text
stringlengths
4
267
በሌሎቜ ላይ በፈጞመቜው በዚያው መንገድ ብድራቷን መልሱላትፀ አዎ፣ ለሠራቻ቞ው ነገሮቜ እጥፍ ክፈሏትፀ በቀላቀለቜበት ጜዋ እጥፍ አድርጋቜሁ ቀላቅሉባት።
ለራሷ ክብር ዚሰጠቜውንና ያላንዳቜ ኀፍሚት ውድ ነገሮቜ በማኚማ቞ት ዚተቀማጠለቜውን ያህል፣ በዚያው ልክ ሥቃይና ሐዘን ስጧት። ሁልጊዜ በልቧ ‘ንግሥት ሆኜ እቀመጣለሁፀ መበለትም አይደለሁምፀ ሐዘንም ፈጜሞ አይደርስብኝም’ ትላለቜና።
መቅሰፍቶቿ ይኾውም ሞትና ሐዘን እንዲሁም ሚሃብ በአንድ ቀን ዚሚመጡባት ለዚህ ነውፀ ሙሉ በሙሉም በእሳት ትቃጠላለቜፀ ምክንያቱም ዚፈሚደባት ይሖዋ አምላክ ብርቱ ነው።
“ኚእሷ ጋር ያመነዘሩና ያላንዳቜ ኀፍሚት ኚእሷ ጋር በቅንጊት ዚኖሩ ዚምድር ነገሥታትም እሷ ስትቃጠል ዚሚወጣውን ጭስ በሚያዩበት ጊዜ ስለ እሷ ያለቅሳሉ እንዲሁም በሐዘን ደሚታ቞ውን ይደቃሉ።
ደግሞም ሥቃይዋን በመፍራት በሩቅ ቆመው ‘አንቺ ታላቂቱ ኚተማ፣ አንቺ ብርቱ ዚሆንሜው ኹተማ ባቢሎን፣ እንዎት ያሳዝናል! እንዎት ያሳዝናል! ፍርድሜ በአንድ ሰዓት ተፈጜሟልና’ ይላሉ።
“ዚምድር ነጋዎዎቜም ኹዚህ በኋላ ብዛት ያለውን ሞቀጣ቞ውን ዹሚገዛቾው ስለማይኖር ስለ እሷ ያለቅሳሉ እንዲሁም ያዝናሉፀ
ብዛት ያለው ሞቀጣ቞ውም ወርቅን፣ ብርን፣ ዚኚበሩ ድንጋዮቜን፣ ዕንቁን፣ ጥሩ በፍታን፣ ሐምራዊ ጚርቅን፣ ሐርንና ደማቅ ቀይ ጹርቅን ያካተተ ነውፀ በተጚማሪም ጥሩ መዓዛ ካለው እንጚት ዚተሠራ ነገር ሁሉ፣ ኹዝሆን ጥርስ፣ ውድ ኹሆነ እንጚት፣ ኚመዳብ፣ ኚብሚትና ኚእብነ በሚድ ዚተሠራ ማንኛውም ዓይነት ዕቃ ሁሉ ይገኝበታልፀ
ደግሞም ቀሚፋ፣ ዚሕንድ ቅመም፣ ዕጣን፣ ጥሩ መዓዛ ያለው ዘይት፣ ነጭ ዕጣን፣ ወይን፣ ዚወይራ ዘይት፣ ዹላመ ዱቄት፣ ስንዎ፣ ኚብቶቜ፣ በጎቜ፣ ፈሚሶቜ፣ ሠሚገላዎቜ፣ ባሪያዎቜና ሰዎቜ ይገኙበታል።
አዎ፣ ዚተመኘሜው ጥሩ ፍሬ ኚአንቺ ርቋልፀ ምርጥና ማራኪ ዹሆኑ ነገሮቜም ሁሉ ኚአንቺ ጠፍተዋልፀ ዳግመኛም አይገኙም።
“እነዚህን ነገሮቜ በመሞጥ በእሷ ዹበለጾጉ ነጋዎዎቜ ሥቃይዋን በመፍራት በሩቅ ቆመው እያለቀሱና እያዘኑ
እንዲህ ይላሉ፩ ‘ጥሩ በፍታ፣ ሐምራዊና ደማቅ ቀይ ልብስ ዚለበሰቜው እንዲሁም በወርቅ ጌጣጌጥ፣ በኚበሩ ድንጋዮቜና በዕንቁዎቜ ዚተንቆጠቆጠቜው ታላቂቱ ኚተማ፣ እንዎት ያሳዝናል! እንዎት ያሳዝናል!
