠር ፍላጎት የቀይ ባሕር እና የኤደን ባሕረ ሰላጤ ተዋሳኝ የአፍሪቃ ቀንድ አገራት የአብዛኛዎቹ የወደብ ልማት በገልፍ መንግሥታት እጅ እየወደቀ መምጣቱ እሙን ነው። ለአብነትም፣ ከኤርትራ አሰብ (በኤምሬቶች DP World)፣ ከሶማሊያ ሞቃዲሾ (በቱርክ Albayrak) እና ሆብዮ (ኳታር Mwani)፣ ከሶማሌ-ላንድ በርበራ (በኤምሬቶች)፣ ከፑንት ላንድ ቦሳሶ (በኤምሬቶች)፣ ከሱዳን ፖርት-ሱዳን (በመንግሥት ያለ) እና ሱዋኪን (ቱርክ እና ኳታር)፣ ከጅቡቲ (ከኤምሬቶች ወደ ቻይና የዞረ በማሪታይም ሲልክ ሮድ ፕሮጀክት የተያዘ)… ተጠቃሽ ናቸው።
ኣብ ኤርትራ ፈጻሚ ጉዳይ ኤምባሲ ኣሜሪካ ዝነበሩ፡ ስተቨ ዎከር “እቲ ሕሱም ወጻዒ ምሳና ኣሎ” ብዝብል ኣርእስቲ፡ ብ5 መስከረም 2022 ዘኣትላንቲክ/THE ATLANTIC ኣብ ዝተባህለት ጋዜጣ ኣብ ዘስፈርዎ ሓተታ፡ “ኤርትራ፡ ሰብኣዊ መሰላት ብኣሰንባዲ ደረጃ ዝገሃሰላ ሃገር እያ” ዝብል ምስክርነቶም ኣሕዲሶም። እቶም ኣንበሳድር ኣብ 2019 ናብ ኤርትራ ምስተመደቡ፡ በቲ ብቕዲ ኢጣልያ ዝተቐርጸ ህንጻታትን ኩነታት ኣየርን ኣስመራ ተመሲጦም ከም ዝነበሩ፡ ደሓር ግና ፖለቲካዊ ኰነታት ኤርትራ ምስ ተረድኡ ዘሰንብድ ኮይኑ ከም ዝረኸብዎ ኣብቲ ጽሑፎም ኣስፊሮም። እቶም ኣንበሳደር፡ ኤርትራ ናይ ሓሳብ ፍልልይን ተቓውሞን ዘይፍቀዳ፡ ናይ ፕረስ ናጽነት ዘየብላ፡ ዜጋታታ ደረትን ግሉጽነትን ናብ ዘየብሉ ወተሃደራዊ ኣገልግሎት ብቐጻሊ ክኣትዉ ዝግደዱላ፡ ምርጫ ዝበሃል ዘይረኣየት፡ ኣብ ልዕሊ ህዝባ ቀጻሊ ጃምላዊ መእሰርቲ ዝካየዳን ብሰንኪዚ ኣብ ሽቑርርታ ዝነብርን ሃገር እያ ዝብል ዝርዝር ምስክርነቶም ኣብቲ ኣብ ጋዜጣ ዘኣትላንቲክ ዝወጸ ጽሑፎም ኣስፊሮም። እቶም ኣንበሳደር ኣብቲ ሓተታኦም “ብሓደ ሰልፊ ዝምራሕ ሕሱም ምልኪ ሕጂ’ውን ኣብ ኤርትራ ኣሎ” ምስ በሉ፡ ንህዝባ ዘየርብሕ ክነሱ፡ “ስለምንታይ ኤርትራ ኣብ ጉዳይ ሩሲያ ኣንጻር ዩክረይን ተሰሊፋ?” ዝብል ሕቶ ኣዘራራቢ ምዃኑ እውን ጠቒሶም። ኣተሓሒዞም ድማ ቤላሩስ፡ ሶርያን ሰሜን ኮርያን ኣንጻር ዩክረይን ክስለፋ እነለዋ ምናልባት ዝረኽበኦ ረብሓ ይህልወን ምስ በሉ፡ ናይ ኤርትራ ምኽንያት ግና ካብ ምድጋፍ ምልካዊ ምምሕዳር ዝነቅል እዩ ኢሎም። ስተቨ ዎከር፡ ናይ ሓደ ሰልፊ በሓቲ ምምሕዳር፡ ብመሰረቱ ኣዕናዊ እዩ ምስ በሉ፡ ብሰንክዚ ፖለቲካዊ በሓትነት ኤርትራውያን ኣብ ሃገሮም ኮነ ካብ ሃገሮም ናብ ወጻኢ ናይ ምንቅስቓስ ነጻነት ዘየብሎም ምዃኖም መርኣያ ምልክን ዕብለላን እዩ ኢሎም። ምስዚ ብምትሕሓዝ ድማ ኤርትራ ብድሕረትን ስእነትን ቁጠባ እትሰቐዮ ዘላ ከይኣኽላ፡ ዜጋታታ ብገዛእ ገንዘቦም ካብ ባንክ ካብ 5 ሺሕ ናቕፋ ንላዕሊ ከውኡ ዘይክእሉላ፡ ብኢንተርኔት ዝተሓገዘ ዘመናዊ ናይ ባንክ ኣጠቓቕማ ዘየተኣታተወት፡ ሃገር እያ ኢለሙዋ። ኣብ ኤርትራ ዝምደቡ ኣንበሳድራት ከካብ ሃገሮም ሒዘምዎ ዝመጹ ንህዝቢ ኤርትራ ዝሕግዝ መደባት ምትግባሩ ከምዘይክእሉ ጠቒሶም ከኣ፡ ከምቲ ኣብ ኤርትራ ዝገዝእ ዘሎ ስርዓታት ንዝኣመሰሉ ምምሕዳራት ብኹሎም ወገናት ክምከቱን ክቃልዑን ከም ዝግባእ ኣብቲ ንህልዊ ኩነታት ዝምልከት ትንተናኦም ኣስፊሮም። ኣንበሳደር ስተቨን ወከር ኣብ ኤርትራ ኣብ ዝነበርሉ፡ ኣብ ኣስመራ ኮይኖም፡ ናብ ሲንፖዚየም ኤሪሳት 2022፡ ብዘመሓላለፍዊ ሰፊሕ መልእኽቲ፡ ንምምሕዳር ህግደፍ ብምቅላዕ ኣገዳሲ ኣስተዋጸኦ ዘበርከቱ ኣሜሪካዊ ዲፕሎማት ምዃኖም ዝፍለጥ እዩ።
በቲ ሓማም ተታሒዙ ዘሎ፤ቅድሚ 10 ማዕልታት ብኢቦላ ኣብ ሌጎስ ንዝሞተ ላይበሪያዊ ዝሓከመ ናይጀሪያዊ ዶ/ር ምዃኑ ተፈሊጡ’ሎ።ምንስቴር ጥዕና ናይጀሪያ ኦኒየቡቺ ቹክው ሎማዕንቲ ሰኒ ከምዝገለፅዎ ካልኦት ሸሞንተ ሰባት እውን ክግለሉ ከምዝተገብረን ናይ ሰለስተ ሰባት ውፅኢት ምርመራ እውን እናተፀበዩ ምዃኖምን ሓቢሮም። እዚ ከምዚ ኢሉ እናሃለወ ናይ ዩናይትድ ስቴትስ ማእኸላት ምቁፅፃር ሕማማት ኣብዚ ዓመት እዚ ብሰንኪ ኢቦላ ህይወት ልዕሊ 800 ሰባት ናብ ዝስኣና ሰለስተ ሃገራት ምዕራብ ኣፍሪካ ጊኒ፣ሲየራ ሊዮንን ላይበሪያን 50 ክኢላታት ጥዕና ኣብ መወዳእታ እዚ ሒዝናዮ ዘለና ወርሒ ክልእኽ እዩ። ናይ ዩናይትድ ስቴተስ ዳይረክተር ማእኸላት ምቁፅፃርን ምክልኻልን ሕማማት ዶ/ር ቶም ፍራይደን እቲ ሕማም ኣብዚ ሕዚ እዋን ኣብ ሴየራ ሊዮንን ላይበሪያን ካብ ቁፅፅር ወፃኢ እንተኾነ እውን ምቁፅፃር ግን ይክኣል እዩ ኢሎም። እቶም ክኢላታት ንቶም ሕሙማት ኣብ ምርካብ፣ሕክምና ክረኽቡ ኣብ ምርግጋፅ፣ካበይ ከምዝመፁ ኣብ ምፍልጣ፣ንሰባት ኣብ ምምሃርን ኣብ ዝእመሰሉን መዳያት ክሕግዙ እዮም። ኣብ ላይበሪያ ንሕሙማት ክሕክም ከሎ በቲ ቫይረስ ዝተትሓዘ ኣሜሪካዊ ዶ/ር ኬንት ብራንትሊ ፍሉይ መሳርሒታት ብዝተግጠመላ ነፋሪት ኣቢሉ ብቕድሚ ትማሊ ቀዳም ናብ ዩናይትድ ስቴትስ ተመሊሱ’ሎ።
ምስ ምዕጻው ናጻ ጋዜጣታት ኣብ መስከረም 2001 ዝተኣስረ ጋዜጠኛ ኣማኑኤል ኣስራት ንዝሓለፉ 19 ዓመታት ደሃይ እኳ እንተ ዘይብሉ ኣብ ዝኸፍአ ቤት ማእሰርቲ ዒራዒሮ ተዳጒኑ ከም ዘሎ ይእመን። ኤርትራዊ ገጣሚ፡ ሃያሲን ዋና ኣሰናዳኢ ጋዜጣ ዘመን ነበርን ኣማኑኤል ኣስራት ተሸላሚ ተባዕ ኣህጉራዊ ጸሓፊ ከም ዝተሰየመ ኣብ ጽንብል ሽልማት ፐን ፒንተር 2020 ተሓቢሩ። እዚ ሽልማት ኣብ ጽሑፋዊ ሞያኦም ንፍርሒ ምውልዋልን ሰጊሮም ሓለፋ ትብዓት ንዘርኣዩ ጸሓፍቲ ዝወሃብ’ዩ። ተዓዋቲ ፐን ፒንተር 2020 ሊንቶን ክወሲ ጆንሰን’ዩ ኣብቲ ብ12 ጥቅምቲ 2020 ብመገዲ ብሪቲሽ ኮንስል ዝተጋብአ ናይ ማዕዶ (ኦንላይን) ምዕዳል ሽልማት ሓቢሩ። ኣማኑኤል ኣስራት ምስ ምምስራት መኣድታት ስነ-ጽሑፋት ኣብ ፈለማ 2001 ዝተኸስተ ዳግም ምብርባር ስነ-ግጥሚ ኤርትራ መሪሕ ተራ ዝተጻወተ’ዩ። ገጣሚ፡ ሓዳሚን ተሸላሚን ኣማኑኤል ኣብ ግጥምታቱ ንሓያሎ ማሕበራዊ ሕሰም፡ ኲናትን ሳዕቤናቱን፡ ፍቕሪን ተስፋን ብዕምቈት የንጸባርቕ። ብሕልፊ እኳ ደኣ ዝበዝሑ ስነ-ጥበበኛታት ንዂናት ዝቕስቅስ ስራሕ ከፍርዩ እንከለዉ፡ ኣማኑኤል ግን ‘ኣበሳ ኲናት’ እዩ ኣርእዩ። ምስ ብጾቱ ኣብ 2001 ዝጀመራ መድረኽ ስነ-ጽሑፍ “ቍርሲ ቀዳም ኣብ ጥዓሞት” ኣብ ካልኦት ኵርናዓት ኤርትራ’ውን ተመሳሳሊ ተበግሶ ንኽዕንብብ ዓቢ ድፍኢት ኰይና’ያ። ኣብታ ብዋና-ኣሰናዳእነት ዝዓየለ ዝነበረ ጋዜጣ ዘመን’ውን፡ ኣማኑኤል፡ እንተስ ብጽሑፋቱ ወይ’ውን ካልእ መገዲ ንስነ-ጽሑፍ ኤርትራ ኣብ ምማእዛን መሪሕ ግደ ነይሩዎ። ኣብ 2001 ዝጀመረ ኣንጻር ላዕለዎት መራሕቲ መንግስቲ ነበር፡ ጋዜጠኛታትን ተመሃሮ ዩኒቨርስቲን ዝተኻየደ እዱድ ዘመተ ግን ንሓያሎ ግዳይ ገይሩ’ዩ። ብ23 መስከም 2001 ምስ ካልኦት ብጾቱ ጋዜጠኛታት ተጨውዩ ዝተወስደ ኣማኑኤል እምበኣር ክሳብ ሕጂ ደሃይ የብሉን። ብዛዕባ ኵነታት እሱራት ጋዜጠኛታትን ካልኦትን ዝፍለጥ ነገር የሎን። ወግዓዊ ክሲ ከም ዝተመስረቶም ዝሕብር ኣንፈት’ውን ኣይተረኽበን። ናይ ሕልና እሱራት ንዝተፈላለዩ ሕሰም፡ ብቐንዱ ድማ ስእነት ሕክምና፡ ከም ዝተቓልዑ ግን ንግማቱ ኣየጸግምን። ዋላ’ኳ ተኣማሚንካ ምዝራብ ዘጸግም እንተዀነ፡ ብመሰረት እቶም ናይ መጨረሽታ ዝሰለኹ ምንጭታት–ምስ ምንዋሕ ግዜ ዝህሉ ምዕባለታት ከይተዘግንዐ–ኣማኑኤል ካብቶም ውሑዳት ብህይወት ኣብ ትሕቲ ሕሱም ኵነት ኣብ ዒራዒሮ ዝርከቡ እሱራት’ዩ። ሽልማት ፐን ፒንተር 2020 ሊንቶን ክወሲ ጆንሰን ናይዚ ዓመት’ዚ ተዓዋቲ ፐን ፒንተር ክኸውን ብደያኑ ተሓጽዩ። ደያኑ ኣብ ጋዜጣ ዘ-ጋርዲያን ምኽትል ኣሰናዳኢት ዓምዲ ባህሊ ክሌር ኣምስቲድ፣ ኣሕታሚ ዲያሎግ ቡክስ ሻርሜን ላቭግሮቭ፣ ከምኡ’ውን ደራሲ ማክስ ፖርተር’ዮም ነይሮም። ብመሰረት መግለጺ ደያኑ፤ “ሊንቶን ክወሲ ጆንሰን ገጣሚ፡ ኰኾብ ሙዚቃኛ ሬገ፡ ጐስጓሲን ኰይኑ፡ ንኣስታት ፍርቂ ዘመን ዝኸደ ስራሓቱ ንወለዶታት ዝተርፍ ጽልዋ ባህሊ ገይሩ’ዩ። ዘይጸዓድ ፖለቲካዊ መስመሩን ምርምር ታሪኽን እቶም መለልይታቱ ክዀኑ እንከለዉ፡ ነቲ ዓጺቕ ኣርእስቲ ብዋዛን ሰሓቕን ስለ ዝኽልሶ ድማ ተዘካሪ ይገብሮ።” ብቓላት ሊንቶን ክወሲ ጆንሰን፤ “ንሓደ ዜጋ ኣብ ፍጹም ግሉል ቤት ማእሰርት ንኣስታት 20 ዓመት ምሕያር መርኣያ ናይቲ ዝኸፍአ ምልካዊ ስርዓት’ዩ። ከም መግለጺ ሕውነትን ዝምድናን ብቐንዱ ድማ ኣፍሪቃዊ መበቈል ከም ዘሎኒ መጠን እዚ ሽልማት ምስ ገጣሚ፡ ሓዳሚን ሃያሲን ጋዜጠኛ ኣማኑኤል ኣስራት ክካፈሎን ንኽብሩ ክጽውዕን መሪጸ።” ሓዉ ዳኒኤል ኣስራት ብወገኑ፤ “ነዚ ክቡር ሽልማት ብስም ስድራቤት ኣማኑኤል ኣስራት ክንቀበሎ እንከሎና ሓበን እስመዓና። ንሊንቶን ክወሲ ጆንሰን ፐን ኢንግሊሽን ድማ ስለቲ ዘርኣኹምና ክብሪ ነመገስግን። ኣማኑኤል ንዝሓለፉ 19 ዓመታት ኣብ ማሕዩር ዒራዒሮ ይበሊ ኣሎ። ብህይወት ምህላዉን ዘይምህላዉን’ውን ንፍለጦ የሎን። ነዚ ፍሉይ ብስራት’ዚ ኣማኑኤል ክሰምዖ እንተ ዝኽእል ከመይ ባህ ምበለና። በዚ ኣጋጣሚ ድማ ንማሕበረሰብ ዓለም ንጉዳይ ናይ ሕልና እሱራት ኤርትራ ኣመልኪቱ ጸቕጢ ክግበርን እሱራት ድማ ብዘይ ቅድመ-ኵነት ክፍትሑን ንጽውዕ። ንዘይባትኽ ምትብባዕኩም፡ ጸሎትኩምን ዝኽርኹምን ካብ ልቢ ነመስግን፡” ኢሉ። ኣብቲ ናይ ሽልማት ስነ-ስርዓት “ኣበሳ ኲናት” እትብል ግጥሚ ኣማኑኤል ኣስራት ግጥሚ ብገጣሚት ይርጋኣለም ክትንብበ እንከላ ናይ እንግሊዘኛ ትርጕማ ድማ ብክሌር ኣምስቲድ ቀሪባ። ኣቐዲሞም ንሽልማት ፐን ፒንተር ዝበቕዑ ጸሓፍቲ ለምን ሲሳይ (2019)፡ ቺማማንዳ ንጎዚ ኣዲቺ (2018)፡ ማይክል ሎንግሊ (2017)፡ ማርጋረት ኣትዉድ (2016)፡ ጀምስ ፈንቶን (2015)፡ ሳልማን ራሺዲ (2014)፡ ቶም ስቱፓርድ (2013)፡ ካሮል ኣን ዳፍይ (2012)፡ ዳቪድ ሀር (2011)፡ ሃኒፍ ኩሬሺ (2010)፡ ከምኡ’ውን ቶኒ ሃሪሰን (2009) ከዀኑ እነከለዉ፡ “ተባዓት ተቓለስቲ” ተባሂሎም ነዚ ሽልማት ዝተኻፈሉ ድማ በፍቃዱ ሃይሉ (2019)፡ ዋሊድ ዓብዱልኼር (2018)፡ ማህቨሽ ሳበት (2017)፡ ኣሕመዱር ራሺድ ቾውድሪ (ቱቱል) (2016)፡ ራይፍ ባዳዊ (2015)፡ ማዜን ዳርዊሽ (2014)፡ ሳማር ያዝበክ (2012)፡ ሮበርቶ ሳቪያኖ (2011) ሊድያ ካቾ (2010)ን ዛርግናር (ማዎንግ ቱራ) (2009)ን እዮም። ኣማኑኤል ኣስራት ናይ ፈለማ “ፐን እጽሕፍ” (PENWrites) ዝተሰየመ ንስድራቤት እሱራት ጋዜጠኛታትን ጸሓፍቲን ኣብ ዝተኻየደ ናይ ምትብባዕ ደብዳበታት ምስዳድ ጐስጓስዩ። እቲ መደብ ድጋፍ መተባብዒ ደብዳበታት ብመገዲ ፐን ኢንግሊሽ ዝተበገሰ’ዩ። ፐን ኢንግሊሽ ንሓደ ዓመት ዝኸይድ ዘመተ ምጽሓፍ ደብዳበ ንስድራቤት ናይ ሕሉና እሱራት ጸሓፍቲ ጀሚሩ ኣሎ። ኣማኑኤል ኣስራት ቦኽሪ ናይዚ ዘመተ’ዚ ተረቋሒ ጸሓፊ’ዩ ነይሩ። ኣካይዲት መደብ ሓደጋ ዘንጸላሉዎም ጸሓፍቲ ካት ሎቃስ ከም ዝጠቐሰቶ፡ “ንኣማኑኤል ኣስራት ነዚ ክብሪ’ዚ ክንሽልሞ ምኽኣልና ሓበን ይስመዓኒ። ብህወይት ሃልዩስ ኣስታት ድሕሪ ዕስራ ዓመት ምስ ስድራኡ ዝራኸበሉ መዓልቲ ክንርኢ ድማ ሃንቀው ንብል። እዚ ሽልማት’ን ኣቐዲሙ ዝነበረ ጐስጓሳትን ኵነታቱ ኣቓልቦ ኣብ ምሃብን ንስድራቤቱ ሓቦ ኣብ ምስናቕን ኣበርክቶ ክህሉዎ ድማ እትስፎ፡” ኢላ። ንዓሰርተታት ዓመታት፡ ፐን፡ ንእሱራት ብዘይክሲ ዝተቐየዱ፡ መሰሎም ዝተገፈፎምን ዝተቐትሉን ጸሓፍቲ ኣብ ምጥባቕ ነጢፉ። ኣባላት ፐን ድማ ናይ ድጋፍ ደብዳበታት ንእሱራት ጸሓፍቲ ኣብ ምስዳድ ሓደ ካብቲ ዘካይዶ ዘሎ ነዊሕ ዝጸንሐ ልምዲ’ዩ። ኣማኑኤል ኣስራት ኣብ ጥሪ 2016’ውን ብፐን/ኦክስፋም ምስ ካልኦት ቱርካዊን ግብጻዊን ጸሓፍቲ ብምዃን ሽልማት ሓርነት ሓሳብካ ምግላጽ ተሸሊሙ ነይሩ። “ኣበሳ ኲናት” እትብል ተዓዋቲት ግጥሚ ኣማኑኤል’ውን ብቴድሮስ ኣብርሃምን ምትሕብባር ዳቪድ ሹክን ፈለማ ናብ 16 ቋንቋታት ብምትርጓማ ሰፊሕ ተነባብነት ረኺባ’ያ። ኣማኑኤል ሓደ ካብቶም ብመገዲ ፐን ኤርትራ ኣብ ጋዜጣ ዘ-ጋርዲያን ሸፈነ ዝረኸቡ ሽዱሽተ እሱራት ጋዜጠኛታት’ውን እዩ።
በኦንላይን ካሲኖዎች ውስጥ ያሉ የተጫዋቾች ቁጥር በየቀኑ በፍጥነት እየጨመረ ነው, እና በዚህ ምክንያት, ብዙ አዳዲስ የመስመር ላይ ካሲኖዎች ወደ ገበያ እየገቡ ነው. ነገር ግን የደንበኛው የመጀመሪያ ስጋት ይህ የመስመር ላይ ካሲኖ እምነት ሊጣልበት ይችላል ወይ የሚለው ይሆናል። ተጫዋቾቹ ኢንቨስት ሲያደርጉ እና ገንዘባቸውን ሲያወጡ እና አካውንት ሲፈጥሩ ብዙ መረጃዎችን እና የፋይናንሺያል መረጃዎችን ይመዘግባሉ, ስለዚህ ጥንቃቄ ማድረግ ተገቢ ነው. ለረጅም ጊዜ በንግድ ውስጥ የቆዩ ካሲኖዎች ብዙ ደንበኞች ስላሏቸው ሊታመኑ ይችላሉ, ነገር ግን ስለ አዲሱ የመስመር ላይ ካሲኖዎችስ? በዚህ ጽሑፍ ውስጥ አዲስ የተከፈቱ ካሲኖዎችን እንዴት ማመን እንደሚችሉ እናብራራለን። ስለዚህ ማንበብዎን ይቀጥሉ እና ይወቁ። ፍቃድ ያለው መሆኑን ያረጋግጡ በህጋዊ መንገድ ለመስራት የመስመር ላይ ካሲኖዎች የቁማር ፈቃድ ማግኘት እንዳለባቸው ሊያውቁ ይችላሉ። የቁማር ፈቃዶችን የሚሰጡ ጥቂት ባለስልጣናት አሉ, ስለዚህ መጀመሪያ ማድረግ ያለብዎት ነገር መጫወት የሚፈልጉት የመስመር ላይ ካሲኖ ፈቃድ ያለው መሆኑን ወይም አለመሆኑን ማረጋገጥ ነው. ለኦንላይን ካሲኖ፣ ከባለሥልጣናት ፈቃድ ማግኘት ቀላል አይደለም፣ ምክንያቱም አዲስ ካሲኖ ብዙ መሰናክሎችን ማጽዳት እና ለፍትሃዊነት፣ ደህንነት እና ምስጠራ ጥብቅ መስፈርቶችን ማክበር አለበት። ስለዚህ፣ ሲፈቀድ እና በመስመር ላይ ሲለጠፍ እምነት ሊጣልበት እንደሚችል እርግጠኛ መሆን ይችላሉ። ውሂቡ በሁሉም የመስመር ላይ ካሲኖዎች የገቢር ፈቃድ ያላቸው መነሻ ገጽ ላይ ይፋ ይሆናል። የፍቃድ ቁጥሩ እና ፈቃዱ በስክሪኑ ግርጌ ላይ መታየት አለባቸው። እርግጠኛ ለመሆን, ያንን በተለይ ማመን ይችላሉ አዲስ ካዚኖ መስመር ላይ, የፍቃድ ቁጥሩን ማስታወሻ መውሰድ እና ወደ መቆጣጠሪያው ድረ-ገጽ ቀጥተኛ ግንኙነት ከሌለ ተጨማሪ ምርምር ማድረግ ይችላሉ. አተገባበሩና መመሪያው የምንኖረው ከነሱ ጋር ከተስማማ በኋላ ማንም ሰው ውሎችን እና ሁኔታዎችን በሚያነብበት ዓለም ውስጥ ነው፣ እና ማንንም አንወቅስም ምክንያቱም ከባድ ስራ ሊሆን ይችላል። ነገር ግን የመስመር ላይ ካሲኖን ማመን ከፈለጉ ውሎቻቸውን እና ሁኔታዎችን ማንበብ አለብዎት። ማረጋገጥ ያለብዎት ውሎች እና ሁኔታዎች ናቸው። ይህ ካዚኖ ፍትሃዊ መወራረድም መስፈርቶች ያቀርባል? በትልልቅ ድሎች ላይ የመውጣት ገደብ አለ? የተለያዩ ዓይነቶች አሉ አስተማማኝ የክፍያ ዘዴዎች ይገኛል? መስፈርቶችዎን የማያሟሉ ደንቦችን እና ሁኔታዎችን ካገኙ ያንን የመስመር ላይ ካሲኖን ከዝርዝርዎ ውስጥ በማውጣት ወደሚቀጥለው ይሂዱ እና እስኪረኩ ድረስ ተመሳሳይ ነገር ያድርጉ። ግምገማዎችን ያንብቡ የሚቀጥለው እርምጃ በመስመር ላይ ካሲኖ ላይ እውነተኛ ልምዳቸውን ስለሚካፈሉ የተለያዩ ደንበኞች ግምገማዎችን ማንበብ ነው። ስለ ተለያዩ የአደጋ ዓይነቶች ስለሚማሩ ግምገማዎችን ማንበብ በጣም ይረዳዎታል። አሁንም ካሲኖን በተመለከተ ብዙ ግምገማዎች ከሌሉ እና 2-3 ብቻ እና ሙሉ በሙሉ አዎንታዊ ከሆነ ግምገማዎች ሊከፈላቸው ስለሚችሉ እንደዚህ ካሉ የመስመር ላይ ካሲኖዎች መራቅ አለብዎት። ነገር ግን ፈቃድ ካላቸው እና ደንቦቹ እና ሁኔታዎች እርስዎን ካረኩ ከዚያ ስለሱ መጨነቅ አያስፈልግዎትም። ከደንበኛ አገልግሎት ጋር ይወያዩ በመስመር ላይ ካሲኖ ላይ ያለው የደንበኞች አገልግሎት ብዙ ጊዜ የሚጫወቱ ከሆነ ምን እንደሚጠብቁ ብዙ ግንዛቤን ይሰጥዎታል። የቀጥታ ውይይት ባህሪን በመጠቀም የደንበኞችን አገልግሎት ለማግኘት እና ጥቂት ጥያቄዎችን በመጠየቅ ስለ ካሲኖው የበለጠ ማወቅ ይችላሉ። በፈለኩ ጊዜ የደንበኞች አገልግሎት እንዴት ማግኘት እንደምችል ስለማንኛውም ነገር የደንበኛ አገልግሎትን ትጠይቃለህ? እና ስለምሰጧቸው ማስተዋወቂያዎች እና ስለ ፍቃድ አወጣጥዎ እንኳን ሊጠይቋቸው ይችላሉ። ከነሱ ምን ያህል መረጃ እንደሚያገኙት በእርስዎ ላይ የተመሰረተ ነው፣ እና ወዳጃዊ እና አስተማማኝ የሚመስሉ ከሆነ፣ እዚያ ጥሩ ልምድ ሊኖርዎት ይችላል። የንፅፅር ጣቢያ አዲሱን ጨምሮ እያንዳንዱን የመስመር ላይ ካሲኖ የሚያወዳድሩ ድረ-ገጾች ስላሉ የንፅፅር ጣቢያን መጠቀም ውጤታማ ሊሆን ይችላል። በስምምነቱ፣ በተለያዩ ጨዋታዎች፣ የፍቃድ አይነት እና ሌሎች በርካታ ነገሮች ላይ መረጃ ይሰጣሉ። ይህ ብዙ ጊዜን ከመቆጠብ በተጨማሪ አዲስ የመስመር ላይ ካሲኖን በተቻለ መጠን ደህንነቱ በተጠበቀ መንገድ እንዲያገኙም ያስችልዎታል። ሞባይል ስልኮቹን ስታወዳድሩ ልታስቡበት ትችላላችሁ ስለዚህ ከመግዛትህ በፊት የትኛው የተሻለ እንደሆነ ድህረ ገፆቹን አወዳድር ነገር ግን ገንዘባችሁን እዛ የምታወጡት ካሲኖው እምነት የሚጣልበት መሆኑን ለማረጋገጥ ከዚህ በፊት የተነጋገርናቸውን እርምጃዎች ተግባራዊ አድርጉ። . ለምን አዲስ የተገነባ ካዚኖ ይምረጡ? እስከ አሁን ድረስ ካነበቡ በኋላ የድሮ ካሲኖዎች ያለ ምንም ምርመራ ሊታመኑ እንደሚችሉ እያሰቡ ሊሆን ይችላል, ታዲያ ለምን እዚያ አይጫወቱም? ይህ ስጋት መፈጠሩ ተገቢ ነው። አዲስ የተገነቡት ካሲኖዎች በገበያው ውስጥ ቦታቸውን መገንባት ይፈልጋሉ, ስለዚህ ለዚያ ተጫዋቾችን ለመሳብ ልዩ የሆነ ነገር ማድረግ አለባቸው. ስለዚህ, አዲስ የተገነቡ የመስመር ላይ ካሲኖዎች በጣም ለጋስ እና ማራኪ የሆኑ ቅናሾችን ይሰጡዎታል. በተጨማሪም, ሁሉንም በተደጋጋሚ ያስጀምራሉ በጣም የቅርብ ጊዜ እና ተወዳጅ ጨዋታዎች, አንዳንዶቹ የቆዩ ድረ-ገጾች እንዲኖራቸው ትንሽ ረዘም ያለ ጊዜ ይወስዳሉ. በአንድ ገበያ ውስጥ ለተወሰነ ጊዜ ምንም ነገር አልተለወጠም, አዲስ ካሲኖ ልዩ ልምድ እና ትኩስ ነገር ያቀርባል. ስለዚህ፣ አዲስ ከተገነቡት ካሲኖዎች ውስጥ ማንኛቸውም ሊታመኑ ይችላሉ ብለው ካሰቡ፣ እዚያ ባለው ልዩ ልምድ መደሰት ይችሉ ይሆናል። መደምደሚያ ጊዜ እያለፈ ሲሄድ የመስመር ላይ ካሲኖዎች በጣም ተወዳጅ እየሆኑ መጥተዋል፣ እና አዳዲስ ካሲኖዎች እየተከፈቱ ነው፣ ስለዚህ እነዚያን የመስመር ላይ ካሲኖዎችን ለማመን ፈቃድ ያላቸው መሆኑን ማረጋገጥ፣ ውሎቻቸውን እና ሁኔታዎችን ማንበብ፣ ግምገማዎችን ማንበብ፣ ከደንበኛ ድጋፍ ጋር መወያየት እና በመጨረሻም ማረጋገጥ ያስፈልግዎታል። , አንድ ንጽጽር ድረ ገጽ ላይ አዳዲስ ካሲኖዎችን አወዳድር. ይህን በማድረግ፣ ካሲኖው የእርስዎን መስፈርቶች የሚያሟላ ከሆነ፣ የድሮ የመስመር ላይ ካሲኖዎች አሁን የማይሰጡዋቸውን አዳዲስ እና ልዩ ነገሮችን መደሰት እና ሊለማመዱ ይችላሉ።