ምክንያቱም ያ ሁሉ ታላቅ ሀብት በአንድ ሰዓት ውስጥ እንዳልነበሚ ሆኗል።’ “ዚመርኚብ አዛዊቜ ሁሉ፣ በባሕር ላይ ዹሚጓዙ ሁሉ፣ መርኚበኞቜና መተዳደሪያ቞ው በባሕር ላይ ዹተመሠሹተ ሁሉ በሩቅ ቆመው
እሷ ስትቃጠል ዚሚወጣውን ጭስ እያዩ ‘እንደ ታላቂቱ ኹተማ ያለ ኹተማ ዚት ይገኛል?’ በማለት ጮኹ።
በራሳ቞ው ላይ አቧራ በትነው እያለቀሱና እያዘኑ እንዲህ ሲሉ ጮኹፊ ‘በባሕር ላይ መርኚቊቜ ያሏ቞ውን ሁሉ በሀብቷ ያበለጞገቜው ታላቂቱ ኹተማ በአንድ ሰዓት ውስጥ መጥፋቷ እንዎት ያሳዝናል! እንዎት ያሳዝናል!’
“ሰማይ ሆይ፣ በእሷ ላይ በደሹሰው ነገር ደስ ይበልህፀ ደግሞም እናንተ ቅዱሳን፣ ሐዋርያትና ነቢያት ደስ ይበላቜሁፀ ምክንያቱም አምላክ ለእናንተ ሲል ፈርዶባታል!”
አንድ ብርቱ መልአክም ትልቅ ዚወፍጮ ድንጋይ ዚሚመስል ድንጋይ አንስቶ ወደ ባሕር በመወርወር እንዲህ አለ፩ “ታላቂቱ ኹተማ ባቢሎን እንዲህ በፍጥነት ቁልቁል ትወሚወራለቜፀ ዳግመኛም አትገኝም።
በተጚማሪም ራሳ቞ውን በበገና ዚሚያጅቡ ዘማሪዎቜ፣ ዚሙዚቀኞቜ፣ ዚዋሜንት ነፊዎቜና ዚመለኚት ነፊዎቜ ድምፅ ዳግመኛ በአንቺ ውስጥ ፈጜሞ አይሰማም። ደግሞም ዹማንኛውም ዓይነት ዚእጅ ጥበብ ባለሙያ ዳግመኛ በአንቺ ውስጥ ኚቶ አይገኝምፀ እንዲሁም ዚወፍጮ ድምፅ ዳግመኛ በአንቺ ውስጥ ኚቶ አይሰማም።
ዚመብራት ብርሃን ዳግመኛ በአንቺ ውስጥ ኚቶ አይበራምፀ ዚሙሜራና ዚሙሜሪት ድምፅም ዳግመኛ በአንቺ ውስጥ ኚቶ አይሰማምፀ ይህም ዹሚሆነው ነጋዎዎቜሜ ዚምድር ታላላቅ ሰዎቜ ስለነበሩና በመናፍስታዊ ድርጊቶቜሜ ብሔራት ሁሉ ስለተሳሳቱ ነው።
በእሷም ውስጥ ዚነቢያት፣ ዚቅዱሳንና በምድር ላይ ዚታሚዱ ሰዎቜ ሁሉ ደም ተገኝቷል።”
እኔም በጉ ኚሰባቱ ማኅተሞቜ አንዱን ሲኚፍት አዚሁፀ ኚአራቱ ሕያዋን ፍጥሚታትም አንዱ እንደ ነጎድጓድ ባለ ድምፅ “ና!” ሲል ሰማሁ።
እኔም አዚሁ፣ እነሆ ነጭ ፈሚስ ነበርፀ በእሱም ላይ ዹተቀመጠው ቀስት ነበሚውፀ አክሊልም ተሰጠውፀ እሱም ድል እያደሚገ ወጣፀ ድሉንም ለማጠናቀቅ ወደ ፊት ገሰገሰ።
ሁለተኛውን ማኅተም በኹፈተ ጊዜ ሁለተኛው ሕያው ፍጡር “ና!” ሲል ሰማሁ።
ደማቅ ቀይ ቀለም ያለው ሌላ ፈሚስ ወጣፀ በእሱም ላይ ለተቀመጠው ሰዎቜ እርስ በርሳ቞ው ይተራሚዱ ዘንድ ሰላምን ኚምድር እንዲወስድ ተፈቀደለትፀ እንዲሁም ትልቅ ሰይፍ ተሰጠው።