ከዝግጅት ክፍሉ:- “አድዋን የሚያህል ወታደራዊ ድል ስለምን ወደ ፖለቲካዊ ድል መቀየር ተሳነን?“ በሚል ርዕስ የመጀመሪያውን ክፍል ማቅረባችን ይታወሳል፤ ሙሉው ጽሁፍ እዚህ ላይ ይገኛል፡፡ በዚህኛው ክፍል ሁለት ዕትም እርግማን ሁለት “ሚኒልክ ኤርትራን ሸጠ፤ ትግራይን በደለ” የሚለው ርዕስ ዳሰናል፡፡ የኢትዮጵያ አገራዊነት ታሪክ ተፃሪሪ ትርጓሜና የዘመናዊት ኢትዮጵያ አገር ምስረታ ሂደት የተመዘዙ መንታ ሰበዝ ናቸው፡፡ “ቅኝ ግዛት” vs “አገር ምስረታ፣ ማቅናት/ግንባታ” የሚሉ ተፃራኒ ትርጓሜዎች እንዳሉ ሁሉ፤ “አገር ሻጭ” እና “ባንዳ” የሚሉ የፖለቲካ እርግማኖች የዘመናዊት የኢትዮጵያ የታሪክ ገጽታ አካል ሆነው ቀርበዋል፡፡ ማንነትን የታከከ የታሪክ ትርጓሜ ባለበት ሁኔታ እነዚህ ብያኔዎች ሊጠፉ የማይችሉ የታሪክ ፍም እሳቶች ናቸው፡፡ በዚህም የተነሳ በገዥዉ ኃይል ፊት ታሪክ ትምህርት መሆኑ ቀርቶ ፍርድ ቤት ሆኗል፡፡ አፄ ዮሐንስ አራተኛ ከእርሱ በፊት እንደነበረው ዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስም ሆነ ከኋላው እንደተከተሉት ነገሥታት በሚያሟግት የታሪክ ምዕራፍ ውስጥ ያለፈ መሪ ነው፡፡ አፄ ዮሐንስ ወደ ስልጣን የመጣበት መንገድ ምኒልክ ወደስልጣን ለመውጣት ከተጓዘበት የዲፕሎማሲ መንገድ የሚለይ አደለም፡፡ ስልጣን የኃይል ሁሉ ማዕከል በሆነበት ቦታ ገባሪነትን መካድ ለኢትዮጵያ መሳፍንቶች የተለመደ ባህሪ ነበር፡፡ በውጭ ኃይሎች ድጋፍ የጦር መሳርያ አቅምን ማጠናከር፤ ጊዜና ወቅት ጠብቆ ወደ ንግሥና መንበር መውጣት፤ የዮሃንስ እና የምኒልክ መንታ ገፀ-ባህሪያት ናቸው፡፡ አፄ ሚኒሊክ “የጣልያን ተላላኪ ባንዳ ነበር” ማለት የሚቀናቸው የትግራይ ብሔረተኛ ልሂቃን የዮሐንስን የቀደመ የታሪክ እድፍ ተስቷቸው አይጠቅሱትም፡፡ የስዊዝ ሰው የሆነው ሙሲንጀር ፓሻ የጊዜው ያገር ጥናት ተጓዥ መንገደኛ ነበር፡፡ ይህ ሰው በምጽዋና በከረን አመታትን አሳልፈዋል፡፡ የወቅቱ ደጃች ካሳ (ዮሐንስ) እና የእንግሊዞችን ግንኙነት በማቃናት ቀዳሚ ሰው ነበር፡፡ በዚህ ሰው አገናኝነት ከእንግሊዞች ጋር የተወዳጀዉ ደጃች ካሳ ለናፒየር ጦር የመቅደላ መንገድ ሁነኛ ጠቋሚ ነበር፡፡ ያለ አንዳች ግነት ስለ ሥልጣን ለውጭ ኃይሎች በመታመን (ባንዳ፡- ለባዕድ ሥርዓት ታማኝነትን ማሳየት) አስገባሪውን (አፄ ቴዎድሮስን) በመክዳት ባገኘው የጦር መሳርያ ድጋፍ ታግዞ ወደ ስልጣን የወጣው ቀዳሚው ንጉሠ ነገሥት አፄ ዮሐንስ አራተኛ ነው፡፡ ከዚህ በፊት የነበሩ መሳፍንቶች ለአብነት በቴዎድሮስ ዘመን እንደ አገው ንጉሴ ያሉ መሳፍንቶች ከውጪ መንግስታት ጋር ቢፃፃፉም በውጭ ሀይሎች የጦር መሳሪያ ድጋፍ ወደ ሥልጣን ለመውጣት የተሳካለት መሳፍንት አልነበረም፡፡ ከዳጃች ካሳ (ዮሐንስ በስተቀር)!! የአፄ ምኒልክ መንገድ ከዚህ ብዙ የራቀ መሆኑን መካድ ያስተዛዝባል፡፡ የአፄ ምኒልክ እና የጣልያኖች ግንኙነት ከአፄ ዮሐንስ የንግስና ዘመን ይጨምራል፡፡ ሚኒሊክ የዘር ሀረጉን የሚስበው ከአፄ ልብነ ድንግል ነው፡፡ ከዚያም ባለፈ የንጉሥ ሣህለ ሥላሴ የልጅ ልጅ የኃይለ መለኮት ልጅ በመሆኑ የመሀል ኢትዮጵያን ግዛት በመቆጣጠርና የደቡብ እና ምዕራብ ኋላም የምስራቅ ኢትጵያ ግዛቶችን በመጠቅለል ወደ ንጉሠ ነገሥትነቱ የመውጣት ምኞት ነበረው፡፡ ለዚህም ይመስላል አፄ ዮሐንስ ከነገሰበት 1964-1870 ዓ.ም ለተከታታይ ሰባት ዓመታት ለአፄ ዮሐንስ ሳይገብር የሥልጣን ተፎካካሪና የዙፋን ወደረኛ ሆኖ የተቀመጠ፡፡ በነገራችን ላይ በነዚህ ጊዜያት የአፄ ምኒልክ ማኅተም “ንጉሠ ነገሥት” ይል ነበር፡፡ በተመሳሳይ መልኩም የአፄ ዮሐንስ ማኅተም “ንጉሠ ነገሥት” ይል ነበር፡፡ (ጸሐፌ ትዕዛዝ ገብረ ሥላሴ፣ ተክለ ፃዲቅን፣ ሀሎርድ ማክስን ያጤኗል) በሁለቱ ወደረኞች ማሀከል የነበረውን የሥልጣን ሽኩቻ ተክለ ፃዲቅ መኩሪያ በውብ ብዕሩ “አንዲቷ ኢትዮጵያ በዮሐንስና በምኒልክ ተከፍላ የሁለት ነገሥታት ሀገር ሆነች፡፡ ሁለቱም በቤገ-ምድርና በጎጃም፣ በወሎ፣ በላስታ አውራጃ ላይ የውስጥ ፍልምያ ሲያሳዩ፤ እንደዚሁም የውጪ መንግስታትን ወዳጅነት አጥብቀው በደብዳቤና በየመልክቶቻቸው አማካኝነት ይሻሙ ነበር፡፡ ሁለቱም የውጭ ሀገር መንግሥታት ወዳጅነት የሚሻሙት አጠገባቸው ባሉት ሀገር ጎብኝና ነጋዴዎች ወይም ምጥዋ በሚቀመጡት ቆሲሎቻቸው ጎን ባላንጣን አስጠልቶ ራስን ለማስወደድ ነው (አፄዮሐንስ እና የኢትዮጵያ አንድነት ፤ ገፅ 57)” ሲል ይገልፀዋል፡፡ በሁለቱ ወደረኞች መሀል የነበረው የስልጣን ሽኩቻ መጋቢት 14 ቀን 1870 ዓ.ም ልቼ ላይ በምኒልክ ይቅርታ ጠያቂነት ዕርቅ ቢወርድም ተከታዮቹን አስራ አንድ ዓመታት (1871-1881) ምኒልክ የግዛት ወሰኑን ወደ ደቡብ ምዕራብ እና ምስራቅ ኢትዮጵያ ክፍሎች በማስፋት የመሬት ይዞታውን (Land power) የግብር መሰብሰብ አቅሙን እና የጦር መሳሪያ ክምችት ሀይሉን በማጠናከር ስራ ተጠምዶ ነበር፡፡ ዓመታዊ ግብሩን በማስገባት ዮሐንስን የሚያዘናጋው ምኒልክ የጦር መሳሪያ ክምችቱና የሰራዊት ብዛት ሲጨምር እንጂ ሲቀንስ አልታየም፡፡ ጣሊያኖች በእንግሊዝ ችሮታ ምፅዋን በቁጥጥር ስር አድርገው ወደ አገር ውስጥ በሚገባ ማንኛውም አይነት እቃ ላይ ተፅኖ ሲያደርጉ አፄ ዮሐንስ የምኒልክ ከጣሊያን ጋር መቀራረብ አልወደደውም ነበር፡፡ የምኒልክ እና የጣልያኖች ወዳጅነት በውጫሌ ውል የወዲያው ግፊት (immediate cause) ሆኖ እስከተፈጠረው የአድዋ ጦርነት ጊዜ ድረስ ቆይቶል፡፡ ጣሊያኖች የወቅቱ ጠላታቸውን አፄ ዮሐንስ እንዲዳከምላቸው አፄ ምኒልክን ለማቅረብ መሞከራቸው የቀኝ ግዛት መሀንዲሶች ዘዴ ይመስላል፡፡ ይህም ሆኖ በርከት ያለ የጦር መሳሪያ ያስታጠኩትን ምኒልክ መጠርጠራቸው አልቀረም፡፡ ይህን ጉዳይ የታሪክ ጸሃፊዉ ፕሮቲ ክሪስ “Empress Taytu and Menilek II” በሚል መጽሀፉ የወቅቱ የጣሊያን መንግስት ወኪል የነበረው አንቶሎኒ በምኒልክ የበዛ መሳሪያ ክምችት ያደረበትን ስጋት ለምኒልክ አንስቶ እንደ ተማፀነው ጽፏል፡፡ ለምኒልክ፣ ለጣይቱ፣ ለራስ ዳርጌና ለአዛዥ ወልደ ፃዲቅ እንዲሁም ለሁለት አስተርጓሚዎች እንደየ ማዕረጋቸው ሥጦታዎችን ካጎረፈ በኋላ ምኒልክ ያገኘውን መሳሪያ ጣሊያኖችን ለመውጋት እንዳይጠቀምበት በክርስቲያናዊ ደንብ መሃላ ይፈፅምለት ዘንድ ተማፅኖ ነበረ (ገፅ 57-8 ይመልከቱ) የውጫሌው ውል ተደራዳሪ እና ፈራሚ የነበረው ጣሊያናዊው አንቶኖሊ እንደሚለው 1880 ዓ.ም ላይ (ከውጫሌ ውል አንድ ዓመት ቀደም ብሎ መሆኑ ልብ ይሏል) ምኒልክ የደቡብ፣ የምዕራብ እና የምስራቅ የኢትዮያ ግዛቶችን ጨምሮ 196,000 (አንድ መቶ ዘጠና ስድስት ሺህ) ሰራዊት እንደነበረው ሮቢስን “The Attempt to Establish a protectorate over Ethiopia” በሚለው መጽሃፍ (ገፅ 66) ይነግረናል፡፡ በነዚህ ጊዜያት ሁሉ አፄ ዮሐንስ በስም ደረጃ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ሆኖ በሰሜን ኢትዮጵያና አካባቢው (ብቻ) የተገደብ እንቅስቃሴ ያደርግ ነበር፡፡ የአፄ ዮሐንስ የንግሥና ዘመን ፍፃሜ ሦስት አመታት ሲቀረው ሚኒሊክ (የሐር ላይ ባንዴራውን ሲያውለበልብ) በግዛት ወሰን፣ በግብር ማሰሰባሰብ፣ በጦር መሳሪያ ክምችትና በዲፕሎማሲ የበላይበት አፄ ዮሐንስን ይበልጠው ነበር፡፡ የአፄው የንግሥና ዘመን እየተሸረሸረ የመጣ ለመሆኑ ምኒልክ በተለየ ሁኔታ የአስራ አንድ አመታት (1871-1881 ዓ.ም) የሥልጣን ግስጋሴ ይነግረናል፡፡ በነዚህ ጊዜያት አፄ ዮሐንስ የውጭ ኃይሎች ፍልሚያ ቢኖርበትም ምኒልክን ለማስቆም ከቶውንም አልሞከረም፡፡ ይህ ሁኔታ ከማዘንና ከርህራሄ የመጣ ሳይሆን የአካባቢው የተፈጥሮ ሀብት መመናመንና የማህበራዊ መሰረት መጥበብ ተከትሎ ከተፈጠረ የአቅም መዛል የመጣ ነበር፡፡ የዛሬዋ ኤርትራ ይህንን ስያሜ ከመያዝዋ በፊት “ባህረ ነጋሽ፣ ምድረ ሌማሴን፣ ከበሳ” በመባል ትጠራ ነበር፡፡ ኤርትራ የሚለው መጠሪያም ሆነ ፖለቲካዊ ቁመና ያገኘችው ጣልያን የቀይ ባህር ጠረፍን ታክካ ወደ አካባቢው መዝለቋ ኋላም መስፋፋቷ ከተመዘገበበት 1879 ዓ.ም ወዲህ ነው፡፡ (በተለይም የዘውዴ ረታን፤ የተከስተ ነጋሽን ሥራዎች ያጤኗል) በዚህም ጊዜ ደግሞ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት አፄ ዮሐንስ ነበር፡፡ ከ1864-1881 ዓ.ም በኢትዮጵያ ውስጥ የተደረጉ ታላላቅ ጦርነቶች (ተድአሊ፣ ኩፊት፣ ጉራዕ፣ ጉንደት {ጉንዳጉዲ}) ኢትዮጵያ በድል የተወጣችው በአፄ ዮሐንስ ዘመነ መንግስት ነበር፡፡ ወራሪው የግብፅ ኃይል በጉንደት እና በጉራዕ ተከታታይ ሽንፈት፤ ሌላ ጊዜ አውሳ ላይ በአፋሮች እጅ ወድቆ የግብፅ ጦር አፋር በረሃ ላይ የቀረው፤ በአፄ ዮሐንስ የንግስና ጊዜ ነበር፡፡ ጣልያን የአሉላን እጅ የቀመሠበት ውርድት በሮማ ፒያሳ ቺንኮ ቼንቶ (“የአምስት መቶዎች አደባባይ”) በሚል ያስታውሰዋል፡፡ ዮሐንስ በዚህና መሠል ድሎች የታደለ ቢሆንም አገር ውስጥ “የአቻዎች አውራ” በሚል ከያዘው የንጉሠ ነገሥትነት ማዕረግ የተሻገረ በራሱ አቅም የሚቆጣጠረው መሬት ከምኒልክ አንፃር የተዳከመ ነበር፡፡ የውጭ ኃይል ላይ ያስመዘገበው ድልም የግብፅን ጦር ከመጠራረግ ውጪ የጣልያንን ጦር ከምጽዋና ከአሰብ አካባቢ ማራቅ አልቻለም ነበር፡፡ በራስ አሉላ እንግዳ (አባ ነጋ) የተመራው ጦር ዶጋሊ ላይ የጣልያንን ጦር ከመታ በኋላ ሀያ ሦስት ኪሎ ሜትር በላይ ወደ ማትርቀው ምፅዋ በመሻገር የጣልያንን ጦር ያልወጋበት ሁኔታ በቀጣይ ጊዜያት ጣልያን የዶጋሊን ቁጭቷን በሰሓጢ ላይ (መጋቢት 1880) ያለምንም ወሳኝ ውጊያ ምሽግ ላይ አድፍጦ በመተኮስ የአፄ ዮሐንስ ጦር አታክቶ በመመለሱ ረገድ ተሳከቶለታል፡፡ (ባህሩ ዘውዴን፣ ተክለፃዲቅን፣ ሮሊንስንን…ያጤኗል) ለዲፕሎማሲ ሽፋን ጥለውት የወጡትን ሰሓጢን በኃይል መልሰው ያዙት ዮሐንስ እጁ ላይ የነበሩትን ድሎች መልሰው እንደጉም ይተኑበት እንደነበር የዶጋሊው ጦርነት ጥሩ ማሳያ ነው፡፡ ምናልባት የዶጋሊው ድል በመቀጠል ጦሩ ወደ ምፅዋ የማዝመት ሁኔታ ቢኖር ድል ከኢትዮጵያ ጋር መሆን በቻለ ነበር፡፡ ሠላም ያልተገኘባቸው የአፄ ዮሐንስ ድሎች ኤርትራ ሙሉ በሙሉ ለመቆጣጠር ለተስፋፊው የጣልያን ጦር ምቹ ጊዜ እየፈጠሩ እንደነበር ከዶጋሊ ድል በኋላ በአፄው መሪነት ሰማንያ ሺህ ጦር በማዝመት የተሞከረው የሰሓጢ ጦርነት የጣልያንን ይዞታ በማጠናከር የዮሐንስን የድል ተስፋ በማጨለም የተደመደመ መሆኑ ነው፡፡ ሰሓጢ ዮሐንስ ከጣልያኖች ጋር ለመጨረሻ ጊዜ የተያየባት የስንብት ቦታ ሆነች፡፡ ዮሐንስ እጅግ በሚያስቆጭ መልኩ መተማ ላይ ሲሰዋ፤ በምፅዋ፣ አሰብ፣ አስመራ፣ ሰሓጢና ቆላማው ክፍል ተወስኖ የነበረው የጣልያን ጦር ያለምንም ጊዜ ማባከን የደጋውን ክፍል ወረረው፡፡ (ዘውዴ ረታን፣ ተክለፃዲቅን፣ ባህሩን … ያጤኗል) ቀደም ሲል በወቅቱ የጣልያኑ ጠቅላይ ሚኒስተር ፍራንቺስኮ ክርስቲ “ኤርትራ” በሚል የተሰየሙና አካባቢዎችና የደጋውን ክፍል ጠቅልለው ከሰሜን ኢትዮጵያ ግዛት ነጠሉት፡፡ የዮሐንስ ያልታሰበ ሞት ለምኒልክ የስልጣን በር ሲከፍት ለጣሊያን ጦር “ኤርትራ” የሚል ግዛት እንዲረከብ ዕድል ፈጠረለት፡፡ በተደጋጋሚ ጦርነት የደቀቀው የሰሜን ኢትዮጵያ ጦር ከዮሐንስ ሞት በኋላ መበታተን ዕጣ ክፍሉ ሆነ፡፡ እስከዚህ የታሪክ ሂደት ድረስ ምኒልክ በኤርትራ ጉዳይ አንዳች የሚያገባው ነገር አልነበረም፡፡ ጣልያን በቀይ ባህር ዳርቻ የምትቆናጠጥበት ዕድልን ያገኘችው በ1862 ዓ.ም በጣልያናዊው ጂሴፔ ሳፔቶና “ሩባቲኖ” የተባለ የመርከብ ኩባንያ ጋር ተቀናጅተው ከአፋሩ ሱልጣን መሀመድ ሃሰን አሰብን ገዝተው ነው፡፡ በዚህ ጊዜ እንኳን ምኒልክ አፄ ዮሐንስም ንጉሠ ነገሥት አልሆነም፡፡ የያኔዋ ኢትዮጵያ በአፄ ተክለጊዮርጊስ ነበር የምትመራው፡፡ የኋላ ኋላ ይህ የግል ይዞታ የነበረው ወደብ ወደ ጣልያን መንግስት ሲጠቃለልም ሆነ እንግሊዝ ከአፄ ዮሐንስ ጋር አድዋ ላይ “የሂወት ውል” እየተባለ የሚጠራውን ስምምነት ስትፈራረም እና እንግሊዝ በሶስት ወራት ልዩነት ስምምነቱን አፍርሳ ነሃሴ 1876 ዓ.ም ምፅዋን ለጣሊያን ስታስረክብ ምኒልክ በደቡብ ዘመቻ እንደተጠመደ ነበር፡፡ አፄ ዮሐንስ 150 ኪ.ሜ በማይሞላ ርቀት መቀሌ ላይ ተቀምጦ ሁኔታውን በቁጭት ያስተውል ነበር፡፡ አፍቃሪ ኢትዮጵያ የሆነው የታሪክ ጸሐፊ ሩቤንስን ከላይ በጠቀስነው መጽሃፉ እንዳለው ዮሐንስ ከእንግሊዝ ጋር ያደረገው “የሂወት ውል” አንድ ደካማ ጠላት (ግብጽ) በሁለት ጠንካራ ባላጋራዎች (የጣልያና የሱዳኑን የማሃዲ ንቅናቄ) መተካት ሆነ፡፡ በሂደት የታየውም እንግሊዝ ውሉን ወደ ጎን ገፍታ ምጽዋን ለጣልያን በመስጠት፤ ለጣልያን ወረራ በር ስትከፍት እስላማዊ ተሃድሶንና የሱዳን ብሄርተኝነትን አዳብለው ለተነሱት መሃዲስቶች ደግሞ በኢትዮጵውያንና በኢትዮጵያ ግዛት ላይ በበቀል ስሜት እንዲዘመቱ አደረጋቸው፡፡ የአፄ ዮሐንስ መካር አልቦ የውጪ ግንኙነት ፖሊሲ (የኃይማኖት ፖሊሲዉን ጨምሮ) እና ህብረት ያልታየበት የመተማ ጦርነት ዘመቻ የራሱን የኢትዮጵያን አንገት አስቆረጠ፡፡ የዮሐንስ የታሪክ ሽንፈቶች ለመከላከል ታጥቀው የተነሱ የትግራይ ዘዉጌ ብሄርተኛ ልሂቃን (ህወሓታዊያንና ዮሃንሳዊያን) የኤርትራን ጉዳይ ከምኒልክ ጋር ያዛምዱቱል፡፡ ህወሓት የበረሃ ማኒፌስቶውን ሳጋና ማገር በምኒልክና በአማራ ጥላቻ ላይ በማቆም፤ ሸዋን የስተቶች ሁሉ ቋት በማድረግ ትግራይን የምሉኼ በኩልሄዎች “አገር” (ልብ አድርጉ “አገር” ነው ያልነው!!) ያደርጋታል፡፡ ድህረ – ደርግን ተከትሎ የታሪክ ቅራኔዎችን በዞረ ድምር ሂሳብ ካላወራረድኩ የሚለዉ ህወሓት፤ በምኒልክ የደቡብ እና ምስራቅ ዘመቻዎች የደረሰውን ጥቃት እያስታወሱ ዛሬም ድረስ ቁጭታቸው ያልበረደላቸውን ዘውጌ ብሄርተኞች እያስተባበሩ በምኒልክ ላይ ፖለቲካዊ እርግማን ማውረድ ሥራቸው አድርገውታል፡፡ መንግስታዊ የመዋቅር ድጋፍ ያለው ይሄው ፖለቲካዊ እርግማን ምኒልክን “ኤርትራን የሸጠ” በሚል ከአድዋ ድል ለመነጠል እስከመሞከር የደረሰ የታሪክ ኑፋቄ ስብከት አደባባዩን ተቆጣጥሮታል፡፡ በወደብ አጠቃቀም፣ በንግድና ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ዙሪያ የሚያስተኩረውን የውጫሌን ውል ለኤርትራ መሸጥ እንደ ማስረጃ የሚያቀርቡ የትግራይ ብሄርተኛ ልሂቃን የዮሐንስ “የሂወት ውል” ስምምነት በኢትዮጵያ ላይ ያስከተለውን ጉዳት ማስታወስ አይፈልጉም፡፡ ዛሬ ላይ ብርቅ የሆነው የህብረት ስሜት ትላንት በአባቶቻችን አብሮነት (ህብረት) የታየበትን የአድዋን ድል አሳንሶ በማቅረብ የመበሻሸቂያ መድረክ አድርገውታል፡፡ 100ኛው የአድዋ ድል በዓል ሲከበር “ድሉ የትግራውያን እንጂ የሌሎች አይደለም” በሚል አይናቸውን በጨው አጥበው በአደባባይ ሲከራከሩ የነበሩ ሰዎች ዛሬ ላይ ተገልብጠው “አድዋ ተቀጥላ ድል እንጂ ዋና ዋና ድሎች በአጼ ዮሃንስ ጊዜ የተገኙት ናቸዉ” በማለት (በዘንድሮዉ የአድዋ ድል በዓል አከባበር ላይ አድዋ ከተማ ተገኝቶ ንግግር ያደረገዉን የትግራይ ክልል ኃላፊ አባይ ወልዱን የንግግር ይዘት ያስታዉሷል) ከታሪክ ጋር መላተማቸዉን ቀጥለዋል፡፡ በአጼ ዮሃንስ የንግስና ጊዜ የተገኙ ድሎችን ከፍ አድርጎ ለማድረግ በምኒልክ መሪነት የተገኘዉን የአድዋን ድል ማሳነስ ምን የሚሉት የታሪክ ድህነት ነዉ? በመሀል ቤት በተለያዩ አመታት በሁሉም አዉደ ዉጊያዎች ለኢትዮጵያ ሉዓላዊነት ህይወታቸዉ ያለፈ አባቶች ተረስተዋል፡፡ ሥም አልባ ጀግኖች አስታዋሽ የላቸዉም፡፡ ታሪክን በዜግነት ማዕቀፍ ሳይሆን በዘዉግ መነጽር ማየት የሚቀላቸዉ የህወሓት ሰዎች፤ ጊዜና ሁኔታዎች ፈቅደዉ የአድዋ ድል በአጼ ዮሃንስ መሪነት የተገኘ ቢሆን (ኑሮ) ይሄኔ ድሉ በአፍሪካ ደረጃ እንዲከበር የኢትዮጵያን ህዝብ ካዝና ከማራገፍ አልፎ ለክፉ ቀን ያስቀመጡትን የግዙፉን ኤፈርት ትልቅ በጀት ይዞ ለድል መታሰቢያዉ በድምቀት መከበር እንዲቀሳቀስ ባደረጉ ነበር፡፡ ምኒልክ ላይ ፖለቲካዊ እርግማን ማዉረድ የዮሃንስን የታሪክ ሽንፈቶች የሚያጠፋ ይመስል፤ ትዉልድና የታሪክ ትርጓሜ በተሳሳተ አቅጣጫ እንዲፈስ ማድረጉን ተያይዘዉታል፡፡ ይህ የኑፋቄ መንገድ የነገዋን ኢትዮጵያ በተለይም ትግራዋያንን በመነጠል የሚጎዳ እንጂ ምኒልክን የሚያረክስ አይደለም፡፡ ምኒልክ በስጋ ቢሞትም ኢትዮጵያ እስካልተበተነች ድረስ በመንፈስ ይኖራል፡፡ የምኒልክን የአንድነት ስሜት ጊዜና ወቅቱ በሚጠይቀዉ ማህበራዊ ዕድገት መሰረት በመግራት ኢትዮጵያን ወደከፍታዋ ለማዉጣት አቅሙም ፍላጎቱም የሌላቸዉ የህወሓት ሰዎች፤ ከሙት ሥርዓት ጋር ራሳቸዉን እያላተሙ በምኒልክና በዘመኑ ጀግኖች ተጋድሎ የቆመችዉን ኢትዮጵያ መበዝበዛቸዉን ተያይዘዉታል፡፡ የነገሩ ምጸትም ይሄዉ ነዉ፡፡ ምኒልክን እየረገሙ በረከቱን ለብቻ መብላት፡፡ ዶ/ር ዘዉዴ ገብረ ሥላሴ ኦክስፎርድ ዮኒቨርስቲ ባሳተመለት “Yohannes IV of Ethiopia; A political Biography” በሚል ሥራዉ፤ በ1879 ዓ.ም መጀመሪያ ላይ አጼ ዮሃንስ ለምኒልክ በጻፈለት ደብዳቤ “… በእግዚአብሔር ቸርነት ጣሊያኖች ተዋርደዉና ተንቀዉ ይመለሳሉ” (ገጽ፤199 ላይ ይመልከቱ) ብሎት ነበር፡፡ አጼ ዮሃንስ በርግጥ ስለ ጣልያኖች በዓለም ፊት መዋረድና መሸነፍ በትንበያ መልክ የጻፈዉ ደብዳቤ ልክ ነበር፡፡ አጼዉ ባያሳካዉ እንኳ አባ ዳኘዉ መሪነት በዘመኑ የወንድ የሴት አርበኞች ብርታትና የተዋጣለት ቅንጅት ጣሊያንን ድል መንሳት ተችሏል፡፡ በትግረኛ ቋንቋ “ኢይጥዕሞ መዓር…” እንዲሉ የትግራይ ብሄርተኛ ልሂቃን በተለይም የህወሓት ሰዎች፤ የምኒልክና የዘመኑ ጀግኖች ድል አይጥማቸዉም፡፡ ነገሩ ጣማቸዉም አልጣማቸዉም ምኒልክ ከነሰብዓዊ ድክመቱ ዓምዳ ዉዳድ ለኢትዮጵያ (ለኢትዮጵያ መሰረትና ምሰሶ) ነዉ!! ለመሆኑ አጼ ዮሃንስ ከምኒልክ የተሻለ መሪ ነበር? ታሪኩ ይህን አያረጋግጥም፡፡ የአጼ ዮሃንስ ለባዕድ ሥርዓት (ለእንግሊዝ) የማደግድግ ነገር ብዙ የተባለለት ጉዳይ ነውና ይህን አንዘረዝርም፡፡ ከ1870-1875 ዓ.