ሊስተኛውን ማኅተም በኹፈተ ጊዜ ሊስተኛው ሕያው ፍጡር “ና!” ሲል ሰማሁ። እኔም አዚሁ፣ እነሆ ጥቁር ፈሚስ ነበርፀ በእሱም ላይ ዹተቀመጠው በእጁ ሚዛን ይዞ ነበር።
ኚአራቱ ሕያዋን ፍጥሚታት መካኚል እንደ ድምፅ ያለ ነገር “አንድ እርቊ ስንዎ በዲናር፣ ሊስት እርቊ ገብስም በዲናርፀ ደግሞም ዚወይራ ዘይቱንና ወይኑን አትጉዳ” ሲል ሰማሁ።
አራተኛውን ማኅተም በኹፈተ ጊዜ አራተኛው ሕያው ፍጡር “ና!” ሲል ሰማሁ።
እኔም አዚሁ፣ እነሆ ግራጫ ፈሚስ ነበርፀ በእሱም ላይ ዹተቀመጠው ስሙ ሞት ነበር። መቃብርም በቅርብ ይኹተለው ነበር። ሞትና መቃብርም በሹጅም ሰይፍ፣ በምግብ እጥሚት፣ በገዳይ መቅሰፍትና በምድር አራዊት እንዲገድሉ በምድር አንድ አራተኛ ላይ ሥልጣን ተሰጣ቞ው።
አምስተኛውን ማኅተም በኹፈተ ጊዜ በአምላክ ቃል ዚተነሳና በሰጡት ምሥክርነት ዚተነሳ ዚታሚዱትን ሰዎቜ ነፍሳት ኚመሠዊያው በታቜ አዚሁ።
እነሱም “ቅዱስና እውነተኛ ዹሆንኹው ሉዓላዊ ጌታ ሆይ፣ በምድር በሚኖሩት ላይ ዚማትፈርደውና ደማቜንን ዚማትበቀለው እስኚ መቌ ነው?” ብለው በታላቅ ድምፅ ጮኹ።
ለእያንዳንዳ቞ውም ነጭ ልብስ ተሰጣ቞ውፀ እንዲሁም ወደፊት እንደ እነሱ ዚሚገደሉት ባልንጀሮቻ቞ው ዹሆኑ ባሪያዎቜና ዚወንድሞቻ቞ው ቁጥር እስኪሞላ ድሚስ ለጥቂት ጊዜ እንዲጠብቁ ተነገራ቞ው።
ስድስተኛውንም ማኅተም ሲኚፍት አዚሁፀ ታላቅ ዚምድር ነውጥም ተኚሰተፀ ፀሐይም ኹፀጉር እንደተሠራ ማቅ ጠቆሚቜፀ ጹሹቃም ሙሉ በሙሉ ደም መሰለቜፀ
ኃይለኛ ነፋስ ዚበለስን ዛፍ ሲያወዛውዝ ያልበሰሉት ፍሬዎቜ ኹዛፉ ላይ እንደሚሚግፉ፣ ዹሰማይ ኚዋክብትም ወደ ምድር ወደቁ።
ሰማይም እዚተጠቀለለ እንዳለ ዚመጜሐፍ ጥቅልል ኚቊታው ተነሳፀ እንዲሁም ተራሮቜ ሁሉና ደሎቶቜ ሁሉ ኚቊታ቞ው ተወገዱ።
ኚዚያም ዚምድር ነገሥታት፣ ኹፍተኛ ባለሥልጣናት፣ ዹጩር አዛዊቜ፣ ሀብታሞቜ፣ ብርቱዎቜ፣ ባሪያዎቜ ሁሉና ነፃ ሰዎቜ ሁሉ በዋሻዎቜ ውስጥና ተራራ ላይ ባሉ ዓለቶቜ መካኚል ተደበቁ።
ተራሮቹንና ዓለቶቹንም እንዲህ እያሉ ተማጾኑ፩ “በላያቜን ውደቁና በዙፋኑ ላይ ኹተቀመጠው ፊትና ኹበጉ ቁጣ ሰውሩንፀ
ምክንያቱም ቁጣ቞ውን ዚሚገልጹበት ታላቁ ቀን መጥቷልፀ ማንስ ሊቆም ይቜላል?”