ም ድረስ በነበሩ ዓመታት አጼ ዮሃንስ በትግራይ፣ በወሎ፣ በዋጅራቱ፣ በራያና አዘቦ የሚኖሩትን ኢትዮጵያዊ ሙስሊሞች በሙሉ በግድ ኦርቶዶክስ ክርስትናን እንዲከቀበሉ “ሰማይ ዓምድ የለዉ፤ እስላም ሀገር የለዉ” የሚል አዋጅ አወጀ፡፡አዋጁ ግልጽ ነዉ፡፡ ክርስትናን ያልተቀበለ የመሬት ባለቤት ሊሆን አይገባም፤ በያኔዋ የኢትዮጵያ ግዛት ዉስጥም መኖር አይችልም ለማለት ነዉ፡፡ ቀሳዉስትን ከጦር ሠራዊቱ ጋር ይዞ የዘመተዉ አጼ ዮሃንስ፤ በጊዜዉ ያደረሰዉን አጠቃላይ ክስተት በብሔራዊ ቤተመዛግብትና ቤተ መጽሐፍት ኤጀንሲ የሚገኘዉ “ታሪከ ነገሥት” እንዲህ ይተርክልናል “መከራዉን የፈሩ እስላሞች በልባቸዉ ሳያምኑ ባፋቸዉ ብቻ ‹አምነናል› እያሉ ተጠመቁ፡፡ ሥጋ ወደሙ ከተቀበሉ በኋላ በስዉር ካፋቸዉ እያወጡ እስከ መጣል ደረሱ፡፡ መከራዉን ያልፈሩት እስላሞች ግን ‹ክርስቲያን ከመሆን ሞት ይሻለናል› እያሉ እኩሉ በሞተ፣ እኩሉም በእስራት፣ እኩሉም በመወረስ፣ እኩሉም ካገር እየወጡ በመሰደድ ተቀጡ (ታሪከ ነገሥት፤ገጽ 75 ላይ ይመልከቱ)”፡፡ ከዚህ የማይፋቅ የታሪክ ማስረጃ እንደምንረዳዉ አጼ ዮሃንስ በኢትዮጵያዊያን ሙስሊሞች ላይ የከፋ ቅጣት ማድረሱን ነዉ፡፡ የአጼዉ የኃይማኖት ፖሊሲ ጸረ-እስልምና እንደነበር ለንግስት ቪክቶሪያ በላከላት ደብዳቤ ላይ በግልጽ አስቀምጦታል “ባገሬ አዘቦ የሚባል የኦሮሞ እስላም አገር አለ፡፡ ከርሱ ሽፍታ ተነሳብኝ፡፡ እርሱን ለማጥፋት ዘመትሁ፡፡እርሱንም በእግዚአብሔር ኃይል አጠፋሁት” ኢትዮጵያዊያን ሙስሊሞች በኢትዮጵያ ታሪክ ዉስጥ በተፈራረቁ ነገስታት እንደተበደሉ የማይካድ እዉነታ ነዉ፡፡ የአጼ ዮሃንስን ያህል ያስጨነቃቸዉ ንጉሥ ግን ከቶዉንም ያለ አይመስልም፡፡ በሀበሻ ምድር ሙስሊሞችን ብቻ እየለየ እንዲያሳድድ ተፈቶ የተለቀቀ እብድ ዉሻ ይመስል የወሎ ሙስሊሞችን እንዲህ አራቆቷቸዋል “(አጼ ዮሃንስ) አልጠመቅም ያለዉን እስላም ወሎ ከረሙ፡፡ ከእስላም ወገን በኃይማኖቱ የጸናዉና ጉልበት ያለዉ ወደ መተማ እየተሰደደ ከድርቡሽ ጋር ተደባለቀ፡፡ እኩሉም ወደ ሐረርና ቀቤና፣ ወደ ጅማ ተሰደደ፡፡ በዚሁም ምክንያት በያዉራጃዉ ሁሉ ሽፍታ ብቻ ሆነ፡፡ በየጅረቱም ሁሉ መጋደልና የሰዉ ደም መፍሰስ ሆነ (ታሪከ ነገሥት፤ ገጽ 60)”፡፡ የአጼ ዮሃንስ የከረረ የኃይማኖት ፖሊሲ መነሻዉ ግልጽ ይመስላል፡፡ የአጼዉ መሰረት ትግራይ ነዉ፡፡ በትግራይ ዉስን የሠራዊት ኃይል የጊዜዋን ኢትዮጵያ ማስከበር የሚታሰብ አይደለም፡፡ ወዲህም ለአጼ ቴዎድሮስ የዉድቀት መፋጠን የካህናቱ እጅ እንዳለበት ተረድቷል፤ ኃይማኖታዊ ፖሊሲዉን ተከትሎ ከአዉሮፓ መንግሥታት የጦር መሳሪያ ድጋፍ እንደሚያገኝ አስቦ ነበር፡፡ (ለንግስት ቪክቶሪያና ለንጉሥ ዊልያም አራተኛ እንዲሁም ለፈረንሳይ መንግስት የላከቸውን የደብዳቤ ይዘቶች ያጤኗል) በዉጤቱ ግን ዛሬም ድረስ በዞረ ድምር የታሪክ ቅራኔ ቁስል ያልሻረ የኢትዮጵያዊያን ሙስሊሞች ቂምና መሃዲስቶችን በተቀላቀሉ ኢትዮጵያዊ ሙስሊሞች ትብብር መተማ ላይ በተካሄደዉ ጦርነት የንጉሠ ነገሥትነት ዘመኑን አሳጠረ፡፡ አልፎ ተርፎም የጎንደርና አካባቢዉ ህዝብና ታሪካዊ ቅርሶች ወደሙ፡፡ አጼ ዮሃንስ የጎጃሙን ንጉሥ ተክለ ሃይማኖት ከምኒልክ ጋር አደመብኝ በሚል ለራሱ እንኳን ኋላ ላይ ሲያስበዉ የዘገነነዉን እልቂት በጎጃም ገበሬዎች ላይ ፈጽሟል፡፡ አጼ ዮሃንስ የቅጣት ሰይፉን መዞ ፊቱን ወደ ጎጃም ሲያዞር የጎጃም ገበሬዎች፡- “በላይኛዉ ጌታ በባልንጀራዎ በቅዱስ ሚካኤል በባልንጀራዎ በጽላተ ሙሴ በነጭ አበዛዎ ጎጃምን ይማሩት ፈሪም አንልዎ” የሚል ተማጽኖ ቢያሰሙም ከመዐቱ አልተረፉም፡፡ አፈወርቅ ገብረ ኢየሱስ “አጤ ምኒልክ” በሚለዉ መጽሃፉ “የትግሬ ወታደር ቄሱን ተበተስኪያን፣ ገበሬዉን ከዱሩ፣ ነጋዴዉን ተመደብሩ እያወጣ ጨረሰዉ (ገጽ፣ 54)”፤ “ጎጃምን የመሰለ ደግ አገርም ሦስት ወር ሙሉ በትግሬ አንበጣ ተደመደመ” (ገጽ፣52) በሚል በወቅቱ የደረሰዉን እልቂትና ዉድመት ይገልጸዋል፡፡ አጼ ዮሃንስ ለራስ ዳርጌ በጻፈዉ ደብዳቤ “በእኔም በድሃዉም ኃጢአት እንደሆን አይታወቅም አገሩን (ጎጃምን) ሳጠፋ ከረምሁ” (ኀሩይ ወልደ ሥላሴ፤ የኢትዮጵያ ታሪክ፣ ከሳባ እስከ ታላቁ የአድዋ ድል፤ ገጽ 179 ይመልከቱ) በማለት ጸጸቱን ይገልጻል፡፡ በኢትዮጵያ የነገሥታት ታሪክ በተለይም በኢትዮጵያ ዘመናዊ ታሪክ ሂደት ወስጥ ብዙ ሰብዓዊ ጥፋት እንደደረሰ መካድ አይቻልም፡፡ ነገሥታቱ ከሰብዓዊነት አኳያ “አለማወቅ” የሚባል ሰብዓዊ ጉድለት እንደነበረባቸዉ “ፍትሐ ነገስት”ን በማስታወስ መረዳት አይከብድም፡፡ ከሁሉ በላይ ደግሞ የነገሥታቱ ሠራዊት ይህ ነዉ የሚባል ቋሚ ደመወዝ የሌለዉ በመሆኑ ዘመቻ በወጡ ቁጥር ቅጥ ካጣ ጭካኔቸዉ ጋር የገበሬዉን ንብረት መዝረፍና ማዉደም የሰርክ ተግባራቸዉ ነበር፡፡ በዚህ መሰል አሰቃቂ ሂደት የተጨፈለቁ የማህበረሰብ ክፍሎች፤ ጉዳት የደረሰባቸዉ ወገኖች መኖራቸዉ እሙን ነዉ፡፡ እንደዚህ ባሉ ዘመቻዎች የቀደሙትን ነገሥታት ገትተን የዘመናዊት ኢትዮጵያ መስራትች አባቶች የሆኑት የቴዎድሮስ፣ የዮሃንስ እና የምኒልክ ሠራዊት በተፈራራቂነት በገባራቸዉ ላይ ጥፋት አድርሰዋል፡፡ በጊዜ ሂደት መጠኑ እየቀነሰ ቢሄድም ገባሮቹ በባርነት ተፈንግለዋል፡፡ መሬታቸዉንም ተነጥቀዋል፡፡ ባህላዊና ሰብዓዊ ክብራቸዉ የተረገጡም አሉ፡፡ ትልቁ ቁም ነገር የዚህን ሁሉ ግፍ መደባዊ ይዘት መረዳቱ ላይ ነዉ፡፡ ታሪክን ገልብጦ ማንበብ የሚቀላቸዉ የህወሓት ሰዎች በዘመናዊት ኢትዮጵያ ዉስጥ የአገር ምስረታ ሂደት ዉስጥ የደረሱ ጥፋቶችን ከአንድ ቋንቋ ተናጋሪ በዳይነት (አማራ) ጋር ብቻ ለማያያዝና ቂምን ወደ ትዉልድ ለማሻገር ሥርዓተ-ትምህርት ከመቀየር ሐዉልት እስከ መስራት ድረስ የዘለቀ እኩይ ድርጊት ላይ ተጠምደዋል፡፡ በዉጤቱም አገራዊ የጋራ ማንነቶችን (የጋራ ጸጋና መከራዎቻችን፤ ድልና ሽንፈቶቻችን) እየጠፉ አካባቢያዊ ማንነት አለቅጥ ተወጥሯል፡፡ እንዲህ ያለዉ አዝማሚያ መጨረሻዉ አገር በመበተን የሚቆም ብቻ አይደለም፡፡ ይልቁንስ ሁኔታችን ለርስ በርስ ጦርነት የቀረበ ሆኗል፡፡ በአገራችን የፖለቲካ ባህል በአሳዛኝ መልኩ እየበረታ የመጣ ክፉ በሽታ አለ፡፡ እርሱም ኃላፊነት መዉሰድ አለመቻል፡፡ ይህ ክፉ ልማድ ከ1960ዎቹ ትዉልድ የጀመረ ቢሆንም በድህረ-ደርግ በአደባባይ ዘዉጋዊ ልባስ አግኝቶ ማንነትን የታከከ ታሪክ ትርጓሜ ተንተርሶ አገሪቷን ወደ ብተናና እልቂት እየገፋት ይገኛል፡፡ ይህ ጉዳይ ዛሬ ላይ ከቁጥጥራቸዉ ቢወጣም የህወሓት ሰዎች በተጠና መልኩ ሲተገብሩት የኖሩት ጉዳይ ነዉ፡፡ ለህወሓት ሰዎች ታሪክ ትምህርት ሳይሆን ፍርድ ቤት ነዉ፤ አንዱን ንጉሥ ኮንነዉ ሌላዉን የሚያጸድቁበት፡፡ ከሦስት አመት በፊት የአጼ ምኒልክ 100ኛ ሙት ዓመት መታሰቢያ ቀን የትኛዉም ዩኒቨርስቲም ሆነ እንደ ባህልና ቱሪዝም ያሉ መንግስታዊ ተቋማት በአገር አቀፍ ደረጃ ሳያከብሩት አልፏል፡፡ አሳፋሪዉ ነገር “የኢትዮጵያ አርበኞች ማህበር”ም የገዥዎችን ቁጣ ፈርቶ ዝምታን መርጦ ማለፉ ነበር፡፡ በጊዜዉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን (እንደ ሥርዓቷ) ሰማያዊ ፓርቲ በየግላቸዉ አቅማቸዉ በፈቀደ መጠን አክብረዉት ነበር፡፡ በአንጻሩ መጋቢት 2/2009ዓ.ም የትግራይ ክልል ደራሲያን ማህበርና መቀሌ ዩኒቨርስቲ በመተባበር የአጼ ዮሃንስን 128ኛ የሙት ዓመት መታሰቢያ በደመቀ መልኩ አክብረዉታል፡፡ ዮሃንስ ከነሰብዓዊ ጉድለቶቹ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ነበር፡፡ በተለያዩ አዉደ ዉጊያዎች ከዉጭ ወራሪ ኃይሎች ጋር በጀግንነት ተፋልሟል፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ ደንበር ላይ የተዋደቀ ብቸኛዉ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት ነዉ!! በዚህና መሰል ጉዳዮች ታሪክ ከነድል-ሽንፈቶቹ ሲያሥታዉሰዉ ይኖራል፡፡ጥያቄው ለዮሃንስ የተሰጠዉ ክብር ለምኒልክ ሲሆን ለምን ይነፈጋል? የህወሓትና አክራሪ የትግራይ ብሄርተኞች ዮሐንስ የፈጸመዉን ሰብዓዊ ጥፋት ወደ ጎን ትተዉ በታሪክ ፍርዳቸዉ ነጻ ሊያወጡ ሲሞክሩ፤ ስለ ምኒልክ ለምን የብዜትና ፈጠራ ታሪኮችን በፖለቲካ ርግማን መልኩ ሲያዘንቡ ይታያል? ዮሃንስ በፈጸመዉ ጭፍጨፋ ታሪክ ነጻ ካወጣዉ ምኒልክንስ ታሪክ ስለምን ይኮንነዋል? ለዚህ ነዉ ለህወሓት ሰዎች ታሪክ ትምህርት ሳይሆን ፍርድ ቤት ነዉ የምንለዉ፡፡ ዮሃንስን ከፍ አድርጎ ምኒልክ ላይ የፖለቲካ ርግማን የሚያወርድ የመቀሌ ችሎት!! በመስመር መሀል የትግራይ የአካዳሚያ ልሂቃን፣ ህዝባዊ የታሪክ ጸሃፍት፤ የ“አረና ፓርቲ አመራሮች” እና ብዙሃኑ የትግራይ ወጣቶች የመቀሌዉ የታሪክ ፍርድ ችሎት አጨብጫቢዎች መሆናቸዉን ስንታዘብ አድዋን የሚያህል ወታደራዊ ድል ስለምን ወደ ፖለቲካዊ ድል መቀየር እንደተሳነን ይገለጽልናል፡፡ የከረረ ዘዉጌ ብሄርተኝነት የክፉ ዉሾች ጉሮኖ ነዉ፡፡ ከታሪክ ዝንባሌ የመነጨ ሲሆን ደግሞ የአሳሞች ጋጥ ይሆናል (የጆርጅ ኦርዌል፤ Animal farm ላይ ያሉትን አሳማዎች ያስታዉሷል) አገራዊ ጅግኖቻችን እያወረድን ዘዉጋዊ ጀግና ማድረጋችንን ከቀጠልን የአድዋ ድል መንፈስ ፍጹም እየራቀን እንጅ እየቀረበን ሊመጣ አይችልም!! (በቀጣይ ዕትማችን ከአድዋ ድል በዓል አከባበር ጋር ተያይዞ ከአዲሱ የአማራ ዘዉጌ ብሄርተኛ ቡድን ላይ የታዘብናቸዉን እና የጽሁፉን ማጠቃለያ እናቀርባለን) ማሳሰቢያ፤ በተለይ በስም ወይም በድርጅት ስም እስካልተጠቀሰ ድረስ በጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ® ላይ የሚወጡት ጽሁፎች በሙሉ የጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ®ንብረት ናቸው፡፡ ይህንን ጽሁፍ ለመጠቀም የሚፈልጉ ሁሉ የዚህን ጽሁፍ አስፈንጣሪ (link) ወይም የድረገጻችንን አድራሻ (https://www.goolgule.com/) አብረው መለጠፍ ከጋዜጠኛነት የሚጠበቅና ህጋዊ አሠራር መሆኑን ልናሳስብ እንወዳለን፡፡
ኣብ ዙርያ ዓለም ዝረኣ ዘሎ ዋዒ ጽዑቅ: ተደጋጋሚን ንንውሕ ዝበለ ጊዜ ዝጸንሕን እናኾነ ይመጽእ ኣሎ። እቲ ኣብ ኣህጉር ኣውሮጳ ይራኣይ ዘሎ ግና፣ ፍልይ ዝበለን ከም ኣባሃህላ ተመራመርቲ ድማ "ንምርድኡ ዘጸግም እዩ" ይብሉ። መበገሲ እቲ ኣብ ወርሒ ሓምለ ንኣውሮጳ ዘጓነፋ መሸምበባ ዋዒ፣ ተደጋጊሙ ዘጋጠመ ብርቱዕ ዋዒ፣ ጠንቁ፣ ለውጢ ኩነታት ኣየር (ክሊማ) እዩ። ኣብ ዙርያ ዓለም’ውን ዝራኣይ ጸገም ኮይኑ ንረክቦ። ተመራመርቲ እቲ ኣብ ኣህጉር ኣውሮጳ ዝረኣ ዘሎ ዋዒ (ሙቀት)፣ ምሒር ዝበርተዐ እዩ ይብሉ። ኣብ ፈረንሳ ቤተ ፈተነ መጽናዕቲ ኩነታት ኣየር ዝነጥፍ ራበርት ቮውተር ከምዚ ይብል፣"መሸምበባ ዋዒ ኣዝዩ ተደጋጋሚን ጽዑቅን ኮይኑ ኣሎ። እቲ ኣብ’ዚ ቀረባ ዘጋጠመ ሙቀት፣ መቀጸልታ ናይ’ቶም ብተደጋጋሚ ዘጋጠሙ ጸገማት ሙቀት እዩ።" ንሱ ወሲኹ "መጽናዕትና ክሳብ ክንደይ ሓደገኛ ዋዒ ከጋጥም ከምዝኽእል ምርዳእ የኽእለና እዩ፣ ካብኡ ሰጊሩ ግና ነቲ ኣብ ኣውሮጳ ዘጋጠመ ብርቱዕ ሙቀት ኣቀዲምና ንክንፈልጥ ግና ኣይሕግዘናን" ይብል። "እቲ ኣገባብና ኣቐዲሙ ክፈልጦ ዝኽእል ከምዚ ዝበለ ብርቱዕ ዋዒ ስለምንታይ ከምዘጋጥመና ክርዳኣና ኣይከኣለን።እዚ ኣገባብና፣ ኣብ’ዞም ዝሓለፉ 100 ዓመታት፣ ናይ 1.5-2 ዲግሪ ወሰኽ ዋዒ ኣቀዲሙ ንምፍላጥ ሓጊዙና እዩ። ወሰኽ 4 ዲግሪ ግና ክፈልጥ ኣይኽእልን።" ተመራመርቲ መልሲ ንምርካብ ይጽዕሩ ኣለው። ኣብ ዩኒቨርሲቲ ኣምስተርዳም ዝነጥፍ ዲም ኮሞ ብወገኑ "መንቀሊ እቲ ንኣውሮጳ ዘጥቀዐ ብርቱዕ ዋዒ፣ ማዕበል ኣየር እዩ" ይብል። ክብ ኣብ ዝበለ ስፍራ ዝነፍስ ‘ጀት ስትሪም’ ይብልዎ፣ ንኩነተ ኣየር ኣውሮጳ ኣዝዩ ኣገዳሲ እዩ። ገለ እዋን፣ እዚ ንፋስ’ዚ ኣብ ክልተ ይኽፈል። እዚ ኩነት’ዚ ተመሊሱ ንኩነታት ኣየር ኣውሮጳ፣ ሓዊ ክተፍእ ይገብሮ። ለውጢ ክሊማ፣ እዞም ኣብ ክልተ ዝምቀሉ ኣንፈታት፣ ተደጋጊሞም ንከጋጥሙ’ውን ጠንቂ ይኾኑ። ኮሞን መሳርሕቱን፣ እቲ ንምዕራብ ኣውሮጳ የጓንፎ ዘሎ ብርቱዕ ዋዒ ከመይ ከምዝመጽእ ንምትንታን ፈቲኖም እዮም፣ "እወ ‘ኩነተ ጀት ስትሪም’ ብሕልፊ ኣብ ምዕራባዊ ክፋል ኣውሮጳ ይውስኹ ከምዘለው ተዓዚብና ኣለና። ስለዚ፣ መንቀሊ’ቶም መሸምበባ ዋዒ ኣብ ምዕራብ ኣውሮጳ፣ እቶም ተደጋጊሞም ዝኽሰቱ ዘለው ‘ጀት ስትሪም’ እዮም።" ደርቂ’ውን ጠንቂ ንኣውሮጳ ገጢሙዋ ዘሎ ማዕበል ዋዒ ክኸውን ይኽእል እዩ። ኣብ ዙሪክ ዘላ ተመራማሪት ክሊማ ሶንያ ሰንሰቭራትናይ ‘ዝነቀጸ መሬት ማለት፣ ናብ ኣየር ዝበንን ሃፋየለን(ኢቫፖ ትራንስፓይረሽን) ማለት እዩ" ትብል። "ኢቫፖ ትራንስፓይረሽን፣ መብዛሕትኡ ጊዜ፣ ብዙሕ ሓይሊ እዩ ዝጥቀም። እዚ ማለት፣ መሬት ስለዝደረቀ ኢቫፖ ትራንስፓይረሽን ክፍጸም እንተዘይ ኪኢሉ፣ እቲ ሓይሊ ንኩነታት ኣየር እዩ ዘርስኖ።" ንሳ ወሲኻ፣ እቲ ሎም ዘበን ዘጋጠመ ደርቂ መበገሲኡ’ውን እዚ ክኸውን ይኽእል እዩ ትብል። "ደረቅ መሬት፣ ነቲ ኣብ ኣውሮጳ ዝተራኣየ መሸምበባ ዋዒ ጠንቂ ኮይኑ ከምዘሎ ንጹር ምልክት ኣሎ።" ኣብ ኣየርላንድ ዩኒቨርስቲ ማዮንዝ ትመራመር ኪኢላ ፊዚክስ ሌቭክ ቄሳር ብወገና "ኣብ ውቅያኖሳት ዘጋጥም ኩነተ ኣየር’ውን መንቀሊ ዋዒ ክኸውን ከምዝኽእል ትእምት። ሰሜናዊ ክፋል ውቅያኖም ኣትላንቲክ ምዝሓል ስለዝጀመረ፣ ኣህጉር ኣውሮጳ’ውን ካብ ዋዒ ክትገላገል እያ፣ እንተኾነ፣ ነቲ ኣብ ኣውሮጳ ክረኣ ዝቀነየ ኩነታት ሙቀት መበገሲኡ፣ ኣብ ውቅያኖሳት ዝተኸሰተ ነገር ኣይኮነን" ትብል። "ክፋል ሰሜናዊ ውቅያኖስ ኣትላንቲክ፣ ኣብ’ዚ እዋን’ዚ ዝሑል ኣይኮነን ዘሎ። ስለዚ፣ ነቲ ኣጓኒፉ ዘሎ ነገር፣ ኩነታት ውቅያኖስ ኣበርክቶ ገይሩ ኣሎ ንከይንብል ይሕግዘና እዩ።" ተመራመርቲ፣ ሚስጥር ንኣህጉር ኣውሮጳ ዘጋጥማ ዘሎ ብርቱዕ ዋዒ ንምርዳእ፣ ተወሳኺ መጽናዕቲን ምርምርን ምክያድ ኣገዳሲ እዩ። ንጊዚኡ’ውን እንተኾነ ግና፣ ወርሓት ሰን፣ ሓምለን ነሓሰን፣ ንኣውሮጳ፣ ወርሓት ብርቱዕ ዋዒ ኮይኖም ክቅጽሉ እዮም ይብሉ። ተመራማሪ ቫውተር "ለንደን ክሳብ 40 ዲግሪ ሴንቲግሬድ ተመዝጊቡላ ኣሎ። ሓደ ሰብ ከምዚ ከምዝኾነ ቅድሚ ዕስራ ዓመት እንተዝነግረኒ፣ ንክኣምኖ ምተጸገምኩ ነይረ' ይብል። ካብ’ኡ ተበጊሱ ኣውሮጳዊያን፣ ኣብ’ዚ ካብ በጻሕናስ፣ ንቀጻሊ ዓመታት እምባኣር ክሳብ 50 ዲግሪ ሴንትግሬድ ዋዒ ተጸበዩ ብምባል የዳልዎም።
ትናንት ሰኞ በሞቃድሾ በተደረገው ጋዜጣዊ መግለጫ እንደተመለከተው የሶማሊያ ሰብአዊ ጉዳዮች ልኡካን ቡድን ሶማልያ ውስጥ ከ6 ሚሊዮን በላይ ሰዎች እስከዛሬ ከፍተኛ በሆነው ድርቅ ተጠቅተዋል፡፡ አብዱርሃማን አብዲሸኩር ዋርሳሜ በድርቁ እየተጎዳ ያለው ህዝብ የሶማልያን ህዝብ ግማሽ ሊያክል ምንም አልቀረውም ይላሉ፡፡ ዋርሳሜ ድርቅ ከ84ቱ የሶማሌ አውራጃዎች 72 ያህሉን ጎድቷል ብለዋል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ስድስት የሚሆኑት በከፍተኛ የምግብ እጥረት የተጠቁ በመሆናቸው ከወዲሁ ከፍተኛ ረሃብ በመሰለ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ ናቸው፡፡ ዋርሳሜ "ሰዎቻችን አሁን መሞት ጀምረዋል፡፡ ሞት ጀምሯል፡፡ ረሀብ በአንዳንድ አካባቢዎች እያንዣበበ ድርቅም ወደ ረሀብ እየተቀየረ ነው፡፡ በአገር ውስጥና በውጭ ያሉ ሶማልያውያን አንዳንድ ኃላፊነቶችን በመውሰድ ሊያግዙን ይገባል፡ " ይላሉ ልኡካን ቡድኑ በረሃብ የሞቱት ሶማሌዎች ምን ያህል እንደሆኑ በቁጥር አልገለጹም፡፡ እርዳታ ለሚያስፈልጋቸው ሰዎች ግን እገዛ እንዲደረግ ጠይቀዋል፡፡ ዋርሳሜ አሁን ያለው ድቅር "በአርባ ዓመት ውስጥ የከፋው ነው፡፡ ወደ 700ሺ የሚጠጉ ሶማልውያውያንን ከየገጠሩ እያፈናቀለ በየከተሞች አቅራቢያ እንዲሰፍሩ አድርጓል" ይላሉ፡፡ ዋርሳሜ እንደሚገልጹት የተባበሩት መንግሥታትና የረድኤት ድርጅቶች 1.4 ቢሊዮን ዶላር የጠየቁ ሲሆን ከእዚህ ውስት ያገኙት 58 ሚሊዮን ዶላር ብቻ መሆኑን ይናገራሉ፡፡ ዓለም አቀፍ የረድኤት ድርጅቶቹ ብዙ ትኩረት የሰጡት ለኮቪድ 19 ወረርሽኝ፣ ለሩሲያው የዩክሬን ጦርነት፣ ለአፍጋኒስታን፣ ለሶሪያና የመን ቀውሶች መሆኑን ዋርሳሜ ተናግረዋል፡፡ የሰብአዊ ጉዳዮች ልኡካኑ ጨምረው እንደገለጹት ባላፈው ዓመት ሳደረግ ቀርቶ ዘንድሮ የተደረገው የሶማልያ ምርጫ ብዙ ትኩረት ያገኘ በመሆኑ ለሰብአዊ እርዳታው ምንም ትኩረት አልተሰጠውም፡፡
ለእርስዎ ማጨጃ የሚሆን ትክክለኛውን መተኪያ ምላጭ እንደላክን ለማረጋገጥ፣ እባክዎን የኦሪጂናል ዕቃ አምራች # ወይም የቢላዎን መለኪያ (ከላይ ከግራ ወደ ታች በስተቀኝ Blade ወይም ከላይ ከቀኝ ወደ ግራ በስተግራ ርዝመት ይለኩ)። በባለቤትዎ መመሪያ ወይም ክፍሎች ዝርዝር ውስጥ የአምራችዎን ክፍል ቁጥር ያረጋግጡ።የተዘረዘረው OEM # ከዚህ ቁጥር ጋር መመሳሰል አለበት።የአምራችህ ክፍል ቁጥር ካልተዘረዘረ በነፃ ስልክ ቁጥር 800-345-0169 ይደውሉልን እና ሙሉ የቢላ ማከማቻችንን እንፈትሻለን፣ እና/ወይም ለእርስዎ እንደምናገኝ እናያለን! ቢላዎችን በሚጭኑበት ጊዜ እባክዎ የማጨጃ አምራቹን የመጫኛ መመሪያዎችን ይከተሉ።እነዚህን መመሪያዎች አለመከተል በንብረት ላይ ጉዳት፣ በግል ጉዳት ወይም ሞት ሊያስከትል ይችላል። እኛ "ጥራት ከፍተኛ-ጥራት ነው, ኩባንያ የበላይ ነው, ሁኔታ የመጀመሪያው ነው" ያለውን አስተዳደር መርህ መከተል, እና በቅንነት መፍጠር እና ሁሉም ሸማቾች ጋር ስኬት እናካፍላለን OEM ቻይና ቻይና ሙቅ.የሣር ማጨጃ Bladeበከፍተኛ ጥራት (9GW-1.4)፣ በማንኛውም ዕቃዎቻችን ላይ ፍላጎት ካሎት ወይም በብጁ ግዢ መወያየት ከፈለጉ፣ እኛን ለመያዝ ምንም ወጪ ሊሰማዎት አይገባም። የኦሪጂናል ዕቃ አምራች ቻይና ማጨጃ እና የሳር ማጨጃ ዋጋ፣ ብዙ ታማኝ ደንበኞችን በበለጸጉ ልምድ፣ የላቀ መሳሪያዎች፣ የሰለጠኑ ቡድኖች፣ ጥብቅ የጥራት ቁጥጥር እና ምርጥ አገልግሎት እናሸንፋለን።ሁሉንም እቃዎቻችንን ዋስትና መስጠት እንችላለን.የደንበኞች ጥቅም እና እርካታ ሁሌም ትልቁ ግባችን ናቸው።እኛን ማነጋገርዎን ያረጋግጡ።እድል ስጠን, አንድ አስገራሚ ያቅርቡ.