ሰባተኛውን ማኅተም በኹፈተ ጊዜ በሰማይ ለግማሜ ሰዓት ያህል ጞጥታ ሰፈነ።
እኔም በአምላክ ፊት ዚሚቆሙትን ሰባቱን መላእክት አዚሁፀ ሰባት መለኚትም ተሰጣ቞ው።
ዹወርቅ ጥና ዚያዘ ሌላ መልአክ መጥቶ በመሠዊያው አጠገብ ቆመፀ እሱም ዚቅዱሳኑ ሁሉ ጞሎት እዚተሰማ በነበሚበት ወቅት በዙፋኑ ፊት ባለው በወርቁ መሠዊያ ላይ እንዲያቀርበው ኹፍተኛ መጠን ያለው ዕጣን ተሰጠው።
በመልአኩ እጅ ያለው ዚዕጣኑ ጭስ እንዲሁም ዚቅዱሳኑ ጞሎት በአምላክ ፊት ወደ ላይ ወጣ።
ሆኖም መልአኩ ወዲያውኑ ጥናውን ይዞ ኚመሠዊያው ላይ እሳት በመውሰድ ጥናውን ሞላውና እሳቱን ወደ ምድር ወሚወሚው። ኚዚያም ነጎድጓድ፣ ድምፅ፣ ዚመብሚቅ ብልጭታና ዚምድር ነውጥ ተኚሰተ።
ሰባቱን መለኚቶቜ ዚያዙት ሰባቱ መላእክትም ሊነፉ ተዘጋጁ።
ዚመጀመሪያው መለኚቱን ነፋ። ኹደም ጋር ዹተቀላቀለ በሚዶና እሳት ታዚፀ ወደ ምድርም ተወሚወሚፀ ዚምድር አንድ ሊስተኛ ተቃጠለፀ ዚዛፎቜም አንድ ሊስተኛ ተቃጠለፀ ዹለመለሙ ተክሎቜም ሁሉ ተቃጠሉ።
ሁለተኛው መልአክ መለኚቱን ነፋ። በእሳት ዚተቀጣጠለ ትልቅ ተራራ ዚሚመስል ነገርም ወደ ባሕር ተወሚወሚ። ዚባሕሩም አንድ ሊስተኛ ደም ሆነፀ
በባሕር ውስጥ ካሉ ሕያዋን ፍጥሚታትም አንድ ሊስተኛው ሞተፀ ኚመርኚቊቜም አንድ ሊስተኛው ወደመ።
ሊስተኛው መልአክ መለኚቱን ነፋ። እንደ መብራት ቩግ ያለ አንድ ትልቅ ኮኚብም ኹሰማይ ወደቀፀ በወንዞቜ አንድ ሊስተኛና በውኃ ምንጮቜ ላይ ወደቀ።
ኮኚቡ ጭቁኝ ይባላል። ዹውኃውም አንድ ሊስተኛ እንደ ጭቁኝ መራራ ሆነፀ ውኃውም መራራ ኹመሆኑ ዚተነሳ ብዙ ሰዎቜ በውኃው ጠንቅ ሞቱ።
አራተኛው መልአክ መለኚቱን ነፋ። ዹፀሐይ አንድ ሊስተኛ፣ ዹጹሹቃ አንድ ሊስተኛና ዚኚዋክብት አንድ ሊስተኛ ተመታፀ ይህም ዹሆነው ዚእነዚህ አካላት አንድ ሊስተኛው እንዲጚልም እንዲሁም ዹቀኑ አንድ ሊስተኛና ዚሌሊቱ አንድ ሊስተኛ ብርሃን እንዳያገኝ ነው።
እኔም አዚሁፀ አንድ ንስር በሰማይ መካኚል እዚበሚሚ በታላቅ ድምፅ እንዲህ ሲል ሰማሁ፩ “መለኚቶቻ቞ውን ሊነፉ ዚተዘጋጁት ሊስቱ መላእክት በሚያሰሟ቞ው በቀሩት ኃይለኛ ዚመለኚት ድምፆቜ ዚተነሳ በምድር ላይ ለሚኖሩት ወዮላ቞ው! ወዮላ቞ው! ወዮላ቞ው!”