መበል 17 ደረጃ ሒዛ ዝቐነይትን ብሕማቕ ቁመናኣ ትሳቐ ዘላን ኤቨርተን ንማንቸስተር ዩናይትድ ኣብ ሜዳኣ ጉዲሰን ፓርክ ዓዲማ ዘካየደቶ ግጥም፡ ብመንገዲ ወዲ 21 ዓመት ተጻወታያ ሓንቲ ጎል ተሓጊዛ ብጸቢብ 1 ብ 0 ተዓዊታ ወጺኣ። ማን ዩናይትድ ኣብዚ ዓመተ-ስፖርት ራብዓይ ደረጃ ሒዛ ጸወታኣ ክትዛዝም እትገብሮ ቃልሲ ሕጂውን መኻልፍ የጋጥማ ኣሎ። ኣጥቃዒ ማን-ዩናይትድ ራሽፎርድ ዝነኣሰ ተጸዋታ 200 ፕሪሚየር ሊግ ጸወታታት ዘካየደ ተጸዋታይ ትባሂሉ ኣብ ዝተጸወዓሉ ጸወታ፡ ክለተ ሓደገኛ ፈተነታት ኣካይዱ፡ እንተኾነ ብ ሓላው ልዳት ኤቨርተን ጆርዳን ፒክፎርድ ፈሺለን። ንኣሰልጣኒኣ ራልፍ ራንግሊክ ናይ ምቕያር መደብ ዘለዋ ማን ዩናይትድ፡ ጽቡቕ ጸወታ’ኳ እንተኣርኣየት ሽቶ ግን ክሰልጣ ኣይከኣለን፣ ብፍላይ ሮናልዶ ኣብ መወዳእታ ደቃይቕ ዝፈተና ኣዝያ ጽብቕቲ ፈተነ፡ ሓንቲ ነጥቢ ሒዛ ክትምለስ ዘኽእላ ዕድል ኢያ ኔራ። ድሕሪዚ ውጽኢት፡ ደግፍቲ “ዘ ሬድ ዴቪልስ” ዓቢ ሻቕሎት ኮይኑዎም ዘሎ ጉዳይ ክርስትያኖ ሮናልዶ ኢዩ። ኣብታ ክለብ ይጸንሕ’ዶ ይኸውን? ዝብል ሻቕሎት። ኒውካስትል ተዓዊታ ትማሊ ምሸት ኣብ ቅድሚ ደገፍታ ንዎልቭስ ዓዲማ ጸወታኣ ዘካየደት ኒውካስል ዩናይትድ፡ ድሕሪ ዕረፍቲ ኣብ መበል 72 ደቒቕ ብመንገዲ ፍጹም ቅላዕ ካብ ክሪስ ዉድ ዝረኸበታ እንኮ ሽቶ ተሓጊዛ 1 ብ 0 ተዓዊታ። ዝሓለፈ ሰሙን ብቶተንሃም ሆትስፐር 5 ብ 1 ብገፊሕ ዝተሳዕረት ኒውካስትል፡ ካብ ናብ ታሕታዋይ ሊግ እንግሊዝ ዝወርዳ ታሕተዎት 3 ክለባት ብ 10 ነጥቢ በሊጻ፡ ብ 34 ነጥቢ መበል 14 ደረጃ ትርከብ።
ደምሴ ሥራ የሌለው ክርስቲያን ነው፤ እርሱና ቤተሰቡ በልተው የሚያድሩት ምግብ ለመግዛት የሚያስችል በቂ ገንዘብ የሚያገኘው አልፎ አልፎ ነው። የሚረዳው ዘመድ እንኳ አልነበረም። «ለነገ እንዳልጨነቅ እግዚአብሔር ለምን በቂ ገንዘብ አይሰጠኝም?» ሲል ያስባል። «ሥራ የማገኘው እንዴት ነው? ለኑሮ የሚያስፈልገንን ገንዘብ የማገኘው ከየት ነው?» ብታመም የምታክመው በምኔ ነው? በማለት ስለ ወደፊት ኑሮው እጅግ ይጨነቃል። «ብሞትስ፣ ባለቤቴንና ልጆቼን ማን ይንከባከባቸዋል?» እነዚህ አሳቦች ውስጡን ሰርስረው ለጭንቀት ዳረጉት። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) ፍርሃትና ጭንቀት አሳባችንን በቀላሉ የሚቆጣጠሩት ለምንድን ነው? ለ) ዮሐ 14፡1-4 እና ዕብ 11፡10፥ 16 አንብብ። እነዚህን ምንባቦች ከሕይወታችን ጋር ብናዛምድ ጭንቀትን እንድናሸንፍ እንዴት ይረዱናል? ጭንቀት የሚመነጨው ካለማመን ነው። «ምግብና ልብስ ከየት እናገኝ ይሆን?» እያልን የምንጨነቅ ከሆነ፥ ክርስቶስ በየዕለቱ የሚያስፈልገንን ነገር ለማሟላት የገባልንን ቃል ዘንግተናል ማለት ነው (ማቴ. 6፡25-34)። ስለወደፊቱ የምንጨነቅ ከሆነ፥ ክርስቶስ «የነገ» ጌታ እንደ ሆነ ዘንግተናል ማለት ነው። ስለ ጤንነታችን የምንጨነቅ ከሆነ፥ ክርስቶስ ታላቁ ሐኪም እንደ ሆነ ረስተናል ማለት ነው። እንዲሁም፥ ስለ ቤተሰቦቻችን የምንጨነቅ ከሆን፥ ክርስቶስ እኛ ከምንወዳቸው በላይ እንደሚወዳቸውና አስፈላጊውን እንክብካቤ እንደሚያደርግላቸው ዘንግተናል ማለት ነው። ደቀ መዛሙርቱ ክርስቶስ ተለይቷቸው እንደሚሄድ ባወቁ ጊዜ በጣም ተጨነቁ። ከሦስት ዓመት በላይ ከክርስቶስ ጋር ኖረዋል። ሥራቸውንም ትተው ነበር። በዚህ ላይ ድሆች ነበሩ። ወደፊት ምን ይገጥማቸዋል? ያለ ክርስቶስ የሕይወትን ማዕበል እንዴት ይቋቋሙታል? ስለሆነም፥ ክርስቶስ በአካል ከእነርሱ ጋር በማይኖርበት ጊዜ የወደፊት ሕይወታቸው እንዴት እንደሚሆን የተለያዩ እውነቶችን በመንገር ያጽናናቸዋል። ዮሐንስ 14-17 ኢየሱስ፥ ደቀ መዛሙርቱ ስለ እርሱ፥ ስለ መንፈስ ቅዱስና ስለ ደቀ መዝሙርነት ሕይወት እንዲነዘቡ የሚፈልጋቸውን አንዳንድ አጠቃላይና እጅግ ጠቃሚ እውነቶችን አካትቶ ይዟል። ኢየሱስ ለተከታዮቹ ዘላለማዊ የመኖሪያ ስፍራ እንደሚያዘጋጅ ቃል ገባ (ዮሐ 14፡1-4) ምን ጊዜም ቢሆን መለያየት ሥቃይ አለበት። ክርስቶስ ወደ ሰማይ ተመልሶ መሄዱ በደቀ መዛሙርቱ ላይ የመለየትን ሥቃይና ጥርጣሬ እንዳያስከትልባቸው በማሰብ የተለያዩ እውነቶችን አስተማራቸው። እነዚህ እውነቶች እያንዳንዱ ክርስቲያን ዛሬ ሊያውቃቸውና ከሕይወቱ ጋር ሊያዛምዳቸው የሚገቡ ናቸው። የክርስቶስ ተከታዮች በብርቱ መከራና ሥቃይ መካከል በተስፋ ሊኖሩ የሚችሉት እንዴት ነው? ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ ሁለት ዐበይት እውነቶችን አስጨብጧል፡- ሀ. ደቀ መዛሙርቱ ሁልጊዜ በእግዚአብሔርና በክርስቶስ ላይ ያላቸውን እምነት አጽንተው መያዝ አለባቸው። እምነት እንዴት እንደሚሠራ ባናውቅም፥ እግዚአብሔር በሰጠው ቃል ላይ ተመሥርቶ መኖር ነው። የእግዚአብሔርን የተስፋ ቃሎች በማወቅና በእነዚህ ቃሎች ላይ የተመሠረተ ሕይወት ለመምራት በመቁረጥ፥ ተስፋችንን አጽንተን እንይዛለን። ተስፋ ቆርጠን የምንጨነቀው ዓይኖቻችንን ከእግዚአብሔር ላይ ስናነሣ፥ የተስፋ ቃሎቹን ስንረሳና ፍጹም የተስፋ ቃሎቹን ከሕይወታችን ጋር ሳናዛምድ ስንቀር ነው። ለ. የክርስቶስ ተከታዮች ዓይናቸውን በዘላለሙ ተስፋ ላይ ማድረግ አለባቸው። ክርስቶስ ደቀ መዛሙርቱን እንደማይተዋቸው፥ በሰማይም እነርሱ የሚኖሩበትን ስፍራ እንደሚያዘጋጅላቸው ቃል ገብቶላቸዋል። ስለሆነም፥ በእግዚአብሔር አብ መንፈሳዊ ቤት፥ ኢየሱስ ለተከታዮቹ ሁሉ የመኖሪያ ስፍራ ያዘጋጅላቸዋል። ሕዝቡ ሁሉ ወደ እርሱ ዘንድ ሲሄዱ በአንድ ትልቅ ቤት ውስጥ እንደማይታጎሩና በዘላለሙ ስፍራ እግዚአብሔር ለልጆቹ ለእያንዳንዳቸው የተለየ ስፍራ እንደሚያዘጋጅላቸው ከክርስቶስ ትምህርት መገንዘብ ይቻላል። የውይይት ጥያቄ፡- ዓይናችንን በዘላለሙ ተስፋ ላይ ማድረጋችን በእምነታችን ጸንተን እንድንቆም የሚረዳን እንዴት ነው? በኢየሱስ ማመን ወደ እግዚአብሔር የሚያደርስ መንገድ ነው (ዮሐ 14፡5-14) መንገድ ወደምንፈልግበት ስፍራ እንድንደርስ ስለሚረዳን፥ በጣም አስፈላጊ ነገር ነው። ነገር ግን ትክክለኛው መንገድ የትኛው እንደ ሆነ ማወቅ አለብን። ደቀ መዛሙርቱ ወደ እግዚአብሔር አብና በሰማይ ወደሚገኘው ወደ ዘላለማዊ ቤታቸው በሚያደርሰው ትክክለኛው መንገድ ላይ እየተጓዙ መሆናቸውን ለማረጋገጥ ፈልገው ነበር። ክርስቶስም ብርቱ በሆኑ ቃላት የሚከተለውን ምላሽ ሰጥቷቸዋል፡- ሀ. ኢየሱስ «እኔ መንገድ፥ እውነትና ሕይወት ነኝ፤’ በእኔ በቀር ማንም ወደ አብ ሊመጣ አይችልም» አላቸው (ዮሐ 14፡6)። ይህ ክርስቶስ የተናገረው ስድስተኛው «እኔ ነኝ» የሚለው ዐረፍተ ነገር ነው። በዚህ ንግግሩ ኢየሱስ ወሳኝ አሳቦችን ሰንዝሯል፤ ወደ ሰማይ እናደርሳለን የሚሉ ሰው ሠራሽ መንገዶች እንዳሉ ቢገልጽም፥ ሁሉም ግን እውነተኛ መንገዶች እንዳልሆኑ አመልክቷል። በራሳቸው መንገድ ወደ ሰማይ ለመድረስ የሚጥሩ ሰዎች፥ ካሰቡት ሊደርሱ አይችሉም። በመሐመድ፥ በቡድሃ ወይም በተከታዮቻቸው የሚያምኑ ሰዎች፥ መንግሥተ ሰማይ ሊገቡ አይችሉም። ማንም ሰው ወደ እግዚአብሔር ሊደርስ የሚችለው በክርስቶስ በማመን ብቻ ነው። ምንም እንኳ ዛሬ ወደ እግዚአብሔር የሚያደርሰው መንገድ አንድ ብቻ ነው የሚለው አሳብ በዓለም ላይ ተወዳጅነት ባይኖረውም፥ መጽሐፍ ቅዱስ የሚያስተምረን ግን ይህንን ሐቅ ነው። ይህ ክርስቲያኖች በራሳቸው ያመጡት አሳብ ሳይሆን፥ ክርስቶስ ራሱ የተናገረው ነው። ክርስቶስ ወደ እግዚአብሔር የሚያደርሰው ብቸኛው መንገድ እርሱ ራሱ እንደ ሆነ ተናግሯል። ክርስቶስ እውነትን ሁሉ የያዘ አምላክ በመሆኑ፥ እውነት የሆነውን አሳብ ማስተማር ብቻ ሳይሆን፥ ወደ እግዚአብሔር የሚያደርስ እውነተኛ መንገድም ነው። እንዲሁም፥ መንፈሳዊም ሆነ ሥጋዊ ሕይወትን የሚቆጣጠረው ክርስቶስ ነው። ስለሆነም፥ የዘላለም ሕይወት የሚገኘው በክርስቶስ አማካይነት ብቻ ነው። ለ. ክርስቶስ የእግዚአብሔር አብ ትክክለኛ እንደራሴ ነው። ወደ ክርስቶስ መመልከት፥ ወደ እግዚአብሔር እንደ መመልከት ያህል ነው። ኃይላቸው፥ ባሕርያቸውና ዓላማቸውም አንድ ነው። ክርስቶስ ፈቃዱን ለአብ ስላስገዛ፥ አብ የነገረውን ብቻ ተግባራዊ ያደርጋል፤ ደግሞም ከእርሱ ጋር በፍጹም ስምምነት ስለሚሠራ፥ የአንዱ ሥራ የሌላውም ነው። (ማስታወሻ፡የሥላሴን ሕልውና የካዱና «ኢየሱስን ብቻ» እናመልካለን የሚሉ ተከታዮች እንደሚያስተምሩት በዚህ ክፍል ክርስቶስ ከአብ ጋር አንድ አካል መሆኑን እየገለጸ አይደለም። የተለያዩ አካላት መሆናቸው በዚህም ሆነ በሌሎች ክፍሎች ግልጽ ነው። ዮሐንስ የሚናገረው ግን በመካከላቸው ስላለው ፍጹም ስምምነትና የጋራ አንድነት ነው። እግዚአብሔር አብና እግዚአብሔር ወልድ ድርጊቶችን ሁሉ በጋራ ተስማምተው ያከናውናሉ።) ሐ. የክርስቶስ ተከታዮች ከእግዚአብሔር ጋር የጠበቀ ግንኙነት በማድረግ ደስ ይሰኛሉ። እነርሱም ክርስቶስ ካደረጋቸው ነገሮች የበለጠ እንደሚያደርጉ ገልጾአል። ኢየሱስ እንዲህ ሲል ምን ማለቱ ነው? ኢየሱስ እንዲህ ሲል እኔ ካደረግሁት ተአምር የበለጠ ታደርጋላችሁ ማለቱ እንዳልሆነ ግልጽ ነው። እርሱ ለማለት የፈለገው ግን፥ እኔ ካገለገልሁት ሕዝብ የበለጠ ቁጥር ያለውን ሕዝብ ታገለግላላችሁ ማለቱ ነው። ክርስቶስ በሥጋዊ አካል ስለ ተወሰነ፥ በአንድ ጊዜ በብዙ ቦታዎች ላይ ለመገኘት አይችልም ነበር። ስለሆነም፥ የሚያገለግለው የተወሰኑ ሰዎችን ብቻ ነበር። ነገር ግን የክርስቶስ ተከታዮች በሕይወታቸው ውስጥ ካለው መንፈስ ቅዱስ የተነሣ ብዙ ሰዎችን ለመድረስ ይችላሉ። የክርስቶስ ተከታዮች በዓለም ሁሉ ሲሰራጩ፥ በክርስቶስ ኃይል ብዙ ተአምራትን ይሠራሉ። በኢየሩሳሌምና በይሁዳ ሳይወሰኑ እስከ ምድር ዳርም ይደርሳሉ። ተአምራቱም አሁን ተግባራዊ በመሆን ላይ ናቸው። ከሁሉም የሚልቀው ተአምር የክርስቶስ ተአምር ይሆናል። ይህም የክርስቶስ ተከታዮች የእግዚአብሔር መሣሪያዎች ሆነው በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሰዎችን ወደ መንፈሳዊ ጎዳና መመለሳቸው ነው። ደቀ መዛሙርቱ ኢየሱስ ያለውን ዓይነት የኃይል ምንጭ ሊኖራቸው ይችላል። በክርስቶስ አማካይነት ከእግዚአብሔር አብ ጋር ኅብረት ልናደርግ እንችላለን። ልጆቹ እንደ መሆናችን መጠን፥ ከእግዚአብሔር አብ ጋር ጥብቅ ግንኙነት ካለንና ክርስቶስ እንዳደረገው ፈቃዳችንን ለእግዚአብሔር ፈቃድ የምናስገዛ ከሆነ፥ እግዚአብሔር የምንጠይቀውን ሁሉ ለእኛና በእኛ አማካይነት ተግባራዊ ያደርጋል። ይህ እውነት የሚሆነው ፈቃዳችንን ለእግዚአብሔር ፈቃድ ስናስገዛና የምንጸልይባቸው ነገሮች እግዚአብሔር እንዲከናወኑ የሚፈልጋቸው ሲሆኑ ብቻ ነው። የውይይት ጥያቄ፡- ሀ) እንዳንድ ሰዎች ልመናችን ምንም ይሁን ምን፥ ትክክልም ይሁን ስሕተት፥ እግዚአብሔር ጸሎታችንን ሁሉ ለመመለስ ቃል ገብቶልናል ይላሉ። ይህ የተስፋ ቃል ምን ማለት ይመስልሃል? ለ) ጸሎቱ ላልተመለሰለት ሰው ምን ምላሽ ትሰጠዋለህ? (ማብራሪያው የተወሰደው በ ኤስ.አይ.ኤም ከታተመውና የአዲስ ኪዳን የጥናት መምሪያና ማብራሪያ፣ ከተሰኘው መጽሐፍ ነው፡፡ እግዚአብሔር አገልግሎታቸውን ይባርክ፡፡)
በኔዘርላንድ የሚገኝ የይግባኝ ፍ/ቤት እ.አ.አ በ2017 ዓ.ም በጦር ወንጀለኝነት ጥፋተኛ የተባሉትን ኢትዮጵያዊ አቶ እሸቱ ዓለሙን የዕድሜ ልክ እስራት ትናንት ረቡዕ አጽንቷል። የ67 ዓመቱ ተከሳሽ በኢትዮጵያ በ1960 ዎቹ እና በ1970ዎቹ በነበረው ጨካኝ ኮሚኒስት ሥርዓት ወቅት የጦር ወንጀል ፈጽመዋል ሲል በደች የሚገኝ ፍ/ቤት የጥፋተኝነት ብይን ከአምስት አመታት በፊት ሰጥቶ ነበር። አቶ እሸቱ ዓለሙ የ2017 ፍርድ እንዲቀለበስላቸው ይግባኝ ጠይቀው የነበረ ቢሆንም በሄግ የሚገኘው የይግባኝ ፍ/ቤት ግን በ1960ዎቹ መጨረሻና በ1970ዎቹ መጀመሪያ ላይ በኢትዮጵያ በመንግሥቱ ኃይለማሪያም አመራር በተፈጸመው የቀይ ሽብር ዘመቻ ተሳታፊ ነበሩ ሲል ውሳኔውን አጽንቷል። አቶ እሸቱ በመታመማቸው ምክንያት በይግባኝ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ ላይ ሳይገኙ ቀርተዋል። አንዳንድ የጉዳዩ ባለሞያዎች እንደሚሉት ወደ 150,000 የሚጠጉ የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች፣ ምሑራንና የፖለቲካ ሰዎች በወቅቱ የነበረው ስርዓት ተቃዋሚዎቹን ለማጥፋት ባደረገው ዘመቻ በጭካኔ ተገድልዋል። የሂውማን ራይትስ ዎች በበኩሉ የቀይ ሸብሩን ዘመቻ “በአፍሪካ በመንግስት የተፈጸመ ስልታዊ የጅምላ ግድያ” ሲል ይገልጸዋል። አቶ ዓለሙ እአአ በ1978 በጎጃም ክፍለ ሀገር የደርግ ተወካይ የነበሩ ሲሆን፣ በወቅቱ ደርግ በክፍለ ሀገሩ ከተቃዋሚዎቹ አንዱ ከነበረው ከኢህአፓ ጋር ሲፋለም ነበር። ፍ/ቤቱ እንዳለው “በተከሳሹ እውቅናና ተሳትፎ” የጦር ወንጀል በክፍለ ሃገሩ ይፈጸም ነበር። በእንግሊዝኛ በተጻፈው የይግባኝ ፍ/ቤቱ ውሳኔ ጭማቂ መሰረት በመቶዎች የሚቆጠሩና አብዛኞቹ ወጣት ተማሪዎች የሆኑት ሰለባዎች ካለ በቂ ምክንያት ተይዘው ኢሰብአዊ በሆነ ሁኔታ የታሰሩ ነበር። አንዳንዶች በከፋ ሁኔታ ሲደበደቡ አብዛኞቹ ደግሞ ካለ ፍርድ ሂደት ወደ እስር ቤት ይጋዙ ነበር። በርካታ ቁጥር ያላቸው ሰለባዎች ደግሞ በሞት ተቀጥተዋል። “የሞት ቅጣቱ በተከሳሹ አመራር ሰጪነት በጭካኔ ይፈጸም ነበር” ብሏል ፍ/ቤቱ። አቶ ዓለሙ በ2017 የጥፋተኝነት ውሳኔ በተሰጠበት የፍርድ ሂደቱ መጀመሪያ ላይ በስሜት ተሞልቶ ባደረገው ንግግር በደርግ ላይ የቀረበውን ውንጀላ ተቀብሎ ነገር ግን እርሱ በግሉ የፈጸማቸው አለመሆናቸውን ለዳኞች ገልጾ ነበር። አቶ ዓለሙ በደች ፍ/ቤት ጉዳያቸው ሊታይ የቻለው ከ1990ዎቹ መጀመሪያ ላይ ጀምሮ ኔዘርላንድ ውስጥ መኖር በመጀመራቸውና በ1998 የሀገሪቱን ዜግነት በመቀበላቸው ነው። ኮሎኔል መንግስቱ አሁን በዚምባብዌ ሲገኙ፣ የሃገሪቱ ፍ/ቤት እአአ በ2006 በዘር ማጥፋት ወንጀል የጥፋተኝነት ብይን ሲሰጥ፣ በኋላም በሌሉበት የሞት ፍርድ ወስኖባቸዋል።
BK8 በእስያ ገበያ ውስጥ ካሉት አዲስ የመስመር ላይ የቁማር ጣቢያዎች አንዱ ነው። እ.ኤ.አ. በ2014 የጀመረው ቬንቸር ከስፖርት ውርርድ ገበያዎች እስከ ድንቅ የመስመር ላይ የቁማር ጨዋታዎች ድረስ ሰፊ የቁማር አማራጮችን ይሰጣል። ቀደም ቦላ ንጉሥ በመባል የሚታወቀው, BK8 ካዚኖ ፈቃድ እና ኩራካዎ ስልጣን ውስጥ ቁጥጥር ነው. Games ቀደም ሲል እንደተጠቀሰው BK8 ከስፖርት ደብተር ጋር ቁማር ነው። የቁማር ክፍል እንደ የቅርብ ጊዜ የመስመር ላይ የቁማር ጨዋታዎች ይመካል ቁማር፣ ቦታዎች እና ሎተሪዎች ፣ ከሌሎች ጋር። ከመደበኛው RNG የመስመር ላይ የቁማር ጨዋታዎች በተጨማሪ BK8 በገበያ ላይ ካሉ አንዳንድ ምርጥ የቀጥታ አከፋፋይ ጨዋታዎች ጋር የቀጥታ ካሲኖ ሎቢ አለው። Withdrawals ገንዘብ ማውጣትን በተመለከተ፣ አማራጮች ከተቀማጭ ገንዘብ ጋር እንደሚመሳሰሉት ጥቂት ናቸው። ያሉት የማውጣት አማራጮች የአካባቢ ባንክ ማስተላለፍ፣ PayTrust88፣ Eeziepay እና Help2Pay ብቻ ናቸው። ስለ BK8 ካሲኖ ያለው መልካም ነገር ሁሉንም አሸናፊዎች የውርርድ መስፈርቶችን እስካሟሉ ድረስ መዋጮቸውን የሚከፍል የታመነ ተቋም መሆኑ ነው። ምንዛሬዎች BK8 ካዚኖ ምንዛሬዎች ጋር በተያያዘ ተጫዋቾች ምርጫ ሰፊ ክልል ያቀርባል. ተጫዋቾች እንደ የኢንዶኔዥያ ሩፒያ (IDR)፣ የማሌዥያ ሪንጊት (MYR)፣ የታይላንድ ባህት (THB) እና የቬትናም ዶንግ (VND) ያሉ የ fiat የገንዘብ ምንዛሬዎችን በመጠቀም መጫወትን መምረጥ ይችላሉ። ከ fiat የገንዘብ ምንዛሬዎች በተጨማሪ፣ BK8 ተጫዋቾች እንደ ቢትኮይን (BTC) እና ethereum (እንደ ቢትኮይን (BTC) እና ethereum () ያሉ cryptos በመጠቀም እንዲጫወቱ ያስችላቸዋል።ETH). Bonuses BK8 ካዚኖ ለሁለቱም የስፖርት ውርርድ ደጋፊዎች እና የመስመር ላይ ካሲኖ ተጫዋቾች ማስተዋወቂያዎች አሉት። በካዚኖ ክፍል ውስጥ ያሉ አዳዲስ ተጫዋቾች ጥሩ የእንኳን ደህና መጣችሁ ጉርሻ አላቸው። ሌሎች ማስተዋወቂያዎች ጉርሻዎችን እንደገና መጫን ፣ የልደት ጉርሻዎች, ሪፈራል ጉርሻዎች, cashback, ወዘተ. እባክዎ ልብ ይበሉ፣ እነዚህ ማስተዋወቂያዎች በውርርድ መስፈርቶች የተያዙ ናቸው። Languages ከሁሉም የዓለም ክፍሎች የመጡ ተጫዋቾችን ለማገልገል ዓላማ ካላቸው ብዙ ዓለም አቀፍ ካሲኖዎች በተለየ BK8 ካዚኖ የእስያ ክልል ተጫዋቾችን ለማገልገል ነው። ካሲኖው በእንግሊዝኛ እና በተለያዩ የእስያ ቋንቋዎች ይገኛል፣ ኢንዶኔዥያኛ፣ ማላይኛ፣ ታይላንድ፣ ቻይንኛእና ቬትናምኛ። ተጫዋቾች በማንኛውም ጊዜ ወደ ተመራጭ ቋንቋቸው መቀየር ይችላሉ። Software ሁሉም ተጫዋቾች የሚወዱት ነገር እንዳላቸው ለማረጋገጥ BK8 ካዚኖ ከአብዛኞቹ ከፍተኛ የካሲኖ ሶፍትዌር ገንቢዎች ጋር ተባብሯል። ዝርዝሩ Microgaming፣ Play 'n GO፣ Spadegaming፣ Pragmatic Play Ltd.፣ Mega888፣ Asia Gaming፣ ፕሌይቴክ, TopTrend Gaming፣ Asia Gaming፣ SA Gaming፣ Funky Games፣ Game Play፣ 918Kiss፣ Allbet፣ Dream Gaming፣ ወዘተ Support አዲስ ካሲኖ ቢሆንም BK8 ካዚኖ ሁሉንም የደንበኛ ጥያቄዎችን የሚንከባከብ የታመነ የምርት ስም ነው። ኦፕሬተሩ የ24/7 የቀጥታ ውይይትን ያካተተ የመልቲ ቻናል ድጋፍን አስቀምጧል። ተጨዋቾች ፈጣን ግብረ መልስ ስለሚያገኙ የቀጥታ ውይይት ድጋፍ ምርጡ አማራጭ ነው። ከቀጥታ ውይይት በተጨማሪ ቁማርተኞች በስልክ፣ በWeChat እና በዋትስአፕ ድጋፍ ማግኘት ይችላሉ። Deposits BK8 ተጫዋቾች ወደ ጨዋታው ከመግባታቸው በፊት ሂሳባቸውን እንዲጭኑ የሚጠይቅ እውነተኛ ገንዘብ ካሲኖ ነው። እንደ አለመታደል ሆኖ ብዙ የማስቀመጫ ዘዴዎች የሉም። በአሁኑ ጊዜ ተጫዋቾች የአካባቢ ባንክ ማስተላለፍን በመጠቀም ማስገባት ይችላሉ, እና ሶስት የክፍያ በሮች ብቻ; PayTrust88, Eeziepay እና Help2Pay. ዝቅተኛው እና ከፍተኛው የተቀማጭ ገደብ አለ።
10ኛው የኢትዮ ፓልተሪ ኤክስፖ እና 6ኛው የአፍሪካ እንስሳት አውደርእይና ጉባኤ ከጥቅምት በአካል ከጥቅምት 18-20 እንዲሁም ከጥቅምት 22- ህዳር 22 2014 ዓ.ም ደግሞ በበይነመረብ ይደረጋል ተብሏል፡፡ አዘጋጆቹ ፕራና ኤቨንትስ እና መቀመጫውን ሱዳን ያደረገው ኤክስፖ ቲም በዛሬዉ እለት እንዳስታወቁት፣ በአዉደርዕዩ ላይ ከተለያዩ ሃገራት የተዉጣጡ የዘርፉ አንቀሳቃሾች ይሳተፉበታል፡፡ አዉደርዕዩ ለዘርፉ አስፈላጊ የሆኑ ቴክኖሎጂዎች የሚቀርቡበት ከመሆኑም ባሻገር ያሉበትን ችግሮች በመፈተሽ መፍትሄ የሚሆኑ ግብዓቶች የሚገኙበት እንደሚሆንም አዘጋጆቹ ተናግረዋል፡፡ ለ3 ቀናት ቆይታ እንደሚኖረዉ የተነገረዉ ይህ አዉደርዕይ በስካይ ላይት ሆቴል የሚካሄድ ሲሆን ከ3 ሺህ በላይ የሚሆኑ ሰዎች ይጎበኙታል ተብሎ እንደሚጠበቅም ኢትዮ ኤፍ ኤም ከአዘጋጆቹ ሰምቷል፡፡ በአዉደርዕዩ ላይም ከኢትዮጵያ፣ ሱዳን፣ ኔዘርላንድስ፣ ጀርመን፣ ሀንጋሪ እና ከሌሎችም ሃገራት የመጡ በዘርፉ የተሰማሩ ኩባንያዎች ይሳተፉበታል ተብሏል፡፡ የዓለም አቀፉ የምግብና እርሻ ድርጅት/ፋኦ/ ሪፖርት እንደሚያመለክተዉ ኢትዮጵያ በ2030 456 ሺህ ቶን የከብት ስጋ፣14 ሺህ 231 ቶን ወተት፣96 ሺህ ዶሮ፣54 ሺህ ቶን እንቁላል እንዲሁም 265ሺህ ቶን የበግና ፍየል ስጋ እንደምትጠቀም ግምቱን አስቀምጧል፡፡